Quantcast
Channel: እኔ የምለዉ
Viewing all 475 articles
Browse latest View live

‹‹የምሁር የመምራት አቅም በውጤቱ ይመዘናል››

$
0
0

ዶ/ር ዓለም መብራህቱ፣ የዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዚዳንት

አዲሱን የዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከአራት ዓመት በፊት ጀምሮ በምክትል ፕሬዚዳንትነት በማገልገል ላይ የሚገኙት ዶ/ር ዓለም መብራህቱ፣ አንደኛና ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በፊዚክስ ዲፓርትመንት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል፡፡ ለአጭር ጊዜ በመቐለ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት ካገለገሉ በኋላ በጀርመን የዶክትሬት ዲግሪያቸውን አጠናቀዋል፡፡ ከዚያም ተመልሰው በመቐለ ዩኒቨርሲቲ የተፈጥሮ ሳይንስ ፋካልቲ ዲን ሆነው ሠርተዋል፡፡ ቀደም ሲል በአንዳንድ አካባቢዎች ተፈጥሮ ከነበረው ሁከት ጋር ተያይዞ ገዢው ፓርቲና መንግሥት እየወሰዱዋቸው ባሉ ዕርምጃዎች፣ በዩኒቨርሲቲው ስላለው ወቅታዊ የመማር ማስተማር ሁኔታን በተመለከተ የማነ ናግሽ ዶ/ር ዓለም መብራህቱን አነጋግሯቸዋል፡፡

ሪፖርተር፡- በአገሪቱ ተከስቶ የነበረው ሁከት በአሁኑ ጊዜ እየተረጋጋ ነው፡፡ ከፍተኛ ትኩረት ከተሰጣቸው የመንገሥት ተቋማት መካከል ደግሞ ዩኒቨርሲቲዎች ናቸውና ከዩኒቨርሲቲዎች ማኅበረሰቦች ጋር የተካሄዱ ውይይቶች ምን ያህል ውጤታማ ናቸው ይላሉ?

ዶ/ር ዓለም፡- የተካሄደው ሥልጠና በእርግጥ ከወቅታዊ ጉዳዮች ጋር እንዲዛመድ ተደርጓል እንጂ ሦስተኛ ዓመቱን ይዟል፡፡ በአምስት ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት የነበረው ጉዞ ምን እንደሚመስል በአጭር ተጨምቆ የቀረበበት ሁኔታ ነበር፡፡ በትክክል የተፈጸሙና ያልተፈጸሙ፣ እንዲሁም የተገኘውን ድልና ድክመት የዳሰሰ ነበር፡፡ በሁለኛ ደረጃ የጋራ መግባባት መፍጠር የሚደረስበት ነበር፡፡ እንዲሁም ደግሞ በትምህርት ጥራት ላይ የተገኘውን ውጤትና የነበረውን ድክመት የሚያሳይ ነበር፡፡ የተቀሩት ደግሞ እያንዳንዱ ዩኒቨርሲቲ ባለፉት የትምህርት ዘመን ምን እንደሚመስልና ለሚቀጥለው የትምህርት ዘመን ምን ዕቅድ እንደተያዘ የሚመለከቱ ነበሩ፡፡ እናም ሥልጠናው ብዙ ሰው እንደሚለው በወቅታዊ ሁኔታ ላይ የተቃኘ አይደለም፡፡ በእርግጥ በመሀል በመሀል መነሳቱ አልቀረም፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች የተነሱ ሁከቶች ምክንያታቸው ምንድን እንደሆነ፣ ከኋላ የሚገፉት እነማን እንደሆኑ የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ በተለይ ደግሞ ዜጎችን የሚቀርፀው መምህር ለይቶ ማወቅ ስላለበት ጉዳዮቹ ተነስተው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ አንድ ተማሪ ወላጆቹ በሚከፍሉት ግብር የተሠራን ሕንፃ የሚያፈርስበት ምክንያት አይኖርም፡፡ ጥያቄዎች አሉ፣ ከዩኒቨርሲቲ አስተዳደር ጀምሮ እስከ መንግሥት አስተዳደር ብልሹ አሠራሮችና የመልካም አስተዳደር ችግሮች አሉ፡፡ ጥያቄ መነሳት አለበት፡፡ እንደ አቅጣጫ የተያዘውም የሚጠይቅ ማኅበረሰብ መፍጠር አለብን የሚል ነው፡፡ የራስን ንብረትና በመከራ የተሠራች ነገርን ግን ቀና ብሎ ማየት የለበትም፡፡ ራሱን በራስ እንደ ማጥፋት ነው፡፡ ጥያቄው እስካልተመለሰለት ድረስ በአግባቡ መጠየቅና መሞገት ግን አለበት፡፡ ይህንን ነው የተነጋገርነው፡፡

በዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ የመነጋገር ችግር የለብንም፡፡ ሁሌም በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ውይይት እናደርጋለን፡፡ እንደ ባህል ይዘነዋል፡፡ በአጠቃላይ ግን ዘንድሮ የተደረጉ ውይይቶች በእርግጥ ትንሽ ለየት ያሉ ናቸው፡፡ የተለያዩ ስትራቴጂካዊ ጥያቄዎች ተነስተዋል፡፡ እኛም ለሚመለከታቸው አካላት አስተላልፈናል፡፡ ምላሽ እያገኙ ናቸው፡፡ መንግሥትም ውይይቶች እንዲካሄዱ ያደረገው እሳት ለማጥፋት ወይም ተራ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት አልነበረም፡፡ ከተማረው ኃይል ግብዓት ስለሚፈልግ ነው፡፡ በተለይ መምህር ተማሪውን መምራት ካለበት ጠንቅቆ ማወቅ ይኖርበታል፡፡ ተማሪዎች ገና ልጆች ናቸው፡፡ በቀላሉ ሊሳሳቱ ይችላሉ፡፡ ዋናው መምህር ነው ትልቅ ሚና የሚጫወተው፡፡ የሥልጠናዎቹ ዋና ስበትም ይኼ ነበር ለማለት ነው፡፡ በውጤቱም በአገሪቱ የተፈጠረው ሰላም እንዳለ ሆኖ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሁከት ሳይሆን የሰላምና የዕውቀት ማዕከሎች ሆነዋል፡፡ ያልተለመዱ ጥያቄዎች የሉም ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን በብዙ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት መፍጠር ተችሏል የሚል እምነት አለኝ፡፡

በተለይ ከውጭ ኃይሎች ጣልቃ ገብነት ጋር ተያይዞ መግባባት ተፈጥሯል፡፡ ለምሳሌ ግብፅ እዚህ የምትገባበት ምን ምክያት አላት? ኢትዮጵያን ለማተራመስ ካስቀመጠቻቸው ስትራቴጂዎች ዘጠነኛውን እየተጠቀመች ነው የሚሉ አሉ፡፡ ምንም ያህል ቅሬታ ቢኖር ግብፅ የምትፈታው አይደለም፡፡ ሁኔታውን ለመጠቀም ስለፈለገች ነው፡፡ እዚህ ላይ በዩኒቨርሲቲ ማኅበረሰቡ ውስጥም፣ በአገር ደረጃም፣ በዜጎች መካከልም የጋራ አመለካከት መፍጠር ያስፈልጋል፡፡ ሰው እንደአቅሙ ነው የሚያጠፋው፣ ትንሽ ጥፋት የለም፡፡ የመጀመሪያሙ መድኃኒት ራሱን መፈተሽ አለበት፡፡ ለምሳሌ ሁለት ከተለያዩ ብሔረሰቦች የመጡ ተማሪዎች ሲጋጩ የብሔር ጉዳይ አድርጎ ማሰብ አያስፈልግም፡፡ በሁለት ግለሰቦች መካከል ነው ግጭት የተፈጠረው፡፡ ከጀርባ በዚህ የሚጠቀሙ አይጠፉም፡፡ የራሳቸውም ሥሌት አላቸው፡፡ የእነሱ መጠቀሚያ መሆን ግን አያስፈልግም፡፡ በምንም ተዓምር አንድ ሕዝብ እንደ ሕዝብ የሌላ ሕዝብ ጠላት የሚሆንበት ምክንያት የለም፡፡ ጠላት ሆኖም አያውቅም፡፡ ሃይማኖተኛ ሕዝብ ነው፡፡ በሕዝብ ደረጃ ተደርጎ የሚያውቅ ጥፋት እስካሁን የለም፡፡ አንዳንድ ሰዎች ስለትግራይ የሚስሉት ይታወቃል፡፡ ሕዝቡ በተለየ ተጠቃሚ ነው፣ በተለየ ለምቷል ይባላል፡፡ እያንዳንዱ ተማሪ ኮምፒዩተር እንዳለው ጭምር ይወራል፡፡ ተማሪዎች እዚህ መጥተው ሕዝቡን ሲመለከቱ ሲያዝኑና ሲፀፀቱ ብዙ ጊዜ የምናስተውለው ነው፡፡ ስለዚህ እኛ የምንፈልገው ተማሪው መሬት ላይ ያለን እውነት እንዲያውቅ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በተወሰኑ የአገሪቱ አካባቢዎች የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት ገዢው ፓርቲ በጥልቀት ለመታደስ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አስታውቋል፡፡ ለጊዜው መረጋጋት ተፈጥሯል፡፡ በዚህ አካሄድ የተከሰተውን ችግር በዘላቂነት መፍታት ይቻላል ብለው ያስባሉ?

ዶ/ር ዓለም፡- እንግዲህ ትልቅ ኃላፊነት ላይ ያለ አካል የተለያዩ ፈተናዎች ሊገጥሙት የግድ ነው፡፡ ለምን ገጠመው አይባልም፡፡ ሕወሓት/ኢሕአዴግም ዕድሜው ረዘም ያለ ነው፡፡ በዚህ ጉዞ ብዙ ችግር ገጥሞት ማለፍ ችሏል፡፡ በቃ ዛሬ አበቃለት ሲባል ብዙ ጊዜ ወድቆ ይነሳል፡፡ ሰው በተፈጥሮው ስህተት ላይሠራ አይችልም፡፡ ደረጃው ነው የሚወሰነው፡፡ መድኃኒቱም ግምገማ ማድረግ ነው፡፡ ድርጅቱ ብዙ ድሎችን አስመዝግቧል፡፡ ነገር ግን በተገኘው የልማት ዕድገት ላይ ብቻ ተዘናግቶ መቀመጥ አያስፈልግም፡፡ ምናልባትም በደንብ ቢሠራ ከተገኘው ዕድገት በላይ መሄድ ይቻል ነበር፡፡ እናም ውሱንነቶቹ አሁን የሆነ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ እሱን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

ሪፖርተር፡- የተከሰተውን ቀውስ ለመፍታት ገዢው ፓርቲ በተለይ በመንግሥት ደረጃ አዲስ ካቢኔ አቋቁሟል፡፡ ብዙዎች የካቢኔው አባላት ከዩኒቨርሲቲ የመጡ ምሁራን ናቸው፡፡ እንዴት ያዩታል?

ዶ/ር ዓለም፡- በመጀመሪያ አካሄዱ በጣም ጥሩ ነው፡፡ በተደረገው ግምገማ መሠረት ለውጥ ለማምጣት መንግሥት ቁርጠኛ መሆኑን አሳይቷል፡፡ በውጤት ደረጃ ግን እንግዳ ሰዎች በካቢኔው እንዲካተቱ ተደርገዋልና ትክክለኛነቱ መመዘን የሚቻለው ሰዎቹ የሚያመጡት ለውጥ ታይቶ ይሆናል፡፡ የእኔ እምነት አዲሱ የምሁራን ኃይል የሕዝብና የመንግሥትን ፍላጎት ተገንዝቦ ሥራውን ያከናውናል የሚል ነው፡፡ ምክንያቱም አብዛኞቹ በሚኒስትር ደረጃ የተመደቡ ምሁራን ከዩኒቨርሲቲዎች የመጡ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ደግሞ ከ40 በላይ ዩኒቨርሲቲዎች ነው ያሉት፡፡ ዩኒቨርሲቲዎቹ የተማረ ኃይል የያዙ ናቸው፡፡ ሰዎቹ ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር ቅርበት ስለነበራቸው በሰፊው ማንቀሳቀስ ይችላሉ፡፡ እስካሁን ዩኒቨርሲቲው ውስጥ ያለው ማኅበረሰብ ተቺ ብቻ ነበር፡፡ ከአሁን በኋላ እሱን የሚመስል ሰው ከፍተኛ ቦታዎች ላይ ስለተቀመጠ፣ ተቺ ብቻ ሳይሆን በየዘርፉ ተናቦ መሥራት ይችላል፡፡ ምክንያቱም የነበረው ቅሬታ ሥልጣን ላይ የነበሩ ሰዎች አቅም የላቸውም የሚል ነው፡፡ አሁን አቅም አላቸው የሚባሉ ሰዎች ቦታው ላይ እንዲቀመጡ ተደርገዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲዎች እዚህ ላይ በትብብር ለመሥራት ይችላሉ፡፡ የምሁሩ የመምራት አቅም በውጤቱ ይመዘናል፡፡

ሪፖርተር፡- ሕወሓትን ጨምሮ አንዳንድ አባል ድርጅቶች የተጠበቀውን ያህል የአመራር ለውጥ አላደረጉም ተብለው እየተተቹ ነው፡፡

ዶ/ር ዓለም፡- የአመራር ለውጥ ማድረግ አንድ መፍትሔ ነው፡፡ ግን የችግሩን ጥልቀት አምኖ መቀበል ነው፡፡ ግምገማ እየተካሄደ ነው ገና አልተጠናቀቀም፡፡ በግምገማዎቹ መጀመሪያ የምንጠብቀው ችግሩ ላይ መተማመን መቻል ነው፡፡ እሱ ሆኗል፡፡ ቀጥሎ የሚሆነው ዕርምጃ መወሰድ ነው፡፡ እሱ ገና አልተገባም፡፡ ምን እንደሚሆን በቅርቡ የምናየው ይሆናል፡፡ በእርግጥ አንድን ሰው በሌላ መተካት ብቻውን ለውጥ ያመጣል የሚል እምነት የለኝም፡፡ በአጠቃላይ የኅብረተሰቡን ፍላጎትና ችግር የሚረዳ አመራር መፍጠር ትልቁ ነገር ነው፡፡ ዋናው ቁም ነገር ኅብረተሰባዊ ለውጥ ማምጣት ነው፡፡ እስካሁን ብቁ ወጣቶችና ምሁራን ወደ አመራር ለመምጣት የተደረገው ጥረት እምብዛም የሚደነቅ አልነበረም፡፡ ወጣቱ ራሱ ግን ተቀምጦ መጠበቅ የለበትም፡፡ የሚገባውን ለማግኘት መንቀሳቀስ አለበት፡፡ መጠየቅ አለበት፡፡ በእርግጥ ነባሩ አመራርም ዕድሉን መንፈግ የለበትም፡፡ ለማንኛውም ግምገማዎቹ ሲጠናቀቁ የምናየው ይሆናል፡፡

ሪፖርተር፡- በትግራይ እንደ ክልል ከድርጅቱ (ሕወሓት) ውጪ የተለየ አስተሳሰብ የሚያራምዱ ወጣቶችን መፈረጅና እንደ ጠላት የማየት አዝማሚያ ይታያል፡፡ ድርጅቱ በዚሁ የመታደስ እንቅስቃሴው የአቋም ለውጥ ያደርጋል ብለው ያምናሉ?

ዶ/ር ዓለም፡- ልዩነቱ እዚህ ላይ ነው፡፡ ደርግን እንኳን ማሸነፍ የሚቻል ከሆነ አሁን ምን ያቅታል? ዛሬ የተለየ አስተሳሰብ በመያዙ የሚታሰር ሰው የለም፡፡ አንድ ባለሥልጣን ላይጥመው ይችላል፡፡ ሊጥመው የግድ አይደለም፡፡ መጀመሪያ አንድ ሰው በትክክኛ መንገድ መሆን አለበት፡፡ በነገርህ ላይ ከኢሳት ጋር ሆነው የትግራይ ሕዝብ ከጎንደር ይውጣ የሚሉ ትግርኛ ተናጋሪዎች ነበሩ፡፡ የተለየ ሐሳብ የያዘ ሰው ግን በሐሳብ ነው የሚመታው፡፡ በንፅፅር ያየን እንደሆነ የፈለግነውን ተናግረን ተኝተን ነው የምናድረው፡፡ ለመቃወም አስበሃል፣ ሬዲዮ አዳምጠሃል ተብሎ ሰው የሚገደልበት አገር ነበር፡፡ እና አሁን ያለው ወጣት አጉርሱኝ ባይ ነው፡፡ መጎራረስ ቢኖር ጥሩ ነው፡፡ ሕወሓት በጣም የዋህ ድርጅት ሆኖ ወጣቶቹን አይዞህ ና እዚህ ሁን እንዲሁ ሁን ቢላቸው ጥሩ ነበር፡፡ ግን የወጣቱ ድርሻ ምንድነው? ለምንድነው በር እስኪከፈትልህ የምትጠብቀው? ራስህ ከፍተህ ለምን አትገባም? በሩ ጠባብ ከሆነም ትተህ መሸሽ የለብህም፣ እስከ መጨረሻ መታገል ነው፡፡ በእኔ እምነት ችግሮች አሉ፡፡ ወጣቱ ግን እየሸሸ ነው፡፡ ከታንክ ጋር የሚጋፈጥ ሰው የነበረበት አገር፣ አሁን በተለያዩ አቅጣጫዎች እየጠፋ ነው፡፡ አንዳንዱ በሱዳን አንዳንዱ በሶማሊያ እየሸሸ ነው ያለው፡፡ ይህ መሠረታዊ ለውጥ አያመጣም፡፡ ለውጥ የሚመጣው ችግሩን በመጋፈጥ ነው፡፡ ሰው እየተሰደደ፣ ፍትሕ እያጣ ዙረህ የምትሄድ ከሆነ ነገሩ እኔ ላይ እስካልደረሰ ነው፡፡ ስለዚህ መፍትሔው ያለው በራሳችን ውስጥ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በመማር ማስተማር ዙሪያ የትምህርት ጥራት ለማስጠበቅ ምን እየሠራችሁ ነው?

ዶ/ር ዓለም፡- የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በአገር ደረጃ የተዘጋጁ ፓኬጆች አሉ፡፡ እነሱን በመከተል የተሻለ የትምህርት ጥራት ለማረጋገጥ እንሞክራለን፡፡ ሆኖም በዚሁ ፓኬጅ ብቻ የትምህርት ጥራትን ማሻሻል አይቻልም፡፡ ጥራት በባህሪው ብዙ ጊዜ የሚወስድ ነው፡፡ በአንድ ጊዜና በአንድ ቦታ የሚረጋገጥ አይደለም፡፡ ስለሆነም ከዚህ ጋር በተያያዘ በተለይ በክልል ደረጃ፣ የትምህርት ቢሮ ዋና አገናኝ ሆኖ ከመቐለ ዩኒቨርሲቲና ከአክሱም ዩኒቨርሲቲ በጋራ  የምንሠራው ሥራ አለ፡፡ በውጤቱም ተማሪዎቻችን የተሻለ አካዴሚያዊ አቅም ይዘው እንዲወጡ ጥረት እያደረግን ነው፡፡ በተለይ ደግሞ በብዙ የትምህርት ማዕከላት እየተሠራበት ያለው የትምህርት ሠራዊት በመባል የሚታወቀው ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጠንክሮ የገባበት ነው፡፡ በዚህም በ2007 ዓ.ም. በነበረው የዩኒቨርሲቲዎች ደረጃ እኛ ጋር ከጀመሩ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል በአንደኛ ደረጃ የተቀመጥንበት ሁኔታ አለ፡፡ የተማሪዎች ቁጥር ብዛት አለው፡፡ ጥራቱንም የጠበቀ እንዲሆን ነው የተደረገው፡፡ እንደ አገር የሚጎድሉን ነገሮች እንዳለ ግልጽ ሆኖ በትምህርት ጥራት ላይ አንደራደርም፡፡ ተማሪዎችና መምህራን ተደጋግፈው የሚሄዱበትን ሥርዓት ነው የዘረጋነው፡፡ ችግሮች ሲታዩም አፋጣኝ መፍትሔ እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ ሌላው የትምህርት ጥራት ለማስጠበቅ አስፈላጊ የሚባሉ ግብዓቶች እንዲሟሉ አድርገናል፡፡ ለምሳሌ ተማሪዎቻችን በሙሉ በአንድ ጊዜ ቤተ መጻሕፍት መጠቀም ቢፈልጉ፣ ይህንን ፍላጎት ግምት ውስጥ ያስገቡ አራት ትልልቅ ቤተ መጻሕፍት ሠርተናል፡፡ ሁለቱ እያንዳንዳቸው 2,500 ተማሪዎች በአንድ ጊዜ የመያዝ አቅም ያላቸው ናቸው፡፡ ሁለቱ ደግሞ በአንድ ጊዜ ከ3,500 በላይ ተማሪዎች ማስተናገድ የሚችሉ ናቸው፡፡ ዲጂታል ላይብረሪ ደግሞ ከ500 በላይ ኮምፒዩተሮች ያሉትና በአገር ደረጃ በግንባር ቀደምነት የሚያስቀምጠንና ዘመናዊ የሆነ የቪዲዮ ፋሲሊቲ ያለው አለን፡፡ አንድ የታወቀ ፕሮፌሰር ጀርመን፣ አሜሪካ ወይም ደግሞ እንግሊዝ አገር ውስጥ ሆኖ እዚህ ትምህርት መስጠት ይችላል ማለት ነው፡፡ ይኼንን ቴክኖሎጂ አስገብተናል፡፡ በእርግጥ የእኛ መምህራን ብዙዎቹ ወጣቶች ናቸው፡፡ ጥልቅ ተሞክሮ ላይኖራቸው ይችላል፡፡ በእርግጥ በአካዴሚያዊ ብቃታቸው ከፍ ያሉትን ነው የምንመርጠው፡፡ ተሞክሮ የሌላቸው ግን በራሳቸውና በዩኒቨርሲቲው ጥረት እንዲለምዱ እየተደረገ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- የአካባቢውን ማኅበረሰብ በመደገፍና ምርምር በማካሄድ ላይስ ምን ያህል ተሳክቶላችኋል?

ዶ/ር ዓለም፡- ከ2004 ዓ.ም. ጀምረን ምርምሮች እያካሄድን ቆይተናል፡፡ በ2004 ዓ.ም. ዘጠኝ፣ በ2005 ደግሞ 23 እያልን መጥተን በ2008 ዓ.ም. 60 ምርምሮች አድርገናል፡፡ በእርግጥ በምርምሮች የጥልቀትና የስፋት ውሱንነት እንደሚኖረን እናምናለን፡፡ ምርምሮቹ በሁሉም ጉዳይ ላይ የሚካሄዱ ናቸው፡፡ ከተፈጥሮ ሳይንስ እስከ ማኅበረሰባዊ ሳይንስ በተለይም ደግሞ ከንብ አርቢነትና ከበለስ ጋር በተያያዘ ብዙ ጥናቶች አድርገናል፡፡ በርካታ የምርምር ርዕሶች ቀርበው በውድድር ያሸነፉት ላይ ነው ምርምር እንዲካሄድ የምናደርገው፡፡ እስካሁን ያልነካነው ዘርፍ የለም ማለት ይቻላል፡፡

ሪፖርተር፡- ብዙ ዩኒቨርሲቲዎች ምርምር ያካሂዳሉ፡፡ ሆኖም የምርምሮቹ ውጤቶች ተግባራዊ የሚደረጉበት ሁኔታና ችግር ፈቺ የሚሆኑበት ዕድል የለም ተብሎ ይተቻል፡፡

ዶ/ር ዓለም፡- ከአቅምና ከተቀባይ ወገን በኩል ደግሞ ከአመለካከት ችግር ጋር ተያይዞ ነው፡፡ በኅብረተሰባችን ውስጥ ችግሮች በጥናትና በምርምር ይፈታሉ የሚል ብዙም የተለመደ አመለካከት የለም፡፡ ለምሳሌ የምርምር ግምገማ ቀን አካሂደን ነበር፡፡ የምርምሮቹ ግኝቶች ለተጠቃሚው አካል እንዲደርሱ የሚደረግበት አሠራር ነው፡፡ ሆኖም የምርምሮቹ ተጠቃሚዎች እንኳን ሊጠቀሙባቸውም ብቻ ሳይሆን ተጠርተው የማይገኙበት ሁኔታም አለ፡፡ አንዱ ችግር ይኼ ነው፡፡ በአጥኚዎቹ በኩል ደግሞ የቀረበውን ሐሳብ ወደ መሬት እንዲወርድ የማድረግ ውሱንነት አለ፡፡ እሱም ሆኖ በርከት ካሉ አርሶ አደሮች ጋር በመሆን ከአርቢነትና ከአምራችነት፣ እንዲሁም ከጤና አጠባበቅ ጋር በተያያዘ ተግባራዊ የሆኑ ምርምሮች አሉን፡፡ የሚፈለገውን ያህል አልሄድንም እንጂ ምርምሮቹ ለሚመለከታቸው አካላት ደርሰው ተፈጻሚ የሚሆኑባቸው ጥሩ ጅምሮች አሉ፡፡

ሪፖርተር፡- በቅርቡ ለምሳሌ ከቱሪዝም መስህብነት ጋር ተያይዞ ዓለም አቀፍ ጉባዔ አካሂዳችሁ ነበር፡፡ አንዳንድ ከፍተኛ ባለሥልጣናትም በመድረኩ ላይ ተገኝተው የቀረቡ የምርምር ሐሳቦችን ተግባራዊ ለማድረግ ቃል ገብተው ነበር፡፡ በተለይ በትግራይ ክልል ሰፊ የእርሻ መሬት በሌለበት ግብርናን እንደ መር ፖሊሲ ከመጠቀም ይልቅ ቱሪዝምና ሌሎች ዘርፎች ላይ እንዲያተኩር ታስባላችሁ ወይ?

ዶ/ር ዓለም፡- ትክክል ነው፡፡ ዓላማው እሱ ነው፡፡ በእርግጥ በአገር ደረጃም ሆነ በክልል ደረጃ እርሻ ሳያድግ ለውጥ ይመጣል የሚል እምነት የለንም፡፡ መሠረተ ልማቱ የለንም፡፡ እያንዳንዱ ገበሬ መጀመሪያ በልቶ ማደር አለበት፡፡ ይኼ ሲባል ግን ግብርና ላይ ብቻ ተተክሎ፣ ሌሎች አማራጮች መታየት የለባቸውም ማለት አይደለም፡፡ ለምሳሌ በትግራይ ክልል ውስጥ ምሥራቅ ትግራይን ይዘህ እስከ መሀል ትግራይ፣ ገርዓልታ፣ ጉንዳጉንዶ፣ ደብረዳሞ ብዙ ቅርሶችና ፀጋዎች ነው ያሉት፡፡ የአክሱምን ትተን፡፡ አብዛኛው ሕዝባችን የሚተዳደረው በእርሻ በመሆኑ ባለበት እንዲለወጥና እንዲዘምን ማድረግ ያለብንም ቢሆን፣ ቱሪዝምና ሌሎች አማራጮች በዘላቂነት መዘንጋት የለባቸውም፡፡ አቅም ካልወሰነን በስተቀር በደንብ ከተሠራበት አውሮፓውያን ወደ ሌላ አገር አይሄዱም ነበር፡፡ ምክንያቱም ብዙ አስደናቂ ቅርሶች ነው ያሉን፡፡ አየራችን ምቹ ነው፡፡ ኅብረተሰባችን እንግዳ ተቀባይ ነው፡፡ ለአውሮፓውያን ደግሞ በጣም ቅርብ ነን፡፡ ሆኖም ፀጋዎቻችንን አሟጠን አልተጠቀምንበትም፡፡ ግብርና ራሱ እንኳን በበሬ ከማረስ አላወጣነውም፡፡ በብዙ መልኩ እስራኤልን ብትወስድ እንዴት በግብርና ልቀው እንደሄዱ ተመልከት፡፡ እዚህ እኛ ጋ ያለው መሬት በእጅጉ የተሻለ ነው፡፡ ነገር ግን አላዘመነውም፡፡ እሱንም ቢሆን አሟጠን እየተጠቀምንበት አይደለም፡፡

ሌሎች አማራጮች ግን ዞሮ ዞሮ የተማረ የሰው ኃይል ሲፈጠር ነው ወደ ኢንዱስትራላይዜሽን መሸጋገር የሚቻለው፡፡ ቱሪዝምም እንዳለ ነው፡፡ ቋንቋ የሚያውቅ፣ የሚመራ ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም ነው የትምህርት ጥራት ላይ ማተኮር አለብን የምንለው፡፡ ለሁሉም አማራጮች ማጠንጠኛው እሱ ስለሆነ፡፡ ለምሳሌ በዩኒቨርሲቲያችን ለዚህም ነው የአርኪዮሎጂ ዲፓርትመንት እንዲከፈት ያደረግነው፡፡ በእጃችን ውስጥ ያለውን ሀብት ገና አልተጠቀምንበትም፡፡ ከሌሎች ጋር አብረን መሥራት አለብን፡፡ ቅድም ያነሳኸው ዓለም አቀፍ የቅርስ ጉባዔ ለሦስተኛ ጊዜ አዘጋጅተናል፡፡ ብዙ ባለሥልጣናትና የሚዲያ አካላት ተገኝተዋል፡፡ የመጀመሪያው ደረጃ ምርምር ማድረግና ማስተዋወቅ ነው ብለን ስለምናምን ነው፡፡ በጣም የሚገርመው እስከ ዛሬ ኢትዮጵያ የሦስት ሺሕ ዓመት ሥልጣኔ እንዳላት ነበር የሚነገረው፡፡ አሁን እዚሁ አካባቢ በተገኘው ቅርስ ደግሞ ከአራት ሺሕ ዓመታት በፊት እርሻ እንደነበር የሚያመላክቱ ግኝቶች ተገኝተዋል፡፡ አፈ ታሪክ አይደለም፡፡ በፕሮፌሰሮች በካርበን ዴት ተረጋግጠው የተገኙ ናቸው፡፡ ፀሐይ የሞቀ ታሪክ አለን፡፡ ግን በቂ አይደለም፡፡ በሳይንሳዊ ጥናቶች መረጋገጥ አለባቸው፡፡ እስከ ዛሬ ስለአክሱምና የየሓ ሥልጣኔዎች ነበር የምናወራው፡፡ አሁን በጉለመኸዳ አካባቢ የተገኙ ከንግሥት ማክዳ ጋር የሚያያዙ ቤተ መንግሥቶችና ቅርሶች አሉ፡፡ እናም የቱሪዝም አቅማችንን ከፍ ለማድረግ በተለይ ሦስቱ ዩኒቨርሲቲዎች (አክሱም፣ መቐለና ዓዲግራት) በጋራ እየሠሩ ነው፡፡ ትግራይ እንደ ክልል ‹ኦፕን ኤር ሙዚየም› በመባል ነው የሚታወቀው፡፡ ዓለም እንዲያውቀው ግን ማድረግ ይገባል፡፡ ይህ አንድ ምሳሌ ነው፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃም፣ በክልል ደረጃም የምንሠራቸው በርካታ ሥራዎች አሉ፡፡

 

Standard (Image)

ዶናልድ ትራምፕ ፕሬዚዳንትነታቸው በምርጫ ቅስቀሳቸው ካስተጋቡት ይለይ ይሆን?

$
0
0

   እ.ኤ.አ. በ2015 በዲሴምበር ወር ቢዝነስ ኢንሳይደር የተባለው የአሜሪካ ጋዜጣ አንድ አስገራሚ ቃለ ምልልስ ይዞ ወጥቶ ነበር፡፡

   በዓመቱ ዴሞክራቷ ሒላሪ ክሊንተንን በማሸነፍ በዓለም በከፍተኛ ደረጃ አነጋጋሪ የሆነ አጋጣሚ የፈጠሩት ዶናልድ ጆን ትራምፕ፣ የሪፐብሊካን ፓርቲ ተወካይ ሆነው ለመወዳደር ትግል የሚያደርጉበት ወቅት ነበር፡፡

  በዋና ዋና ሚዲያ ተቋማት በመጀመርያ እምብዛም ግምት ያልተሰጣቸው ትራምፕ ተቀናቃኞቻቸውን እየጣሉ ቀስ በቀስ እየገሰገሱ ነበር፡፡ ዶናልድ ትራምፕ በቅስቀሳቸው ዘረኝነትን የተላበሱ፣ የአናሳ መብቶችን የሚያጎድፉና ስደተኞችን የሚያብጠለጥሉ መሆናቸው የበርካታ ሰዎችን ቀልብ ስቦ ነበር፡፡ ይሁንና በዚህ አያያዛቸው እንኳን የአሜሪካ ፕሬዚዳነት ሆነው ሊመረጡ የሪፐብሊካን አቻዎቸውንም ያሸንፋሉ ተብሎ የተሰጣቸው ግምት ዝቅተኛ ነበር፡፡

ታዋቂውን የፊልም ባለሙያ ማይክል ሙርን ያነጋገረው ቢዝነስ ኢንሳይደር ግን አስገራሚ ትንበያ ይዞ ወጥቶ ነበር፡፡ ማይክል ሙር በዚህ ቃለ ምልልስ፣ ‹‹እመኑኝ ትራምፕ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ለመሆን የሪፐብሊካን አቻዎቹን ያሸንፋል፤›› የሚል የብዙዎችን ግምት የሚፃረር አስተያየት ሰጥቶ ነበር፡፡

ማይክል ሙር የፖለቲካ አስተያየት በመስጠት ከሚታወቁት የፊልም ደራሲዎች መካከል ግንባር ቀደም ሲሆን፣ በዚሁ አስተያየቱ ግን በብዙዎች ተወቅሷል፡፡

‹‹የምነግራችሁ ቀልድ አይደለም፡፡ ወደ ጨለማው ዓለም እያመራን መሆናችንን ያኔ ሰዎች ሊሰማቸው ይጀምራል፤›› የሚል ማብራርያም ነበረበት አስተያየቱ ላይ፡፡ ማይክል ሙር ባለፈው ሐምሌ ወር  ደግሞ ከቢል ማኸር ጋር በቴሌቪዥን ባደረገው ቃለ ምልልስ ዋናዎቹ ሚዲያዎች የትራምፕ መገስገስን በቸልታ ማየታቸውን ተችቶ ነበር፡፡ ለኦስካር ተሸላሚው፣ ‹‹ይቅርታ የእናንተን መንፈስ እየረበሽኩ እንዳይሆን እንጂ ትራምፕ ቀጣዩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ይሆናል፤›› ብሎ ነበር፡፡ ማይክል ሙር የተለየ አቋም የያዘበትንና ትራምፕን በእርግጠኝነት ያሸንፋሉ ያለበትን ምክንያትም አብራርቷል፡፡ የመጀመርያው በአሜሪካ ዓበይት የሚላቸውን ክልሎች (ሚቺጋን፣ ኦሀዮ፣ ዊስኮንሲንና ፔንሲልቫንያ) ላይ ለማሸነፍ የተከተሉትን ስትራቴጂ ነው፡፡ ቢልየነሩ ትራምፕ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ከፕሬዚዳንትነት ወንበር የሚጠብቁት ምንም ቁሳዊ ነገር አለመኖሩን ለማሳመን፣ መላ ቤተሰባቸውን ይዘው ቅስቀሳ ውስጥ በመግባታቸው የአብዛኛውን መራጭ ልብ ሊያሸንፍ ይችላል በማለት ገምቶ ነበር፡፡ ‹‹አሜሪካን እንደገና ትልቅ አደርጋታለሁ፤›› በሚለው ባዶ ቅስቀሳቸው የሚታለል አሜሪካዊ ቁጥር ቀላል አይሆንም ብሎም ነበር፡፡

በአራተኛ ደረጃ የማይክል ሙር ግምት አሜሪካ ውስጥ ቁጣ ያደረባቸው ነጮች ድምፅ ያገኛሉ የሚል ነው፡፡ በተለይ ዕድሜያቸው ከ35 ዓመት በላይ የሆኑ ነጭ መራጮችን ቁጥራቸው 40 ሚሊዮን መሆኑንና በምርጫው ቀን ቁጣቸውን ለመግለጽ በእርግጠኝነት በነቂስ ወጥተው ድምፃቸውን ይሰጣሉ ብሎ ነበር፡፡

አፈንጋጩ ትራምፕ

ተመራጩ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ድላቸውን አስመልክተው በሰጡት አስተያየት ‹‹የሁሉም አሜሪካዊያን ፕሬዚዳንት እሆናለሁ፤›› ብለዋል፡፡ ቀደም ሲል በቅስቀሳ ወቅት ሴቶች፣ ሙስሊም አሜሪካኖች፣ ጥቁር አሜሪካኖች፣ ሜክሲካኖችና በአጠቃላይ ነጭ ያልሆኑ አሜሪካዊ ስደተኞች ላይ የሰጧቸው አስፈሪ አስተያየቶች ከአሜሪካ ጀምሮ እስከ አውሮፓ፣ እስያና አፍሪካ ድረስ ሥጋት የጫሩ በመሆናቸው የሁሉም አሜሪካኖች ፕሬዚዳንት እሆናለሁ የሚለው ንግግራቸው ከቀድሞው አወዛጋቢ ዘረኛ ንግግቸው በተቃራኒ፣ አሜሪካውያንን በሙሉ በእኩልነት አስተዳድራለሁ እንደማለት ተወስዷል፡፡  የእሳቸውን መመረጥ ተከትሎ ግን አንዳንድ ክስተቶች እየተስተናገዱ ይገኛሉ፡፡ ትራምፕ ሒላሪ ክሊንተንን አሸንፈው የአሜሪካ ተመራጩ ፕሬዚዳንት ከሆኑ በኋላ በአገሪቱ ዋና ዋና ከተሞች ከፍተኛ ተቃውሞ እየተካሄደ ይገኛል፡፡ የአውሮፓ ኅብረትን ጨምሮ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ትራምፕ በአንዳንድ ቅስቀሳዎች ላይ ለተጠቀሙባቸው አስተያየቶች ማብራሪያ እንዲሰጡ እየጠየቁ ናቸው፡፡ ከኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ጀምሮ ከበርካታ አገሮች የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክትም እየደረሳቸው ይገኛል፡፡ ከሩሲያም እንዲሁ፡፡

ትራምፕ 45ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሆነው ሲመረጡ አሜሪካ ከተለያዩ አገሮች ጋር የነበራትን ወዳጅነት ከአገሪቱ ጥቅም አንፃር እንደሚከልሱት፣ ቁጥር አንድ ባላንጣ ተደርጋ ከምትታየው ሩሲያ ጋር ሳይቀር አብረው እንዲሚሠሩ፣ አሜሪካ ከመሥራቾቹ መካከል የሆነችበትን የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (NATO) አባል አገሮች ደኅንነት የመጠበቅ ግዴታ እንደሚኖራት ተናግረዋል፡፡ ቀደም ሲል ግን ድርጅቱ ጊዜ ያለፈበት ነው ማለታቸው አይዘነጋም፡፡

ከሩሲያ ጋር አብረው ለመሥራት እንደሚፈልጉ የተናገሩት ትራምፕ አክራሪው እስላሚክ ስቴትን (አይኤስ) ለማጥፋት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ በቅስቀሳው ከኮነኗቸው ግለሰቦች መካከል ላለፉት ስምንት ዓመታት አሜሪካን በፕሬዚዳንትነት የመሩት ባራክ ኦባማን አንዱ ሲሆኑ፣ አይኤስን የፈበረኩ ናቸው፣ አሜሪካ ውስጥ አልተወለዱምና የመሳሰሉ አስተያየቶች መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡

በትራምፕ ድል ማግሥት አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል ተፎካካሪያቸው ሒላሪ ክሊንተን አንዷ ሲሆኑ፣ ‹‹የአሜሪካ ህልም ሁሉንም ዓይነት ሰው አቅፎ ለመያዝ ይህንን ያህል ሰፊ ነው፤›› ብለዋል፡፡ የኦባማም አስተያየት ተመሳሳይ ነው፡፡

ተፎካካሪያቸው የያዙት አቋም በዘረኝነትና በፋሽስትነት የሚመደብ ቢሆንም፣ የአሜሪካ ህልም ለእንዲህ ዓይነት ሰውም ቦታ ይሰጣል የሚል ይመስላል የእነ ኦባማ አስተያየት በሲኤንኤን እንደተተነተነው፡፡

ዘረኛው ፕሬዚዳንት?

ቮክስ የተባለው ታዋቂ ሌላ ሚዲያ ያስተናገደው አንድ ጽሑፍ፣ ‹‹የትራምፕ ማሸነፍ የማይበገርና የማይተመን የዘረኝነት ኃይልን አሳታዋሽ ነው፤›› ሲል አስፍሯል፡፡

አሸናፊው ትራምፕ እንዲህ ዓይነት አቋሞች ይዘው የአሜካውያንን ድምፅ ያሸነፉበት ምክንያት የተለያዩ ትንታኔዎች እየሰጡበት ይገኛሉ፡፡ ትራምፕ በአንዳንድ ጋዜጠኞች ከዘረኝነት ጋር በተያያዘ ለሚቀርቡባቸው ጥያቄዎች በምላሻቸው፣ ‹‹የሚገርማችሁ እኔ በዚህ ዓለም ካለው ዘረኛ ዝቅተኛው ነኝ፤›› በማለት ያስተባብላሉ፡፡

ኒውዮርክ ታይምስ ባሰባሰበው መረጃ መሠረት ግን፣ ዶናልድ ትራምፕ እ.ኤ.አ. ከ1970ዎቹ ጀምሮ እስከ 2011 ከአሥር በላይ የዘረኝነት ንግግሮችና ድርጊቶች ተመዝግቦባቸዋል፡፡ የመጀመሪያው እ.ኤ.አ. በ1973 በሪቻርድ ኒክሰን አስተዳዳር ዘመን የተፈጸመ ሲሆን፣ የትራምር ኩባንያ ለጥቁር ቤት አላከራይም በማለቱ ክስ ተመሥርቶባቸው ጥፋተኛ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ ሌላው እ.ኤ.አ. በ1990 ጆን ኦዶኔል በተባለው ደራሲ (የትራምፕ ፕላዛ ሆቴል ፕሬዚዳንት) የተጻፈው መጽሐፍ እንዳሰፈረው፣ ትራምፕ በጥቁር አካውንታንት ላይ የሰጡት አስተያየት ነው፡፡ ‹‹ጥቁር ሰዎች ገንዘቤን እየቆጠሩት ነው! በጣም ያስጠላል፡፡ ገንዘቤን እንዲቆጥሩት የምፈልገው ልቅም ያለ ሙሉ ልብስ የለበሱ አጭር ነጮች እንዲሆኑ ነው፤›› በማለት ጥቁሮች ሰነፎች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡  ትራምፕ ይህን መጀመሪያ ክደው የነበሩ ቢሆንም፣ እ.ኤ.አ. በ1997 በፕለይ ቦይ ኢንተርቪው አምነዋል፡፡ እንዲሁም ደግሞ በተመሳሳይ በሌላ ጥቁርና ሴት ሠራተኛ ላይ በፈጸሙት የዘረኝነት ድርጊት 200 ሺሕ ዶላር ካሳ መክፈላቸው ተረጋግጧል፡፡

አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ምርጫውን ለማሸነፍ ሲሉ ነው የሚል አቋም አላቸው፡፡ ከእነዚህም ውስጥ በአዲሱ የኢትዮጵያ መንግሥት የካቢኔ ሚኒስትር ሆነው የተሾሙት የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ፣ ምርጫው የአሜሪካ ሕዝብ ፍላጎት እስከሆነ ድረስ የኢትዮጵያ መንግሥት በውጤቱ ደስተኛ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ዶ/ር ነገሪ እንደሚሉት፣ ኢትዮጵያ ከአሜሪካ ጋር ያላት ግንኙነት ታሪካዊና ሥር የሰደደ በመሆኑ፣ በእንዲህ ዓይነት ንፋስ የሚነቃነቅ አይሆንም፡፡

በተለያዩ የዓለም ሕዝቦች ላይ መደናገጥ መፈጠሩን የገለጹት ዶ/ር ነገሪ፣ የምርጫ ቅስቀሰቸው ትንሽ ወጣ ያለና ፍርኃት መፍጠሩን ያምናሉ፡፡ ነገር ግን ‹‹የግሌ›› በሚሉት አስተያየት፣ ትራምፕ ምርጫውን ለማሸነፍ የተጠቀሙበት መንገድ እንደሆነ፣ በተለይ ባራክ ኦባማና ፓርቲያቸው ዴሞክራቲክ ፓርቲ እስከዛሬ የገነቡትን ገጽታ ከሥር መሠረቱ ለማፍረስ ታክቲክ እንደሆነ ያምናሉ፡፡ ዶ/ር ነገሪ ትራምፕ በቅስቀሳ ጊዜ የተናገሩዋቸው አንዳንድ አስተያየቶች በሥልጣን ዘመናቸው ተግባራዊ ይሆናሉ ብለው አያምኑም፡፡ ‹‹የአሜሪካ ሥልጣን በሕግ ነው የሚመራው፤›› ብለዋል፡፡ የሴኔቱ አባላትና ሌሎች የመንግሥት ተቋማት በጣም ጠንካራ የሥልጣን ማዕከላት መሆናቸውን አስታውሰዋል፡፡

አሜሪካውያን የልባቸውን የሚናገርላቸው አግኝተው ይሆን?

መስከረም መባቻ ላይ ዘ ኢኮኖሚስት “The Art of Lie” በሚል ርዕስ ያቀረበው ጽሑፍ፣ አንድ ፖለቲከኛ ሥልጣን ለመያዝ ምን ያህል ውሸት ሊደረድር እንደሚችል ያትታል፡፡ ትራምፕ የሒላሪ ክሊንተን ቤተሰቦች ከጆንኤፍ ኬኔዲ ግድያ ጀርባ እጃቸው እንዳለበት፣ ፕሬዚዳንት ኦባማ የአሜሪካዊ ዜግነታቸውን በተጭበረበረ ሰነድ ያገኙ መሆናቸውን ወዘተ. በመዘርዘር የመራጮችን ድምፅ ለማግኘት መዋሸታቸው እንደሚቀጥሉበት ይተነትናል፡፡ ጽሑፉ ከዚህ በፊት በዚህ መንገድ ወደ ሥልጣን የመጡ አገር አፍቃሪ የሚመስሉ ውሸታም ሌሎች መሪዎችን ለአብነት ይጠቅሳል፡፡

ዘ ኢኮኖሚስት  ለአቋራጭ ማሸነፊያ ‹‹ስሜት ቀስቃሽና እውነትን የረገጡ ንግግሮችን ማድረግ ነው የሚያስፈልገው፤›› ይላል፡፡ እውነትን አጣመውና ውሸትን አጣጥመው የሚወዳደሩ ፖለቲከኞች አደገኞች ናቸው የሚለው ዘ ኢኮኖሚስት፣ በምርጫ ቅስቀሳ የሚወሩ ነገሮች እምብዛም በሕግ የማያስጠይቁ መሆናቸው ይህንን ለመሰለ አቀራረብ የሚጋብዝ እንደሆነ ይደመድማል፡፡

በቅስቀሳ ወቅት በውሸት የተገባ ቃል በተለያዩ መንገዶች እንደሚጋለጥ ግልጽ ይሁን እንጂ፣ በውሸት ቅስቀሳ ወደ ሥልጣን መምጣት ግን ለዘመናት ወደኋላ ወስዶ ለጭቆና ሊዳርገን ይችላል ይላል፡፡ ‹‹ትራምፕ በውሸት ቅስቀሳዎች ለማሸነፍ ይበቃሉ፤›› ሲልም አትቷል፡፡ ይህንን በመቃረን የነጭ አሜሪካውያን ድምፅ ችላ ተብሎና ሰሚ አጥቶ ቆይቷልና ትራምፕ ትክክለኛ ስትራቴጂ መከተላቸውን የሚናገሩት ደግሞ ማይክል ኮትል የተባሉ ጸሐፊ ናቸው፡፡

‹‹በእርግጥ ትኩረት የሚሹ የኅብረተሰብ ክፍሎች ነበሩ፡፡ የተለየ ቀለም ስላላቸው ሳይሆን የአገሪቱ ኢኮኖሚ ጫፍ ሆነው ቆይተዋል፤›› ብለዋል፡፡ ትራምፕ በክርክራቸው የተሟገቱላቸው ነጭ አሜሪካውያን በተለያዩ መጤዎችና ጥቁር አሜሪካውያን ምክንያት ተጎጂ መሆናቸውን ኮትል ይገልጻሉ፡፡

ኢትዮጵያዊው ሀብቶም በርሀ ዶናልድ ትራምፕ እንደሚያሸንፉ ያምን ነበር፡፡ ‹‹ሌሎች የሪፐብሊካን ተፎካካሪዎችን በሚያሸንፉበት ወቅት ተሸናፊ ፖለቲከኞች ሊናገሩት ያልፈለጉትን፣ ግን ውስጣቸው የነበረን ነገር ትራምፕ አውጥቶ ተናግሮታል፤›› ይላል፡፡ ‹‹ተወደደም ተጠላም ነጭ አሜሪካውያን ለዘመናት በተገነባው ሥርዓት ደስተኞች አይደሉም፡፡ አሁን የልባቸውን የሚናገርላቸው ተገኝቶላቸዋል፤›› ይላል፡፡

አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት ግን ትራምፕን የመረጡ ነጭ አሜሪካውያን በኢኮኖሚ ከሌሎች የተሻሉ እንጂ የወረዱ አይደሉም፡፡ ለምሳሌ አንድ ጥናት የአንድ መካከለኛ ነጭ አሜሪካዊ ገቢ 72 ሺሕ ዶላር መሆኑን፣ ትራምፕን ያልመረጠ የአንድ መካከለኛ ዓመታዊ ገቢ 62 ሺሕ ዶላር ነው ይላል፡፡

ኤዲሰን ሪሰርች የተባለ በኤቢሲ ኒውስ፣ በአሶሼትድ ፕሬስ፣ በሲቢኤስ ኒውስ፣ በሲኤንኤን፣ በፎክስ ኒውስና በኤንቢሲ ኒውስ ጥምረት የተቋቋመ ድርጅት ይፋ ያደረገው መረጃ የሁለቱን ተወዳዳሪዎች የድጋፍ መሠረት አሳይቷል፡፡ በዚህ መረጃ መሠረት ለዶናልድ ትራምፕ 53 በመቶ ወንዶች ድምፅ ሲሰጡ፣ ለሒላሪ ክሊንተን 41 በመቶ ናቸው ድምፅ የሰጡት፡፡ 58 በመቶ ነጭ ወንዶች ትራምፕን ሲመርጡ 37 በመቶ ብቻ ሒላሪን መርጠዋል፡፡ ዶናልድ ትራምፕ ስምንት በመቶ ብቻ የጥቁሮችን ድምፅ ሲያገኙ፣ ሒላሪ ክሊንተን በተቃራኒው 88 በመቶ ድጋፍ አግኝተዋል፡፡ ትራምፕ 29 በመቶ ድምፅ ከስፓኒሽ ተናጋሪዎች ሲደርሳቸው፣ ሒላሪ 65 በመቶ ድምፅ አግኝተዋል፡፡ ከ120 ሚሊዮን በላይ መራጮች ድምፅ በሰጡበት በዚህ ምርጫ፣ በናሙናነት የተወሰደው የ25 ሺሕ መራጮች መሆኑን ኤዲሰን ሪሰርች አስታውቋል፡፡ ይህ በፆታ፣ በዘርና በዕድሜ ላይ የተሠራ መረጃ 53 በመቶ የሚሆኑ ነጭ ሴቶች ትራምፕን ሲመርጡ፣ 43 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ ለሒላሪ ክሊንተን ድምፅ ሰጥተዋል ይላል፡፡ በምርጫው በሕዝብ ድምፅ ሒላሪ 60,274,974 ሲያገኙ፣ ትራምፕ ደግሞ 59,937,338 ድምፅ አግኝተዋል፡፡ ይሁንና ‘ኤሌክቶራል ቮት’ በሚባለው የምርጫ ሥርዓት መሠረት ትራምፕ 290 በማግኘት 228 ያገኙትን ሒላሪን ማሸነፍ ችለዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌዴራሊዝም መምህር አቶ ናሁሰናይ በላይ ግን ዶናልድ ትራምፕ በኅብረተሰቡ ውስጥ ያለውን ስሜት አጥንተው ጥቅም ላይ አውለውታል ብለው ያምናሉ፡፡ ፋሺዝም እንደገና ይመለስ እንደሆነ አመላካች አድርገው የተመለከቱት አቶ ናሁሰናይ፣ የኢኮኖሚ ችግር ቢኖርም እንደዚህ ዓይነት እልም ያለ የዘረኝነት አስተሳሰብ ችግሩን ወደ ውጭ ለመግፋትና ሌሎች ላይ ለማላከክ መዋል እየተለመደ ነው ይላሉ፡፡ የትራምፕ ቅስቀሳም ሆነ የምርጫው ውጤት የነጭ አሜሪካውያንን  የበላይነት ለማንሰራራት መሠረት እየያዘ ለመምጣቱ አመላካች ነውም ይላሉ፡፡

በቅርቡ እንግሊዝ ከአውሮፓ ኅብረት እንድትወጣ የተደረገው እንቅስቃሴ፣ በዴንማርክ፣ በፈረንሣይና በስዊዘርላንድ ተመሳሳይ አዝማሚያዎች ማሳየቱን ለዚህ እንደ አብነት አቶ ናሁሰናይ ይጠቅሳሉ፡፡

ሌላው ለየት ያለ ጉዳይ ደግሞ እ.ኤ.አ. ከ1789 እስከ 2016 ድረስ ባሉት 227 ዓመታት አሜሪካን በፕሬዚዳንትነት ከመሩት ጆርጅ ዋሽንግተን እስከ ባራክ ኦባማ በፖለቲካዊና ወታደራዊ ልምዳቸው መታወቃቸው ነው፡፡ የአሁኑ ተመራጭ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ደግሞ ከሁለቱም የሌሉበት የመጀመሪያ መሪ መሆናቸው አነጋግሯል፡፡ ዶናልድ ትራምፕ ከአወዛጋቢነታቸውና ከነውጠኝነታቸው ጋር ሥልጣን ላይ ሲወጡ፣ በምርጫ ቅስቀሳቸው  ጊዜ ያስተጋቡዋቸውን ተግባራዊ ያደርጋሉ? ወይስ በሲስተሙ ይዋጣሉ? የሚለው ለጊዜው የዓለም መነጋገሪያ የሆነ የወቅቱ ጉዳይ ነው፡፡  

 

Standard (Image)

‹‹ከኢትዮጵያ ጋር ትብብር ለማድረግ የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት ጥያቄዎች እየተከበሩ መሆናቸውን ማረጋገጥ እንፈልጋለን›› ስቴፈን ዲዮን፣ የካናዳ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር

$
0
0

የካናዳ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ስቴፈን ዲዮን ከሰሃራ በታች ወዳሉ አገሮች ኦፊሴላዊ ጉብኝት ሲያደርጉ የመጀመርያቸው ነው፡፡ በናይጄሪያና በኬኒያ ያደረጉትን ጉብኝት አዲስ አበባ ላይ የቋጩት የውጭ ጉዳይ ሚንስትሩ፣ በኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ፣ ከአዲሱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁና ከሌሎች የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር ተገናኝተው ተነጋግረዋል፡፡

ጉብኝቱን አስመልክተው በካናዳ ኤምባሲ የሰጡት መግለጫ እንደሚያመለክተው፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ፣ በአፍሪካ ቀንድ ስላለው የፀጥታና የፖለቲካ ሁኔታ፣ እንዲሁም በሁለትዮሽ የኢኮኖሚ ትብብር ላይ አንዳንድ ጉዳዮችን አንስተው ምክክር አድርገዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ስቴፈን ዲዮን፣ በተለይ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና ከውጭ ጉዳይ ሚንስትሩ ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ ጋር ባደረጉት ሰፋ ያለ ውይይት ቀደም ሲል በኢትዮጵያ ውስጥ ተከስቶ ስለነበረው ሁከት፣ ችግሩ ከቁጥጥር ውጪ እንዳይወጣ የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተመለከተ መነጋገራቸውን የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

በተለይ በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች በተፈጠረው ሁከት ሕይወታቸውን ላጡ ዜጎች ሐዘናቸው የገለጹ ሲሆን፣ አገሪቱ የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት በምታደርገው ጥረት ከአገራቸው ካናዳ የሚጠበቀውን ድጋፍ ሁሉ ለማድረግ ቃል ገብተዋል፡፡ አንዳንድ ቅድመ ሁኔታዎች ግን ያስቀመጡ ይመስላል፡፡

ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ጋር በነበራቸው ቆይታ በቅርቡ በኢትዮጵያ ስለታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ፣ አዋጁን እያስፈጸመ ስላለው ኮማንድ ፖስት፣ እንዲሁም የአዋጁን አፈጻጸም በተመለከተ በዝርዝር መነጋገራቸው የታወቀ ሲሆን፣ በተለይ ሁለት ጉዳዮች ላይ አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ያነሱቸው ነጥቦች ችግሩን ለመፍታት መንግሥት እየወሰደ ስላለው ዕርምጃ ነው፡፡ ችግሩን በተመለከተ ከሞላ ጎደል ኢትዮጵያውያንን ያካተተ ሰፊ ሰላማዊ ውይይት እንዲካሄድና ባለድርሻ አካላት በሙሉ ተሳታፊ እንዲሆኑ ካነሱቸው ነጥቦች የመጀመሪያው ነው፡፡ በዚህ ውይይት በተለይ ወጣቶች ልዩ ትኩረት እንዲያገኙ አጽንኦት ሰጥተውበታል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በውይይት ተሳትፎ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ሊያካሂዳቸው ያሰባቸውን ማሻሻያዎች በተመለከተም በተለይ የወጣቶችን ተሳትፎ ከፍ የሚያደርጉና ፋይዳ እንዲኖራቸው ጠይቀዋል፡፡

የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት መሪ ድርጅቱ ኢሕአዴግ በጥልቀት ከመታደስ አንስቶ፣ በመንግሥት ደረጃ የተለያዩ አሳሪ የተባሉ ሕጎችን ለማየትና የሕገ መንግሥቱን አንቀጾች ጭምር ለማሻሻል ቃል ገብቷል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ስቴፈን ዲዮን ማሻሻያዎቹን በተመለከተ በሰጡት አስተያየት፣ የኢትዮጵያን ሕዝብ በሚጠቅም መንገድና ወቅቱን ያገናዘበ እንዲሆን ጠይቀዋል፡፡

‹‹ባደረግናቸው ውይይቶች ሕዝቡ በሚደረጉ የዴሞክራሲ ውይይቶች ተሳታፊ እንዲሆንና ገንቢ ማሻሻያ እንደሚያስፈልግ እምነቴን ገልጫለሁ፤›› ብለዋል፡፡

በካናዳ ኤምባሲ መግለጫ በሰጡበት ወቅት ከጋዜጠኞች ለቀረቡባቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሲሰጡ፣ ጉብኝቱ በተለይ በአፍሪካ ቀንድ ያለውን የፖለቲካ አለመረጋጋት ለማሻሻል ካናዳ ከኢትዮጵያ ጋር በጋራ በመሥራት መሆኑን የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ በተለይ በሶማሊያና በደቡብ ሱዳን ስለሚሰማሩ የሰላም አስከባሪ ኃይሎች በጋራ ለመሥራት ማሰባቸውን ተናግረዋል፡፡ ‹‹በሰላምና በፀጥታ ጉዳዮች ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በጋራ መሥራት እንፈልጋለን፤›› በማለት፣ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ብሎም በአፍሪካ ሰላምን በማስከበር ወደር የሌላት አገር በመሆኗም አገራቸው በጋራ ለመሥራት እንደምትገደድ አስረድተዋል፡፡

የአካባቢውን ሰላም፣ መረጋጋትና የኢትዮጵያን የውስጥ ጉዳይ በተመለከተ በተለይ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ጋር ባደረጉት ውይይት የሴቶችና የወጣቶችን እኩል ተጠቃሚነት፣ የውኃ አጠቃቀም፣ የሥራ ፈጠራ፣ የቴክኖሎጂ፣ የማዕድን ፍለጋ፣ እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥ አገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ከምትተባበርባቸው መካከል ግንባር ቀደም መሆናቸውን በመግለጫቸው ወቅት አብራርተዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ እንዳሉት ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በወሳኝ የፖለቲካና የዴሞክራሲ ጉዳዮች ላይ አጽንኦት ሰጥተው መክረዋል፡፡ በተለይ ደግሞ የጋዜጠኞች፣ የጦማሪያንና የተቃዋሚዎች በነፃነት የመንቀሳቀስ መብታቸው እንዲከበር ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም መነጋገራቸውን አስረድተዋል፡፡

‹‹ከኢትዮጵያ ጋር ትብብር ለማድረግ እነዚህ የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት ጥያቄዎች በውል እየተከበሩ መሆናቸውን ማረጋገጥ እንፈልጋለን፤›› ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያ የተገኘውን ልማትና ዕድገት ለማስቀጠል ካናዳ የበኩሏን እንደምታደርግ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ‹‹የሕዝቡ ነፃነት የበለጠ በተከበረ ቁጥር ልማቱ የበለጠ ይጨምራል፤›› ብለዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከዴሞክራሲ ግንባታ ጋር በተያያዘ ያነሱዋቸውን ሥጋቶችና የሰጡዋቸውን አስተያየቶች በተመለከተ፣ ከአንዳንድ የሲቪክ ማኅበረሰቦች ጋር ባደረጉት ጥልቅ ውይይት ማንሳታቸውንም ማወቅ ተችሏል፡፡

በተለይ ደግሞ የዴሞክራሲውን ምኅዳር ማስፋት፣ የሐሳብ ነፃነትን ማክበርና የሰዎች መሠረታዊ ነፃነቶች መጠበቅ ለሚታሰበው የፖለቲካ ውይይት ጠቃሚ ቅድመ ሁኔታዎች መሆናቸውን መግለጫቸው ያትታል፡፡

በአካባቢው ሰላምና ደኅንነት፣ በሽብርተኝነት፣ በንግድና በኢንቨስትመንትና በመሳሰሉት ኢትዮጵያ ከካናዳ ጋር ያላት ግንኙነት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ለሚኒስትሩ እንደገለጹላቸው በመንግሥት ሚዲያዎች የተዘገበ ሲሆን፣ ከዴሞክራሲና ከሰብዓዊ መብቶች ጋር ተያይዞ ከሚኒስትሩ ስለተነሱ ሥጋቶች የኢትዮጵያ መንግሥት ምላሽ ምን እንደሆነ ማወቅ አልተቻለም፡፡

የሁለቱ አገሮች ግንኙነት እ.ኤ.አ. ከ1956 የሚጀምር ነው፡፡ ካናዳ ኢትዮጵያን ከሚረዱ ግንባር ቀደም ለጋሽ አገሮች መካከል ነች፡፡ ካናዳ በኢትዮጵያ ኤምባሲዋን የከፈተችው እ.ኤ.አ. በ1957 ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ደግሞ በካናዳ ኤምባሲዋን እ.ኤ.አ. በ1962 ከፍታለች፡፡ እ.ኤ.አ በ2007 ካናዳ ለኢትዮጵያ የሰጠችው ዕርዳታ 90.52 ሚሊዮን ዶላር ነበር፡፡ ይህ ዕርዳታ ከኢትዮጵያ የሁለትዮሽ ዕርዳታ ሰጪዎች አራተኛዋ አገር ያደርጋታል፡፡

እንዲሁም ደግሞ ከኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ግጭት በኋላ፣ በሁለቱ አገሮች ድንበር ከተሰማሩት የተመድ የሰላም አስከባሪ ወታደሮች መካከል 450 ያህሉ የካናዳ ወታደሮች እንደነበሩ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

Standard (Image)

የሕገ መንግሥቱን ቀጣይነት የማረጋገጥ የቤት ሥራዎች

$
0
0

በቅርቡ ካቤኔያቸውን በድጋሚ ያዋቀሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በጽሕፈት ቤታቸው የሚገኙ አማካሪዎችን በተመለከተ ከሰጡት መግለጫ ጋር በተያያዘ፣ የልዩ አማካሪዎች ዕጣ ፈንታ ምን ሊሆን ይችላል በሚል ዜጎች መጠየቃቸው አልቀረም፡፡ ‹‹ጠቅላይ ሚኒስትሩን በአንድ ጉዳይ ማማከር ከአሁን በኋላ ይቀራል፡፡ ይልቁንም የአማካሪ ቡድኑ ወጣት ምሁራንን በሚያሳትፍ መልኩ ደግሞ ይዋቀራል፤›› ብለዋል፡፡

በዚህም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ልዩ የሕግ አማካሪ ሆነው በማገልገል ረጅም ዓመታት ያስቆጠሩት ዶ/ር ፋሲል ናሆምን ጨምሮ የልዩ አማካሪዎች ዕጣ ፈንታ ምን እንደሚሆን ተጠባቂ ሆኗል፡፡ የዶ/ር ፋሲል የመንግሥትን ከፍተኛ አመራር የማማከር ሚና ከንጉሡ ጊዜ የሚጀምር ነው፡፡ ዶ/ር ፋሲል እ.ኤ.አ. በ1968 ከያኔው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ (አሁን አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) በሕግ የመጀመሪያ ዲግሪ ካገኙ በኋላ፣ በአሜሪካ ከሚገኘው የግል ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪያቸውን በሕግ አጠናቀዋል፡፡ ዶ/ር ፋሲል የሕግ መምህር በመሆን አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ማገልገል ጀመሩ፡፡ የሕግ ትምህርት ቤትን በዲንነት ከመሩ ታዋቂና ተፅዕኖ ፈጣሪ ሰዎች መካከል የሚመደቡም ናቸው፡፡

ዶ/ር ፋሲል ቆይተው እ.ኤ.አ. በ1974 የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት ላቋቋመው የሕገ መንግሥት አርቃቂ ኮሚቴ አማካሪ ሆነዋል፡፡ እርግጥ ነው ይህ ረቂቅ ሕገ መንግሥት ሳይፀድቅና ወደ ሥራ ሳይገባ የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት በአብዮት ለመውደቅ ተገዷል፡፡ ‹‹በወቅቱ ከነበረው ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ንጉሣዊ ሥርዓቱ በሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት እንዲመራ ማድረግ የተሻለው አማራጭ ነው የሚል አቋም ይዤ ነበር፤›› በማለት ዶ/ር ፋሲል የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ላይ ከጥቅምት 28 እስከ 29 ቀን 2009 ዓ.ም. መቀሌ በሚገኘው አክሱም ሆቴል ባዘጋጀው ዓለም አቀፍ ኮንፈረንስ መክፈቻ ቀን ላይ ገልጸዋል፡፡

ከዚህ ያልተሳካ ሙከራ በኋላ አገሪቱ ለ13 ዓመታት ያህል ያለ ሕገ መንግሥት ነው የተዳደረችው፡፡ ይሁንና ደርግም ከመውደቁ ጥቂት ዓመታት ቀደም ብሎ በኋላ እ.ኤ.አ. 1987 የፀደቀውን የኢሕዲሪ ሕገ መንግሥት የማርቀቅ ሒደት ውስጥ ገብቶ ነበር፡፡ ዶ/ር ፋሲል ከሌሎች ባለሙያዎች ጋር በመሆን የማርቀቅ ሒደቱ ላይ ተሳትፈዋል፡፡ ዶ/ር ፋሲል፣ ‹‹ኢትዮጵያ በወቅቱ ትመራበት ከነበረው ሥርዓት ወደ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት ለማሸጋገር መልካም ዕድል እነደሆነ ነበር የወሰድኩት፤›› ብለዋል፡፡ ዶ/ር ፋሲል የኢሕዲሪ ሕገ መንግሥት ርዕዮተ ዓለማዊ ጫና ቢኖርበትም፣ የሃይማኖት ነፃነትን ጨምሮ በርካታ መንፈሳዊና የሰብዓዊ መብቶች ድንጋጌዎችን ያካተተ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ ‹‹ረቂቁን ሕገ መንግሥት ለፖሊት ቢሮው አስረክበናል፡፡ ቢሮው በሚፈልገው ጉዳይ ላይ ለውጥ አድርጓል፡፡ ነገር ግን ከሰብዓዊ መብት ጋር የተያያዙ ድንጋጌዎችን እንዳለ በሙሉ ተቀብሏል፤›› ብለዋል፡፡

ዶ/ር ፋሲል በንጉሡ ጊዜም ሆነ በደርግ ዘመን በሙያቸው በሰጡት አገልግሎት እንደሚኮሩ ቢገልጹም፣ በሥራ ላይ ስላለው ሕገ መንግሥት የማርቀቅና የማስፈጸም ሒደት ላይ ስላላቸው አስተዋጽኦ ሲናገሩ ስሜታቸው ሞቅ ይላል፡፡ ኢሕአዴግ ሥልጣን እንደተቆጣጠረ ሕገ መንግሥት የማፅደቅ ሒደቱን እንዲያማክሩ ጠይቋቸዋል፡፡ ‹‹በወቅቱ እኔ ከልቤ የምፈልገው ዓይነት ሕገ መንግሥት በመሆኑ አብሮ ለመሥራት የራስ መተማመን ነበረኝ፡፡ በማርቀቅ ሒደቱም ሆነ በአፈጻጸም ረገድ ባለኝ አስተዋጽኦ ደስተኛ ነኝ፣ ኩራትም ይሰማኛል፤›› ብለዋል፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕግ አማካሪ ከመሆናቸው በፊት መንግሥትን በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች አገልግለዋል፡፡ የፍትሕና የሕግ ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር፣ የሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ መሥራች ፕሬዚዳንትም ነበሩ፡፡ የሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔን ባገለገሉባቸው ዓመታት ብዛትም ተወዳዳሪ የላቸውም፡፡ ዶ/ር ፋሲል ‹‹Constitution for a Nation of Nations›› በሚል ርዕስ መጽሐፍም አሳትመዋል፡፡

‹‹ከአንድ ሕገ መንግሥት ወደ ሌላ ሕገ መንግሥት ወዲያ ወዲህ ማለት ዕጣ ፈንታዬ ሆኗል፤›› በማለት በፈገግታ ታጅበው ከተለያዩ ሕገ መንግሥቶች ጋር ስላላቸውና ስለነበራቸው ቁርኝት ተርከዋል፡፡ በአደጉት አገሮች በለውጥና በአለመረጋጋት ውስጥም ቢሆን ሕገ መንግሥት ሳይለወጥ መቀጠሉ የተለመደ ነው፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ልምድ እንደሚያሳየው በአደጉ አገሮች መንግሥታት በተቀያየሩ ቁጥር ሕገ መንግሥቶች ይቀያየራሉ፡፡ ከዚህ አንፃር ዶ/ር ፋሲል ስላለፉት ሕገ መንግሥታት ያላቸው ቅርብ ዕውቀትና አረዳድ የተሻሉ እሴቶችን፣ መርሆዎችንና ተቋማትን ወደ አዲሱ ሥርዓት ከማሸጋገር አንፃር አንድ አዎንታዊ ጎን እንዳለው የሚገልጹ አሉ፡፡

ይሁንና የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ መምህርት የሆኑት አቶ ሰይፈ ኃይሉ ለተለያዩ ሥርዓቶች ዶ/ር ፋሲል ሳያቋርጡ አገልግሎት እንዴት ሊሰጡ እንደቻሉ ጠይቀዋል፡፡ አቶ ሰይፈ፣ ‹‹ፈጽሞ የተለያዩ ፍልስፍናዎችን የሚያካትቱ ሦስት መንግሥታትን እንዴት ሊያማክሩ ቻሉ?›› ሲሉ ጥያቄያቸውን አቅርበዋል፡፡ ‹‹ላለፉት ሥርዓቶች ሙያዊ አገልግሎት በመስጠት ኩራት ይሰማኛል፡፡ በምችለው መጠን ለማማከር ሞክሬያለሁ፡፡ ሁሌም ቢሆን የምትሠራው ባለው ተጨበጭ ሁኔታ ሥር ነው፡፡ በሃያኛው ክፍለ ዘመን እየኖርክ የ21ኛው ክፍ ለዘመን ሰው ልትሆን አትችልም፤›› ብለዋል፡፡

በመቀሌው ኮንፈረንስ የአቅራቢዎቹን ሐሳብ በመደገፍ ወይም በመንቀፍ የሚሰማቸውን ሐሳብ በነፃነት በማጋራት ረገድ አቶ ሰይፈ ብቻቸውን አልነበሩም፡፡ ኮንፈረንሱ ብዙም ባልተለመደ ሁኔታ ትክክለኛ የአካዴሚ ከባቢ የተስተዋለበት ነበር፡፡ በመሰብሰቢያ አዳራሹ የተገኙት አቅራቢዎችና ተሳታፊዎች በንቃት ሐሳባቸውን ለማጋራት ዳተኝነት አላሳዩም፡፡ ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ለተገኙ ሁነቶችና እሱን ተመርኩዞ ሊፈጠር ስለሚገባው ስምምነትም ያላቸውን ታማኝነት በአብዛኛው አጋርተዋል፡፡ አንጋፋና ከፍተኛ ልምድ ያካበቱት የሕገ መንግሥትና የሰብዓዊ መብት የሕግ ባለሙያዎች እነ ዶ/ር ፋሲል ናሆም፣ ዶ/ር አሰፋ ፍሰሐ፣ ዶ/ር ጌታቸው አሰፋና አቶ ጌታሁን ካሳ ሲጠቀሱ ከወጣት የሕግ ባለሙያዎች እነ ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ፣ አቶ ወንድወሰን ዋኬኔ፣ አቶ የማነ ካሳና አቶ ጀቱ ኢዶሳ ጋር በመጣመር ለኮንፈረንሱና ለተነሱት ርዕሰ ጉዳዮች ነፍስ ዘርተዋል፡፡

በሥራ ላይ ያለው ሕገ መንግሥት ቀጣይነት

የመቀሌው ኮንፈረንስ ‹‹The FDRE Constitution at 20 and Beyond: Towards an Enduring Constitution›› በሚል ርዕስ ጭብጥ የተካሄደ ነው፡፡ በኮንፈረንሱ ላይ ተገኝተው የጥናት ውጤቶቻቸውን ያጋሩት ኤክስፐርቶች ሕገ መንግሥቱ ቀጣይነት እንዲኖረው ቅቡልነት ሊኖረው እንደሚገባና ለሕገ መንግሥቱ ታማኝ የሆኑ ዜጎች የአብላጫውን ድምፅ መያዝ እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡

‹‹Legitmacy, Integrity and Vitality: Perspectives on the Endurance of the FDRE Constitution›› በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት የሕገ መንግሥት ኤክስፐርቱ ዶ/ር ጌድዮን ጢሞቴዎስ፣ የሕገ መንግሥት አርቃቂዎች የሕጎች ሁሉ የበላይ የሆነው ሰነድ ለረጅም ዘመናት እንዲያገለግል አስበው ቢያዘጋጁትም ቀጣይነቱ ግን በተለያዩ ተያያዥነት ባላቸው ምክንያቶች ላይ የተንጠለጠለ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

ዶ/ር ጌድዮን ለሕገ መንግሥት ቀጣይነት አስፈላጊ ከሆኑ ቅድመ ሁኔታዎች ውስጥ ተቀዳሚው ቅቡልነት እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ ቅቡልነት ኅብረተሰቡ ሕገ መንግሥቱን ተገቢና አሳማኝ ነው ብሎ በመቀበሉ የሚገለጽ ነው፡፡ ሌላኛው ምክንያት በሕገ መንግሥቱ ድንጋጌዎችና በተግባር መሬት ላይ ባለው ሁኔታ መካከል ያለው መናበብ ነው፡፡ ሦስተኛው ምክንያት ወይም ቅድመ ሁኔታ ደግሞ የሕገ መንግሥቱ የማደግ አቅም ነው፡፡ ይህም ለአዳዲስ ተጨባጭ ሁኔታዎች በሚሰጠው ምላሽ በዋናነት የሚገለጽ ነው፡፡

ሕገ መንግሥቱ ከኢሕአዴግም ባሻገር ቀጣይነት እንዲኖረው ከማድረግ አኳያ እንቅፋት ሊሆኑ የሚችሉ ጉዳዮች እንዳሉ ዶ/ር ጌድዮን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም በቅድሚያ የጠቀሱት ከሕገ መንግሥቱ ማርቀቅ ሒደት ጋር በተያያዘ ያለውን የቅቡልነት ክፍተት ነው፡፡ በማርቀቅ ሒደቱ የኢትዮጵያዊ ማንነትን ያቀነቅን የነበረው ቡድንን ጨምሮ ቁጥራቸው ቀላል የማይባል ቡድኖች መገለል፣ በተወካዮች ምክር ቤትና በሕገ መንግሥታዊ ጉባዔው ኢሕአዴግ ውስጥ ሕወሓት የበላይነት አለው ተብሎ መታመኑና ዜጎች ተደራጅተው ውጤታማ ተሳትፎ ማድረግ አለመቻላቸው የዚህ የቅቡልነት ክፍተት መገለጫዎች እንደሆኑም አስገንዝበዋል፡፡

ከዶ/ር ጌድዮን በተቃራኒ ዶ/ር ፋሲል ሕገ መንግሥቱ ቅቡልነት የጎደለው አይደለም ሲሉ ተከራክረዋል፡፡ ዶ/ር ፋሲል ቅቡልነት የሚመነጨው ከሕዝቡ ፈቃድ እንደሆነ አስረግጠዋል፡፡ በ27,000 ቀበሌዎች 15 ሚሊዮን ዜጎች በሕገ መንግሥት ማርቀቅ ሒደቱ መሳተፋቸው የሚያረጋግጠው የቅቡልነት ችግር አለመኖሩን ነው ሲሉም ሞግተዋል፡፡ ዶ/ር ፋሲል ‹‹The Making of the FDRE Constitution: Exploring the Original Legitimacy›› በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጽሑፍ የፖለቲካ መረጋጋት ሌላኛው ቁልፍ የቅቡልነት መገለጫ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

አንድ ተሳታፊ እንደ ኢሠፓ፣ መኢሶንና ኢሕአፓ ያሉ ፓርቲዎች በሒደቱ እንዳይሳተፉ ለምን ተከለከሉ ሲሉ ለዶ/ር ፋሲል ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ ‹‹ሕዝቡ የታገለው እነሱን ለመጣል ነው፡፡ አባላቱ ወንጀል ፈጽመው ነበር፡፡ አመራሩም በቁጥጥር ሥር ውሎ ነበር፡፡ በተለይ ኢሠፓ ዕድል ካገኘ ጦርነቱን መቀጠል ነበር የሚፈልገው፡፡ እኛ ደግሞ ሰላም ነበር የምንፈልገው፡፡ እናም እነሱን አካተን ጦርነት ውስጥ እንግባ እንዲሉን ዕድል መስጠት ነበረብን?›› በማለት ዶ/ር ፋሲል መገለላቸው ተገቢ ነው ብለው ተከራክረዋል፡፡

በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ የሕግ መምህር የሆኑት አቶ ሙሉ በየነ ሕገ መንግሥት ካለፈው ሥርዓት የተለየ አዲስ ሥርዓት ለማምጣት ዋነኛ መሣሪያ ከመሆኑ አኳያ፣ ካለፈው ሥርዓት ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያለውን የተወሰነ አካል ከሒደቱ ማግለሉ የማይቀር ነው ሲሉ ተከራክረዋል፡፡ ዶ/ር ጌድዮን ግን በጉዳዩ ላይ የተለየ አመለካከት ነው ያላቸው፡፡ ‹‹ካለፈው ሥርዓት ጋር ቁርኝት አለው በማለት ቁጥሩ ቀላል የማይባል ማኅበረሰብ ክፍልን ማግለል አይቻልም፡፡ ባለፈው ሥርዓት ያለውን መንገድ ለመከተል ብንመርጥ እንኳን በምን ያህል መጠን እንለወጥ? በምን አቅጣጫ እንለወጥ? የሚሉት ጉዳዮች ራሳቸው ሁሉን አቀፍ፣ አሳታፊና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መልኩ መወሰን አለባቸው፤›› ብለዋል፡፡ አቶ ሙሉ ፓርቲዎቹ በአካል ባይወከሉም ሐሳባቸውስ አልተስተናገደም ነበር ወይ ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ ዶ/ር ጌድዮን ከኢሕአዴግ ሕገ መንግሥታዊ ራዕይና ፍላጎት የተለየ አመለካከት የነበራቸው አካላት ሐሳብም ጭምር አልተስተናገደም ሲሉ ተከራክረዋል፡፡ ከኮንፈረንሱ ጥናት አቅራቡዎች አንዱ አቶ ምስክር ታሪኩ የቅቡልነት ዝቅተኛው መሥፈርት ምን እንደሆነ ጠይቀዋል፡፡ ዶ/ር ጌድዮን በጥያቄው ላይ በሰጡት አስተያየት፣ ‹‹ቅቡልነትን በቁጥር ልትለካው አትችልም፡፡ ሕዝቡ ሕገ መንግሥቱ ባቋቋማቸው ተቋማት ላይ አመኔታ አጥቶ ቅሬታና በደሉን ለማሰማት ኢ ሕገ መንግሥታዊ አካሄድን ከመረጠ ግን የቅቡልነት ችግር እንዳለ ግልጽ ነው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹Making constitutions Endure from Below: Issues of Constitutional Loyalty in Multinational Federal Politics›› በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሑፋቸውን ያቀረቡት የሕገ መንግሥት ኤክስፐርትና የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የሕግ መምህር አቶ ወንድወሰን ዋኬኔ ሕገ መንግሥታዊ ታማኝነት የአንድ ሕገ መንግሥት ቀጣይነትን ከሚወሰኑ ጉዳዮች አንዱ መሆኑን በዝርዝር አስረድተዋል፡፡

ለሕገ መንግሥት ታማኝ መሆን ማለት የሕገ መንግሥቱን ሁሉንም አንቀጾች መቀበል እንዳልሆነ፣ በአፈጻጸሙ ላይም የሚስተዋሉ ክፍተቶችን መተቸት ከሕገ መንግሥታዊ ታማኝነት ጋር የሚያገናኘው ነገር እንደሌለ ተከራክረዋል፡፡

አቶ ወንድወሰን በኢትዮጵያ ሕገ መንግሥቱን በተመለከተ ሁለት ጽንፍ የያዙ አቋሞች እንዳሉ አስታውሰዋል፡፡ ኢሕአዴግ ሕገ መንግሥቱን ፍፁም አድርጎ መስበኩም ሆነ ተቃዋሚዎች የችግሮች ሁሉ ምንጭ ሕገ መንግሥቱ ነው ማለታቸው የሚያዋጣ እንዳልሆነ አመልክተዋል፡፡

ዶ/ር ጌድዮንና ሌሎች ጥናት አቅራቢዎች ከሕገ መንግሥቱ ቅቡልነት ባልተናነሰ በሕገ መንግሥቱ መሠረት ጉዳዮችን የመከወን ችግር ጎልቶ መውጣቱን ገልጸዋል፡፡ ለዚህ እንደ አብነት በዶ/ር ጌድዮን የተጠቀሱት ከፌዴራል መዋቅሩ ጋር ተጻራሪ የሆነ የውሳኔ አሰጣጥ ሥርዓት፣ አገሪቱ በተግባር ወደ አንድ ፓርቲ ሥርዓት መሸጋገሯ፣ በየቀኑ የሚከሰቱ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ጥሰቶችና በሕገ መንግሥቱ ነፃና ገለልተኛ ሆነው የተቋቋሙ ተቋማት ወገንተኝነት እያደገና እየጎላ መምጣቱ ናቸው፡፡

በኮንፈረንሱ ‹‹Federalism and the Evolving Conceptions of Unity and Diversity in Ethiopia: Capturing the Emerging Issues›› በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሑፋቸውን ያቀረቡት ዕውቁ የፌዴራሊዝም ኤክስፐርትና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌዴራል ጥናት ተቋም ኃላፊ ዶ/ር አሰፋ ፍሰሐ፣ በቅርቡ አገሪቱ የገጠማት ችግር በሕገ መንግሥቱ መሠረታዊ ሐሳቦችና በተግባር መካከል ልዩነት ከመኖሩ ጋር የተያያዘ ገጽታ እንዳለው አስረድተዋል፡፡

ዶ/ር አሰፋ ሕገ መንግሥቱና የፌዴራል መዋቅሩ ለቡድኖች ራስን በራስ የማስተዳደር መብት ለማጎናፀፍ፣ የዜጎችን ሕይወትና ኑሮ ለማሻሻል፣ አንፃራዊ ሰላምና መረጋጋት ለመፍጠር ያደረገው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ቢሆንም አሁንም የሚቀሩ ብዙ ነገሮች እንዳሉ አስገንዝበዋል፡፡ በተለይ ከፍተኛ ትኩረትና የቅቡልነት መሣሪያ እየሆነ በመጣው የልማት ጉዳይ ላይ ዜጎችና ቡድኖች በበቂ ሁኔታ ተሳታፊ አለመደረጋቸው ችግሮችን ይዞ እየመጣ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ የልማታዊ መንግሥት የዕድገት ሞዴል አውራ ፓርቲ በመፍጠሩ ኢኮኖሚው ሊጠቀም የሚችልበት ዕድል ቢኖርም፣ የሐሳብ ብዝኃነትን በመድፈቅ የራሱ የሆነ ሌላ ችግር መምዘዙንም አስረድተዋል፡፡

የፌዴራል ሥርዓቱ ከተቋማት ይልቅ በፖለቲካ እንደሚመራ በኦሮሚያና በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ከተከሰተው አደጋ ማየት እንደሚቻልም ዶ/ር አሰፋ አስገንዝበዋል፡፡ በተለይ በዚህ ወቅት ከፍተኛ ሚና እንዲጫወቱ በማሰብ በሕገ መንግሥቱ የተቋቋሙ ተቋማት ድምፃቸው አለመሰማቱ የችግሩን መጠን እንደሚያሳይም ጠቁመዋል፡፡

ዶ/ር ጌድዮንም በተመሳሳይ ሕገ መንግሥቱ ለአዳዲስ ሁኔታዎች ምላሽ እየሰጠና እያደገ እንዳይሄድ እንደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት፣ የሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔና ፍርድ ቤቶች ያሉ ተቋማት፣ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሥር ያሉ ምሁራንና የሕግ ባለሙያዎች የሚሰበቅባቸውን አለመፈጸማቸው የራሱን አሉታዊ አስተዋጽኦ ማድረጉንም ጠቅሰዋል፡፡

ሕገ መንግሥቱ ከኢሕአዴግ በኋላ እንዳይቀጥል የሚያደርጉ በርካታ ክፍተቶች ያሉ ቢሆንም፣ የፖለቲካ ስፖንሰሩ ኢሕአዴግ ሥልጣን ቢለቅ እንኳን መቀጠል ያለበት ስለመሆኑ ተከራክረዋል፡፡ ሦስት መሠረታዊ መከራከሪያ ነጥቦችንም ዘርዝረዋል፡፡ የመጀመሪያው ሕገ መንግሥቱ ያስከተለው የፌዴራል መዋቅርና ራስን በራስ የማስተዳደር መብት ቀላል ቁጥር በሌላቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ከፍተኛ ተቀባይነት ያለው መሆኑና ከፍተኛ ከበሬታ የሚሰጣቸው የቤተሰብ የመብት ጥበቃ የተካተቱበት መሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛ ሕገ መንግሥታዊ ባህል ለመፍጠርና ለማስፋፋት ቀጣይነት የሚፈለግ በመሆኑ ነው፡፡ ሦስተኛ አዲስ ሕገ መንግሥት ለማርቀቅ መሞከር ዋጋው እጅግ ከፍተኛ ነው፣ የመከፋፈል አደጋ ያመጣል፣ የፖለቲካ ዋጋውም ቀላል አይሆንም ብለዋል፡፡ 

Standard (Image)

የሶማሊያን ዕጣ ፈንታ የሚወስነው ምርጫና የአልሸባብ እንቅስቃሴ

$
0
0

በ1983 ዓ.ም. የዚያድ ባሬ መንግሥት ከፈራረሰ በኋላ፣ ሶማሊያ ለረዥም ዓመታት በእርስ በርስ ጦርነትና በተለያዩ ግጭቶች ውስጥ አልፋለች፡፡ ሰሞኑን ደግሞ የመጀመሪያውን አገራዊ ምርጫ ለማድረግ በዝግጅት ላይ ትገኛለች፡፡

የዓለም አቀፉን ሚዲያ ቀልብ የሚስበው የሶማሊያ የውስጥ ጉዳይ አለመረጋጋት ብቻም አይደለም፡፡ የዚያድ ባሬ መንግሥት ከተባረረ በኋላ መንግሥት አልባ ሆና ለረዥም ጊዜያት የዘለቀችው ሶማሊያ ከቀዝቃዛው የዓለም ጦርነት ማብቃት በኋላ የዓለምን ሰላምና ደኅንነት እያናጋ ያለው የሽብርተኝነት መናኸሪያም ሆና ነበር፡፡

9/11 በመባል በሚታወቀውና እ.ኤ.አ. በ2001 በአሜሪካ በተፈጸመው ጥቃትና በኬንያና በታንዛንያ ኤምባሲዎቿ የሽብር ጥቃት ሰለባ የሆነችው አሜሪካ፣ ሽብርተኛነትን በመዋጋት ግንባር ቀደም ሆና የምትንቀሳቀስ አገር ናት፡፡ ነገር ግን የሶማሊያ ሁኔታ የራስ ምታት ሆኖባት ቆይቷል፡፡

ከመቼውም ጊዜ በላይ ግን የሶማሊያ ኢስላማዊ ቡድኖች እ.ኤ.አ. በ1999 እንደፈጠሩት ኅብረት ተደራጅተው አያውቁም፡፡ በወቅቱ የሶማሊያ እስላማዊ ፍርድ ቤት ኅብረት በመባል የሚታወቀው ቡድን መላ የደቡብ ሶማሊያ ክፍል ተቆጣጥሮ፣ በኢትዮጵያ ላይ ጅሃድ እስከማወጅ የደረሰበት ሁኔታ አይዘነጋም፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥትም የቡድኑን መገስገስ በትዕግሥት አልተመለከተው ከአንድም ሁለቴ የሽግግር መንግሥቱን ግብዣ እንደ ሽፋን በመጠቀም ጣልቃ በመግባት ድርጅቱን መበታተን ችሎ ነበር፡፡ ሆኖም በወቅቱ የኅብረቱ የወጣቶች ክንፍ እንደ አዲስ በመደራጀት፣ አልሸባብ የተባለውን የሽምቅ ተዋጊ ቡድን አቋቁሞ ይኼው እስከ ዛሬ እየተዋጋ ይገኛል፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን (ተመድ) ዕውቅና ያገኘው ደካማው የሽግግር መንግሥት በወቅቱ ከተለያዩ ጎሳዎች ውክልና አግኝቶ እንዲቋቋም የተደረገው፣ ከመነሻው የኢትዮጵያ መንግሥትና የአሜሪካ መንግሥት ስፖንሰር ባደረጉት የሰላም ሒደት ነበር፡፡

በኢትዮጵያ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነትም የአሜሪካ መንግሥት እጅ አለበት ተብሎ ይታማ የነበረ ሲሆን፣ ሁለቱም አገሮች የሽግግር መንግሥቱን ከአሸባሪ ቡድኖች የመጠበቅ ኃላፊነት እንዳላቸው ሲገልጹ ነበር፡፡ የዘንድሮ የአውሮፓውያን ዓመት ግን ለፌደራላዊ የሽግግር መንግሥቱ ዘመን የሚያበቃበት ነው ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በዚህም የሽግግር መንግሥቱን የሚተካ መደበኛ መንግሥት ይቋቋማል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ምርጫው በኅዳርና በታኅሳስ ወራት ላይ ይከናወናል፡፡

ሒደቱ ምን ይመስላል?

እ.ኤ.አ በ2012 የተቋቋመው ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ፓርላማ ከ135 የጎሳ መሪዎች የተውጣጣ ነው፡፡ በቅርቡ በሚካሄደው ምርጫ ግን የታህታይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ቁጥር ወደ 275 ከፍ የሚል ሲሆን፣ ለላዕላይ ምክር ቤት ደግሞ 54 አባላት ይመረጣሉ፡፡ ይኼው ምክር ቤት ዋናው የአገሪቱ የሥልጣን ባለቤት ተደርጎ የሚታይ ነው፡፡

የምርጫ ሒደቱ የውክልናና የቀጥተኛ ግጽታ ሲኖረው፣ በአገሪቱ ባለው አለመረጋጋትና የፀጥታ ሁኔታ ሳቢያ በቀጥታ ሊካሄድ የታሰበውን ምርጫ ወደ ውክልና  ምርጫ እንዲተካ ተደርጓል፡፡ ያም ሆነ ይህ ባለፈው መስከረም ሊካሄድ ታቅዶ የነበረው ምርጫ ሁለት ጊዜ ተላልፎ በቅርቡ ይጠናቀቃል ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡ ተመራጭ የፓርላማ አባላት በመጪው ታኅሳስ ወር የአገሪቱን ፕሬዘዳንት ይመርጣሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡

የተለያዩ አካላት የምርጫው ሒደት በተለያዩ ውስጣዊና ውጪያዊ ምክንያቶች ሊደናቀፍ ይችላል በማለት ሥጋታቸውን እየገለጹ ነው፡፡ የአሁኑ ፓርላማ አባል የሆኑት አብዲወሊ ካንያር ግን ሒደቱ ላይ እስከ አሁን የቀረበ ከፍተኛ ቅሬታ አለመኖሩን ለአሜካ ድምፅ ራዲዮ ጣቢያ ተናግረዋል፡፡ ‹‹በእርግጥ ምርጫ ነውና ቅሬታ አይኖርም ብሎ መገመት ይከብዳል፤›› ብለዋል፡፡ በአደጉት አገሮች ሳይቀር ዕንቅፋቶችና ቅሬታዎች በምርጫ ወቅት እንደሚቀርቡም አስታውሰዋል፡፡ የተመድ ዋና ጸሐፊ የሶማሊያ ልዩ መልዕክተኛ የሆኑት ማይክል ክቲንግ ግን፣ ምርጫውን በማካሄድ ሒደት አንዳንድ እንቅፋቶች እየገጠሙ እንደሆነ ነው የሚናገሩት፡፡

መልዕክተኛው እንደሚሉት ከሆነ፣ ከሦስት አሥርት ዓመታት ጦርነትና ሕግ አልባነት ጠቅልላ ለመወጣት በመጣር ላይ ባለችው ሶማሊያ በተለይ አልሸባብ ከተባለው የሽምቅ ተዋጊ አሸባሪ ቡድን እያደረሰ ያለው የፀጥታ መስተጓጎል ሒደቱን ጥያቄ ውስጥ ከቶታል፡፡ ሒደቱን በተገቢ መንገድ ሊያከናውኑ የሚችሉ ተቋማት ስለመኖራቸውም ጥያቄ ያነሳሉ፡፡ ‹‹በጥርጣሬ የምመለከተው ጉዳይ ቢሆንም፣ በጥሩ ሁኔታ ይጠናቀቃል የሚል ተስፋ አለኝ፡፡ ምናልባት ግን አንድ ሰው እንዳለኝ ከሆነ የምርጫ ሒደቱ እስከዛሬ በምድራችን ከታዩ የምርጫ ሒደቶች እጅግ የተወሳሰበ ሊሆን ይችላል፤›› ብለዋል፡፡

አካሄዱ ላይ ጥያቄ የሚያነሱም አይጠፉም፡፡ ለምሳሌ ፕሮፌሰር አብዲ ስማታር የተባሉ በሜኔሶታ ዩኒቨርሲቲ የመልክዓ ምድር መምህር ሶማሊያዊ፣ ‹‹ይኼ ምርጫ ሳይሆን መረጣ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ሌሎች ቅሬታዎችም ከዓለም አቀፍ ድርጅቶች እየተሰነዘሩ ይገኛሉ፡፡ ባለፈው ጥቅምት ወር ተመድ፣ የአፍሪካ ኅብረትና የአውሮፓ ኅብረት ባወጡት የጋራ መግለጫ ከወንጀል፣ ከአሸባሪና ከሁከት ድርጊቶች ጋር በተያያዘ ስማቸው የሚነሳ ግለሰቦች ለላዕላይ ምክር ቤት ዕጩ ሆነው መቅረባቸው ያሠጋናል ብለዋል፡፡

ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች ግን ከዕጩዎቹ መካከል ባለፉት አምስት ዓመታት በፍርድ ቤት ወንጀለኛ ሆኖ ያልተገኘ ግለሰብን ከሒደቱ ለማግለል የሚያስችል መንገድ የለም ይላሉ፡፡

አልሸባብና ምርጫ

የኢትዮጵያ ወታደሮች ወደ ሶማሊያ ከዘለቁ ጊዜ ጀምሮም ሆነ በኋላ፣ የአፍሪካ ኅብረት  ሰላም አስከባሪ ኃይል በአገሪቱ ከተሰማራ ጊዜ ጀምሮ አልሸባብ ከዋና ዋና የአገሪቱ ይዞታዎች ለቆ ወጥቶ ነበር፡፡ ከአካባቢው የሚወጡ ሪፖርቶች እንደሚያመለክቱት ቡድኑ ከፍተኛ ሽንፈት እየገጠመው እንደ ድርጅት ህልውናው አደጋ ላይ ወድቆ ነበር፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የሶማሊያ ምርጫ እየቀረበ በሄደ ቁጥር፣ የኢትዮጵያ ወታደሮች በቁጥጥራቸው ሥር የነበሩ የአገሪቱን ደቡባዊ ዋና ከተሞች ለቀው እየወጡ መሆናቸው እየተዘገበ ነው፡፡ እስካሁን የኢትዮጵያ መንግሥት ለዚህ ለማፈግፈግ ውሳኔው የገፋፋው ነገር ግልጽ ባይሆንም ዕርምጃው ለአልሸባብ መልካም ዕድል እንደፈጠረለት እየተነገረ ነው፡፡

አልጄሪያዊው ጋዜጠኛ ሐምዛ አህመድ በቅርቡ የኢትዮጵያ ወታደሮች የለቀቁዋቸው አካባቢዎች ድረስ በመሄድ ባጠናቀረው ዘገባ፣ ከ4,500 በላይ የኢትዮጵያ ወታደሮች ከአሥር በላይ ዋና ዋና ከተሞችን ባለፉት አራት ወራት ውስጥ ለቀው መውጣታቸውን ገልጿል፡፡

አራቱ ከተሞች የተለቀቁት ደግሞ ባለፈው አንድ ወር ውስጥ ነው ብሏል፡፡ እንደ ሐምዛ ሪፖርት፣ አልሸባብ አንዳች ጥይት መተኮስ ሳያስፈልገው የተለቀቁ አካባቢዎች መልሰው በመያዝ ላይ ናቸው፡፡

     ሐምዛ ያነጋገራቸው የአልሸባብ መሪዎች የኢትዮጵያ ወታደሮች አካባቢውን ለቀው እየወጡ ያሉት በአገራቸው ውስጥ በተፈጠረው አመፅ ምክንያት ነው ብለው ያምናሉ፡፡

የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት የቀድሞ ኃላፊ ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ ግን፣ ኢትዮጵያ ወታደሮችዋን ለማፈግፈግ የተገደደችው አገር ውስጥ ካለው ሁኔታ የሚያያዝ እንዳልሆነ ተናግረው ነበር፡፡ እሳቸው እንዳሉት፣ መንግሥት ዕርምጃው ለመውሰድ የተገደደው በፋይናንስ ምክንያት ሲሆን፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በተራው የራሱን አስተዋጽኦ ሊጫወት ይገባል ብለዋል፡፡

ባለፈው ሳምንት ለሪፖርተር ማብራሪያ የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ፣ አልሸባብ የተባለው የሽብር ቡድን እያደረገ በሚገኘው መስፋፋት የኢትዮጵያ መንግሥት ሥጋት የለውም ማለታቸው አይዘነጋም፡፡ በአፍሪካ ኅብረት የሰላም አስከባሪ ኃይል ውስጥ የሚገኘው የኢትዮጵያ ሠራዊት አሁንም በሥራው ላይ መሆኑን፣ ከዚህ ውጪ ያለው ደግሞ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ ጥንቃቄና ኃላፊነት የተሞላበት ስለሆነ የአልሸባብ መስፋፋት በኢትዮጵያ ላይም ሆነ በአካባቢው ሥጋት አይፈጥርም ብለዋል፡፡ 

Standard (Image)

በደቡብ ሱዳን የሪክ ማቻር ተፅዕኖ እያበቃ ይሆን?

$
0
0

ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ በደቡብ ሱዳን ተቀናቃኝ ወገኖች መካከል በአዲስ አበባ የተፈረመው የሰላም ስምምነት ብዙ ተስፋ ተጥሎበት ነበር፡፡ ከቀናት በፊት ዶ/ር ሪክ ማቻር ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገቡ ተከልክለው ከቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት መመለሳቸው ተስፋው ለመበላሸቱ ማሳያ ነው፡፡

ከሱዳን ለመገንጠል ከ20 ዓመታት ያላነሰ ጊዜ የተዋጉት ደቡብ ሱዳናውያን እስካሁን ድረስ ሰላም አላገኙም፡፡ ደቡብ ሱዳን በአፍሪካ ኅብረት አዲሲቷ አገር ተብላ በተመዘገበችበት በአንድ ዓመት ውስጥ የተጀመረው ሁከት፣ ኋላ ላይ ወታደራዊና የብሔር ግጭት እየያዘ ቢመጣም በሁለቱ ቁንጮ ተቀናቃኝ መሪዎች መካከል በተከሰተ አለመግባባት የተጀመረ ነበር፡፡

በነፃይቱ አገር የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪርና በምክትላቸው ዶ/ር ሪክ ማቻር መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ግን፣ ዛሬም ድረስ አገሪቱን ሰላም ነስቷታል፡፡

በኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል ውስጥ ከሚገኙ ኑዌሮች በመወለዳቸው ምክንያት ዶ/ር ማቻር በኢትዮጵያ ይደገፋሉ ለሚለው ወቀሳ ማስረጃ አድርገው የሚያቀርቡት አሉ፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ግን የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በየነ መንግሥታት ድርጅት (ኢጋድ) አማካይነት የማስታረቅ ሚናው በገለልተኝነት ሲወጣ መቆየቱን ያምናል፡፡

ለረዥም ጊዜ የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በመሆን ያገለገሉትና በአሁኑ ወቅት በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር የሆኑት አቶ ሥዩም መስፍን፣ ጉዳዩን በልዩ መልዕክተኛነት ይዘውት ላለፉት አራት ዓመታት ዘልቀዋል፡፡ ሁለቱን መሪዎችና ከጀርባቸው ያሉ ወታደራዊና የፖለቲካ ኃይሎችን በገለልተኝነት የማስታረቅ ኃላፊነት በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በዋናነት ለኢትዮጵያ የተተወ ቢመስልም፣ የኢጋድ አባል የሆኑ ሌሎች ጎረቤት አገሮች በተለይ ኬንያና ኡጋንዳ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሽምግልናው አካል ለመሆን ሞክረዋል፡፡  

የኢጋድ ሸምጋይ ቡድንን በደባልነት የምትመራው ኬንያና እንዲሁም ኡጋንዳ በአብዛኛው ጊዜ ድጋፋቸውን የሚሰጡት ሥልጣን ላይ ላለው ለሳልቫ ኪር መንግሥት እንደሆነ ይነገራል፡፡ በተለይ ኡጋንዳ በኢጋድ ዕውቅና ያልተሰጠው ወታደራዊ ኃይል በጁባ ማስፈሯን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

ከሰላም ሒደቱ ጀርባ ስሙ ገኖ የሚሰማው የኢትዮጵያ መንግሥት ሁለቱም መሪዎች በሸራተን አዲስ የሰላም ስምምነት እንዲፈርሙ ማድረጉ ይታወሳል፡፡ በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ላይ ተፅዕኖ ፈጥረዋል የሚሉ አንዳንድ ሪፖርቶች ወጥተው እንደነበር አይዘነጋም፡፡

በስምምነቱ መሠረት ከቆዩበት ሌላ አገር ወደ ጁባ የተመለሱት ሪክ ማቻር እምብዛም ሳይቆዩ ባለፈው ሳምንት ከቦሌ ኤርፖርት ወደ ደቡብ አፍሪካ ተገደው እንደመለሱ መደረጋቸው እያነጋገረ ይገኛል፡፡ በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በቅርቡ ጁባ በሄዱበት ወቅት ሥልጣን ላይ ካለው መንግሥት ጋር ለመተባበር እንደሚገደዱ፣ በተለይ ዶ/ር ማቻር ከኢትዮጵያ ግዛት ተነስተው ደቡብ ሱዳንን እንዲያጠቁ እንደማይፈቅዱ መናገራቸውን የሱዳን ትሪቡን ዘገባ ያመለክታል፡፡ ዶ/ር ማቻር በፕሬዚዳንቱ የፀጥታ ኃይሎች ጥቃት እንደደረሰባቸውና በዚሁ ሳቢያ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ለሞት መዳረጋቸውን በቅርቡ መዘገቡ ይታወሳል፡፡ በስምምነቱ መሠረት ሊፈጸም የታሰበው የፖለቲካና የጦር ኃይል ውህደትም ውድቅ ሆኗል፡፡

የሁለቱ ተቀናቃኝ ወገኖች በቅርቡ በተወካዮቻቸው አማካይነት በአዲስ አበባ ያደረጉት ውይይት መጠነኛ መግባባት ፈጥሯል ተብሎ የነበረ ቢሆንም፣ ዛሬም ድረስ የታሰበው ለውጥ ተግባራዊ አልሆነም፡፡ ማቻርም በድጋሚ ተቃውሞአቸውን ከደቡብ ሱዳን ውጪ በመሆን እያካሄዱ ይገኛሉ፡፡

የተመድ ዋና ጸሐፊና የፀጥታው ምክር ቤት ይህንን ጥቃት ተከትሎ በድጋሚ የተከሰተው የእርስ በርስ ጦርነት እንዲቆምና ሰላም አስከባሪ ኃይል በአካባቢው እንዲሰማራ ቢወስኑም፣ ተግባራዊነቱ ጥያቄ ውስጥ ገብቷል፡፡ ለችግሩ ተጠያቂ ናቸው የተባሉተ የሁለቱ ጎራ መሪዎች ላይ ሊጣል የታሰበው ማዕቀብና በዘር ማጥፋት ወንጀል እንዲጠየቁ በአሜሪካ የቀረበው ሐሳብም በእንጥልጥል ላይ ይገኛል፡፡ በቅርቡ ግን በማቻር ላይ ማዕቀብ መጣል አለበት ብላለች፡፡

የእርስ በርስ ጦርነቱ ተባብሶ ቀጥሏል

የፀጥታው ምክር ቤት በተለይ ሐምሌ ወር በድጋሚ የተቀሰቀሰውን ጦርነት አጣሪ ቡድን በመላክ ያጣራ ቢሆንም፣ አፋጣኝ ዕርምጃ አልወሰደም ተብሎ እየተተቸ ነው፡፡ ማት ዌልስ የተባሉ የአካባቢውን ግጭት የሚከታተሉ ተመራማሪ፣ ‹‹ምክር ቤቱ ሺሕ ነገር ከሚያወራ በቀውሱ ተጠያቂዎች ላይ ማዕቀብ ቢጥል ምን አለበት?›› ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡

በድጋሚ የተቀሰቀሰውን ግጭት በማብረድ ሰላምን ወደነበረበት መመለስ ካልተቻለና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ አፋጣኝ ምላሽ ካልሰጠ፣ እስከ ዛሬ የተደከመበት የሰላም ሒደትና የሽግግር ፖለቲካ ሙሉ ለሙሉ አደጋ ላይ እንደሚወድቅ የሚሠጉ በርካቶች ናቸው፡፡ የዛሬው ቀውስ ሲከሰት እንደሚችል የፖለቲካ ተንታኞች አስቀድመው አስጠንቅቀው ነበር፡፡

የተመድ ዋና ጸሐፊ ባን ኪ ሙን ከሐምሌ ወር ጀምሮ እየተከናወነ ላለው ቀውስ፣ በአካባቢው የሚገኘው የተመድ ሰላም አስከባሪ ኃይልን ወቅሰዋል፡፡ በደቡብ ሱዳን ያለው ከጎረቤት አገር የተውጣጣ ይኸው ሰላም አስከባሪ ኃይል በኬንያ ጄኔራል ይመራ የነበረ ሲሆን፣ በጁባና በአካባቢው የተቃጣውን ጥቃት መከላከል አልቻለም በማለት ጄኔራሉን አሰናብተዋል፡፡ የኢትዮጵያን ጨምሮ የጎረቤት አገሮች የተውጣጡበት ሰላም አስከባሪ ኃይል በአግባቡ አልመሩም ተብለው ከቦታቸው ጄነራሏ የተነሱባት ኬንያ ግን፣ አንድ ሺሕ ወታደሮቿን እንደምታስወጣ አስፈራርታ ነበር፡፡ ከመካከላቸው 100 ወታደሮችን በቅርቡ ማስወጣቷም ተሰምቷል፡፡

ተመድ በፀጥታው ምክር ቤት ውሳኔ መሠረት ተጨማሪ የሰላም አስከባሪ ኃይሎች በቅርቡ ወደ ጁባ ለመላክ ዝግጅት ላይ ነበር፡፡ ሆኖም በቅርቡ በደቡብ ሱዳንና በሱዳን ድንበር አካባቢ በሁለቱም ተፋላሚ ወገኖች የፀጥታ ኃይሎች መካከል በተቀሰቀሰው ግጭት የ15 ንፁኃን ዜጎች ሕይወት አልፏል፡፡

ለረዥም ጊዜ የቆዩትና የተመድ ሠራተኞችንና ቁሳቁሶችን የሚጠብቁ የጃፓን ሰላም አስከባሪ ኃይሎች በመውጣታቸው ሳቢያ፣ በሌሎች 4,500 ወታደሮች ከመተካታቸው ውጪ እንደታሰበው አዲሱ ተጠባባቂ ኃይል እስከ ዛሬ አልተሰማራም፡፡ በእርግጥ ሩዋንዳ ጠንካራ የፖሊስ ኃይል ወደ ጁባ በመላክ ላይ ትገኛለች፡፡ የሰላም ዕጦቱን ምን ያህል ያረጋጋል የሚለው ወደፊት የሚታይ ይሆናል፡፡   

ዶ/ር ማቻር ሱዳንን ጨምሮ በተለያዩ ጎረቤት አገሮች እየተዘዋወሩ ሲሆን፣ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ኬንያ ወደ አገሯ እንዳይገቡ የሚያስችል ስምምነት እንድትፈራረም አድርገዋል፡፡

ዶ/ር ማቻር በቅርቡ ከደቡብ አፍሪካ ወደ አቡጃ (ናይጄሪያ) በአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት የገጠማቸው ጉዳይ የሚዲያዎችን ቀልብ ስቧል፡፡ ለዶ/ር ማቻር ታደላለች ተብላ የምትታማውና ብዙ ጊዜ የእሳቸው መቆያ ነበረች የምትባለው አዲስ አበባ አቋሟን ቀይራለች ብለው ብዙዎች እንዲጠራጠሩም ምክንያት ሆኗል፡፡

የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትር ዶ/ር ነጋሪ ሌንጮ ግን፣ ጉዳዩ ከፖለቲካ የሚያያዝ እንዳልሆነና ከኢሚግሬሽን ሕግ ጋር የተያያዘ እንደሆነ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ሚኒስትሩ እንደሚሉት ማቻር አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርትን እንደ ትራንዚት በመጠቀም ላይ ሳሉ የኢሚግሬሽንና የዜግነት ጉዳይ መሥሪያ ቤት የአቡጃ ቪዛቸው በመሰረዙ ምክንያት፣ ከኤርፖርቱ ወደመጡበት ወደ ደቡብ አፍሪካ እንዲመለሱ ተደርጓል፡፡ ከዚህ ውጪ የኢትዮጵያ መንግሥት በጉዳዩ ላይ ቀደም ሲል ይዞት ከቆየው የገለልተኛ አስታራቂነት ሚና የተለየ አቋም እንደሌለው ዶ/ር ነገሪ ገልጸዋል፡፡

ዶ/ር ማቻርም ሆኑ እሳቸው የሚመሩት አማፂ ኃይል ከተለያዩ አቅጣጫዎች ተቃውሞ እየተሰማባቸው ቢሆንም፣ የሳልቫ ኪር መንግሥትን ለመጣል ማንኛውንም ዓይነት ጥረት እያደረጉ መሆኑ ታውቋል፡፡ በሌላ በኩል ገለልተኛ ወገኖች የደቡብ ሱዳን ችግር በተቻለ መጠን ፖለቲካዊ መፍትሔ ካልተገኘለት ለአገሪቱም ሆነ ለአካባቢው ሰላም ጠንቅ ይፈጥራል እያሉ ነው፡፡

 

     

Standard (Image)

የሰብዓዊ መብት ይዞታን ለማሻሻል ለፓርላማው የቀረበው ሰነድ

$
0
0

የሰብዓዊ መብት ይዞታ በኢትዮጵያ አከራካሪ ከሆኑ ጉዳዮች ተቀዳሚው ነው፡፡ በሕገ መንግሥቱ 1/3ኛ የሚሆኑት ድንጋጌዎች ሰብዓዊ መብትን የተመለከቱ መሆኑ፣ መሠረታዊ የሚባሉ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ስምምነቶችን አገሪቱ ያፀደቀች መሆኑ፣ በዝርዝር ሕጎችም ትኩረት ያልተነፈገው መሆኑ፣ አፈጻጸሙን የሚከታተሉና የሚቆጣጠሩ ተቋማት የተፈጠሩ መሆናቸው፣ በንድፈ ሐሳቦችና በሕጎች ለሰብዓዊ መብት የተሰጠውን ትኩረት በተግባር እንዳይታይ የተከላከለ አይመስልም፡፡

የሰብዓዊ መብት ይዞታው በሚጠበቀው ደረጃ የተሟላ እንዳልሆነ መንግሥት የሚስማማ ቢሆንም በምን ያህል መጠን ጉድለት እንዳለበት የሚሰጠው ግምገማ ግን ከዜጎቹና ከሌሎች ሦስተኛ ወገን ከሚቀርበው ግምገማ ሲነፃፀር እጅግ ሰፊ የሆነ ልዩነት የሚስተዋልበት ነው፡፡ በተለይ ሲቪልና ፖለቲካዊ መብቶች ላይ ዋነኛው አጥፊና የመብት ረጋጭ ራሱ መንግሥት ነው በሚል የሚቀርበውን ቅሬታ ከተለያዩ ወገኖች መስማት የተለመደ ነው፡፡

ባለፈው ዓመት በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተቀሰቀሰው ተቃውሞና አመፅ ካነሳቸው መሠረታዊ ጥያቄዎች መካከል ይኸው የሰብዓዊ መብት ይዞታ ጉዳይ ተጠቃሽ ነው፡፡ መንግሥት ተገቢና ከሕዝቡ የተነሱ ናቸው ብሎ ከለያቸው አጀንዳዎች መካከልም የሚካተት ነው፡፡

መንግሥት የሰብዓዊ መብት ይዞታን ለማሻሻል ቁልፍ መሣሪያ አድርጎ የወሰደው ብሔራዊ የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሐ ግብርን ነው፡፡ ከመጀመሪያው የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ጋር አብሮ እንዲሄድ ታስቦ ከ2005 ዓ.ም. እስከ 2007 ዓ.ም. ሥራ ላይ የነበረውን የመጀመሪያውን የብሔራዊ የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሐ ግብር አዘጋጅቶ ነበር፡፡

ሁለተኛው የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሐ ግብርም ከሁለተኛው የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ጋር ተናቦ እንዲሄድ ታስቦ የተዘጋጀ ቢሆንም፣ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ፀድቆ በፓርላማው እንዲፀድቅ ታስቦ ለውይይት የቀረበው ማክሰኞ ኅዳር 20 ቀን 2009 ዓ.ም. ነው፡፡ ይህም ከአንድ ዓመት በላይ ወደ ኋላ እንድቀር መደረጉን ያመለክታል፡፡

አዲሱ የድርጊት መርሐ ግብር ምን አዲስ ነገር ይዟል?

የብሔራዊ ሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሐ ግብሩ ዋና ዓላማ በአገር አቀፍ ደረጃ በተቀናጀና ከሌሎች ዕቅዶች በተለይም ከሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ጋር በተጣመረ አኳኋን፣ በሕገ መንግሥቱ ለተረጋገጡ ሰብዓዊ መብቶችና የዜጎች ዴሞክራሲያዊ መብቶች የበለጠ ጥበቃ የሚያበጁ ሥልቶችንና አቅጣጫዎችን መቀየስ ነው፡፡

የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት፣ የመንግሥት ፖሊሲዎች፣ ሕጎች፣ ስትራቴጂዎች፣ ፕሮግራሞች፣ ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ፣ የፌዴራልና የክልል መሥሪያ ቤቶች ዕቅዶች፣ የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርቶች፣ በብሔራዊ ሰብዓዊ መብት  ድርጊት መርሐ ግብር ጽሕፈት ቤቱ አማካይነት የተጠናቀረው የመጀመሪያው የድርጊት መርሐ ግብር አገራዊ የአፈጻጸም ሪፖርት፣ በመንግሥት በይፋ የወጡ አኀዛዊ መረጃዎች፣ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴርና ከሌሎች ፖሊሲ አስፈጻሚ የመንግሥት አካላት የተገኙ መረጃዎች፣ በመንግሥት የተከናወኑ ጥናታዊ ጽሑፎች፣ በተለያዩ የሕዝብ መድረኮች የተነሱ ሐሳቦች፣ በግለሰቦች፣ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኅበራት እንዲሁም በተለያዩ አካላት የተሰበሰቡ ሐሳቦች፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ሁሉን አቀፍ የግምገማ መድረክ የተሰጡ አስተያየቶች፣ ለተለያዩ የተመድና የአፍሪካ ኅብረት የሰብዓዊ መብት አካላት በመንግሥት የቀረቡ ሪፖርቶችና የተሰጡ ግብረ መልሶችና ሌሎች ጠቃሚ የሆኑ ጽሑፎች ለድርጊት መርሐ ግብሩ ዝግጅት በግብዓትነት እንዳገለገሉ ለውይይት የቀረበው ሰነድ ይጠቁማል፡፡

ይህ መርሐ ግብር እንደቀደመው ሁሉ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶችን፣ የኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ባህላዊ መብቶችን፣ ለመብት ተጋላጭ የሆኑ የኅብረተሰብ ክፍሎች መብቶችን፣ እንዲሁም የልማትና የአካባቢ ደኅንነት መብቶችን ይሸፍናል፡፡

የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ይዘት በአጠቃላይ የሚተች ቢሆንም፣ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ይዞታ ግን አደጋ ያንዣበበት እንደሆነ በርካታ ሪፖርቶች ያመለክታሉ፡፡ ይህን ይዞታ ከማጠናከር ይልቅ ይበልጥ እንዲዳከም በማድረግ ረገድ መንግሥት ትልቁን ድርሻ ወስዷል በሚልም ይከሰሳል፡፡

በድርጊት መርሐ ግብሩ ግን መንግሥት ይዞታው የተሻለ እንዲሆን ቁርጠኛ መሆኑንና ይህንንም ለማሳካት ያስችላሉ ያላቸውን አስተዳደራዊና ሕጋዊ ዕርምጃዎች እንደሚወስድ ይፋ አድርጓል፡፡ ዝርዝር የድርጊት መርሐ ግብር የተቀረፀላቸው የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች፣ በሕይወት የመኖር መብት፣ የአካል ደኅንነት መብትና የኢሰብዓዊ አያያዝ ክልከላ፣ የተያዙ፣ በቁጥጥር ሥር የዋሉና በፍርድ የታሰሩ ሰዎች መብት፣ የተከሰሱ ሰዎች መብት፣ ፍትሕ የማግኘት መብት፣ የአመለካከትና ሐሳብን በነፃ የመያዝና የመግለጽ መብት፣ የመደራጀት መብት፣ የሃይማኖትና እምነት ነፃነት መብት፣ የመምረጥና የመመረጥ መብት ናቸው፡፡

በሕይወት የመኖር መብት ይዞታን ለማሻሻል በፖሊስና በማረሚያ ቤት አካላት የኃይል አጠቃቀምና የተጠያቂነት ሥርዓት የሕግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡ በሕይወት የመኖር መብትን ተፈጻሚነት ለማሳደግ የወንጀል ምስክሮችና ጠቋሚዎች ጥበቃ አዋጅን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል አሠራር፣ ሥርዓትና መመርያ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እንደሚደረግም ተመልክቷል፡፡

የአካል ደኅንነት መብትና የኢሰብዓዊ አያያዝ ክልከላን ይዞታ ለማሻሻልም ሁሉም የክልልና የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽኖች፣ የተጠርጣሪ አያያዝ ማንዋሎችን አዘጋጅተው ተግባራዊ እንዲያደርጉ መታቀዱ ተገልጿል፡፡ የወንጀል የምርመራ ሥራ የሚመራበት ዝርዝር መመርያዎችና ማኑዋሎች በጥናት ላይ በመመርኮዝ ለማዘጋጀትም ታቅዷል፡፡ በወንጀል ምርመራ ሒደት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር ከዋሉ በኋላ ከቤተሰብ፣ ከሕግ አማካሪዎቻቸው፣ ከሃይማኖት አባቶቻቸው ወይም ከማንኛውም ሌላ ሰው ጋር በአካል ወይም በሌላ መንገድ እንዲገናኙ የሚደረግበት አግባብና ለወንጀል ምርመራው ውጤታማነት ሲባል ይህ ሊገደብ የሚችልበት ሁኔታን የሚወስን የሕግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እንደሚደረግም ሰነዱ ያትታል፡፡

የተያዙ፣ በቁጥጥር ሥር የዋሉና በፍርድ የታሰሩ ሰዎች መብት ይዞታን ከማሻሻልም አንፃር የዋስትና መብት ለማረጋገጥና የዋስትና አሰጣጥ አሠራር ወጥነትና ፍትሐዊነት እንዲኖረው ለማድረግ፣ የዋስትና አወሳሰን መመርያ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እንደሚደረግ ተመልክቷል፡፡ በወንጀል ምርመራ ሒደት ለምርመራው ውጤታማነትና የሌሎች ተጠርጣሪዎችን መብትና ደኅንነት ከመጠበቅ አንፃር ተጠርጣሪ ለብቻው ተለይቶ የሚታሰርበትን አግባብ የሚደነግግ የሕግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እንደሚደረግም ተገልጿል፡፡ የቅድመ ፍርድ እስር ጊዜን ለማሳጠር ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር ከዋሉ በኋላ የወንጀል ምርመራ የሚጠናቀቅበትን ጊዜ የሚወስን ሕግ ተግባራዊ እንደሚደረግም ተጠቁሟል፡፡

የተከሰሱ ሰዎች መብት ይዞታን ለማሻሻል ደግሞ ተከሳሾች የሚቀርብባቸውን የዓቃቤ ሕግ ማስረጃዎችን አስቀድመው እንዲያውቁና የመከላከያ ማስረጃ እንዲያዘጋጁ የሚያስችል የቅድመ ክስ መስማት አሠራር ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ሕግ ፀድቆ ተግባራዊ እንደሚደረግም ተመልክቷል፡፡ አማራጭ የወንጀል ቅጣቶችን የሚመለከተው ሕግ ዝርዝር መመርያና የአሠራር ሥርዓት ተዘርግቶለት ተግባራዊ እንደሚሆንም ተገልጿል፡፡

ፍትሕ የማግኘት መብት ይዞታ ለማሻሻል መንግሥት ካቀዳቸው ተግባራት መካከልም አማራጭ የሙግት መፍቻ ሕግ፣ እንዲሁም አማራጭ ቅጣቶችን የሚመለከት ሕግ ፀድቀውና የአሠራር ሥርዓቶች ተዘርግቶላቸው ተግባራዊ ማድረግ ተጠቃሽ ነው፡፡

የአመለካከትና ሐሳብን በነፃ የመያዝና የመግለጽ መብት ይዞታን ለማሻሻልም፣ የመገናኛ ብዙኃንና የመረጃ ነፃነት አዋጅ እንዲወጡ የሚጠይቃቸው ማሟያ ሕጎችና የማስፈጸሚያ ሥርዓቶች እንደሚዘረጉ ተገልጿል፡፡ በግለሰቦችና ቡድኖች ላይ ያነጣጠሩ ጥላቻ አዘል ንግግሮችንና ስም ማጥፋትን የሚገዛ ሕግ በጥናት ላይ ተመሥርቶ እንደሚወጣም ተገልጿል፡፡

የሃይማኖትና እምነት ነፃነት መብት ይዞታን ከማሻሻልም አኳያ የሃይማኖትና እምነት ጉዳዮች ላይ የተዘጋጀውን ረቂቅ አዋጅ የሚመለከታቸው የባለድርሻ አካላትና ኅብረተሰቡን በማሳተፍ ግብዓት በማሰባሰብ፣ በማዳበርና በማፅደቅ ተግባራዊ እንደሚደረግ፣ እንዲሁም የሃይማኖት ድርጅቶችና ማኅበራትን የምዝገባ ሥርዓት የሚደነግገው መመርያ ወጥቶ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ ወደ ሥራ እንደሚገባም ተገልጿል፡፡

የድርጊት መርሐ ግብሩ እነዚህንና ሌሎች መብቶች ይዞታን ለማሻሻል የታቀዱ ጉዳዮች በአግባቡ መከናወናቸውን ለማረጋገጥ፣ የክትትልና የግምገማ ሥርዓት በማስቀመጥ ፈጻሚ አካላቱንም ለይቷል፡፡

በመጀመሪያው የድርጊት መርሐ ግብርም በርካታ ነገሮችን ለማከናወን ዕቅድ ተይዞ የነበረ ቢሆንም፣ የዕቅዱ የሥራ ዘመን በ2007 ዓ.ም. ሲጠናቀቅ በሰብዓዊ መብት ይዞታ ላይ ይህ ነው የሚባል መሠረታዊ ለውጥ አላመጣም በሚል የሚተቹ አካላት፣ ከሁለተኛው መርሐ ግብር የተለየ ነገር መጠበቅ አይቻልም ይላሉ፡፡

ከዚህ በተቃራኒ ሁለተኛው የድርጊት መርሐ ግብር ከላይ የተገለጹትን ጨምሮ ዝርዝር የሆኑና በተጨባጭ የሚገመገሙና ተጠያቂነትን የሚያስከትሉ፣ አስተዳደራዊና የሕግ ዕርምጃዎችን በማካተቱ የተሻለ ለውጥ ያመጣል ብለው ተስፋ ያደረጉም አሉ፡፡

የብሔራዊ የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሐ ግብር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ይበቃል ግዛው የመጀመሪያው የድርጊት መርሐ ግብር የተጠበቀውን ያህል ለውጥ ያላመጣው፣ መርሐ ግብሩ አዲስ በመሆኑና የግንዛቤ እጥረት በመኖሩ ነው በማለት ለፓርላማ አባላት ተናግረዋል፡፡ ይህን የመቅረፍ ሥራ እየተከናወነ በመሆኑ ሁለተኛው የተሻለ አፈጻጸም እንደሚኖረውም ተናግረዋል፡፡           

የፓርላማ አባላት ለሦስት ቀናት ውይይት ካደረጉበት በኋላ የድርጊት መርሐ ግብሩ ሐሙስ ኅዳር 22 ቀን 2009 ዓ.ም. እንደሚፀድቅ ይጠበቃል፡፡ 

Standard (Image)

የኢትዮጵያ ወዳጅ ቱርክ በምታካሂደው ፀረ ሽብር ዕርምጃዋ የአጋሮቿን ድጋፍ ትፈልጋለች

$
0
0

እ.ኤ.አ. በ1912 የመጀመሪያውን የኦቶማን ቱርክ ቆንስላ ጄኔራልን በሐረር ካቋቋመች በኋላ የቱርክ ሪፐብሊክ ከሰሃራ በታች አፍሪካ የመጀመሪያውን ኤምባሲ እ.ኤ.አ. በ1926 በአዲስ አበባ ከፍታለች፡፡ በዚህም የኢትዮጵያና የቱርክ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከ100 ዓመታት በላይ የዘለቀ ሆኗል፡፡ አሁንም የሁለቱ አገሮች ግንኙነት ከመቼውም የበለጠ ጠንካራ ነው፡፡ በአፍሪካ ካለው የቱርክ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ውስጥ ግማሽ ያህሉ የሚገኘው በኢትዮጵያ ውስጥ መሆኑ ለዚህ አንዱ ማሳያ ነው፡፡

በሁለቱ አገሮች መካከል በጉልህ የሚታይ ልዩነት ቢኖርም፣ በቅርቡ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ገጥሟቸው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲያውጁ ከመገደዳቸው በፊት ቱርክና ኢትዮጵያ በአንፃራዊነት በበጎ የሚነሱ አገሮች ነበሩ፡፡ እ.ኤ.አ. ሐምሌ 15 ቀን 2016 ከቱርክ ወታደሮች የተወሰኑት መፈንቅለ መንግሥት ለማድረግ ሞክረዋል፡፡ በቱርክ የወቅቱ ፕሬዚዳንት ረሲፕ ታይብ ኤርዶጋን በተመሠረተው ኤኬ ፓርቲ የሚመራው የቱርክ መንግሥት አመራር ቱርክ የበለፀገችና የተረጋጋች ዴሞክራሲያዊ የሙስሊም አገር መሆን ችላለች፡፡ ተቀባይነት ላገኙ የፖሊሲ ማሻሻያዎች ምክንያት የቱርክ ኢኮኖሚ ጤናማ ዕድገት እያስመዘገበ ነው፡፡ የኤርዶጋን መንግሥት ለቱርክ የሠራው ባለፉት አሠርት ዓመታት የነበሩት የቀደሙት መንግሥታት ያልሞከሩትን ነው፡፡ የቱርክ አጠቃላይ ብሔራዊ ምርት በጥቂት ዓመታት ውስጥ በሦስት እጥፍ አድጓል፡፡ የቱርክ የአውሮፓ ኅብረት የአባልነት ድርድር እ.ኤ.አ. በ2005 ነው የተጀመረው፡፡ ቱርክ በኢኮኖሚ ዕድገት ምጣኔ፣ በውጭ ኮንስትራክሽንና አገልግሎት ከቻይና በመቀጠል ሁለተኛ እንድትሆንም አስችሏል፡፡

በተመሳሳይ ኢትዮጵያም ባለፈው ዓመት ችግር ውስጥ በመግባቷ ለዓመት ያህል የቆየው ተቃውሞና አመፅ በሰዎች ሕይወት፣ አካልና የአገር ንብረት ላይ ውድመት ከማስከተሉ በፊት ደካማ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ቢኖራትም፣ በበርካታ ጉዳዮች ላይ በለውጥ ጎዳና ላይ የነበረች አገር ናት፡፡ ነገር ግን በመስከረም ወር 2009 ዓ.ም. ብቻ በአምስት ቀናት ውስጥ 130 የሚደርሱ ኩባንያዎች በኦሮሚያ በከፊልና ሙሉ በሙሉ ወድመዋል፡፡ ሰለባ ከሆኑ የውጭ ኩባንያዎች ውስጥ የቱርክ ይገኙበታል፡፡ ይሁንና ከዚህ ችግር በፊት በግጭት በሚታወቀው የአፍሪካ ቀንድ ውስጥ አንፃራዊ ሰላምና መረጋጋት የተጎናፀፈች፣ ከአሥር ዓመት በላይ በተከታታይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ዕድገት በማስመዝገብ እንደ ዓለም ባንክ ሪፖርቶች በፍጥነት በማደግ ላይ ያሉ አገሮችን ለመቀላቀል የበቃች አገር ነበረች፡፡

በቱርክ የኢትዮጵያ አምባሳደር አቶ አያሌው ጎበዜ ከኅዳር 6 እስከ ኅዳር 11 ቀን 2009 ዓ.ም. በቱርክ መንግሥት ጋባዥነት ቱርክን ለጎበኘው የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ቡድን አንካራ ላይ እንደገለጹት፣ በቅርቡ በኢትዮጵያ የተከሰተው ፖለቲካዊ አለመረጋጋት መሠረታዊ በሚባል ደረጃ በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት የሚፈልጉ የቱርክ ባለሀብቶች ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አልፈጠረም፡፡ አምባሳደር አያሌው በታኅሳስ ወር የቱርክ የኢኮኖሚ ሚኒስትር ኒሃት ዘይቤኪ በርካታ የቱርክ ባለሀብቶችን ይዘው ኢትዮጵያን ለመጎብኘት ፕሮግራም መያዛቸው የዚህ ማረጋገጫ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ አምባሳደር አያሌው፣ ‹‹የቱርክ ባለሀብቶችና ባለሥልጣናት የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ ተገንዝበውታል፡፡ ሁኔታው እንዳይደገምና የባለሀብቱን ቅስም እንዳይሰብር የኢትዮጵያ መንግሥት በርትቶ እንዲሠራ ጠይቀዋል፤›› ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያ የቱርክ አምባሳደር ፋቲህ ኡሉሶይ በበኩላቸው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በርካታ የቱርክ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ለመሥራት ፍላጎት ያላቸው በመሆኑ የቱርክ ኢንቨስትመንት እያደገ ይሄዳል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2015  ቱርክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት የወጪ ንግድ 400 ሚሊዮን ዶላር ያስመዘገበ ሲሆን፣ በቅርቡ አንድ ቢሊዮን ዶላር የማድረስ ዕቅድ አላት፡፡

ሁለቱ አገሮች ጥሩ የሚባል ግንኙነት ያላቸው ቢሆንም አሁን ቱርክ የፈቱላህ ጉለን ንቅናቄን ወይም ቱርክ ድርጅቱን በአሸባሪነት ከፈረጀች በኋላ የፈቱላህ ጉለን አሸባሪ ድርጅት (ፈቶ)ን፣ ከቱርክም ሆነ ከመላው ዓለም ጠራርጋ ለማጥፋት በምታደርገው ትግል ከኢትዮጵያ ብዙ ትጠብቃለች፡፡ እርግጥ ነው ቱርክ ከመሰል ወዳጅ አገሮች ተመሳሳይ ቁርጠኝነትን እየጠየቀች ነው፡፡ ከኢትዮጵያ፣ ከናይጄሪያና ከጋምቢያ ለተውጣጣው የአፍሪካ የጋዜጠኞች ቡድን የቱርክ የፕሬዚዳንትና ጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮዎች፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ የቱርክ ዓለም አቀፍ ልማትና ትብብር ኤጀንሲ (ቲካ) እና የቱርክ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት የሥራ ኃላፊዎች እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያና መሰል ወዳጅ አገሮች በጉዳዩ ላይ ከቱርክ ጋር መሥራት ያለባቸው ለቱርክ ደኅንነት ብቻ ሳይሆን ለራሳቸውም ደኅንነት ሲሉ ነው፡፡ በመፈንቅለ መንግሥት ሙከራውና እሱን ተከትሎ ቱርክ እየወሰደቻቸው ባሉ ዕርምጃዎች፣ ለሙከራው ዋነኛ ተጠያቂ ከተደረገው ፈቶ ጋር በተያያዘ በአሜሪካና በአውሮፓ ኅብረት ላይ ያላትን ጨምሮ ቱርክ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋን ከዚሁ አንፃር ዳግም ለመቃኘት የተገደደች ትመስላለች፡፡

ከዚሁ አንፃር ቱርክ በኢትዮጵያና በሌሎች አፍሪካ አገሮች ቅድሚያ ትኩረት የሰጠችው ከፈቶ ጋር ግንኙነት አላቸው ብላ የምታምንባቸው ትምህርት ቤቶች እንዲዘጉላት ነው፡፡ ቱርክ በቅርቡ ያቋቋመችው ማሪፍ ፋውንዴሽን በኢትዮጵያ የሚገኙ እነዚህን ትምህርት ቤቶች እንዲረከብ ትፈልጋለች፡፡ ፋውንዴሽኑ በቱርክ ፓርላማ ባለፈው መስከረም ወር የተቋቋመው ለዚሁ ዓላማ ነው፡፡

አምባሳደር አያሌው ስለቱርክ ዕቅድ ግንዛቤው እንዳላቸው አመልክተው ኢትዮጵያ በይፋ ምላሽ እንዳልሰጠች፣ ቱርክም ቢሆን በይፋ ጥያቄውን እንዳላቀረበች ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን ጥያቄው በተለያየ መንገድ እንደሚቀርብ አረጋግጠዋል፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ የቱርክን አቤቱታ በራሷ መንገድ እያጣራች ነው፡፡ ጉዳዩ ከሕግ አንፃር ያለውን ተፅዕኖም እናያለን፤›› ብለው፣ በጉዳዩ ላይ ከዚህ በላይ ለመግለጽ እንደማይችሉም አስገንዝበዋል፡፡    

የቱርክ ዓለም አቀፍ ትብብርና ልማት ኤጀንሲ (ቲካ) ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሴርዳር ካም ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ፋውንዴሽኑ እ.ኤ.አ. ለ2017 በጀት ዓመት ከመንግሥት 150 ሚሊዮን ዶላር ተመድቦለታል፡፡ ስለዚህ የአፍሪካ መሪዎች ስለፈቶ ትምህርት ቤቶች ዕጣ ፈንታ ሊጨነቁ እንደማይገባ ገልጸዋል፡፡ ዶ/ር ካም፣ ‹‹የአፍሪካ መሪዎች ለትምህርት ቤቶቹ የተሳለጠ ሽግግር እንደሚፈልጉ እንረዳለን፡፡ ፋውንዴሽኑን ያቋቋምነውም ለዚህ ነው፤›› ብለዋል፡፡ የጉለን ዓለም አቀፍ የትምህርት ቤቶችና ዩኒቨርሲቲዎች መረብ ከ100 በላይ አገሮች ውስጥ ተንሰራፍቶ ይገኛል፡፡

የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራውና ውጤቶቹ

እ.ኤ.አ. ሐምሌ 15 ቀን 2016 በቱርክ ጦር ኃይሎች ሥር በድብቅ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ጥቂት ወታደሮች መፈንቅለ መንግሥት ለማድረግ ሞክረው፡፡ ወታደሮቹ ተዋጊ ጄቶች፣ ታንኮችና ሔሊኮፕተሮችን በመጠቀም ሙከራቸውን ለማሳካት ጥረዋል፡፡ የፕሬዚዳንቱን ቤተ መንግሥት፣ የፓርላማ፣ የፖሊስና ሌሎች የመንግሥት ሕንፃዎችን በቦምብ አጥቅተዋል፡፡ ፕሬዚዳንት ኤርዶጋንንም ለመግደል ሞክረዋል፡፡

የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራው ከ246 በላይ ሰዎች ሕይወት ካጠፋና ከ2,500 በላይ ሰዎችን ለጉዳት ካጋለጠ በኋላ ከሽፏል፡፡ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ካደረጉት መካከልም 100 የሚሆኑት ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡ በቱርክ ባለፉት 50 ዓመታት በአማካይ በየአሥር ዓመቱ መፈንቅለ መንግሥት ተደርጓል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1960፣ በ1971፣ በ1980 እና በ1997 የተከናወኑት ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥቶች ስኬታማ ነበሩ፡፡ እንደ ቱርክ ባለሥልጣናት ገለጻ የመጨረሻው ሙከራ ካለፉት ጋር ሲነፃፀር ፈጽሞ የተለየ ነው፡፡ በማያጠራጥር ሁኔታ መፈንቅለ መንግሥቱን ያከሸፈው የዜጎች እምቢተኝነትና ከመንግሥት ተቋማት ጋር ያደረጉት ትብብር ነው፡፡ ባለሥልጣናቱም ይህ የሕዝብ ምላሽ የተለየ እንዳደረገው ይገልጻሉ፡፡

ሕዝቡ ወደ አደባባይ በመትመም ከመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ አድራጊዎቹ ጋር እንዲተናነቅ ያደረገው የፕሬዚዳንት ኤርዶጋን የቴሌቪዥን መልዕክት ነበር፡፡ ፕሬዚዳንቱ በሲኤንኤን ቱርክ በፌስታይም ባስተላለፉት መልዕክት፣ ‹‹ለእነዚህ ከሃዲዎች ምርጡ ምላሽ ኅብረታችንን ማሳየትና እንደ አገር ተባብረን መቆም ነው፡፡ ለዚች አገር ዕድገት ሲባል የአገሬ ሕዝቦች በአደባባይ በመውጣት እንድትታገሏቸው ጥሪ አደርጋለሁ፡፡ የሕዝብ ኃይል ከማንም በላይ እንደሆነ ሁሌም አውቃለሁ፤›› ብለዋል፡፡

ከዚህ ጥሪ በኋላ በሚሊዮን የሚቆጠር ሕዝብ ወደ አደባባይ ወጥቷል፡፡ ሕዝቡም ሆነ የፀጥታ ኃይሎች ተተኩሶባቸዋል፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ሕይወታቸውን ቢያጡም፣ ሕዝቡ በጀግንነት ከመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ አድራጊዎች ጋር ተፋልሟል፡፡ የተለያየ የፖለቲካ አመለካከት ቢኖራቸውም ዜጎች በአንድነት ሙከራውን አክሽፈውታል፡፡

የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራው ከከሸፈ በኋላ ፕሬዚዳንት ኤርዶጋን ‹‹ለሚሊዮኖች እምነት ምሥጋና ይግባና ሙከራው ከሽፏል፡፡ ሕይወታቸውን መስዋዕት አድርገው ለዴሞክራሲና ለሕግ የበላይነት ያላቸውን ቁርጠኝነት ለማረጋገጥ ለዓለም አስፈላጊ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ ሙከራው ሕዝባችን ለዴሞክራሲ ያለውን መታመን አልቀነሰውም፡፡ በተቃራኒው ዴሞክራሲ በቱርክ በተሻለ ሁኔታ የተደራጀና ሥር የሰደደ መሆኑን ያረጋግጣል፤›› ብለዋል፡፡

ቱርክ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራው የተመራው በፈቶ እንደሆነ ታምናለች፡፡ እንደ ባለሥልጣናቱ ገለጻ፣ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ አድራጊዎቹ በምርመራ ወቅት የፈቶ አባላት መሆናቸውን አምነዋል፡፡

ነገር ግን በስደት አሜሪካ የሚገኙት ፈቱላህ ጉለን ባወጡት መግለጫ ከመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ አድራጊዎቹ ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንደሌላቸው የገለጹ ሲሆን፣ ሁኔታው ራሱ በመንግሥት የተቀናበረ ሊሆን እንደሚችልም አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ ጉለን በዚሁ መግለጫ፣ ‹‹ይህን አድርገናል አልልም፡፡ ልናደርገው ግን እንችል ነበር፡፡ ባለፉት 50 ዓመታት በበርካታ ወታደራዊ መፈንቀለ መንግሥቶች እንደተሰቃየ አንድ ሰው ከእንዲህ ዓይነት መፈንቅለ መንግሥት ጋር ግንኙነት አለህ መባሌን እንደ ስድብ እቆጥረዋለሁ፡፡ ይህን ክስ ሙሉ በሙሉ እክዳለሁ፤›› ብለዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት ጉለን በ55 የወንጀል ክሶች ተቀዳሚ ተከሳሽ ናቸው፡፡ ፕሬዚዳንት ኤርዶጋን አሁን ጉለንና ደጋፊዎቻቸውን እንደ አገሪቱ ጠላት ይወስዷቸዋል፡፡ ይሁንና ከዓመታት በፊት ፈቱላህ ጉለን የፕሬዚዳንት ኤርዶጋን የቀኝ እጅ እንደነበሩ ይነገራል፡፡ የጉለን ንቅናቄ የኤርዶጋን ደጋፊ እንደነበረም መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ኤርዶጋን የአሁኑን ገዥ ፓርቲ እ.ኤ.አ. በ2001 የመሠረቱ ሲሆን፣ ሊበራልና መቻቻልን የሚሰብክ ሥነ መለኮትን የሚያገል የፖለቲካ ፕሮግራም እንደያዘ ይታመናል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2000 በተደረገው ምርጫ የአርዶጋን ኤኬ ፓርቲ በከፍተኛ የሕዝብ ድጋፍ ወደ ሥልጣን መጥቷል፡፡ እንደ በርካታ ምንጮች ገለጻ፣ ኤርዶጋን ያለ ጉለን ዕርዳታ የሕዝቡን ድጋፍ በአጭር ጊዜ ለማግኘት ይቸገሩ ነበር፡፡ ኤርዶጋንም ሆኑ ጉለን ሴኩላር ፖለቲካን (ዓለማዊ) የሚቃወሙ አማኝ ሙስሊሞች እንደሆኑ ይነገርላቸዋል፡፡ ነገር ግን በሒደት በአቀራረባቸው ላይ ልዩነት እያዳበሩ በመምጣታቸው መቃቃራቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

እ.ኤ.አ. በ2013 ፕሬዚዳንት ኤርዶጋንና ቤተሰባቸው በሙስና ወንጀል ምርመራ እንዲደረግባቸው ጥረት ያደረጉት ጉሊኒስቶች እንደሆኑ ይነገራል፡፡ ከዚህ ሙከራ በኋላ መንግሥት ሕጋዊ ዕርምጃ ለመውሰድ እንቅስቃሴ መጀመሩም ይነገራል፡፡ ከ2013 በኋላ በተደረጉ ምርጫዎች ጉለኒስቶች ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ድጋፍ መስጠታቸውን ሪፖርቶች ያመለክታሉ፡፡

ከመንግሥት ግምገማ በተቃራኒ ጉለን በደጋፊዎቻቸው እንደ መንፈሳዊ መሪ ይታያሉ፡፡ ደጋፊዎቻቸው ጉለንን በተለያዩ እምነቶች መካከል ውይይትን የሚደግፉ ለዘብተኛ የእስልምና አስተማሪ ሲሉም ይገልጿቸዋል፡፡ የጉለን አስተምህሮዎችና ጽሑፎች ለዘብተኛ፣ ለምዕራቡ ዓለም የተመቸ ሱኒ እስልምናን የሚሰብክና ለተማሩና ባለሙያ ቱርካዊያን እጅግ የሚስብ እንደሆነም ይነገራል፡፡ ጉለን እስልምናን ከምክንያታዊ አስተሳሰብና ሳይንሳዊ ምርመራ ጋር ማዛመዳቸውን የሚወዱላቸውም አሉ፡፡ በአጠቃላይ የጉለን ሰበካዎች ለዘብተኛ እስልምናን ከበጎ አድራጎትና ሕዝባዊ አገልግሎት፣ ከጠንካራ ሠራተኝነትና ከቢዝነስ እንዲሁም ከትምህርት ጋር እንዳያያዙም ይገለጻል፡፡ ለብዙ ሰዎች ትምህርት ቤቶች፣ ሆስፒታሎችና የዕርዳታ ድርጅቶችን ጨምሮ በጉለኒስቶች የተቋቋሙ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የቱርካውያኑን ማኅበራዊ ችግር ለመቅረፍ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል፡፡

የቱርክ መንግሥት ጉለኒስቶች ጥሩ ሥራ የሚሠሩ በመምሰል የድብቅ አጀንዳቸውን ለማሳካት ይጥሩ እንደነበር ያምናል፡፡ መንግሥት ለአገሪቱ አደጋ መሆናቸውን እንደተገነዘበም የፈቶ አባላትን ከመንግሥት ተቋማት ጠራርጎ ለማስወገድ መንቀሳቀሱን የቱርክ ባለሥልጣናት ለጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡ ይሁንና ድርጅቱ በሚስጥር የሚንቀሳቀስ በመሆኑ ይህን በቀላሉ ማሳካት አልተቻለም፡፡

ቱርክ የፈቶ አባላት በመንግሥት መዋቅር ውስጥ መሰግሰጋቸውን ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ ‹‹የጎንዮሽ የመንግሥት መዋቅር›› ፈጥረው እንደነበር ትገልጻለች፡፡ የፈቶ አባላት ማንነታቸውን በመደበቅ እንደ ጦር ኃይል፣ ፍርድ ቤት፣ የደኅንነት ተቋምና በመሳሰሉ የመንግሥት ተቋማት ውስጥ ቁልፍ ቦታዎችን ይዘው እንደነበርም ተጠቁሟል፡፡ በተለይ በትምህርት ሚኒስቴር፣ በደኅንነት አገልግሎትና በፍርድ ቤቶች የነበራቸው ሚና ጉልህ እንደነበርም ተመልክቷል፡፡ ከቢዝነስም አንፃር ጉለኒስቶች በቱርክ ውስጥ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችንና ትልልቅ ጋዜጦችን፣ የወርቅ ማዕድን ማውጫዎችንና ባንኮችን በባለቤትነት ተቆጣጥረው ነበር፡፡

ቱርክ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 120 መሠረት ፈቶንና አባላቱን ለማጥፋት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አውጃለች፡፡ ፓርላማው አዋጁን እንዲያፀድቀው ሐሳብ ባቀረቡበት ወቅት ፕሬዚዳንት ኤርዶጋን፣ ‹‹ይህ አዋጅ በምንም ዓይነት መንገድ ዴሞክራሲን፣ የሕግ የበላይነትንና የቱርክ ዜጎች መሠረታዊ ነፃነቶችን የሚጥስ አይሆንም፤›› ብለዋል፡፡

ከአዋጁ መፅደቅ በኋላ ቱርክ ከፈቶ ጋር ግንኙነት አላቸው ብላ በጠረጠረቻቸው ግለሰቦችና ቡድኖች ላይ ጠንከር ያሉ ዕርምጃዎችን ወስዳለች፡፡ አንዳንድ ሪፖርቶች እንደሚያሳዩት ከ6,000 በላይ ወታደሮች ታስረዋል፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ ፖሊሶች፣ ዓቃቤ ሕጎችና ዳኞች ወይ ተባረዋል አሊያም ታግደዋል፡፡ ምሁራን፣ መምህራንና የመንግሥት ሠራተኞችም ተመሳሳይ ዕጣ ፈንታ ገጥሟቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ዕርምጃው 125,000 ሰዎችን ከ375 ተቋማት እንዳባረረ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 36,000 ያህሉ በእስር ቤት ሆነው የፍርድ ቤት ቀጠሮ በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡ ጉዳዩን ለመከታተል 70 ዓቃቤ ሕጎች እንደተሰማሩም ተገልጿል፡፡

የቱርክ ባለሥልጣናት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ቱርክ እነዚህን ዕርምጃዎች መውሰዷ ተፈጥሯዊ ምላሽ ነው፡፡ ይሁንና በመፈንቅለ መንግሥት ሙከራውና በቱርክ ዕርምጃ ዙሪያ ጥያቄዎች መነሳታቸው አልቀረም፡፡ ለአንዳንዶች የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራው ከምንም የተነሳ አይደለም፡፡ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ አድራጊዎቹ ለድርጊታቸው የሰጡት ምክንያት መንግሥት በሙስና መዘፈቁንና ከሃይማኖት ነፃ መሆን አለመቻሉን ነው፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች እነዚህ ሥጋቶች በተወሰነ የቱርክ ማኅበረሰብ ውስጥ የሚታመንባቸው እንደሆኑ ይከራከራሉ፡፡

ዕርምጃዎቹም ያለበቂና አስተማማኝ ማስረጃ የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እየጣሱ ናቸው በማለት የሚተቹ አሉ፡፡ ከመንግሥት የተለየ ሐሳብ ያላቸውን ሁሉ በመጨፍለቅ ከፈቶ ጋር በማያያዝ የሚወሰዱ ዕርምጃዎችም፣ የቱርክ ዴሞክራሲና ብዝኃነት ያለው አስተሳሰብ የማራመድ መብት ላይ ትልቅ ጉዳት እየደረሰ ነው በማለት ቅሬታ የሚያቀርቡም በርካቶች ናቸው፡፡

የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራውና የቱርክ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ

ቱርክ ከአፍሪካ ጋር በበርካታ ጉዳቶች ላይ በጋራ እየሠራች ትገኛለች፡፡ በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካ፣ በባህልና በማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ግንኙነት መሥርታለች፡፡

ከዚህ ጠንካራ ግንኙነት አንፃር ፈቶ ጋር እያደረገች ላለው ጦርነት የአፍሪካን ድጋፍ እጅግ ትሻለች፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ ሌሎች የአፍሪካ አገሮችም የፈቶ ትምህርት ቤቶችን ለማሪፍ ፋውንዴሽን እንዲያስረክቡ ትፈልጋለች፡፡ ይሁንና ከጥቂት አገሮች ውጪ ብዙዎቹ መልስ አልሰጡም፡፡

ከአሜሪካ ጋር ጠንካራ ግንኙነት የነበራት ቱርክ፣ አሜሪካ ፈቱላህ ጉለን ከሚኖሩበት ፔንሳልቫኒያ አሳልፋ ለቱርክ ካልሰጠች ያላትን ግንኙነት ለማጤን እንደምትገደድ ገልጻለች፡፡

ወደ አውሮፓ ኅብረት ለመቀላቀል ቱርክ ስታደርገው የነበረው ጥረትም እክል የገጠመው ይመስላል፡፡ የቱርክ መንግሥት የወሰደውን ዕርምጃ ስፋትና ጥልቀት ከተቹት የአውሮፓ አገሮች መካከል የአውሮፓ ፓርላማ የሕግ አውጭ አካላት የቱርክ አባልነት ድርድር በዚሁ ምክንያት እንዲቋረጥ ጠይቀዋል፡፡   

        

Standard (Image)

በጥልቀት መታደስ ጥልቀቱ ምን ድረስ ነው?

$
0
0

ቀደም ሲል ሕወሓት በኋላም በኢሕአዴግ ደረጃ ደርግን የተዋጋው ድርጅት በአገሪቱ ውስጥ አሉ ያላቸውን የዴሞክራሲና የብሔር ጥያቄዎች በጥልቀት የገመገመ ነበር፡፡ የድርጅቱ የውስጥ አወቃቀር ኮሙዩኒስታዊ ገጽታ ነበረው፡፡ ዴሞክራሲያዊነቱና ሕዝባዊነቱም የሚመነጨው ከማርክስምና ሌኒኒዝም ፍልስፍና በሚቀዳ አስተሳሰብ ነበር፡፡

ሕዝቡን ከጭቆና ነፃ ለማውጣት ታጋዩም አመራሩም የታጠቀው ዋና ስንቅም ሕዝባዊነትና መስዋዕት ለመሆን ዝግጁነትን ነበር፡፡

በ1966 ዓ.ም. አብዮቱ ከመፈንዳቱ በፊት በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመንም ሆነ በደርግ ያልተመለሱ የማንነትና የዴሞክራሲ ጥያቄዎችን ለመመለስም፣ ለዘመናት የቆየውን አሃዳዊ ሥርዓት አፍርሶ በፌዴራላዊ ሥርዓት የመለወጥ ፕሮጀክትን እንደ ዓላማ የተያያዘው ነበር፡፡

ይኼ በግራ ዘመም አተያይ የተተነተነው ችግርና መፍትሔ አስፈላጊነትን ጥያቄ ውስጥ የሚከት ዓለም አቀፋዊ የርዕዮተ ዓለም ትግል መብቃት አጋጠመ፡፡ በ1980ዎቹ ውስጥ ያበቃው የምሥራቁና የምዕራቡ ዓለም ርዕዮተ ዓለም ፍጥጫ ቀዝቃዛው የዓለም ጦርነት እየተባለ የሚጠራው ነው፡፡

የ17 ዓመታቱ የትጥቅ ትግል የርዕዮተ ዓለም ግጭት አመላካች አልነበረም፡፡ ሥልጣኑ ያበቃው ደርግም ከአሸናፊው ከኢሕአዴግ ባልተናነሰ ማርክሲስታዊ ሥርዓት ነበር፡፡ ወደ ሥልጣን የመጣው አዲሱ ድርጅትም ራሱን ከዓለም ነባራዊ ሁኔታ ጋር ማጣጣም ነበረበትና በከፊል የምዕራቡ ዓለም መመርያ የሆኑትን ነፃ ገበያ፣ ነፃ አስተሳሰብና የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት በመርህ ደረጃ ለመቀበል ተገዷል፡፡ የምዕራቡ ዓለም ድጋፍም ተችሮታል፡፡ ኢሕአዴግ ያልተቀበላቸው የዓለም ባንክና የአይኤምኤፍ የልማት መርሆች እንዳሉ ሆነው፡፡ ለብዙዎች የመጀመሪያው የድርጅቱ ህዳሴ መባል ያለበት ይኼው የርዕዮተ ዓለም ክለሳ ነበር፡፡ ዛሬም ከ25 ዓመታት በኋላ እነዚህ ጥያቄዎች በኢሕአዴግ ጠረጴዛ ላይ ናቸው፡፡

በፌዴራላዊ አስተሳሰብ የተዘጋጀው አዲሱ የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት በዓለም አቀፍ ደረጃ ስምምነት የተደረሰባቸው የሰብዓዊ መብትና የዴሞክራሲ ቃል ኪዳኖች ያካተተ፣ በብዙዎች ዘንድ ተቀባይነት ያገኘ ሕገ መንግሥት ፀድቆ ተግባር ላይ ውሏል፡፡ ተግባራዊነት ላይ ግን ጥያቄ ይነሳበታል፡፡

ከሕገ መንግሥቱ መረቀቅ በፊት ሥራ ላይ በዋለው የሽግግር መንግሥት ቻርተር ወቅት የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ተሳትፎ ይገኝበታል፡፡ የራሱን አሻራም አሳርፏል፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ በቀደሙት ሥርዓቶች የማንነት ጭቆና ከደረሰባቸው መካከል ተጠቃሽ ነው፡፡ ዛሬ ግን ሥርዓቱ ላይ ከፍተኛ የቅቡልነት ጥያቄ ከተነሳባቸው ክልሎች ግንባር ቀደሙ ሲሆን፣ ባለፈው ዓመት ኅዳር ወር የተቀሰቀሰው አመፅ ለአንድ ዓመት መዝለቁ ይታወሳል፡፡ ቀጥሎም ሁለተኛው ትልቁ ክልል በሆነው ከአማራ ክልል ተመሳሳይ ሁከት ተቀስቅሶ ነበር፡፡

1993 እና 1997

በ1990 ዓ.ም. ከኤርትራ ወረራ በኋላ በተለይ ሕወሓት ውስጥ የተከሰተው ቀውስ ትልቁና ኢሕአዴግንም የነካ፣ በአጠቃላይ ለአዲሱ ሥርዓትም መነቃነቅ የፈጠረ ነበር፡፡ የትግራይ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ ገብሩ አሥራትንና የመከላከያ ሚኒስትር የነበሩትን አቶ ስዬ አብርሃን ጨምሮ፣ የድርጅቱ ከፍተኛ አመራር የነበሩ ከአሥር በላይ ሰዎች ከድርጅቱ እንዲወገዱ ምክንያት የሆነ መሰነጣጠቅ ነበር የተፈጠረው፡፡

በአሸናፊው (በቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ የሚመራ) አካልና ‹‹አንጃ›› ተብለው በተገለሉ ሰዎች መካከል ዛሬም ድረስ የመሰነጣጠቁ አጀንዳ ላይ ስምምነት የሌለ ቢሆንም፣ የኤርትራ ጉዳይና ሙስና ተደጋግመው የሚነሱ ነጥቦች ናቸው፡፡

በአቶ መለስ ዜናዊ የሚመራው ቡድን ድርጅቱ የመበስበስ አደጋ እንደገጠመው ቦናፓርቲዝም በሚል ርዕስ ያቀረበው አጀንዳ ነበር፡፡ በአንጃነት የሚታወቁ ሰዎች ከድርጅቱ መውጣታቸውን ተከትሎ የታወጀው ህዳሴ አገሪቱ በልማት ወደፊት እንድትራመድ አስችሏል ተብሎ ይታመናል፡፡

የኢሕአዴግ ተቃዋሚዎች አብዮታዊ ዴሞክራሲ በመባል የሚታወቀው ሥርዓት ሕገ መንግሥቱን የሚፃረር እንደሆነና ነፃ አስተሳሰብን አይፈቅድም በማለት በተደጋጋሚ ሲወቅሱ ነበር፡፡ በተለይ በ1997 ዓ.ም. ምርጫ ዋዜማ የታወጀው የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መንግሥት ሥርዓት በአገሪቱ ለተከታታይ ዓመታት ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ያመጣ ቢሆንም፣ እሱን የሚመጣጠን የዴሞክራሲ ለውጥ አልመጣም ተብሎም ይተቻል፡፡

ኢሕአዴግን ከትጥቅ ትግል ጀምሮ የሚከታተሉ የምሥራቅ አፍሪካ የፖለቲካ ተንታኝ ፕሮፌሰር አሌክስ ዲዋል፣ ሥርዓቱ እምብዛም ውይይት ያልተደረገበትና በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በጎ ፈቃድ ላይ ብቻ መሬት የወረደ ለድርጅቱ ባዕድ አካሄድ አድርገው ይመለከቱታል፡፡ እሱም ብቻ ሳይሆን ልማታዊ መንግሥት በኢትዮጵያ እንደማይሠራ፣ እንዲያውም እስከዛሬ ድርጅቱ ያስመዘገበውን የኢኮኖሚ ዕድገት ይዞ እንዳይሄድ አድርጎታል በማለት አሌክስ ዲዋል ከሪፖርተር ጋር በነበራቸው ቆይታ አስገንዝበዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በተደጋጋሚ ባደረጉት ንግግርና በተለይ ደግሞ የድርጅቱ ንድፈ ሐሳብ መተንተኛ በሆነው በአዲስ ራዕይ መጽሔት ተደጋግሞ እንደተተነተነው፣ ተቃዋሚዎች የሚያራምዱት የጥፋትና የከሰረ ፖለቲካ መሆኑን፣ ኢሕአዴግ ውስጥ ያለውን የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ በማሸነፍ ‹‹ልማታዊነት›› የበላይነት እንዲኖረው የተቀረፀ እንደሆነ ይከራከራሉ፡፡

ከሥርዓቱ መታወጅ ይያያዝ አይያያዝ በቂ ማረጋገጫ ባይገኝም በአገሪቱ በ1997 ዓ.ም. ምርጫ የታየው የዴሞክራሲ ፍንጭ ለሁለተኛ ጊዜ አልተደገመም፡፡ የምርጫውን ቀውስ ተከትሎ በተከታታይ የታወጁ የሚዲያ፣ የሲቪክ ማኅበረሰብና የፀረ ሽብር አዋጆች የአገሪቱን ፖለቲካ የማያፈናፍን አድርገውታል ተብሎ ይተቻል፡፡ በእርግጥ በሁለቱ ተከታታይ ምርጫዎች በተለይ ደግሞ ባለፈው ዓመት በተካሄደው አምስተኛ ዙር ምርጫ ኢሕአዴግና አጋሮቹ የፓርላማ መቀመጫዎችን ሙሉ ለሙሉ ተቆጣጥረውታል፡፡

የታወጀው የልማታዊ መንግሥት ሥርዓት ስዊድን፣ ደቡብ ኮሪያና ቻይናን የመሳሰሉ አገሮችን በሞዴልነት የሚያስቀምጥ ሲሆን፣ በእነዚህ አገሮች አንድ ፓርቲ ከ30 እስከ 60 ዓመታት በአውራነት የቆየበትና ከፍተኛ የኢኮኖሚ ሽግግር መጥቷል ይላል፡፡ ተቃዋሚዎች ‹‹የአንድ ፓርቲ ሥርዓት›› በማለት የሚተቹት ቢሆንም፣ ኢሕአዴግ ‹‹ጤነኛና ምክንያታዊ›› ተቃዋሚዎች እስኪፈጠሩ ድረስ በ‹‹አውራ ፓርቲ›› ሥርዓት አገር የመገንባት ዓላማ እንዳለው ደጋግሞ ተናግሯል፡፡

ዴሞክራሲን የመገንባት ሒደት በተቃዋሚዎች ፓርላማ መግባትና አለመግባት እንደማይወሰን አቶ መለስ ይሞግቱ ነበር፡፡ ኢሕአዴግ በውስጡ የመከራከርና ሕዝብን የማሳተፍ ባህልና ስትራቴጂ እንዳለው በመናገር፡፡ በዋናነት ግን በተለይ አዲስ ራዕይ በሐምሌ - ነሐሴ 2001 ዓ.ም. ዕትሙ ‹‹የአመራር መተካካት በኢሕአዴግ›› በሚለው ዋና የትንተና ጽሑፉ፣ በመንግሥትና በድርጅት የአመራር መተካካት በትውልዶች የዱላ ቅብብል እንደሚሳካ ያትታል፡፡ ወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ‹‹ሥልጣን እለቃለሁ›› በማለት ለፋይናንሻል ታይምስ የተናገሩበት ጊዜ ሲሆን፣ የአመራር መተካካት የግለሰብ የፍላጎት ሳይሆን በተለይ በትጥቅ ትግል የነበረውን አመራር በአዲስ አመራር የመተካት መርህ የተቀመጠበት ጊዜ ነበር፡፡ በሌላ ዕትም እንደተተነተነው ደግሞ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ብቻውን በራሱ አላስፈላጊ ማኅበራዊ ቀውስ ሊያስከትል እንደሚችልና በዴሞክራሲያዊ ምርጫ አሸንፎ ሥልጣን ላይ የወጣውን የጀርመን የናዚ ሥርዓት በምሳሌነት ያስቀምጣል፡፡ በመሆኑም እንደ 1997 ዓ.ም. ሕዝቡ ቀይ ካርድ ከማሳየቱ በፊት የመበስበስ አደጋ ሳይመጣ በመተካካት መርህ ዴሞክራሲያዊ የአመራር ለውጥ መፍጠር፣ በልማታዊ መንግሥት እንደ አማራጭ መንገድ የተወሰደ ይመስል ነበር፡፡

ፕሮፌሰር ሬኔ ሊፎርት ይህንን የልማታዊ መንግሥትነት ሒደት በተነተኑበትና ‹‹Ethiopia’s Crisis›› በሚል ርዕስ የኢትዮጵያን ያለፈው ዓመት ቀውስ በገመገሙበት ጥናታዊ ጽሑፍ አንድ ከፍተኛ የኢሕአዴግ አመራር አነጋግረው ያገኙት ምላሽ፣ ‹‹ኢትዮጵያ ወደ ካፒታሊዝም ሥርዓት ከመሸጋገሯ በፊት የብዙኃን አስተሳሰብ [የመድብለ ፓርቲ] ሥርዓት አንጫንም፡፡ የተለያዩ መደቦች ሲፈጠሩ ብቻ ራሳቸውን የሚወክል ፓርቲ ያቋቁማሉ፤›› ይላል፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ እየተመኘ ያለው ልማትና ዴሞክራሲ በአንድ ጊዜ እንዲመጣ ሳይሆን፣ መጀመርያ ልማት ከዚያ ቀጥሎ ዴሞክራሲ ነው፤›› የሚል ድምዳሜ ያስቀምጣሉ ፕሮፌሰሩ፡፡     

የቀውሱ አተያይ

ባለፈው ዓመት ኅዳር ወር ለአዲስ አበባና ለኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞች የተዘጋጀውን የጋራ ማስተር ፕላን በመቃወም የተጀመረው አመፅ ለዘጠኝ ወራት ዘልቋል፡፡ ከኦሮሚያ ወደ አማራ ክልልም ተቀጣጥሎ ነበር፡፡ በአብዛኛው እኔ ነኝ ያለ መሪ ያልነበረው ይኼው ድንገተኛ ሁከት በማኅበራዊ ሚዲያ የሚመራና ከኢትዮጵያ ውጭ የሚገኙ አክራሪ የፖለቲካ ኃይሎችም እጃቸውን አስገብተውበታል ተብሎ በተደጋጋሚ ተነግሯል፡፡ የኋላ ኋላም ግብፅንና ኤርትራን የመሳሰሉ የኢትዮጵያ ቁጥር አንድ ጠላት የተባሉ አገሮች እንደነበሩበትም በቂ መረጃዎች መገኘታቸው በስፋት ተገልጿል፡፡

ያም ሆነ ይህ መንግሥት ከመነሻው ጀምሮ የሁከቱን ምክንያት ወደ ውጭ ለመግፋት አለመሞከሩንና ከውስጥ የመነጨ ነው ብሎ እንደሚያምን ገልጿል፡፡ ከመነሻው ግን መንግሥት የተነሳውን ጥያቄ የቢሮክራሲ ማሻሻያ አድርጎ አይቶታል፡፡ ምናልባትም ቀደም ሲል በተለይ በመቐለው አሥረኛው የኢሕአዴግ ጉባዔ የመልካም አስተዳደር ዕጦት የሥርዓቱ አደጋ እየሆነ ነው ብሎ ከመቀበሉ፣ ከአስተዳደርና ከፍትሕ ዕጦት የመነጨ መሆኑን ከማመኑ በላይ ይዘላል ብሎ አላመነም ነበር፡፡ የሕወሓት ነባር ታጋዮችና ወታደራዊ አዛዦች ሌተና ጄኔራል ፃድቃን ገብረ ትንሳዔ (የቀድሞ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታ ማዥር ሹም)፣ እንዲሁም ሜጀር ጄኔራል አበበ ተክለ ሃይማኖት (የቀድሞ አየር ኃይል ዋና አዛዥ) ለረዥም ጊዜ ድምፃቸውን አጥፍተው ከቆዩ በኋላ፣ በተከሰተው ቀውስ ላይ የራሳቸውን አተያይ አስቀምጠው ነበር፡፡ ጉዳዩ የቢሮክራሲ ሳይሆን የሥርዓት ቀውስ መሆኑንና ይህንን የሚመጥን የሥርዓት ማሻሻያ እንዲደረግ መዋቅራዊ የመፍትሔ ሐሳቦች ሰንዝረዋል፡፡

ከመነሻው ከኢሕአዴግ የሐሳብ አመንጪ ሰዎች እምብዛም አወንታዊ ምላሽ ባያገኙም፣ ሌሎች ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችም ተመሳሳይ ሐሳብ አቅርበዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የኢዴፓ መሥራችና የቀድሞ ሊቀመንበር (በአሁኑ ወቅት የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል) አቶ ልደቱ አያሌው ችግሩ የሥርዓት ቀውስ ምልክት እንደሆነ፣ ድርጅቱ እሱን የሚመጥን የሥርዓት ማሻሻያ እንዲያደርግ ጠይቀው ነበር፡፡ በእርግጥ ጫፍ ድረስ ሄደው የሽግግር መንግሥት እንዲመሠረት የጠየቁ ሌሎችም ነበሩ፡፡

መታደስ እስከ ምን? ከማን ጋር?

ሁከቱ ከመነሳቱ በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የሚመሩት አዲሱ መንግሥት በተቋቋመ በመጀመሪያዎቹ ወራት፣ የመንግሥት የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ማዕከል ያደረገው ጥናት ይፋ መሆኑ የሚታወስ ነው፡፡ የሥርዓቱ ችግር በድርጅቱ ጉባዔ ከተገመገመው በላይ መሆኑንም ያመለክታል፡፡ እምብዛም ሳይቆይ ሁከቱ መነሳቱ ኢሕአዴግ ዕርምጃ ከመውሰዱ በፊት እንደተቀደመም በአንዳንዶች ተተንትኗል፡፡

ያም ሆነ ይህ በ2008 ዓ.ም. የተከሰተው ሁከት ኢሕአዴግ ሥልጣን በያዘ በ25 ዓመቱ ውስጥ ከፍተኛው ሆኗል፡፡ ሁከቱን በመደበኛ ሕግና ሥርዓት ከማስከበር በላይ በመሆኑም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እስከ ማወጅ ተደርሷል፡፡ አዋጁ ተፈጥሮ የነበረውን ቀውስ ማስቆም የቻለ ሲሆን፣ በአገሪቱ አንዣብቦ የነበረው በሰላም ወጥቶ በሰላም የመግባት ፍራቻን በማስተካከል የአገሪቱ ሰላም ቀድሞ ወደነበረበት መመለስ ችሏል፡፡ በዚህ መሀል አንድ ነገር እየተጠበቀ ይገኛል፡፡ በመንግሥትና በገዥው ፓርቲ ውስጥ የአመራር ለውጥና ማሻሻያ ማድረግ፡፡

አዋጁ ከመታወጁ ቀደም ብሎ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ለሁለቱም ምክር ቤቶች ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፣ በመንግሥትና በድርጅቱ ውስጥ መሠረታዊ የአወቃቀር ለውጥ እንደሚደረግ ቃል ገብተዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ በገቡት ቃል መሠረት ኢሕአዴግ ለበርካታ ሳምንታት በዝግ ከፍተኛ ግምገማ አድርጓል፡፡ በተናጠልም አባል ድርጅቶቹ በየፊናቸው ከከፍተኛ አመራር ጀምሮ እስከ ታችኛው የአመራር እርከን ድረስ እየተገማገሙ ይገኛሉ፡፡ ከአራቱ አባል ድርጅቶች መካከል ኦሕዴድ ነባር ሊቀመናብርቱን በማሰናበት አዳዲስ አመራሮች ከማምጣቱም በላይ፣ ምሁራንና የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ያልሆኑ ወደ ኃላፊነት በማምጣት ግንባር ቀደም ዕርምጃ መውሰዱ ይታወሳል፡፡ ብአዴንም በብዙዎች እንደተጠበቀው ሊቀመናብርቱን ባያሰናብትም አዳዲስ ምሁራን ወደ ካቢኔ በማምጣት ማሻሻያ ማድረጉን አስታውቋል፡፡ የፌዴራል መንግሥትም ካቢኔውን እንደ አዲስ በማዋቀር ከሚኒስትሮች መካከል ዘጠኙ ባሉበት እንዲቀጥሉ በማድረግ ለ21 አዳዲስ ሚኒስትሮች ሹመት ሰጥቷል፡፡ የብዙዎችን ቀልብ የሳበው በርካታ የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ወደ ከፍተኛ ሥልጣን መምጣታቸው ሲሆን፣ በብዙዎች ዘንድ ምሁራንን አያቀርብም ተብሎ በሚታማው በኢሕአዴግ ታሪክ እንደ አዲስ ምዕራፍ ታይቷል፡፡ ተቃዋሚዎች ግን አሁንም ከአዲሱ ካቢኔ አዲስ ነገር እንደማይጠብቁ ይናገራሉ፡፡

የኢሕአዴግ ዋናው መሥራች ሕወሓት ቀደም ሲል የአመራር መተካካት ማድረጉ ይታወሳል፡፡ አሁንም በከፍተኛ አመራር ደረጃ ግምገማ ተካሂዷል፡፡ በድርጅቱ ውስጥ ፀረ ዴሞክራሲያዊ አሠራር በከፍተኛ ደረጃ መስፈኑን ገምግሟል፡፡ በመንግሥት ደረጃ በቅርቡ የተወሰነ የአመራር ለውጥ አድርጓል፡፡ በኢሕአዴግ ደረጃ በቀረበው በጥልቀት የመታደስ ሰነድ መሠረት እየተገማገመም ነው፡፡ የድርጅቱ መሥራችና አንጋፋ ታጋይ አምባሳደር ሥዩም መስፍን በቅርቡ ‹‹ውራይና›› ለተባለው የትግርኛ መጽሔት በሰጡት ቃለ መጠይቅ፣ ሕወሓት ከሙስናና ከፀረ ዴሞክራሲያዊ አካሄድ ጋር በተያያዘ ውስጡን መፈተሹን ተናግረዋል፡፡ እስከ ዛሬ በተለይ ምሁሩን ያገለለ አካሄድና ነፃ አስተሳሰብን የማይፈቅድ መንገድ እንደነበር መተማመን ላይ መደረሱንም አስረድተዋል፡፡

ካቢኔውን እንደ አዲስ ያዋቀረው ብአዴንም የኢሕአዴግን ሰነድ መሠረት አድርጎ ያለፉትን 15 ዓመታት የክልሉን ጉዞ መገምገሙን የድርጅቱ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አለምነው መኮንን ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ በሰፋፊ መድረኮች ከማዕከላዊ ኮሚቴ ጀምሮ እስከ ወረዳና ዞን አመራሮች ድረስ እስካሁን ድርጅቱ አለኝ የሚላቸው 7,500 የሚደርሱ አባላት ተገማግመዋል፡፡

ድርጅቱ አምስት ዋና ዋና ችግሮች ነቅሶ የለየ መሆኑንና በተለይ ደግሞ ፀረ ዴሞክራሲያዊነት፣ የሕዝቡን አንገብጋቢ ችግሮች አለማዳመጥ፣ የአባላቱ በመርህ የለሽ አመለካከትና በትምክህት የመለከፍንና ዘረኝነትን የመሳሰሉ ጉዳዮች ለይቶ ገምግሟል ብለዋል፡፡ በአጠቃላይ ድርጅቱ ቀና ሲሆን ሊያመጣ የሚችለውን ለውጥ ያህል ድርጅቱ ሲበላሽ ምን ያህል የጥፋት ኃይል ሊሆን እንደሚችል ይናገራሉ፡፡ ‹‹ለሥልጣን ያለው አመለካከትና አተያይ መዛባት›› የችግሮቹ ምንጭ አድርገውም ይመለከታሉ፡፡

ዛሬም የ‹‹አፈጻጸም›› ችግር

አቶ አለምነው እንደሚሉት ኢሕአዴግ ግምገማ የጀመረው በአፈጻጸም ችግር ላይ እንጂ የሥርዓት ለውጥ ለማድረግ አልነበረም፡፡ እንደ እሳቸው እምነት የልማታዊ መንግሥት ፍኖተ ካርታና እሱን ለማስፈጸም የተቀረፁ ስትራቴጂዎች አማራጭ የላቸውም፡፡ አቶ አለምነው፣ ‹‹ያቃተን መስመሩን በተሟላ ሁኔታ ጨብጦና አምኖ የመፈጸም ችግር ነው፡፡ ይኼ መስመር የኢትዮጵያ ሕዝቦች ወደ ብሩህ ጎዳና መርቷቸዋል፤›› ይላሉ፡፡ ‹‹ይህንን መጣል ወደ ጨለማ የሚወስድ መንገድ መከተል ነው፤›› በማለት፡፡

አቶ ሔኖክ ሥዩም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የዶክትሬት ዕጩ ሲሆኑ፣ ከኢሕአዴግ የሚጠበቀው የአመራር መሻሻል እንጂ የአስተሳሰብና የመስመር ለውጥ አይደለም ሲሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ‹‹የሕዝቡ ጥያቄ የመንግሥት ለውጥ ነው ወይ?›› በማለት ጥያቄውን ራሳቸው ውድቅ ያደርጉታል፡፡

ህዳሴ የማድረግ ዕቅድ ቀደም ሲል ተይዞ የነበረ እንጂ ሁከቱን ተከትሎ እንዳልመጣ የአቶ አለምነውን ሐሳብ አቶ ሔኖክ ይቀበላሉ፡፡ ኢሕአዴግም ‹‹የመስመርና የርዕዮተ ዓለም ማሻሻያ ማድረግ ሳይሆን፣ የተያዘውን መስመር ለማስፈጸም የተስተካከለ ቁመና የለኝም፤›› የሚል መነሻ እንዳለው ያምናሉ፡፡ የፓርቲውን አሠራርና አመራር ለመፈተሽና ብቃት ያለው አመራር ለመፍጠር የተሰጠውን ትኩረት ይቀበላሉ፡፡ ጉዳዩ በዚህ ከቀጠለ በሕዝቡ የቀረበው ጥያቄ ምላሽ ያገኛል ብለውም ያምናሉ፡፡ ኢሕአዴግና አባል ድርጅቶቹ የያዙት ‹‹በጥልቀት›› የመታደስ ዘመቻ አዝማሚያ፣ በፓርቲው ውስጥ ፍተሻ የማድረግና የማጥራት እንጂ የመርህና የአስተሳሰብ ለውጥ ለማምጣት አይመስልም፡፡

‹‹የሕዝቡ ጥያቄና ቁጣ በፓርቲ የውስጥ መታደስ መልስ ያገኛል ወይ?›› የሚል ጥያቄ ከቀድሞ የሕወሓት መሥራችና አመራር እንዲሁም የዓረና ትግራይ ፓርቲ መሥራች አቶ ገብሩ አሥራት ይነሳል፡፡ አቶ ገብሩ ህዳሴው የታለመለትን ዓላማ የማሳካት ሁኔታ እንዳለው ይቀበላሉ፡፡ ሆኖም ‹‹ጊዜው የሚጠይቀው መታደስ ከሆነ›› የሚል ቅድመ ሁኔታ ያስቀምጣሉ፡፡

በአንድ ወቅት በምሥራቅ አውሮፓ ከሶሻሊስት አስተሳሰብ ለመውጣት የተደረገው ‹‹ዙሪያ ምላሽ›› የአስተሳሰብ ለውጥ ፍሬያማ መሆኑ ይናገራሉ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የተከሰተው ቀውስ ኢሕአዴግ ከሚከተለው የአብዮታዊ ዴሞክራሲ አስተሳሰብ የመነጨ እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ ‹‹ነፃ አስተሳሰብ አይቀበልም፡፡ ተቃዋሚዎችን በጠላትነት የሚፈርጅ ነው፡፡ ለመታደስ ከሆነ ከዚህ ዓይነት ርዕዮተ ዓለም መውጣት ያስፈልጋል፤›› ይላሉ፡፡ በኢሕአዴግ ዘመን የመታደስ ፍንጭ የታየው በ1997 ዓ.ም. እንደሆነ የራሳቸውን ግልከታ ይገልጻሉ፡፡ አሁንም አንድ ፍንጭ ብቻ ተመልክተዋል፡፡ የምርጫ ሕጉን ለማሻሻል የተገባውን ቃል፡፡ ሆኖም እንደ አቶ ገብሩ እምነት፣ መታደስ ሌሎች በርካታ ፓኬጆችን መያዝ ነበረበት፡፡ ሙስናና ፀረ ዴሞክራሲ አስተዳደር ምንጩ የፖለቲካ ቀውስ ውጤት እንደሆኑ ያምናሉ፡፡ ግምገማውንና የካቢኔ ለውጡንም በአወንታዊ ጎኑ ይመለከቱታል፡፡ ‹‹አሁን ሕዝቡ እየጠየቀ ያለው ግን ከዚህ በላይ ነው፡፡ ጥያቄዎቹ ከድሮ የተለዩ ናቸው፤›› ይላሉ፡፡ በተለይ በተለያዩ አካባቢዎች ‹‹ኦሮሚያ ፈርስት፣ አማራ ፈረስትና ትግራይ ፈረስት›› የሚባሉ አዝማሚያዎች አደገኛ መሆናቸው በመግለጽ፣ ኢሕአዴግ ልብ ገዝቶ ሁሉንም ያካተተና የተፈጠረውን የመበታተን አዝማሚያ ተሻግሮ የሚሄድ መንገድ እንዲቀይስ ይጠይቃሉ፡፡

ንቅናቄውን የአክራሪ ዳያስፖራ እጅ እንደተቀላቀለበት ቢያምኑም፣ በአጠቃላይ የሕዝብ ቁጣ መገለጫ መሆኑን አቶ ገብሩ ያስረዳሉ፡፡ የአንድ ፓርቲ አገዛዝና ʻሌጋሲʼ የሚሉ አስተሳሰቦች እንዲቀሩ በመጠየቅ፡፡

የኢዴፓ የቀድሞ ሊቀመንበር አቶ ሙሼ ሰሙ፣ ‹‹ጥያቄው ባህሪውን ቀይሯል›› በማለት ከአቶ ገብሩ ጋር ተመሳሳይ ምልከታ አላቸው፡፡ በ1993 ዓ.ም. በተወሰነ ደረጃ ህዳሴ መካሄዱን ግን ያምናሉ፡፡ ላለፉት አሥራ አምስት ዓመታት እየተንከባለሉ እዚህ የደረሱት የኑሮ ውድነትና የፍትሕ ዕጦት ጥያቄዎች በተለመደው አካሄድ አይፈቱም ይላሉ፡፡ ‹‹ህዳሴው የፓርቲ የውስጥ ጉዳይ እንጂ የሕዝብ አይደለም፡፡ ጥያቄው ግን የመነጨው ከሕዝብ ነው፤›› በማለት ጥልቅ ውይይት የሚያስፈልገው ከሕዝብ ጋር ነው ይላሉ፡፡ ቀጥተኛ ውይይት በማድረግና የሕዝቡን ጥያቄ በማዳመጥ ብቻ መፍትሔ ይኖራልም ይላሉ፡፡ ‹‹ተሃድሶ ዕድሜ ማራዘሚያ እንዳይሆን›› በማለት እንኳን ራስን በራስ በማደስ፣ የተነሳውን ጥያቄ ከተቃዋሚዎች በመነጋገር ብቻም አይፈታም ይላሉ፡፡ ‹‹ጉዳዩ ከውክልና ወጥቷል፤›› በማለት፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በካሪኩለም የዶክትሬት ዕጩ የሆኑት አቶ አብረሃ ኃይለዝጊ በበኩላቸው፣ የተሃድሶው እንቅስቃሴ የተለየ ስሜት እንዳልፈጠረባቸው ይናገራሉ፡፡ ‹‹በኢሕአዴግ ዘንድ እንደ ፋሽን አዳዲስ ቃላት መፍጠር የተለመደ ነው፤›› በማለት፡፡ ‹‹አሁን የተለየ ችግር ተፈጥሯል›› የሚሉት አቶ አብረሃ፣ የድርጅቱ አዝማሚያ ግን ጥያቄውን ለመመለስ የሚያስችል የተለየ መንገድ እየፈለገ እዳልሆነ ይናገራሉ፡፡

‹‹አንደኛ ነገር መታደስ በዘመቻና በድንገት አይመጣም፡፡ ሁለተኛ ከልብ መታደስም ቢፈልግ ʻማን ይቀበላልʼ የሚል ጥያቄ ይነሳል፡፡ በተደጋጋሚ ብዙ ንቅናቄ ለመፍጠር ቃል ተገብቷል፡፡ ግን አላደረገም፡፡ ጭብጡ ለውጥ የማይመጣ ከሆነ ማንም አያምንህም፤›› ይላሉ፡፡ አቶ አብርሃ፣ ‹‹በ1993 ዓ.ም. የተደረገው ተሃድሶ ለዚህ ቀውስ ካደረሰን ሌላ ማራዘሚያ ተሃድሶ ለምን እናደርጋለን?›› ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡

አቶ አብረሃ በኦሮማያና በአማራ ክልሎች የተደረጉ የአመራር ለውጦችን በአወንታዊ መልክ ያዩዋቸዋል፡፡ የተሃድሶ ምንጭ አድርገው ግን አይመለከቱዋቸውም፡፡ ‹‹ለእኔ ተሃድሶ መሠረታዊ የሆነ የአስተሳሰብ ለውጥ ማምጣት ነው፤›› በማለት ከአቶ ገብሩና ከአቶ ሙሼ ጋር ይስማማሉ፡፡ መደረግ ነበረባቸው የሚሉዋቸው ሕገ  መንግሥቱን ማክበር፣ ግልጽነትንና ተጠያቂነትን ማስፈን፣ እንዲሁም ሕገ መንግሥቱ ውስጥ የተካተቱ የሰብዓዊ መብት ቃል ኪዳኖችን ማረጋገጥ ነበር፡፡ ‹‹አሁን ጊዜ አልፎበታል›› የሚሉት መፍትሔ ሲሆን፣ ‹‹ዛሬ ኢሕአዴግ እጅግ ከሚያምነው ሕዝብ ሳይቀር እምነት አጥቷል፡፡ ይኼ ቢደረግ የምለው መፍትሔ የለኝም፤›› በማለት በተስፋ መቁረጥ ሐሳባቸውን ይቋጫሉ፡፡

ፕሮፌሰር ሬኔ ሊፎርት በኢትዮጵያ ታሪክ የመንግሥት ለውጥ የሚመጣው በገዥው አካል ውስጥ ያፈነገጠ አካል ሲኖር እንደሆነ በመግለጽ፣ የታሰቡ የተሃድሶ እንቅስቃሴዎች ዋናውን የችግሩን ምንጭ የሚነቅሱ ባይሆኑም፣ የቅቡልነት ጥያቄ ውስጥ እየገባ ቢሆንም የኢሕአዴግ ሥርዓት እንዲህ በቀላሉ አይፈርስም በማለት ይደመድማሉ፡፡ ፕሮፌሰሩ በሁከቱ ወቅት በኢትዮጵያ የተለያዩ ክልሎች ውስጥ በመዘዋወር የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን በማነጋገር ካገኙት መረጃ ድምዳሜ ላይ መድረሳቸውንም ገልጸዋል፡፡                       

 

    

Standard (Image)

በዓባይ ጉዳይ የሚሠሩ ፖሊሲ አውጪዎች ከተመራማሪዎች ጋር በቅርበት እንዲሠሩ ተጠየቀ

$
0
0

በሱዳን ዋድ መዳኒ ከተማ ከኅዳር 24 እስከ ኅዳር 26 ቀን 2009 ዓ.ም. የተካሄደው የውኃና መሬት ኢንቨስትመንት ዓውደ ጥናት ተሳታፊዎች፣ በዓባይ ጉዳይ የሚሠሩ ፖሊሲ አውጪዎች ከተመራማሪዎች ጋር በቅርበት እንዲሠሩ ጠየቁ፡፡

የስቶኮልም ዓለም አቀፍ የውኃ ኢንስቲትዩት (ሲዊ)፣ የዓለም አቀፍ የውኃ ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት (ኢውሚ) እና የሱዳን ኃይድሮሊክ ምርምር ማዕከል (ኤችአርሲ) በመተባበር ባዘጋጁት ዓውደ ጥናት የተገኙ ተመራማሪዎች፣ ምሁራን፣ ባለሙያዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ የግል ዘርፉና የሚዲያ ተወካዮች ይህን የጠየቁት በዓውደ ጥናቱ የቀረቡት ጥናቶች በምሥራቃዊ የዓባይ ተፋሰስ የሚከናወኑ የመሬት፣ የውኃና ኢነርጂ ኢንቨስትመንቶች የወደፊት ዕጣ ፈንታን በተመለከተ መሠረታዊ የዕውቀት ክፍተት እንዳለ ከደመደሙ በኋላ ነው፡፡

ከኢትዮጵያ፣ ከግብፅ፣ ከሱዳንና ከደቡብ ሱዳን የተገኙትን ጨምሮ የዓውደ ጥናቱ ተሳታፊዎች በባለስድስት ነጥብ የአቋም መግለጫቸው በአንድ ድምፅ እንደገለጹት፣ የምሥራቃዊ ዓባይ ተፋሰስ ሀብቶችን በጋራ ለመጠቀም የሚደረጉ ትብብሮች በአካባቢው የሚከናወኑ የመሬት፣ የውኃና ኢነርጂ ኢንቨስትመንቶች የወደፊት ዕጣ ፈንታን በተመለከተ ባሉ ዕውቀቶች ላይ የተመሠረቱ ናቸው፡፡ ተሳታፊዎቹ እንዳመለከቱት የአየር ንብረት ለውጥና የሕዝብ ቁጥር ዕድገት በምሥራቃዊ ተፋሰስ በተለየ ሁኔታ ተግዳሮት እየፈጠሩ ከመሆኑ አንፃር ለጠንካራ ውሳኔ ድጋፍ ሰጪ የሆኑ ማዕቀፎችን በመቅረፅ፣ የተሻሉ ፖሊሲዎችን በማዘጋጀት ውጤታማ የሆነ የተፈጥሮ ሀብት አስተዳደር ሥርዓት በማበጀት ምላሽ መስጠት ያስፈልጋል፡፡ በተጨማሪም ፖሊሲዎችና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴዎች ተፈላጊውን ውጤት እንዲያስገኙና ዘላቂ የልማት ውጤት እንዲያስመዘግቡ ከማድረግ አኳያ፣ በአካባቢው ያለው መሠረታዊ የዕውቀት ክፍተት መሟላት እንዳለበት አስምረውበታል፡፡

ቀጣይነት ያለው ውይይትና ምክክርን በሁሉም እርከኖች ላይ ማዳበር የተሻለ ዕውቀት፣ ጠንካራ ማስረጃና ጠንካራና ጤናማ አቅም ለመገንባት፣ ይህንኑ መሠረት አድርጎም የተፋሰሱ አገሮች ሕዝቦች ፍላጎትና የተፋሰሱን ሥነ ምኅዳር ግምት ውስጥ ያስገባ ውሳኔ ለማሳለፍ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለውም ተሳታፊዎቹ አመልክተዋል፡፡

በተለይ የመሬት፣ ውኃና ኢነርጂ ኢንቨስትመንቶች ላይ የሚደረግ ውይይትና ምክክር ቀጣይነት ኖሮት ቢያንስ በዓመት አንድ ጊዜ መደረግ እንዳልበትም ገልጸዋል፡፡ ይህ መሰል መድረኮች ከመንግሥትና ከምሁራን በተጨማሪ ሲቪል ማኅበራትንና ሚዲያን ሊያሳትፉ እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ አንፃር መሰል ዓውደ ጥናቶችን ለማድረግ ስምምነት ላይ የተደረሰ ሲሆን፣ ቀጣዩን ዓውደ ጥናት በግብፅ እ.ኤ.አ. በ2017 ለማድረግ ዕቅዱ ቶሎ መጀመር እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

በዓውደ ጥናቱ ላይ የቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፎች በአካባቢው የተከናወኑና ለማከናወን የታቀዱ የውኃና መሬት ኢንቨስትመንቶች ስለሚኖራቸው ተፅዕኖና ዘላቂነት ባለው ሁኔታ ለማካሄድ፣ መደረግ ስላለባቸው ዕርምጃዎች ዝርዝር መረጃዎችን አቅርበዋል፡፡

ይህ የዋድ መዳኒ ዓውደ ጥናት እ.ኤ.አ. ከ2013 ጀምሮ ‹‹Water Politics in the Nile Basin – Emerging Land Acquisition and the Hydro Political Landscape›› በሚል ርዕስ የተመሪማሪዎች ቡድን ሲያካሂድ ከቆየው ፕሮጀክት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ በስዊድን ምርምር ማዕከል የገንዘብ ድጋፍ የተደረገ ሲሆን፣ የሚፈጸመው ደግሞ በሲዊ፣ በኖርዲክ አፍሪካ ኢንስቲትዩትና በስዊድን የግብርና ሳይንስ ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡

በተጨማሪም ሲዊና ኢውሚ በተመሳሳይ አጀንዳ ላይ የተለያዩ አውደ ጥናቶችን ያዘጋጁ ሲሆን፣ በዚህም ሳይንሳዊ ዕውቀትን ለማሠራጨትና በተመራማሪዎችና በውሳኔ ሰጪ/ፖሊሲ አውጪዎች መካከል መቀራረብ ለመፍጠር ጥረዋል፡፡ ሁለቱ ተቋማት በጋራ ካዘጋጇቸው ዓውደ ጥናቶች መካከል በግንቦት ወር 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የተዘጋጀው ተጠቃሽ ነው፡፡

በዓውደ ጥናቱ የተሳተፉ ኤክስፐርቶች በአካባቢው የሚደረጉ ኢንቨስትመንቶች ዘላቂ እንዲሆኑ፣ የፕሮጀክት ዕቅድና አፈጻጸም ላይ ሊወሰዱ ይገባል ያሏቸው ዝርዝር አካሄዶች ላይ ሐሳባቸውን ሰንዝረዋል፡፡

በተለይ ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል ያሏቸውን አሳሳቢ ጉዳዮችንም አብራርተዋል፡፡ ሰፋፊ የእርሻ ሥራዎችና የውኃ ኃይል ማመንጫ ግድቦች ስለሚፈጥሩት ተፅዕኖ፣ ተፅዕኖውን ለመቀነስና ለመቆጣጠር ስለሚወሰዱ ዕርምጃዎችም ዝርዝር ማብራሪያ ቀርቧል፡፡ የቀረቡት ማብራሪያዎች ላይ ስምምነት መኖሩ ባያጠያይቅም በተወሰኑ ጉዳዮች ላይ ግን ሰፊ ውይይትና ክርክር መደረጉ አልቀረም፡፡

ውይይትና ክርክሩ በምሁራንና በኤክስፐርቶች ብቻ የተገደበ አልነበረም፡፡ ምሁራኑ ከመንግሥት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች ከተወከሉ ፖሊሲ አውጪዎችና ውሳኔ ሰጪዎች ጋርም ውይይትና ክርክር አድርገዋል፡፡

በመካሄድ ላይ ያሉና ሊካሄዱ የታቀዱ መጠነ ሰፊ ኢንቨስትመንቶች በተፈጥሮ ሀብት አስተዳደር፣ በሕጋዊ ግንኙነቶችና ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል ላይ የሚኖራቸው አገራዊና ክልላዊ ተፅዕኖም ላይ ውይይት ተደርጓል፡፡

ፕሮጀክቱ በአጠቃላይ ባለፉት አራት ዓመታት የተለያዩ ተመራማሪዎች በኢትዮጵያ፣ በሱዳን፣ በደቡብ ሱዳን፣ በዩጋንዳና በግብፅ የመስክ ጉብኝት በማድረግ ጭምር ጥናት እንዲያደርጉ አስችሏል፡፡ ከፕሮጀክቱ ውጤቶች መካከል አንዱ ‹‹Land and Hydro Politics in the Nile River Basin – Challenges and New Investments›› የሚል ርዕስ ያለውና ሳንድስትሮም፣ ጃገርስኮግና ኦስቲጋርድ አጋታኢ የሆኑበት መጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፉ የዓውደ ጥናቱ አጀንዳ ጋር የተያያዙ በርካታ የምርምር ሥራዎችን አካቷል፡፡ መጽሐፉ እ.ኤ.አ. በሚያዚያ 2016 የተመረቀ ቢሆንም በዋድ መዳኒ በድጋሚ ተመርቋል፡፡

በዓውደ ጥናቱ ከተሳተፉት ኢትዮጵያዊያን መካከል በኖርዲክ አፍሪካ ኢንስቲትዩት ከፍተኛ ተመራማሪ ዶ/ር አትክልት በየነና በሉንድ ዩኒቨርሲቲ የፒኤችዲ ተማሪና ተመራማሪ አቶ ወንድወሰን ሚቻጎ ሰይድ በመጽሐፉ ኢትዮጵያን በተመለከተ የጻፏቸው ጥናቶች ተካተዋል፡፡

በተጨማሪም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመሬትና ውኃ ጥናት ማዕከል ዳይሬክተር ዶ/ር ጌጤ ዘለቀና በኢውሚ የኢትዮጵያ ቅርንጫፍ የሚሠሩት ልኬ ንጉሤ ጥናት አቅርበዋል፡፡ የኢንትሮ ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈቅአህመድ ነጋሽ፣ አቶ ተፈራ በየነና አቶ ተሾመ አጥናፌ ከውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር፣ እንዲሁም አቶ ዘሪሁን አበበ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በዓውደ ጥናቱ ተሳትፈዋል፡፡              

Standard (Image)

የአዲስ አበባው የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ምርጫና ውስብስብ ስንክሳሮች

$
0
0

የምሥራቅ አፍሪካዊቷ አገር ሩዋንዳ ርዕሰ ከተማ ኪጋሊ 27ኛውን የአፍሪካ ኅብረትን ዓመታዊ የመንግሥታትና ርዕሰ ብሔሮችን ጉባዔ እንደ እ.ኤ.አ. ከሐምሌ 17 እስከ 18 ቀን 2016 ነበር ያዘጋጀችው፡፡ በወቅቱም ከሚጠበቁ ጉዳዮች ውስጥ ትልቁን ሥፍራ የያዘው ኅብረቱን ለቀጣይ አራት ዓመታት በዋና በሊቀመንበርነት ማን ሊረከበው እንደሚችል ነበር፡፡ በተለይም ከሁለቱ ቀናት ጉባዔ ቀደም ብሎ የመጀመሪያዎቹን አራት ዓመታት የሥራ ዘመናቸውን አጠናቀው የነበሩትና ለሁለተኛ ጊዜ ከመወዳደር ራሳቸውን ያገለሉት የወቅቱ ሊቀመንበር ዶ/ር ንኮሳዛና ድላሚኒ ዙማን ለመተካት፣ ከሦስት አገሮች የተወከሉና ኅብረቱ ከተመሠረተበት እ.ኤ.አ. ከ1963 ጀምሮ ለመጀመሪያ ጊዜ በርከት ያሉ ዕጩዎች መቅረባቸው ነበር፡፡

ይህ ደግሞ ለሊቀመንበርነቱ የሚደረገውን ፉክክር ከምንጊዜውም በላይ ተጠብቂ እንዳደረገው ተነግሮለታል፡፡ እንዲሁም ይኸው ምርጫ በወቅቱ የአኅጉሪቱ መሪዎች አብላጫውን ድምፅ ለየትኛው ዕጩ ሊለግሱ ይችላሉ የሚለው የበርካቶችን ቀልብ ገዝቷል፡፡ ለዚህም ተጨማሪ ምክንያት ሆኖ የሚነሳው ከኪጋሊው ጉባዔ አራት ዓመታት ቀደም ብሎ በነበረው ተመሳሳይ ምርጫ፣ የአሁኗ ሊቀመንበር ዶ/ር ድላሚኒ ከቀድሞው ሊቀመንበር ጋቦናዊው ዣን ፒንግ ጋር ከእልህ አስጨራሽ ትግል በኋላ አሸናፊ ሆነው ወደ መንበሩ መምጣታቸውም እንደነበር አይዘነጋም፡፡

በዕጩነትም ቀርበው ዕጣ ፈንታቸው በኪጋሊ ይወሰናል ተብሎ ቀርበው የነበሩትም የቦትስዋና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ዶ/ር ፔሎኖሚ ቬንሰን ሞይታይ ከደቡባዊ አፍሪካ የልማት ትብብር አገሮችን (ሳድክ)፣ ኡጋንዳዊቷ (ከፖለቲካዊ ሚናቸው ይልቅ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት የረጅም ዓመታት ልምድ ያካበቱት) ዶ/ር ስፔሺዮዛ ንያይጋጋ ዋንዲራ ካዚብዌ የምሥራቅ አፍሪካን ማኅበረሰብ አገሮችን በመወከል፣ እንዲሁም የኢኳቶሪያል ጊኒ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የምዕራባዊ አፍሪካ የኢኮኖሚክ ማኅበረሰብ (ኢኮዋስ) አገሮችን የወከሉት አጋፒቶ ምባ ሞኩይ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ጉባዔው የተጠናቀቀው የሦስቱን ዕጩዎች አሸናፊ ሳይለይ ነበር በይደር በሚቀጥለው ወር በአዲስ አበባ ለሚዘጋጀው ጉባዔ የተላለፈው፡፡ ከሦስቱ አንዱ ዕጩ አሸናፊ የሚያደርገውን የ54ቱን አባል አገሮች መሪዎች ድምፅ ቢያንስ የ2/3ኛውን ድምፅ ማግኘት ይጠበቅባቸው የነበረ በመሆኑ ነው፡፡

የኅብረቱ መዋቅራዊ ሥርዓት

እ.ኤ.አ. ሐምሌ 9 ቀን 2002 የቀድሞው አፍሪካ አንድነት ድርጅት (አአድ) ወደ አፍሪካ ኅብረት ሲቀየር፣ የኅብረቱ የመጨረሻ የውሳኔ ሰጪነት ሥልጣን ያለው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ በመባል የሚታወቀው አካል የሁሉንም አባል አገሮች ርዕሳነ ብሔሮችና መንግሥታት የተካተቱበት ነበር፡፡ የዚህ ጉባዔ ሊቀመንበር ከእነዚሁ የአባል አገሮች መሪዎች በዙር ለአንድ ዓመት የሚመረጥ ቢሆንም፣ ሚናውም የኅብረቱ ስማዊ ሥልጣን እንዳለው ነው የሚታመነው፡፡ ይህ ጉባዔ የወቅቱ ሊቀመንበር በሆኑት የቻድ ፕሬዚዳንት ኢድሪስ ዴቢ የሚመራ ሲሆን፣ በመጪው ጥር ወር ከኅብረቱ የመሪዎች 28ኛ ጉባዔ በኋላ ይጠናቀቃል፡፡ የአፍሪካ ኅብረትን በዋና ጸሐፊነት የሚያስተዳድረውና በተዋረድ ሁለተኛው አካል የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሆኖ፣ በአዲስ አበባ መቀመጫውን ያደረገ ነው፡፡ የኮሚሽኑም ዋና ሊቀመንበር በመሆን በኅብረቱ የበላይ ውሳኔ ሰጪው ጉባዔ ለአራት ዓመታት የሥራ ዘመን የሚመረጥ ነው፡፡ ዋና ተግባሩን በተመለከተም የኅብረቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ፣ የኮሚሽኑ ሕጋዊ ወኪልና የሒሳብ ሹምነትን ያጠቃልላል፡፡ ተጠሪነቱም ቢሆን በቀጥታ ለአፍሪካ ኅብረት አስፈጻሚ ካውንስል (ምክር ቤት) ይሆናል፡፡

የሥራ ዘመናቸው ባለፈው ዓመት የተጠናቀቀው ተሰናባቿ ሊቀመንበር የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ የአገር ውስጥ ሚኒስትር የነበሩት ዶ/ር ድላሚኒ ዙማ ናቸው፡፡ ምክትላቸው ደግሞ ኬንያዊው ኤራስተስ ምዌንቻ ሲሆኑ፣ በኅብረቱ የአሠራር ሥርዓት መሠረት የእሳቸውም የሥራ ዘመን ከሊቀመንበሯ እኩል ተጠናቆ ለአዲሱ ተመራጭ ምክትል ሊቀመንበር በማስረከብ ይሰናበታሉ፡፡

እንደሚታወቀው የኮሚሽኑን ሊቀመንበርነት ለተሿሚው ግለሰብ ሊያስገኝ የሚችለው ዝናና አኅጉራዊ ዕውቅና ብቻ ሳይሆን ወክለው ለመጡበት አገርና አካባቢያዊ ቀጣና የሚያጎናጽፈው አስተዋጽኦ ጉልህ ተደርጎ ስለሚቆጠር ምርጫው ትልቅ ሥፍራ ሊሰጠው ችሏል፡፡ ይህ ደግሞ የአዲስ አበባውን የመሪዎቹን ጉባዔ ከፍ ባለ ጉጉት እንዲጠበቅ ከወዲሁ ማድረግ ችሏል፡፡ ሌላው ምክንያት በ27ኛው ጉባዔ ላይ ቀርበው በነበሩት ሦስት ዕጩዎች ላይ ሦስት ዕጩዎች ተጨምረው ፉክክሩ ወደ ስድስት ቢያድግም የኡጋንዳዋ ዕጩ ዶ/ር ካዚምብዌ ከዕጩነት ራሳቸውን በማግለላቸው፣ አምስት ዕጩዎች እየተፎካከሩ ነው፡፡

ከእነዚህም ውስጥ በቀዳሚው ያልተሳካ ምርጫ የምሥራቅ አፍሪካ ማኅበርን ወክለው በዕጩነት የቀረቡትን ዶ/ር ካዚምብዌን ተክተው የቀጣናው ሌላ ዕጩ ሆነው ብቅ ያሉት ኬንያዊቷ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የ55 ዓመቷ አሚና መሐመድ አዲስ ክስተት በመሆን ብቅ ብለዋል፡፡ እንዲሁም የቀድሞው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ልዩ ልዑክ በመሆን ሲያገለግሉ የነበሩት ሴኔጋሊያዊው አብዱላዬ ባቲሊ ለኮሚሽኑ ሊቀመንበርት አራተኛው ዕጩ ሆነው በቅርቡ ተቀላቅለዋል፡፡ ነገር ግን ከዕጩዎቹ ለየት ባለ የፖለቲካ ማንነታቸው አምስተኛው ዕጩ ሆነው የቀረቡት ቻዳዊው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የተቃዋሚ ፖለቲካ መሪ ሙሳ ፋኪ መሐማት አንዱ ክስተት ሆነዋል፡፡ የምርጫ ፉክክሩ ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ቀስ በቀስ ወደ ጋለና የከረረ ወደሚመስል ደረጃ መድረሱን የሚያሳዩ ፍንጮች መታየት ጀምረዋል፡፡

ከሁለት ወር ያነሰ ጊዜ ብቻ የቀረው ምርጫም፣ የአፍሪካ ኅብረት በታሪኩ ካደረጋቸው ምርጫዎች በተለየ ሁኔታ የፉክክሩ ግለት ከመሟሟቁ ባሻገር፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ዕጩዎች በይፋ በሕዝብ ፊት ክርክር ማድረጋቸው ነው፡፡ ቢመረጡ ምን ምን ሊያከናውኑና ሊያሻሽሉ የሚችሉ አጀንዳቸውን እንዲገልጹ መደረጉ መጪውን ምርጫ ቀልብ ሳቢ አድርጎታል፡፡ ዓርብ ኅዳር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. በአፍሪካ ኅብረት የመሰብሰቢያ አዳራሽ ዕጩዎቹ የመጀመሪያቸውን ክርክር ሲያደርጉ ቀጥታ የቴሌቪዥን ሥርጭት ሲያገች ኅብረቱ በራሱ ድረ ገጽ፣ ማኅበራዊ ገጾችና በቀጥታ ሥርጭት ለአፍሪካዊያን አሠራጭቷል፡፡

ለጎስቋላዋ አኅጉር ያላቸው ህልም

ለቻይናው የሚዲያ ተቋም ሲሲቲቪ በወኪል ጋዜጠኝነት በማገልገል ላይ በሚገኘው ግሩም ጫላና ባልደረባው አወያይነት (Moderators) ዓርብ ምሽት የመጀመሪያውን ክርክር ያካሄዱት አምስቱ ዕጩዎች፣ ከተመረጡ ለአኅጉሪቱ ሊሠሩ የሚችሉትን ዕቅድ በተጨማሪ ለተነሱላቸው ጥያቄዎች መልሶቻቸውን ሰጥተዋል፡፡ ነገር ግን ከሁሉም ዕጩዎች መደመጥ እንደተቻለው በአብዛኛው ጉዳዮች ባሏቸው ዕይታዎች ላይ ከመከራከር ይልቅ፣ በቀጥታ ለታዳሚዎቻቸው ሐሳባቸውን ሲገልጹ አምሽተዋል፡፡ ከታዳሚዎች ጋር በወሳኝና በአንገብጋቢ አኅጉራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ ስምምነት ያላቸው ይመስል ነበር፡፡

ለአብነትም ያህል በወጣቶች ጉዳይ ሁሉም ዕጩዎች ያላቸውን ዕይታና ሊሠሩ በሚገቡዋቸው ጉዳዮች ላይ ተመሳሳይ አቋም መጋራታቸው ተስተውሏል፡፡ ‹‹በወጣቶቻችን ላይ የግድ ማንኛውንም መዋዕለ ንዋይ ሆነ ሌላ አስፈላጊ ነገሮችን ሁሉ ልናፈስ ይገባል… በተጨማሪም በአኅጉራችን ባሉ ቦታዎች ሁሉ ግጭቶችን ለመፍታት ወጣቶች ቦታ ተሰጥቷቸው ተሳትፏቸውን ልናረጋግጥ ይገባናል…›› በማለት ነበር የኬንያዋ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሚና መሐመድ የገለጹት፡፡ ሴኔጋላዊው ባቲሊ በበኩላቸው፣ ከሥራ አጥነት ጋር ተያይዞ ያለውን የወጣቶች ችግር ለመቅረፍ በአኅጉሪቱ መጠነ ሰፊ የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በክርክር ሥነ ሥርዓት ወቅት ሌላው የተነሳው የንግድ እንቅስቃሴን ወደላቀ ደረጃ ማሳደግና በአባል አገሮች መካከል ውህደትን የማጠናከር ጉዳይ ሌላው የመከራከሪያ አጀንዳ ነበር፡፡ ‹‹እኔ ከተመረጥኩ አባል አገሮች ቪዛን በተመለከተ ያሉዋቸውን ሕጎችን እንዲከልሱ እተጋለሁ፡፡ ማንኛውም ነገር ከቪዛ በኋላ ነው የሚመጣው፤›› በማለት ዕቅዳቸውን የገለጹት ቦትስዋናዊዋ ዕጩ ቬንሰን ሞይታይ ናቸው፡፡

የቻድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሙሳ ፋኪም በተመሳሳይ አጀንዳ ያላቸውን ዕቅድ ባስረዱበት ወቅት፣ ‹‹ዛሬም ድረስ ነፃነታችን ከተረጋገጠ ከ60 ዓመታት በኋላ ከአንድ ሥፍራ ወደ ሌላ ሥፍራ ያለምንም ችግር (ያለምንም ቪዛ) መሸጋገር የማንችልበትን ሁኔታ ይዘን ልንቀጥል አይገባንም፡፡ የፈለገ ዘመዶቹ ወይም የቤተሰብ አባላት ወደሚገኙበት ሥፍራ ያለ ገደብ እንዲንቀሳቀስ የሚደረግበትን ሁኔታ ለማምጣት እሠራለሁ፤›› ሲሉ ነበር ያስረዱት፡፡

በተጨማሪም አምስቱ ተፎካካሪ ዕጩዎች ተመሳሳይ ወይም ተቀራራቢ አቋም ያሰሙበት ሌላኛው ፍሬ ነገር፣ አባል አገሮች ኅብረቱ ሥራውን ለማከናወን የሚያስፈልገውን የፋይናንስ ድጋፍ በተመለከተ የፖለቲካ ቁርጠኝነት እያሳዩ ባለመሆናቸው፣ ከአኅጉሩ ውጪ በሚገኝ ገንዘብና ዕርዳታ ላይ መንጠላጠሉን ያሳዩበት ጉዳይ ሆኖ ተስተውሏል፡፡

‹‹ይህ ትልቅ ቅሌት ነው፡፡ አፍሪካ ሁሉም ነገር አላት፡፡ አሁን የሚያስፈልገው በጎ ፈቃደኝነት ወይም ቅንነት ብቻ ነው፤›› በማለት አፍሪካ ራሷን መርዳት የምትችልበት ሀብት እጥረት እንደሌለባት ጨምረው ያስረዱት ሙሳ ፋኪ ነበሩ፡፡

ሴኔጋላዊው ባቲሊ በበኩላቸው፣ ‹‹አፍሪካ አኅጉራችንን በተመለከተ ሁላችንም ሞራላዊ ግዴታችን ልንወጣ የሚገባን ትክክለኛው ጊዜ ላይ ነን፤›› ብለዋል፡፡

ባህል ሆኖ የቆየው የባዕድ ልሳን ተፅዕኖ

የዘንድሮውን ምርጫ ከቀደሙት ጊዜያት የተለየ ገጽታ ያላበሰው በተሳታፊ ተፎካካሪ ዕጩዎች የቁጥር መብዛት ብቻ ሳይሆን፣ የዕጩዎች ስብጥር ለቦታው መሥፈርት ብቃት፣ የትምህርት ደረጃና ልምድ የገዘፈ ክብደት መሰጠቱ ጎልቶ እየታየ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በኅብረቱም ታሪክ ሆነ ቀደም ባለው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (አአድ) ታሪክ ለሊቀመንበርነቱ ቦታ እንደ ቀዳሚ መመዘኛ ወይም ባህል ተደርጎ የቆየው፣ አባል አገሮችን በሚናገሩት ቋንቋ መሠረት አድርጎ በፈረቃ ከሁለት ቀጣናዎች የመምረጥ ባህል ነበር፡፡ በተለይ የአንግሎፎንና የፍራንኮፎን (እንግሊዝኛ ተናጋሪና ፈረንሣይኛ ተናጋሪ) የተባሉ ሁለት ጎራዎችን መሠረት ያደረገ ምርጫ ነበር፡፡ በዘንድሮው ምርጫ የቀረቡት ዕጩዎች በአንፃሩ ከሁለቱ ጎራዎች በተጨማሪ ሌሎች ቋንቋዎች (ዓረቢኛና ስፓኒሽ) ተናጋሪዎች ተካተውበት በመቅረባቸው፣ ልማዳዊውን የመምረጫ መሥፈርት በማስቀረት የተሳታፊ ግለሰቦች ብቃትና ልምድ ወይም ልሂቅነትን (Merit Based) ያደረገ ምርጫ ሳይሆን አይቀርም የሚል ግምት ተሰጥቶታል፡፡ በእርግጥ ይህ ግምት እውነት ከሆነ በበጎ ሁኔታ ቢታይም፣ ለሌሎች ግን ብዙም እየተዋጣላቸው አይመስልም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ለምርጫው ውጤት ብቸኛ ወሳኙ የአባል አገሮች መሪዎች ብቻ መሆናቸው ይጠቀሳል፡፡

ኬንያዊቷ አሚና መሐመድና ቦትስዋናዊው ዶ/ር ቬሴንት ሞይታይ የእንግሊዝኛ ተናጋሪ ጎራውን ሲወክሉ፣ ሴኔጋላዊው ባቲሊ የፈረንሣይኛ ተናጋሪውን በመወከል ለመመረጥ ዘመቻውን የተቀላቀሉ ናቸው፡፡ ሌላኛው ዕጩ የኢኳቶሪያል ጊኒው ሞኩይ ከምዕራቡ ቀጣና ቢገኙም የስፓኒሽ ተናጋሪ ናቸው፡፡ አምስተኛው ዕጩ ቻዳዊው ፋኪ ፈረንሣይኛና ዓረቢኛ ተናጋሪ ናቸው፡፡ የዕጩዎች ቁጥር መብዛትና የቋንቋ ስብጥራቸው እ.ኤ.አ. ጥር 31 ቀን 2017 ለሚደረገው ምርጫ የአባል አገሮች መሪዎችን ከቀጣናዊ ወገንተኝነት ይልቅ፣ ለዕጩ ግለሰቦች ብቃትና ልሂቅነት ትኩረት ለመስጠት ያስገድዳቸዋል የሚለው መላምት እያደገ መጥቷል፡፡

‹‹ብልጥ ልጅ እየበላ…›› የሞሮኮ ዳግም አመጣጥ

የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር የሥራ ዘመን ለአራት ዓመታት የሚቆይ ሲሆን፣ ለሁለተኛ ጊዜ መወዳደር ይችላል፡፡ ዶ/ር ድላሚኒ ዙማ በራሳቸው ፈቃድ ለሁለተኛ ጊዜ መወዳደሩን ባለመፈለጋቸው ቢወጡም፣ በኅብረቱ ትልቅ ተፅዕኖ አላቸው ከሚባሉት አንዷ የሆነችው አገራቸው ደቡብ አፍሪካ ዕድሉን ጎረቤታቸውና የሳድክ አባል ለሆነችው ቦትስዋናዊ ዕጩ ድጋፏን በይፋ ለመስጠት የቀደማት አልነበረም፡፡ ይህም ደግሞ በኪጋሊው ጉባዔ ታይቶ የነበረ መሆኑ ይጠቀሳል፡፡ ቦትስዋናዊዋ ዶ/ር ሞይታይ ከአብላጫው 2/3ኛ ድምፅ በጥቂት ዝቅ ያለ ውጤት ቢያገኙም፣ ከሦስቱ ተወዳዳሪዎች ግን ከፍተኛ ድምፅ አስመዝግበው እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ይህ ደግሞ በቀጣዩ የአዲስ አበባ ጉባዔ እኚሁ ዕጩ የማሸነፍ ዕድላቸው የተሻለ ሊሆን እንደሚችል ከኪጋሊው ጉባዔ በኋላ ተገምቶም የነበረ ቢሆንም፣ የኋላ ኋላ ግን የኬንያዊቷ አሚና መሐመድ ወደ ፉክክሩ መቀላቀል የጉባዔውን ተጠባቂነት ከፍ አድርጎታል፡፡ አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች በድጋሚ የሚጠበቀውን የአብላጫ ድምፅ በዕጩዎች ማሟላት አስቸጋሪ እንዳይሆንና ድጋሚ ምርጫው ወደ ተጨማሪ ዙሮች እንዳይሸጋገርም እያሰጋቸው ነው፡፡ ይህ ደግሞ ዶ/ር ድላሚኒ ዙማ ለተጨማሪ ጊዜ በቢሮአቸው እንዲቆዩ የኮሚሽኑ አስፈጻሚ ጉባዔ ሊጠይቃቸው ይችላል፡፡ አለበለዚያ ጊዜያዊ የሽግግር ሊቀመንበር ወደመምረጡ ፊቱን ሊያዞር ይችላል፡፡

ወትሮም ምርጫው የአባል አገሮች መሪዎችን ሽኩቻ የሚመስል ክርክር ውስጥ የሚከታቸው ሲሆን፣ እንደየመጡበት ቀጣና የየራሳቸውን ቋንቋ ተናጋሪ ዕጩዎችን ለማስመረጥ ፍጭት ውስጥ ሲገቡ ነበር፡፡ ምናልባትም ይህ ዓይነቱ ሽኩቻ ሌላ ዓይነት ይዘው ያለው የአቋም ልዩነት ሊፈጥር ይችላል የሚል እምነት ያሳደረ አዲስ ጉዳይ ብቅ ብሏል፡፡ ይህም ከ32 ዓመታት መገለል በኋላ ዓረባዊቷ ሞሮኮ ወደ አባልነቷ ለመቀላቀል በእንቅስቃሴ ላይ መሆኗ ነው፡፡

ሞሮኮ ለሕዝባዊት ሰሃራዊ ዓረብ ዕውቅና በመስጠቱ ሳቢያ እ.ኤ.አ. በ1984 ከአፍሪካ አንድነት ድርጅት አባልነት ረግጣ በመውጣት ተቃውሞዋን ከውጭ ሆና ስታስተጋባ መቆየቷ ይታወሳል፡፡ እስካሁንም ድረስ ሰሃራዊ ዓረብን እንደ ግዛቷ በመቁጠር በአኅጉራዊው ተቋሙም ሆነ በሌሎች የተሰጣትን ዕውቅና ለማስቀልበስ አቋሟን እንዳፀናች ነው፡፡ ነገር ግን ከሦስት አሠርት ዓመት መገለል በኋላ አሁን ወደ አፍሪካ ኅብረትነት ወደተቀየረው ተቋም በመመለስ፣ ከውስጥ ሆኜ እታገላለሁ በሚል አዲስ የአቋም ለውጥ ‹‹ሕፃን ልጅ እየበላ ያለቅሳል›› ዓይነት ስትራቴጂ ይዛ ነው ብቅ ያለችው ሲሉ የፖለቲካ ተንታኞች ይገልጻሉ፡፡

የድጋሚ አባልነት ጥያቄዋም በአዲስ አበባው ጉባዔ ተቀባይነት አግኝቶ አባል አገሮች እንኳን ደህና ለቤትሽ አበቃሽ ብለው እንደሚቀበሏት ይጠበቃል፡፡ ሞቅ ላለው አቀባበል ደግሞ የሞሮኮዋ ንጉሥ መሐመድ ስድስተኛ የደለበ የገንዘብ ካዝና ትልቁ ሚስጥር ሊሆን እንደሚችል እየተነገረ ነው፡፡ ንጉሡም ቢሆኑ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኅብረቱ ተፅዕኖ አላቸው የሚባሉ አገሮችን ጨምሮ የተለያዩ አገሮች መሪዎችን በስልክ ሲያባብሉ መቆየታቸው ይነገራል፡፡ ወደ ኅብረቱ በሙሉ ቀልብ መመለሳቸውን እንደማሳያ የኢኮኖሚና የፖለቲካ አጋርነታቸውን ለማሳየት የንግድና የኢንቨስትመንት ስምምነቶች ማድረግ ጀምረዋል፡፡ ለአብነትም ያህል 3.7 ቢሊዮን ዶላር የሚፈስበት የማዳበሪያ ፋብሪካ በኢትዮጵያ ለመገንባት የተደረገው ስምምነት አንድ ማሳያ ነው፡፡ እንዲሁም ከሩዋንዳ መንግሥት ጋር 18 ያህል ስምምነቶች ተደርገዋል፡፡  

መቀመጫውን ጆሃንስበርግ ያደረገው ኢንስቲትዩት ኦፍ ሴኩሪቲ ስተዲ (አይኤስኤስ) የተባለው ተቋም ባቀረበው ጥልቅ ሪፖርት የሞሮኮን የመመለስ ፍላጎት አስመልክቶ ባሳተመው ትንታኔ፣ ‹‹አስደሳች የመልሶ መቀላቀልና የምዕራብ ሰሃራዊን ዕውቅና ለማስነሳት ያለሙ ጥንድ ስትራቴጂዎች›› ይዛ መመለሷን ገልጿል፡፡ ሞሮኮ በፈረንሣይኛ ተናጋሪዎችና በመካከለኛው የአፍሪካ አገሮች እንደ አለት የጠነከረ ድጋፍ እንዳላት የሚገልጸው አይኤስኤስ፣ የደቡብ አፍሪካዊቷ ዶ/ር ድላሚኑ ዙማ ከኅብረቱ ሊቀመንበርነት መነሳት አጥብቃ እንደምትፈልገውም ይገልጻል፡፡ በተለይ ዶ/ር ዙማ ሞሮኮ ከሌሎች አገሮች ጋር መልካም ግንኙነት እንዳይኖራት ፍላጎት አላቸው የሚል እምነትና በአገሮች ተቀባይነት እንዳይኖራት ተፅዕኖ ያደርጋሉ የሚል ድምዳሜ መኖሩን ያብራራል፡፡

ይህ ደግሞ ሚዛን የሚደፋ ሀቅ ከሆነ ዶ/ር ዙማ ከአገሮች ጋር በተለይም ከደቡብ አፍሪካ፣ ከዚምባቡዌና ከአልጄሪያ ጋር በመጣመር የሞሮኮን የመመለስ ጥያቄ ውድቅ ለማድረግ፣ ወይም የመመለሻ በሩን ዝግ ሆኖ እንዲቆይ ግፊት ሲያደርጉ ቆይተዋል የሚል ግምት አሰጥቶታል፡፡ በተጨማሪ ሞሮኮ ተመልሳ የምዕራብ ሰሃራዊን ዕውቅና በማስነሳት ከአባልነት የማስወገድ ህልሟ እውን እንዳይሆን አድርጓል የሚል አንድምታ እንዳለው የአይኤስኤስ ትንታኔ ያብራራል፡፡ በኪጋሊው ጉባዔ በተለይ የምዕራብ አፍሪካ ፈረንሣይኛ ተናጋሪ አገሮች ለቦትስዋናዋ ዶ/ር ቬንሰን ሞይታይ ድምፅ ከመስጠት ይልቅ በድምፀ ተአቅቦ ለማለፍ መወሰናቸውን አይኤስኤስ አመልክቷል፡፡ በመጪው ጉባዔ ግን ለቦትስዋናዋ ዕጩ ድምፃቸውን የነፈጉት የምዕራብ አፍሪካ አገሮች አዲስ ሆነው ለሚቀርቡት ዕጩ ሴኔጋላዊው ባቲሊ ድጋፋቸውን እንደሚቸሩ የጥናት ተቋሙ ግምቱን አስቀምጧል፡፡ ሴኔጋልም ብትሆን ለሞሮኮ ወደ ኅብረቱ መመለስ ስትታትር የቆችና የምዕራባዊ ሰሃራዊን ከኅብረቱ መወገድ የራሷን ቅስቀሳ ስታደርግ መቆየቷንም አውስቷል፡፡

ይሁን እንጂ በሌላ በኩል ኬንያዊቷ አሚና መሐመድና አገራቸው የሞሮኮን መመለስ ደጋፊ እንደሆነች ይኸው ተቋም ይገልጻል፡፡ ይህ እውነታ ደግሞ ምናልባትም አሚና እንግሊዝኛ ተናጋሪ ከሆኑ አገሮች ውስጥ የደቡብ አፍሪካ፣ የዚምባቡዌንና የአልጄሪያን ድጋፍ በምርጫው ወቅት ላያገኙ ይችላሉ ተብሎ ይገመታል፡፡ በተጨማሪም የአሚና በዕጩነት መቅረብ የሞሮኮ ደጋፊ የሆኑ አገሮችን ድምፅ የመስጠት ፍላጎት ለሁለት ሊከፍለው እንደሚችል፣ ለባቲሊ ሊሆን የሚችለውን ድምፅ በመቀነስ ለቦትስዋናዋ ዶ/ር ቪሴንት ሞይታይ የዕድል በር የሚከፍት አጋጣሚ እንደሚፈጥር ፍንጭ ይሰጣል የሚልም እምነት እንዳለው የጥናት ተቋሙ አመልክቷል፡፡

ከዘ ሔግ የሚመጣው ሌላው ፈተና

ለአዲስ አበባው ጉባዔ መሪዎቹ በምርጫውም ሆነ በሌሎች ተያያዥ አኅጉራዊ ጉዳዮች በተቀራረበ አቋም ሆነ የጋራ ውሳኔ ላይ እንዳይደርሱ፣ አይሲሲ የተባለው ዓለም አቀፍ የወንጀል ፍርድ ቤት ጉዳይ ተጠባቂ መሆኑን ሌሎች ማሳያዎች ሊነሱ ይችላሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የዓርብ ዕለቱ የዕጩዎች ክርክር ከመዘጋጀቱ በፊት በነበረ የቅድመ ክርክር ዝግጅት ወቅት የተፈጠረ አንድ ዓብይ ክስተት እንደነበረ ዘገባዎች አመልክተዋል፡፡ ለዕጩዎች ለማቅረብ ታስበው ከነበሩ የውይይት አጀንዳዎች መካከል የአይሲሲ ጉዳይ መነሳቱ፣ በራሱ ከዋናው የክርክሩ ዕለት በፊት አወዛጋቢ ሆኖም ነበር፡፡ በተለይም ኬንያዊቷ ዕጩ አሚና ከአይሲሲ አባልነት የመውጣት ጉዳይን የተመለከተ አጀንዳ የሚነሳ ከሆነ፣ ከክርክሩ ራሳቸውን ሊያገሉ እንደሚችሉ አስፈራርተው እንደነበር ከናይሮቢ የወጡ መረጃዎች አመልክተው ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት ደግሞ ቀድሞ ክርክሩን ለመምራት ተቀጥራ የነበረችውን ደቡብ አፍሪካዊ ጋዜጠኛ ካሪማ ብሮውንን ከአወያይነት ሚና ውጪ እንደሆነች ጋዜጠኛዋ ከሳምንት በፊት ገልጻለች፡፡ ‹‹ለምን እንዳስቀሩኝ እንኳ ማብራሪያ አልተሰጠኝም፤›› ያለችው ጋዜጠኛዋ፣ ‹‹ቀደም ብለን ልናነሳቸው የነበሩ ጥያቄዎች አጠቃላይ ሰብዓዊ መብቶችን የሚመለከቱ ከመሆናቸው ጋር በተያያዘ ነበር፡፡ የአይሲሲን አጀንዳ ለማንሳትም አቅደን ነበረ፤›› በማለት ገልጻለች፡፡

ኬንያ እ.ኤ.አ. ከ2007 ድኅረ ምርጫና በቀጠለው ብጥብጥ ከአንድ ሺሕ በላይ ኬንያውያን ተገድለው ከነበረበት ሁኔታ ጋር፣ የኬንያ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታና ምክትላቸው ዊሊያም ሩቶ ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ድረስ ለመቅረብ መገደዳቸው ይታወሳል፡፡ እንዲሁም በአይሲሲ የእስር ማዘዣ የተቆረጠባቸው የሱዳን ፕሬዚዳንት ኦማር ሐሰን አል በሽር ከአንድ ዓመት በፊት ደቡብ አፍሪካን በጎበኙበት ወቅት፣ ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ አሳልፈው ከመስጠት ይልቅ ተፈላጊውን ‹‹ወንጀለኛ›› መሪ ወደ ካርቱም አስመልጠዋቸዋል የሚል ውዝግብ ተቀስቅሶ ደቡብ አፍሪካ ከአይሲሲ አባልነት ለመውጣት ሒደቱን ጀምራለች፡፡

የኬንያ ፕሬዚዳንትና ምክትላቸው ላይ ተመሥርቶ የነበረው ክስ በኋላ እንዲቀር የተደረገ ቢሆንም፣ የኬንያ መንግሥት የአፍሪካ አገሮች ከሮሙ ስምምነት አባልነት እንዲወጡ መወትወቱን ቀጥሎበታል፡፡ ደቡብ አፍሪካም የኬንያን ዕርምጃ አጥብቃ መደገፏን በጉልህ እያሳየች ትገኛለች፡፡ እንዲሁም ከኬንያም ሆነ ከሱዳን ጋር የተጠበቀ ግንኙነትና ወዳጅነት ያላት ኢትዮጵያም ብትሆን የሮሙ ስምምነት ፈራሚ ባትሆንም፣ የፀረ አይሲሲ አቋምን በግምባር ቀደምትነት ከሚያራምዱ አገሮች አንዷ ነች፡፡ ይህንኑም የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ይህንን በተለያዩ አኅጉራዊና ዓለም አቀፋዊ መድረኮች በግልጽ ያራምዱ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ከእሳቸውም ሕልፈት በኋላ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ገና በጠዋቱ ወደ ሥልጣን መንበሩ ከመጡበት ጊዜ ጀምሮ ይህንኑ ተመሳሳይ አቋም አጠናክረው ቀጥለውበታል፡፡ ይልቁንም፣ ‹‹ፍርድ ቤቱ በአፍሪካ ላይ ብቻ ለይቶ ያነጣጠረና የዘረኝነት ሴራ እየፈጸመ ነው፤›› በማለት ትችት እ.ኤ.አ. በ2013 በአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ ላይ ማቅረባቸው አይዘነጋም፡፡    

በዚህም ጉዳይ መጪው ጉባዔ የምርጫ ተግባሩን በቀላሉ ለማከናወን ያዳግተዋል የሚል ግምት ከወዲሁ እየተሰጠው ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ካለፉት ሦስት ዓመታት ጀምሮ ከአይሲሲ ለመውጣት መደበኛ ሒደት የጀመሩት ደቡብ አፍሪካ፣ ቡሩንዲና ጋምቢያ ናቸው፡፡ ነገር ግን ምንም እንኳ የፀረ አይሲሲ የዘመቻ ጩኸት ጎልቶ እየተሰማ ቢመጣም፣ በአኅጉሪቷ እየታየ ያለው ገጽታ ግን እየተወሳሰበ ነው የሚሉ ተንታኞች ይደመጣሉ፡፡ ለአብነትም ያህል በጥቅምት ወር በዘ ሔግ በተስተናገደው 15ኛው ‹‹አሴምብሊ ኦፍ ስቴት ፓርቲስ›› የአይሲሲ አባል አገሮች ጉባዔ ለፍርድ ቤቱ ድጋፋቸውን በመግለጽ፣ ሊጠናከር እንደሚገባው ድምፃቸውን አጉልተው ሲናገሩ ከተደመጡት አገሮች አብዛኞቹ የአፍሪካ አገሮች ነበሩ፡፡ በተለይም ቦትስዋና፣ ጋና፣ ቡርኪና ፋሶ፣ ሌሴቶ፣ ማሊ፣ ናይጄሪያ፣ ቱኒዚያ፣ ሴኔጋልና ኮትዲቯር በዋነኝነት ይጠቀሳሉ፡፡  

የእነዚህ አገሮች አሠላለፍ ደግሞ በተለይም በኬንያዊቷ ዕጩ ላይ የራሱ የሆነ አስቸጋሪ ተፅዕኖ ማሳረፉ የማይቀር ነው፡፡ ኬንያ የያዘችውን ፀረ አይሲሲ አቋሟን ካልተወች የምዕራብ አፍሪካ አገሮች ድምፅ ወደ ቦትስዋናዊዋ ዕጩ ሊያጋድል እንደሚችልም ፍንጭ ይታያል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ ከግማሽ በላይ በሳድክ ጎራ ሥር ያሉ የደቡባዊው አፍሪካ አገሮች ድምፅ ደግሞ ፀረ አይሲሲ አቋም ካላቸው አገሮች ጎራ ለተወከሉት ለአሚና መሐመድና ለባቲሊ ሊያጋድል ይችላል፡፡ በአመዛኙ ደግሞ ወደ ባቲሊ ሊያጋድል እንደሚችል የማይቀር ነው፡፡  ሌላው መጠነኛ ውስብስብ ጉዳይ ተደርጎ መነሳት የሚችለው ጉዳይ አይሲሲ ለመልቀቅ የመውጫ በሩን እያማተሩ ካሉት አገሮች ውስጥ ደቡብ አፍሪካ፣ ቡሩንዲና ጋምቢያ የተጋፈጡት የፖለቲካ ወይም የደኅንነት ቀውስ በራሱ ይጠቀሳል፡፡

የአፍሪካውያን ወጣቶች ሥራ አጥነት፣ ወደ ሜዲትራኒያን በአደገኛ ሁኔታ አቋርጦ ወደ አውሮፓና መካከለኛው ምሥራቅ መፍለስ፣ ድህነትና የሰብዓዊ መብት ረገጣዎች በአኅጉሪቷ የገዘፉ ፈተናዎች በመሆን መቀጠላቸው በስፋት ይተችበታል፡፡ በእነዚህ ሁሉ ፈተናዎች የአዲስ አበባው ጉባዔ የአኅጉሪቱን መሪዎች እ.ኤ.አ. ከጥር 30 እስከ 31 ቀን 2017 ለማስተናገድ ከሁለት ወራት ያነሱ ጊዜያት ቀርተውታል፡፡ ምናልባትም ጉባዔው የአፍሪካ ኅብረትን ስም በአዎንታዊም ሆነ በአሉታዊ ጎኑ ሊያስጠራ የሚችል ታሪክ አስመዝግቦም ሊያልፍ ይችላል ተብሎም እየተጠበቀ ነው፡፡ 

Standard (Image)

የ22 ዓመቱ ፌዴራሊዝም ሲመዘን

$
0
0

የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ለፌዴራላዊ ሥርዓት ምሥረታ መሠረት ሲሆን፣ ብሔርና ብሔረሰቦችን የኢትዮጵያ ሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤቶች ያደርጋል፡፡ በዚህም የተነሳ ከግለሰቦች መብት ይልቅ የቡድን መብትን ያስቀድማል፡፡ የቋንቋ፣ የብሔርና የሃይማኖት ብዝኃነት ትኩረት ካገኙ ጉዳዮች ተጠቃሽ ናቸው፡፡

ሕገ መንግሥቱ ከፀደቀ እነሆ 22 ዓመታት አለፉ፡፡ ዘንድሮ በታሪካዊቷ የምሥራቅ ኢትዮጵያ ከተማ ሐረር ተከብሮ የዋለው ኅዳር 29 የብሔር ብሔረሰቦች ቀን ሲሆን፣ ይኸው ሕገ መንግሥት የፀደቀበት ቀን ነው፡፡

የፌዴራሊዝም ሥርዓት በኢትዮጵያ ሲታወጅ ዕልል ብለው የተቀበሉ ያሉትን ያህል፣ ሥርዓቱ እንግዳ የሆነባቸውም ጥቂት አልነበሩም፡፡ ባህላቸውና ቋንቋቸው ተዘንግቶና ተረስቶ፣ በማንነታቸው እንዲያፍሩ መደረጋቸውን የሚያስቡ ወገኖች በፀጋ ሲቀበሉት፣ በቀደሙት ሥርዓት አካላትና በሌሎች ወገኖች ደግሞ እንደ አጥፊና አፍራሽ ዕርምጃ ታይቶ ነበር፡፡ ሥርዓቱን ከሚደግፉ ምሁሯን መካከል የሆኑት ፕሮፌሰር እንድርያስ እሸቴ፣ ‹‹በአምባገነኑ ውድቀት ዋዜማ የነበሩት ተቃውሞዎች ታሪክና ማንነት፣ ኢትዮጵያ ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በምታደርገው ሽግግር ዋና የፖለቲካ መሣሪያ በብሔር ላይ የተመሠረተ ፌዴራሊዝም ሥርዓት መሆኑን ያሳያል፤›› ብለው ነበር፡፡

የፌዴራል ሥርዓቱን ከሚቃወሙት መካከል ደግሞ ኢትዮጵያዊነት ተሠራበት ብለው የሚያምኑትን አስኳል እንዳፈረሰ የሚሰማቸው አሉ፡፡ ሥርዓቱን በታኝ፣ ፀረ አንድነት፣ ፀረ ኢትዮጵያዊ አድርገውም ይሥሉታል፡፡ በእርግጥ የቀድሞዋ ኢትዮጵያ ‹‹የብሔረሰቦች እስር ቤት›› ነበረች ብለው የጻፉ ያሉትን ያህል፣ እነዚህ የአዲሱ ሥርዓት ተቃዋሚዎች ዘረኝነት፣ ጠባብነትና የመሳሰሉ ቅፅሎችን ለአዲሱ ሥርዓት ሲሰጡ በተደጋጋሚ ተሰምተዋል፡፡

በወቅቱ ከወጡ የፕሬስ ኅትመቶችና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች ማረጋገጥ እንደሚቻለው፣ የአዲሱ ሥርዓት አመንጪዎችም ሥርዓቱን ለመከላከል ተቃዋሚዎቻቸውን ‹‹ጠላቶች››፣ ‹‹የቀድሞ ሥርዓት ናፋቂዎች›› እና ‹‹ትምክህተኞች›› የመሳሰሉ አጠቃቀሞች ያዘወትሩ ነበር፡፡ የቃላት ጦርነቱ ዛሬም ድረስ የተጠናቀቀ ባይሆንም፣ በ1997 ዓ.ም. አወዛጋቢ ምርጫ የከፍታውን ጫፍ ነክቷል፡፡

ራሳቸውን እንደ አሸናፊና ተሸናፊ አድርገው የሚቆጥሩ ኢትዮጽያዊያን ልሂቃን ስለአንድነት ያላቸው አመለካከት ፅንፍ እንዲይዙ ያደረጋቸው ይመስላል፡፡ ከዚህ የሚመነጨው አስተሳሰብ አንዱ ሌላውን ለመጣል የሚጠቀምበት መንገድ ተደርጎም ይታያል፡፡

የኢትዮጵያ ፌዴራሊዝም ከየት ወዴት?

በደርግ ሥርዓት መጨረሻ አዲሱ የኢሕአዴግ ሥርዓት አዲስ የአገር ግንባታ ፕሮጀክት ይዞ ቢመጣም፣ አገሪቱን ከመበታተን ይታደጋል ብሎ የሚያምን እምብዛም አልነበረም፡፡ አዲሱን የፌዴራል ሥርዓት እንደ ጦር የፈሩት፣ ዛሬም ድረስ የኢትዮጵያ አንድነት ፀር አድርገው ይመለከቱታል፡፡ በተለይ ደግሞ የፌዴራል ሥርዓቱ ዋና መሠረት ብሔር መሆኑ፣ ኢትዮጵያ የዩጎዝላቪያ ዕጣ ፈንታ እንዳይገጥማት ሥጋታቸው ከፍ ያለ ነበር፡፡

የአገሪቱ ህልውና ግን እንደተፈራው ችግር አልገጠመውም፡፡ የፌዴራል ሥርዓቱ እንደተፈራው ኢትዮጵያን አልበተናትም፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በአንድ ወቅት በጉዳዩ ላይ ተጠይቀው ምላሽ ሲሰጡ፣ ‹‹ኢትዮጵያ የቆመችው አሸዋ ላይ አይደለም፡፡ በዚሁ ሥርዓት ከተበታተነች ግን ድሮም መሠረቷ የተናጋ ነበር፤›› ብለዋል፡፡

ኢሕአዴግ አዲስ አበባ ሲገባ ኤርትራ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በቀላሉ ብትገነጠልም፣ ጨቋኝ ከሚሏት አገር ለመገንጠል ሲታገሉ የነበሩ ሌሎች ኃይሎች ሳይቀሩ፣ በሒደቱ ተሳታፊ ሆነው ሕዝባቸውን አሳምነው በኢትዮጵያ ጥላ ለመቀጠል ወስነዋል፡፡

ለኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት መሠረት የሆኑት የለንደኑ፣ የፓሪሱና የአዲስ አበባው ጉባዔዎች ተጠቃሽ ሲሆኑ፣ የቀድሞ ኤፌዴሪ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በሜሪላንድ ዩኒቨርሲቲ ፕሮግራም ላይ ተገኝተው በሰጡት ገለጻ፣ በተደረጉ ሕዝባዊ ውይይቶችና ጥናቶች ራስን በራስ የማስተዳደር መብት ለሚሰጠው አዲሱ ሥርዓት የተለያዩ ክልሎች ድጋፋቸውን ከፍ ያለ ነበር ብለዋል፡፡ ሥርዓቱ ዝቅተኛ ድጋፍ ያገኘው በአዲስ አበባ (67 በመቶ) እና በጋምቤላ (59 በመቶ) ነበር፡፡ ከፍተኛውን ድጋፍ ያገኘው በአፋር (97 በመቶ) እና በኦሮሚያ (95 በመቶ) ነበር ሲሉም አስረድተዋል፡፡

በእርግጥ ሕዝባዊ ድጋፋቸውን ምን ድረስ እንደሆነ መገመት ባይቻልም፣ ዛሬም ድረስ ግን በተለያዩ አካባቢዎች እንወክለዋለን የሚሉትን ሕዝብ ለማስገንጠል ጫካ የገቡ አሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል በአገሪቱ ፓርላማ በሽብርተኝነት የተፈረጁት ኦብነግና ኦነግ ተጠቃሾች ናቸው፡፡

 የኢትዮጵያ አገር ግንባታ ሥርዓት ተቃርኖ በተቃዋሚዎችና በገዢው ፓርቲ በኢሕአዴግ ብቻ የሚስተዋል አይደለም፡፡ በተቃዋሚዎች መካከል የእርስ በርስ ሽኩቻ ሲፈጥርም ይስተዋላል፡፡ ኅብረ ብሔራዊ አደረጃጀት ይዘው የተዋቀሩና አንድነትን የሚያስቀድሙ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ብሔርን መሠረት አድርገው የተመሠረቱትን ቁጥር አንድ ጠላት አድርገው ይመለከቷቸዋል፡፡

ሁለቱም ዓይነት ፓርቲዎች አብረው ገዢውን ፓርቲ የሚፋለሙበት ‹‹አማካይ›› ሥፍራ እንዲፈጥሩ፣ የኢሕአዴግ መሥራችና የቀድሞ የመከላከያ ሚኒስትር አቶ ስዬ አብረሃ ባቀረቡት ጥናት መክረው ነበር፡፡ ከቀድሞው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ጋር በመሆን አቶ ስዬ አንድነት ለፍትሕና ለዴሞክራሲ ፓርቲን ተቀላቅለው መድረክ የተሰኘ ስብስብ መፍጠራቸው የሚታወስ ነው፡፡ የማታ ማታ ግን ቀድሞም በአቋም እሳትና ጭድ ናቸው ተብለው ሲተቹ የነበሩት አንድነት መድረክም ተለያይተዋል፡፡ በኋላ በተለያዩ አጋጣሚዎች ሁለቱም የቀድሞ የኢሕአዴግ ሰዎች አንድነትን ጥለው ወጥተዋል፡፡ አቶ ስዬ አሁንም ድረስ በጉዳዩ ላይ የሰጡት አስተያየት ባይኖርም፣ ዶ/ር ነጋሶ ግን ከአንድነት አራማጅ ኃይሎች ጋር በጋራ መሥራት አይቻልም የሚል አስተያየት መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡

በውጭ ያሉት አክራሪ ተብለው የሚፈረጁት የዳያስፖራ ተቃዋሚዎችም አገር ውስጥ ካሉት በላይ የተለያየ ፅንፍ የያዙ እንደሆኑ የሚነገር ሲሆን፣ አልፎ አልፎ የኢሕአዴግን መንግሥት ለመጣል ብቻ የመተባበር መንፈስ ያሳያሉ፡፡ ለአንዳንድ የፖለቲካ ታዛቢዎች ግን ትብብሩ ‹‹የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው›› ከሚል መርህ ውጪ አንዳችም መሠረት የለውም፡፡

የአንድነትና የብዝኃነት ገጽታ

ሚሊዮን ሺበሺ የተባሉ ጸሐፊ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ብዙ ጊዜ የመንግሥት አቋም በሚንፀባረቅበት ‹‹አጀንዳ›› ዓምድ ላይ ‹‹ኅብረ ብሔራዊ ፌዴራሊዝም›› በሚል ጽሑፋቸው፣ ‹‹በፌዴራላዊ የመንግሥት አወቃቀር ዕይታ አንድነት ወይም ኅብረት ማለት ብዝኃነትን በማክበርና በጋራ ጥቅምና ፍላጎት ላይ በመመሥረት አብሮ የመቀጠል ውሳኔ (ውል) ስምምነት ማለት ነው፤›› ብለዋል፡፡ ቀጥለውም ብዝኃነትን መሠረት አድርጎ የሚዋቀር የፖለቲካ ሥርዓትን ደግሞ ኅብረ ብሔራዊ የፌዴራል ሥርዓት እንደሚባል ይገልጹታል፡፡ በባለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት የፌዴራል ሥርዓቱን ስኬት በሚያጎላው ጽሑፍ፣ የመሠረት ልማትና የኢኮኖሚ ዕድገት፣ የሰብዓዊና የዴሞክራሲያዊ ጥያቄዎች መመለስና የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ዕውን እንዲሆን ማስቻሉን ያትታሉ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በዘንድሮ የብሔር ብሔረሰቦች በዓል ላይ ተገኝተው ባሰሙት ንግግር፣ ‹‹የፌዴራል ሥርዓቱ ኢትዮጵያዊነት መንፈስ የተላበሰና አንድነትን መሠረት ያደረገ ነው፤›› በማለት ከተለመደው ወጣ ያለ አስተሳሰብ አራምደዋል፡፡ በመንግሥት ደረጃ የአቋም ለውጥ እየተደረገ ስለመሆኑ ማሳያ መስሏል፡፡

በቅርቡ መንግሥታቸው ያደራጀው አዲሱ ካቢኔ፣ ከዚህ በፊት ከተለመደው የ‹‹ብሔር ውክልና›› እና ‹‹የፖለቲካ ታማኝነት›› መሠረት ያደረገ ሹመት በአመዛኙ በመሸሽ፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግርም ከዚህ በፊት ወደ ልዩነት ያደላል ተብሎ ሲታማ የነበረውን ብሔር ተኮር ፌዴራሊዝም ወደ ‹‹ኅብረ ብሔራዊነት›› እያመራ ነው ወይ የሚል ውይይት እያጫረ ነው፡፡

‹‹ኅብረ ብሔራዊ›› ጽንሰ ሐሳብን ብዙ ጊዜ የብሔር ተኮር አደረጃጀት በመቃወም አንድነትን የሚያራምዱ ወገኖች ሲጠቀሙበት የኖረ አገላለጽ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት የከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናትም ሆነ የመንግሥት ሚዲያዎች በብዛት እየተጠቀሙበት ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ በቅርቡ በኢቢሲ በተላለፈው ዘጋቢ ፊልም ‹‹ዴሞክራሲያዊ ብሔርተኝነትና ኅብረ ብሔራዊ ፌዴራሊዝም›› የሚለው ይገኝበታል፡፡ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ በበኩላቸው በዓሉን አስመልክተው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ‹የአገራችን ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀደም ባሉት ዘመናት በመካከላቸው የነበረውን የተዛባ ግንኙነት በማረም፣ በመከባበር፣ በመቻቻልና በመፈቃቀድ ላይ የተመሠረተ ኅብረ ብሔራዊ አንድነትን በይበልጥ እያጎለበቱ ይገኛሉ፤›› ማለታቸው ይገኝበታል፡፡ ባለፉት 22 ዓመታት አገሪቱ በርካታ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ስኬት ያስመዘገበች መሆኗን የገለጹት ፕሬዚዳንቱ፣ ‹‹ይሁን እንጂ በእነዚህ ዓመታት የመልካም አስተዳደር ችግር፣ ኪራይ ሰብሳቢነትና የሃይማኖት አክራሪነት ዋና ዋና የህዳሴ ጉዞአችን ተግዳሮቶች ነበሩ፤›› ሲሉ ተደምጠዋል፡፡

‹‹መልካም አስተዳደር›› እና ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነት›› የመሳሰሉት በኢሕአዴግ መዝገበ ቃላት ውስጥ ከፍተኛ ቦታ ያላቸው ሲሆኑ፣ የፌዴራሊዝም ዋነኛ የማዕዘን ድንጋይ ከሆነው የአስተሳሰብ ልዩነት ይመነጫል ተብሎ የሚታመነው የብዙኃን ፓርቲ ፖለቲካ ጉዳይ ግን ጠቅላይ ሚኒስትሩም፣ ፕሬዚዳንቱም ሆነ የኢሕአዴግ ደጋፊ ጸሐፊዎችም ሲያነሱት አይስተዋልም፡፡

ከ22 ዓመታት በኋላ ወዴት?

አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች በቅርቡ የተፈጠረው ሁከትና አመፅ ሥርዓቱን ተቃውሞ ዩተደረገ መሆኑን ሲገልጹ፣ በዋናነት ከኦሮሚያ አካባቢ የመነጨው ተቃውሞ ግን ለፌዴራል ሥርዓቱ አፈጻጸም ጉድለትም አመላካች ነው ይላሉ፡፡

ፌዴራል ሥርዓቱ በታወጀባቸው የመጀመሪያ አሥርና ከዚያ በላይ ዓመታት ዋናው የፖለቲካ አጀንዳ የብሔር መብት መከበር ላይ ያተኮረ ብቻ እንደነበር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌዴራሊዝም ጥናት ማዕከል ተባባሪ ፕሮፌሰር (ዶ/ር) ዘመላክ አየለ ለሪፖርተር ያስረዳሉ፡፡ እሳቸው እንደሚሉት ይህ አዝማሚያ ብሔርተኝነትን ያጎላ ሲሆን፣ መንግሥት የአገሪቱን አንድነት ለመጠበቅ የኢኮኖሚ ልማት ማፋጠን፣ አገራዊ አጀንዳ የሚቀሰቅሱ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ማከናወንና የመሠረተ ልማት ግንባታዎችን እንደ አቅጣጫ ይዞ ነበር፡፡ ሆኖም በቅርቡ ለአሥር ወራት የዘለቀው ሕዝባዊ አመፅ የኢኮኖሚ ዕድገት ማምጣት ብቻውን ሥርዓቱ በዘላቂነት ለማስቀጠል ዋስትና አለመሆኑን ማሳያ መሆኑን ያምናሉ፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር መንፈስም ከዚህ አኳያ ተመልክተውታል፡፡

መንግሥት ሕገ መንግሥታዊ ማሻሻያ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን በቅርቡ ሲገልጽ፣ ብዙዎች መገንጠልን የሚፈቅደው አንቀጽ 39 እንዲከለስ የጠበቁ ይመስላሉ፡፡ ዶ/ር ዘመላክ ግን፣ ሕገ መንግሥቱ ላይ ወሳኝ የሚባል ማሻሻያ ሳያደርጉ አፈጻጸሙን ማረም እንደሚሻል ያሳስባሉ፡፡ ሕገ መንግሥቱ እንዳይነካ የሚፈልጉም ይኖራሉ በማለት፡፡

“Are Federal System Better than Unitary System?” በሚል ርዕስ የቦስተን ዩኒቨርሲቲ ሦስት አጥኚዎች ባደረጉት ምርምር፣ ‹‹አሃዳዊ ሥርዓት እንደ መርህ ከጥቅም ውጪ እየሆነ መጥቷል፡፡ ይህንን ሥርዓት የሚደግፍ አንድም አሳማኝ ጽንሰ ሐሳብ አልተገኘም፤›› በማለት ይንደረደራሉ፡፡

ተመራማሪዎቹ ከፌዴራሊዝም ሥርዓት የሚመነጭ አንዱ አዲሱ ባህሪ፣ ‹‹የውሳኔ አሰጣጥ ሥርዓት ከአንድ ማዕከል አውጥቶ ወደ ዳር ይወስዳል›› ካሉ በኋላ፣ በውሳኔውም ላይ ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት (Veto Power) ዳር ላይ የተቀመጡ ቁጥራቸውም በርከት ያሉ እንደሚሆኑ ያስረዳሉ፡፡

ምናልባትም አንዱ የፖለቲካ ተንታኝ ምክንያቱን ሲያስረዱ ከፍተኛ የማስተዳደር ሥልጣንና ሀብት በእጃቸው ያስገቡ ክልሎች ጉልበትና አቅም ካገኙ በማዕከላዊ መንግሥት ላይ ሊያምፁ ይችላሉ በማለት ነው፡፡ ለዚህም አመላካች የሚሆነው በአንዳንድ ክልሎች ውስጥ የሚታየው (የአገር ለአገር የሚመስል) ግንኙነት አዝማሚያና ከሌሎች ክልሎች የሚመጡ ዜጎችን እንደ የሌላ አገር ዜጋ የማየት ዝንባሌ ይጠቀሳል፡፡ የፌዴራሊዝም የመጨረሻ ግብ አንድነት ማምጣት ሲሆን፣ ተቃራኒውን እየሆነ እንዳይሆን ሥጋት አለ፡፡

የፌዴራሊዝም አንዱ ገጽታ ሥልጣንን ወደ ታች ወደ ሕዝብ የማውረድ (Decentralization) ሲሆን፣ የቦስተኑ አጥኚዎች በተለይ በደሃና ጠንካራ የፖለቲካ ተቋማት በሌሉባቸው አገሮች የአካባቢ አስተዳዳሪዎችና ባለሥልጣናት በቀላሉ ለሙስና የመጋለጥ፣ እንዲሁም ለድርጊታቸው ተጠያቂ የመሆን ዕድል ዝቅተኛ መሆኑንና ፀረ ዴሞክራሲያዊ አሠራር የማስፈን አዝማሚያ ሰፊ እንደሆነ ይደመድማሉ፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት የሁከቱና የቀውሱ መነሻ ምክንያት የ‹‹መልካም አስተዳደር›› ችግር በማለት ጉዳዩን ቀላል አድርጎ የማቅረብ አዝማሚያ የሚታይበት ቢሆንም፣ የተከሰተው ቀውስ ከዚህ ዓይነት ሥልጣንን ከታለመለት ዓላማ ውጪ ጥቅም ላይ በመዋሉ የተነሳ እንደሆነ ግን ተቀብሏል፡፡

አንዳንድ ምሁራን የፌዴራል ሥርዓትን በቀጥታ ከብዝኃነት አስተሳሰብ ጋር የሚያስተሳስሩት ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት በኢትጵያ ካለው ወቅታዊ የአውራ ፓርቲ ፖለቲካ ጋር እንደሚቃረን ይሞግታሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል ከምስት ዓመታት በፊት በአዲስ አበባ በተካሄደው አምስተኛ የፌዴራሊዝም ዓለም አቀፍ ጉባዔ ተሳታፊ የነበሩት ማንዳል ማናንዳር የተባሉት የኔፓል ዜጋ ሪፐብሊካ በተባለው ሚዲያ እንዳስነበቡት፣ ‹‹የኢትዮጵያ ፌዴራል ሥርዓት ለብዙኃኑ ሰላምና መረጋጋት አምጥቷል፡፡ ሆኖም ፓርቲን ከአገር የመለየትና የአንድ ፓርቲ አስተሳሰብን በብዙኃን አስተሳሰብ የመተካት ተግዳሮት ተጋርጦበታል፤›› በማለት አደጋውን አመላክተው ነበር፡፡ ምናልባትም ለልዩነት ዕውቅና መስጠት የማይፈልገው ኢሕአዴግ አንድ ፓርቲና አንድ አስተሳሰብ በማራመድ ቀድሞ በሕገ መንግሥቱ ሳይቀር ያሰፈረውን አስተሳሰብ በሚቃረን መንገድ እየተጓዘ እንዳይሆን ሥጋታቸውን የሚገልጹ አሉ፡፡

አንዳንድ የቀውስ ወቅት ተንታኞች ሁከቱ ሥርዓቱ በሚመራበት የአውራ ፓርቲ አስተሳሰብ ላይ የተነሳ ተቃውሞ በማድረግ የሚመለከቱ ሲሆን፣ ዶ/ር ዘመላክ ግን በዋና ዋና ፓርቲዎች መካከል ስምምነት የተመሠረተ እንደሆነ የአንድ ፓርቲ የበላይነት በፌዴራል ሥርዓቱ ላይ ተፅዕኖ ላይኖረው ይችላል ይላሉ፡፡ ስምምነት ስለመፈጠሩ ግን በመጠራጠር፡፡ አቶ ልዑልሰገድ ታደሰ የተባሉ ተመራማሪ፣ “can Diversity be Accommodated: The case of Ethiopia” በሚለው ጥናታቸው፣ ‹‹ዴሞክራሲ በሌለበት እውነተኛ የፌዴራል ሥርዓት መገንባት አይቻልም፤›› የሚል ክርክር በማቅረብ፣ በኢትዮጵያ በሕገ መንግሥቱ ዕውቅና የተሰጣቸው የዴሞክራሲና የብዝኃነት ጽንሰ ሐሳቦች ቢኖሩም እነዚህን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችሉ ጠንካራ የዴሞክራሲ ተቋማት አለመኖራቸው፣ በሥርዓቱ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሮበታል ይላሉ፡፡

በተጨማሪም የፌዴራል ሥርዓቱ አንዱ ዓላማ የብሔር ግጭቶችን ማስወገድና ማስቀረት ቢሆንም፣ ግጭት ሲከሰት ለመፍታት የሚያስችሉ ጠንካራ ተቋማትና የግጭት አፈታት ዘዴዎች እንደሌሉም ይከራከራሉ፡፡ እንዲሁም በፌዴራል መንግሥትና በክልል መንግሥታት መካከል ያለውን ያህል፣ በክልል መንግሥታት የእርስ በርስ (Horizontal) ግንኙነት ላይ በቂ አሠራር የለም ይላሉ፡፡

አሁን ባለችው ኢትዮጵያ ልዩነትን ከማስፋት ይልቅ በማጥበብ፣ ትምክህትና ጥበት የሚባሉ አስተሳሰቦችን ወደ ጎን በማለት፣ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የጋራ ዕድላቸው መመሥረት ያለበት ከታሪካቸው የወረሱትን የተዛባ ግንኙነት በማረምና የጋራ ጥቅማቸውን በማሳደግ፣ መብቶቻቸውንና ነፃነታቸውን በጋራና በተደጋጋፊነት በማሳደግ አንድ የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ የመገንባት አስፈላጊነት ላይ በሕገ መንግሥቱ ያደረጉትን ስምምነት ከመተግበር የተሻለ አማራጭ የላቸውም የሚለው ድምፅ እያየለ ይመስላል፡፡ ይህም በአገሪቱ መሪዎችና ባለሥልጣናት ጭምር መቀንቀን ጀምሯል፡፡ ለኅብረ ብሔራዊ አንድነት መንገዱም እንደ መንደርደሪያ እየታየ ነው፡፡ 

Standard (Image)

ኢትዮጵያ በጆን ማርካኪስ ምልከታ

$
0
0

በአገሪቷ ታዋቂ የሆኑት ግሪካዊው ጆን ማርካኪስ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ ጥልቅ ዕውቀትን ያዳበሩ ምሁር ናቸው፡፡ የመጀመርያ ዲግሪያቸውን በፖለቲካል ሳይንስ የትምህርት ዘርፍ ከብሩክሊን ኮሌጅ፣ ሁለተኛ ዲግሪንና ፒኤችዲያቸውን በመንግሥትና የአፍሪካ ጥናት ዘርፍ ከታዋቂው ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል፡፡ በአፍሪካ አገሮች ኢኮኖሚ በተለይም በኢትዮጵያና በአፍሪካ ቀንድ በሚገኙ አጎራባች አገሮች ከፍተኛ ጥናት አድርገዋል፡ የሕይወታቸውን ረዥም ጊዜ በማስተማር ያሳለፉት ጆን ማርካኪስ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ዘ ሲቲ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኒውዮርክና ኒውዮርክ በሚገኘው በሴንት ጆንስ ዩኒቨርሲቲ አስተምረዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በተለያዩ አፍሪካ አገሮች በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች በቦትስዋና፣ ሌሴቶ፣ ስዋዚላንድና ዛምቢያ የካበተ ልምዳቸውን በማስተማር አካፍለዋል፡፡ እኚህ ምሁር በኢትዮጵያ ውስጥ ታሪካዊ የሚባሉ መጻሕፍትን ለአብነትም ‹ኢትዮጵያ አናቶሚ ኦፍ ኤ ትራዲሽናል ፖሊቲ›፣ ‹‹ክላስ ኤንድ ሪቮሉሽን ኢን ኢትዮጵያ››፣ ‹‹ናሽናል ኤንድ ክላስ ኮንፍሊክት ኢን ዘ ሆርን ኦፍ አፍሪካ›› እና ‹‹ፓስቸራሊዝም ኦን ዘ ማርጂን›› የመሳሰሉትን አበርክተዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ‹‹ዘ ግሪክ ኢን ብላክ አፍሪካ›› የሚለው መጽሐፋቸው ግሪክ ከአኅጉሪቷ ጋር ያላትን ግንኙነት በጥልቀት የሚያሳይ ነው፡ ከመጻሕፍቶቻቸው በተጨማሪ የተለያዩ የምርምር ወረቀቶችን የብሔር ብሔረሰቦች መብት፣ እምነትና የብሔር ግጭቶች፣ አርብቶ አደር፣ አገራዊ ውህደት፣ ድንበር ዘለል ንግድና የአካባቢያዊ ፀጥታና የመሳሰሉ ጉዳዮች ላይ በተለያዩ መድረኮች ላይ አቅርበዋል፡፡ በቅርቡ የወጣው ‹‹ኢትዮጵያ ዘ ላስት ቱ ፍሮንትየርስ (Ethiopia The Last Two Frontiers) የሚለው መጽሐፋቸውም ኢትዮጵያን ከኅብረ ብሔር ዘውዳዊ አገዛዝ ሥርዓት ወደ ዘመናዊ ኅብረ ብሔር ውህደት ለማሸጋገር በሚደረገው ሒደት ላይ የሚገጥሙ ውጣ ውረዶችን ለሚስገነዘብ ነው፡፡ አዲሱን መጽሐፋቸውና ኢትዮጵያ ውስጥ ስለነበራቸው ልምድና ቆይታ በተመለከተ ጥበበ ሥላሴ ጥጋቡኮጆን ማርካኪስ ጋር ቆይታ አድርጋለች፡፡

ሪፖርተር፡- ወደኋላ አሥርት ዓመታት ልመልስዎትና ወደ ኢትዮጵያ መጀመርያ እንዴት ሊመጡ ቻሉ?

ጆን ማርካኪስት፡-በጊዜው ኢትዮጵያ ለመምጣት ምንም ዓይነት ዕቅድ አልነበረኝም፡፡ በአጋጣሚ ነው የመጣሁት፡፡ አሜሪካ የዩኒቨርሲቲ ትምህርቴን በፖለቲካል ሳይንስ የትምህርት ዘርፍ ተመረቅኩኝ፡፡ ከፖለቲካል ሳይንስ በተጨማሪ የአፍሪካ ጥናት (አፍሪካን ስተዲስ) ጠለቅ ያሉ ኮርሶችን ወስጃለሁ፡፡ በዚያን ጊዜ አፍሪካ እንደ አኅጉር ብዙ እንቅስቃሴዎች እንደ ፀረ ቅኝ ግዛት፣ የቅኝ ግዛት ጥሎ ያለፈውን አሻራ ከሥር መሠረቱ ለማጥፋት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች፣ አገራዊ ብሔርተኛ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ቅስቀሳዎች የተሞላበት ወቅት ነበር፡፡ ነፃ በወጣችው አዲሷ አፍሪካ የነፃነት ታጋይ ሰዎች እንደ ጋናዊው ክዋሜ ንክሩማህ መኖራቸው እኔም ፊቴን ወደ አፍሪካ እንዳዞር አድርጎኛል፡፡ በናይጄሪያ ሥራ መኖሩን ሰምቼ ጓዜን ጠቅልዬ መጣሁ፡፡ ነገር ግን በናይጄሪያ ወጥቶ የነበረው ሥራ ክፍት አለመሆኑን ሰማሁ፡፡ ሌሎች የአፍሪካ አገሮች አማራጭ እንዳለ ብጠይቅም ብቸኛው አማራጭ ብዙዎች ያልፈለጉት ሥራ ኢትዮጵያ መሆኑ ተነገረኝ፡፡ ስለኢትዮጵያ ብዙ አላውቅም ነበር፡፡ ከዚህ በተጨማሪም እንደ ሌሎቹ የአፍሪካ አገሮች አገራዊ ብሔርተኛ ፖለቲካ ፓርቲዎች አለመኖሩ ለእኔ ተመራጭ አገር አልነበረችም፡፡ ነገር ግን ምንም ዓይነት አማራጭ ባለመኖር ጉዞዬን ወደ ኢትዮጵያ አቀናሁ፡፡ የመጣሁበት ወቅት አፄ ኃይለ ሥላሴ አገሪቷን በከፍተኛ ጥንካሬ ያስተዳድሩ በነበሩበት እ.ኤ.አ. በ1965 ነው፡፡ አዲስ አበባም ከገባሁ በኋላ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ፖለቲካል ሳይንስ የትምህርት ክፍል አቀናሁ፡፡ የዲፓርትመንቱ ኃላፊ በዕድሜ ገፋ ያሉ አጥባቂ የካቶሊክ እምነት ተከታይ የፖላንድ ዜግነት የነበራቸው ሰው ነበሩ፡፡ ዩኒቨርሲቲውን በበላይነት ሲያስተዳድሩ የነበሩት ጀሱይትስ በተለያዩ አገሮች የሚገኙ የካቶሊክ ዕምነት ተከታዮችን በመምህርነት ይቀጥሩ ነበር፡፡ ተማሪዎቹ ማጨስም ሆነ መጠጣት አይፈቅድላቸውም፡፡ የዲፓርትመንቱ ኃላፊ የሚሰጧቸውን የተለያዩ ኮርሶች በሚያሳየኝ ወቅት በጣም የገረመኝ ስለኢትዮጵያ ምንም ዓይነት ኮርስ አለመኖሩ ነው፡፡ ለምን ስለኢትዮጵያ ፖለቲካ ወይም መንግሥት ተማሪዎቹን እንደማያስተምሯቸው ጠየቅኩኝ፡፡ የሰውየውም መልስ እንደዚህ ዓይነት ጉዳዮችን አናስተምርም የሚል ነው፡፡ ነገሩን በቀላሉ ልተወው ስላልፈለግኩኝ ለምን የሚል ጥያቄ አቀረብኩ፡፡ እርሱም የፖለቲካ ጉዳይ የንጉሡ ሥራ ብቻ ነው፡፡ ሌላው ሕዝብ አይመለከተውም አለኝ፡፡ በመገረም ተማሪዎቹ በዚህ ጉዳይ ላይ ምን እንደሚያስቡ ጠየቅኩኝ፤ እርሱም ተማሪዎቹ ስለፖለቲካ ማሰብ አይገባቸውም አለኝ፡፡ ተማሪዎቹን ባወቅኳቸው ወቅት ያስቡ የነበረው ፖለቲካ ብቻ ነበር፡፡ ሌላ ምንም አያስቡም፡፡

ሪፖርተር፡- በምን የትምህርት ዘርፍ ለማስተማር ነበር የተመደቡት?

ጆን ማርካኪስ፡- የምዕራባዊያን በተለይም የአሜሪካን የመንግሥት አወቃቀር፣ የእርስ በርስ ባለ ሁለት ሕግ አውጪ ምክር ቤት ስለመሆኑ፣ እንደሁም ስለዴሞክራሲያዊ መንግሥታት አስተምር ነበር፡፡ እነዚህ ጉዳዮች እንኳን ኢትዮጵን አፍሪካን የሚመለከቱ  አይደሉም፡፡ ተማሪዎቹ ስለማስተምረው ጉዳይ ምንም ዓይነት የማወቅ ፍላጎት አልነበራቸውም፡፡ ማወቅም ማውራትም የሚፈልጉት ስለአብዮቱ ብቻ ነበር፡፡

ሪፖርተር፡- በወቅቱ የነበሩት ተማሪዎች እንደነ ካርል ማርክስ፣ ሌኒን፣ ፍራንዝ ፋኖንና ማኦ በመሳሰሉት ከፍተኛ ተፅዕኖ አድሮባቸው የነበረ ወቅት ነው፡፡ እርስዎ የሚያስተምሯቸው ጉዳዮች ከእነሱ ርዕዮተ ዓለም ጋር እንዴት ሊያስማሙ ቻሉ?

ጆን ማርካኪስ፡- በጣም አስቸጋሪ ወቅት ነበር፡፡ በዲፓርትመንቱ ስለኢትዮጵያ ፖለቲካ ምንም አስተያየት እንዳንሰጥ ተነግሮን ነበር፡፡ ነገሩ እኔም ስለኢትዮጵያ ፖለቲካ ምንም አላውቅም፡፡ ምንም ፍላጎት ስለሌላቸው ሐሳቦች ነበር የማስተምረው፡፡ በዚህም የተነሳ ተማሪዎቹ ችላ ማለት አመጡ፡፡ ብዙዎቹ የእኔን ክፍል ትምህርት ይቀራሉ፡፡ ከመጡም ጥያቄዎችን አይጠይቁም፡፡ ድንገት ጥያቄም ከጠየቁ እኔን አውቀው ለማሳፈርና ለመረበሽ የሚወረወሩ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ አብዩቱ ለኢትዮጵያ ጠቃሚ ነው ብለህ ታስባለህ? ይሉኝ ነበር፡፡ እኔም ለስለስ ባለ ቋንቋ ‹‹ማሻሻያ ይሻላል›› በማለት እመልስ ነበር፡፡ የመጀመርያ ዓመት በጣም ፈታኝ ነበር፡፡ ከተማሪዎቹ ጋር የነበረኝን ግንኙነት ከቀን ወደ ቀን እየተሻሻለ ባለመምጣቱ፣ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ ያስተምሩ የነበሩ መምህራንን ምክር ጠየቅኩኝ፡፡ መምህራኑም ከአሜሪካ በመምጣቴ የሲአይኤ ወኪል ሰላይ በማለት ሊጠረጥሩኝ እንደሚችሉ ነገሩኝ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ተማሪዎቹ በአሜሪካ ፖለቲካ ላይ ፍላጎት አለመኖሩ ተጨማሪ ምክንያት እንደሆነ አሳወቁኝ፡፡ የነበሩኝ ተማሪዎች ፅንፈኛ የግራ ዘመም ፖለቲካን አቀንቃኝ ነበሩ፡፡ በኢትዮጵያ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ከፍተኛ ሥፍራ ያላቸው እንደነ ብርሃነ መስቀል ረዳ፣ ገብሩ መርሻ፣ ዋለልኝ አማኑኤል፣ ጥላሁን ግዛው ተማሪዎቼ ነበሩ፡፡ ተማሪዎቹ የሚያነቡዋቸው መጻሕፍት ለምሳሌ የፍራንዝ ፋኖንን ‹‹ሬችድ ኦፍ ዘ ኧርዝ››፣ የማኦን ‹‹ኦን ኮንትራዲክሽን››፣ የሌኒን ‹‹ኋት ኢዝ ቱ ቢ ደን›› ነበሩ፡፡ እነዚህ መጻሕፍትን እኔ ያላነበብኳቸው ናቸው፡፡ እነዚህ ጓደኞቼም ተማሪዎቼ የሚያነቡትን መጻሕፍት እንዳነብ፣ እንዲሁም ሐሳባቸውን በግልጽ በክፍል ውስጥ እንዲያስተላልፉ እንድፈቅድላቸውና ስለኢትዮጵያም በጥልቅ እንድመረምር ነገሩኝ፡፡ የተማሪዎቹ የልብ ምት የነበረው የመሬት ጥያቄ ነበር፡፡ የመሬት ጥያቄ ተማሪዎቼ በተለያዩ ሰላማዊ ሠልፎች እንደ መፈክር ይዘው መውጣት የጀመሩበት ወቅት ነበር፡፡ የሁለተኛውን ዓመት ሳስተምር ተማሪዎቼ ተሻሽለው የተለያዩ ፖለቲካዊ ጉዳዮችን መወያየት ጀመርን፡፡ ተማሪዎቹም እየቀረቡኝና እያመኑኝ መጡ፡፡ በሚቀጥሉት ዓመታት ግንኙነታችን እየጠነከረ መጣ፡፡ በተለያዩ ወቅቶች የዲፓርትመንቱ አባላት አንድ ላይ የምንሰባሰብባቸው ፓርቲዎች ነበሩን፡፡ በአንደኛው ፓርቲ ላይ ተማሪዎቼ ኮካ ኮላ እየጠጡ ነበር፡፡ እኔም ቢራ ወይም ሌላ አልኮል የለም ወይ? ብዬ ጠየቅኩኝ፡፡ ተማሪዎቹም ጀሱይቶች እንደማይፈቅዱ ነገሩኝ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ አልኮል ካልተጠጣ ምን እንደሚጠጣ ስጠይቅ ‹ጠጅ› ብለው መለሱልኝ፡፡ ጠጅ አምጡልኝ ብዬ ጠይቄ ጠጅ መጠጣት ጀመርኩ፡፡ ከጠጅ በተጨማሪም ሲጋራም ማጨስ ቀጠልኩ፡፡ እነሱም ሁለት ጊዜ ሕጉን ተላለፍክ አሉኝ፡፡ ግንኙነታችን እያደገ ጓደኛሞች ለመሆንም የበቃነው ከዚያ በኋላ ነው፡፡ ስለንጉሡ አገዛዝም ማንበብና ማወቅም ጀመርኩ፡፡ ዘውዳዊው ባህላዊና ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰ አገዛዝ ነው፡፡ ሕዝቡ በማኅበረሰቡ ውስጥ ያለውን ሚና እንዲሁም ቦታ ጠንቅቀው የሚያውቁበት ሥርዓት ነው፡፡ ማኅበረሰቡ በመደብ የተከፋፈለና ታላላቅ ሰዎች ወይም ባላባቶች ፊት ሲቀርቡ በምን መንገድ ማሸርገድ እንዳለባቸው የተረዱበት ጊዜ ነው፡፡ ያ ወቅት ወደ መካከለኛው ዘመን ተመልሶ መኖር ማለት ነው፡፡ ነገር ግን እንደ አገር (ስቴት) ሁሉ ነገር እየሠራ ነበር፡፡ የዘውዳዊው አገዛዝ አፄ ኃይለ ሥላሴ በፍፁም የበላይነት የአገሪቷን ጉዳይ የሚያስተዳድሩበትና የሚቆጣጠሩበት ሥርዓት ነበር፡፡ በፍፁም የበላይነት የመቆጣጠሪያቸው ማሳያ በግል ጉዳዮች እንደ ፍቺ ባሉት ሁሉ ጣልቃ ይገቡ ነበር፡፡ በጣም ድንቅ ሰው ነበሩ፡፡ ወደኋላ በተለያዩ ጉዳዮች ስማቸው በጭቃ ተለውሶ ቢጠፋም፣ አሁን ሳስበው በግርማ ሞገስ የተሞሉና ግሩም ሰው ነበሩ፡፡ የዘውዳዊውን ሥርዓት በቁጥጥራቸው ሥር አድርገው እያንዳንዱ ጉዳይ ውስጥ ጣልቃ በመግባት አገሪቷ እንደ አገር እንድቀጥል ያደረጉ ንጉሥ ነበሩ፡፡ ይኼ ማለት ግን አገዛዛቸው ችግር አልነበረውም ማለት አይደለም፡፡ በተለያዩ አካባቢ የነበሩ ሕዝቦች ከነበረው ሥርዓት ጋር ሊጣጣሙ አልቻሉም፡፡ ይኼንን ፍፁማዊ ሥርዓትም ለማስቀጠል እክሎች መፈጠር ጀመሩ፡፡ ኢትዮጵያ ከጥቁር አፍሪካውያን አገሮች መካከል ትልቅና በጦር መሣሪያዎች የታጠቀ ሠራዊት ነበራት፡፡ ይኼ የጦር ኃይል እንደ አሜሪካና ስፔይን ባሉ አገሮች የተለያዩ ሥልጠናዎችና የጦር መሣሪያዎችን በመረዳት ይታገዝ ነበር፡፡ ኤርትራና ሶማሊያ የነበሩ ግጭቶችን ለማቀዛቀዝ ጦሩ ዘምቶ ነበር፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የጎጃም ገበሬ ያነሳውን አመፅ ለመቆጣጠር ወታደሩ ከብዶት ነበር፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ ሠራዊት መዋጋት የሚችለውና የሠለጠነበት መንገድ ጦሩ አንድ ቦታ ላይ ሰፍሮ ተቃራኒውን በማጥቃት ላይ ነው እንጂ፣ በሽምቅ ውጊያ ምንም ዓይነት ልምድ አልነበረውም፡፡ ኢትዮጵያ ለነበረችበትም የሽምቅ ውጊያ ወታደሩ መፍትሔ ሊያመጣ አልቻለም፡፡ ከዚህም በላይ ወታደሩ በተለያዩ ብሔሮችና መደቦች የተከፋፈለ በመሆኑ በጦር አዛዦች ላይ አመፅ ማስነሳት ጀመረ፡፡ ከችግሮቹም አንዱ መንስዔ የነበረው በባሌ ሰፍሮ የነበረው ወታደር ከፍተኛ የሆነ የውኃ ችግር ማጋጠሙ እንዱ ነው፡፡ የጦር ሠራዊቱ መፍረክረክ ሲያጋጥመው የንጉሡ አገዛዝም ቀስ በቀስ መውደቅ ጀመረ፡፡

ሪፖርተር፡- ለተማሪዎቹ ማርክሲዝም ተመራጭ ርዕዮተ ዓለም ለምን ሆነ? ዓለም አቀፍ በነበረው የካፒታሊዝምና የማርክሲዝም ርዕዮተ ዓለም ክፍፍልን ተከትሎ ነው ወይስ ማኅበረሰቡ ውስጥ የነበረው በመደብ የተከፋፈለ መዋቅር መነሻ ሆኖ ነው? የመደብ ጥያቄስ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ዋና ጥያቄ ለምን ሆነ?

ጆን ማርካኪስ፡- የማርክሲዝም ርዕዮተ ዓለም ቅኝ ግዛት በተገዙና በተጨቆኑ ሕዝቦች ነፃ የማውጫ ርዕዮተ ዓለም ተደርጎ ታይቶ ነበር፡፡ እንደነ ቻይና፣ ቬትናም፣ አልጄሪያ፣ አንጎላ፣ ሞዛምቢክና ደቡብ አፍሪካ ባሉ አገሮች የርዕዮተ ዓለሙ ዋነኛ አቀንቃኞች ነበሩ፡፡ በዚያን ወቅት የነበሩትም ተማሪዎች ወደዚህ ርዕዮተ ዓለም ማጋደል ይኼንኑ የዓለም አቀፉን አቅጣጫ ተከትሎ ነው፡፡  የማርክሲዝም ርዕዮተ ዓለም ለነበረው ሁኔታ መልስ የሚሰጥ ነበር፡፡ ተማሪዎቹ በአቋራጭ የሚፈለገውን ልማትም ለማምጣት ሶሺሊዝምን እንደ መፍትሔ ነበር ያዩት፡፡ ፊውዳላዊው አገዛዝ በካፒታሊዝም ርዕዮተ ዓለም ውስጥ ሳያልፍ ወደ ሶሺያሊዝም ርዕዮተ ዓለም ገብቶ በፍጥነት ልማት የሚመጣበትን መንገድ መቀየስ ጀመሩ፡፡ ይኼ ደግሞ የሚሆነው የፊውዳሊዝምን አገዛዝ ካስወገዱ ብቻ ነበር፡፡ በተለይም ለዚህ ሁሉ መሠረት የሆነው የመሬት ጥያቄ ጊዜውን ጠብቆ እንደሚፈነዳ ቦምብ ነው ያዩት፡፡ በተለይም በአንዳንድ አካባቢዎች ይኼ የመሬት ጥያቄ ከብሔር ጥያቄ ጋር ተያይዞ በደቡብ ኢትዮጵያ ባሉ አካባቢዎች ከፍተኛ ችግር ሊያመጣ እንደሚችል ተማሪዎቹ ተገንዝበውታል፡፡ ‹‹መሬት ላራሹ›› የሚለው ጥያቄም እየታዩ ያሉትን ቀውሶችና ሊከተሉ የሚችሉ ከፍተኛ ብጥብጦች የአገሪቷን እንደ አገር የመቆም ህልውና ከፍተኛ ችግር ውስጥ እንዳይከታት ለመመለስ ነበር፡፡

ሪፖርተር፡- የብሔር ብሔረሰቦችን ጥያቄ እንደነ ዋለልኝ መኮንን ያሉ የተማሪዎች ንቅናቄ አራማጆች አንስተውት ነበር፡፡ የዘውዳዊው አገዛዝ የነበረውስ ፖሊሲ ምን ይመስላል?

ጆን ማርካኪስ፡--አፄ ኃይለ ሥላሴ የመዋሀድ ፖሊሲን ያራምዱ ነበር፡፡ የተለያዩ የብሔር ልዩነቶች ለአገሪቷ መረጋጋት ችግር ሊፈጥሩ እንደሚችሉ ተረድተውታል፡፡ የባህል ውህደትን መፍጠርና በተመሳሳይ (በአንድ) ማንነት ላይ የተመሠረተ ብሔራዊ አንድነትን መፍጠር ከጥንት ጀምሮ ሲንከባለል የመጣ ሐሳብ ነው፡፡ የነበረውም ዕቅድ በተለያዩ አካባቢዎች ለምሳሌ በደቡብ አካባቢ የነበሩ ማኅበረሰቦችን የኦርቶዶክስ ክርስቲያን ዕምነት ተከታይና አማርኛ ቋንቋ ተናጋሪ በማድረግ በአንድ ባህል መዋጥ ነው፡፡ የነበረውም አገዛዝ ይኼንን የመዋጥ (አሲሚሌሽን) ፖሊሲ በከፍተኛ ግፊት ያራምድ ነበር፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች ይኼ የመዋጥ ፖሊሲ የተሳካ ነው ለማለት ያስደፍራል፡፡ ምክንያቱም በቁጥር ብዙ የሆኑ ሰዎች ወደ ኦሮቶዶክስ ክርስቲያንነት ተቀየሩ የቦታ ስሞች ለምሳሌ አዳማ ወደ ናዝሬት ተቀየረ፡፡ የገዢውን ክፍል ለመቀላቀል ክርስቲያን መሆንና አማርኛ ማውራት እንደ ግዴታም ተወስዷል፡፡ ይኼ ፖሊሲ በሕዝቡ ዘንድ በጥልቀት ለመስረፅ ረዘም ያሉ ዓመታትን ይወስዳል፡፡ ይኼ የመዋጥ ፖሊሲም አልጋ ባልጋ አልሆነም፡፡ ከተለያዩ አካባቢዎች ተቃውሞ ገጥሞታል፡፡ ዋለልኝ አማራ ነበር፡፡ ነገር ግን ይኼ በግድ የመዋጥ (ፎርስድ አስሚሌሽን) ሐሳብን በከፍተኛ ሁኔታ ተቃውሞታል፡፡ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ብቻ አልነበረም፡፡ በተጨማሪም የኦሮሞ ማኅበረሰብ ተቃውሞታል፡፡ በተለይ የሶማሌ ሕዝብ የመዋጥ ፖሊሲ ምን እንደሆነ በቅጥ አልተረዳውም፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች በኤርትራ፣ በኦጋዴንና በባሌ የነበሩ የአመፅ እንቅስቃሴዎች ማዕከላዊውን ሥርዓት እያዳከሙት መጡ፡፡ በመጨረሻም ለመውደቂያው ምክንያት ሆኑ፡፡ ደርግ ሥልጣን እንደወሰደም ለእነዚህ ችግሮች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት ሞክሯል፡፡ ወደ ተማሪዎች እንቅስቃሴ እንመለስና ተማሪዎቹ የማርክሲዝም ርዕዮተ ዓለምን የመረጡበትም ምክንያት ማርክሲዝም በጽንሰ ሐሳብ ደረጃ ሁሉንም ልዩነቶች በተለይም የብሔር ልዩነትን እኩል የሚያደርግና ሠራተኛውንና ገበሬውን አንድ የሚያደርግ ሥርዓት በመሆኑ ነው፡፡ የመደብ ጥያቄዎች እልባት ከተገኘላቸው የብሔር ጥያቄዎችም መፍትሔ ያገኛሉ ብለው ያምናል፡፡ ዋናው መመለስ ያለበት የመደብ ጥያቄ ነው ይሉ ነበር፡፡ ደርግም ይኼንን ርዕዮተ ዓለም ከተማሪዎች በመውሰድ ሠራተኛውን ገበሬውንና ሁሉንም ሕዝብ የሚከፋፍለው የመደብ በመሆኑ፣ የመደብ ጥያቄ መመለስ አለበት ለማለት ሐሳብ ማንፀባረቅ ጀመረ፡፡ ሌላው ከተማሪዎች ደርግ የወሰደው ሐሳብ መሬትን የጭሰኛ በማድረግ የገባር ሥርዓትን ማስወገድ ነው፡፡ መሬትን በመንግሥት ቁጥጥር ሥር (ናሽናላይዝ) ማድረግን ነው፡፡ ደርግ በመሬት ላይ የወሰደው ዕርምጃ ኢትዮጵያን አንድ ዕርምጃ ወደፊት ያራመደ መሆን ይችል ነበር፡፡ ከዘውዳዊ የአገዛዝ ሥርዓት በመለየትም ኢትዮጵያ የኅብረ ብሔር አገር መሆኗንም በተወሰነ መልኩ ዕውቅና ሰጥቷል፡፡ አፄ ኃይለ ሥላሴ እ.ኤ.አ. በ1950ዎቹ በአሜሪካ ኮንግረስ ተገኝተው ኢትዮጵያ በሙስሊም አገሮች የተከበበች የክርስቲያን ደሴት ነች ብለው ግማሹ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሙስሊም በሆነበት ሁኔታ ተናግረዋል፡፡ የወታደራዊ አገዛዙም በቀደመው ሥርዓት የተደረጉ ስህተቶችን ፈጽሞ ለማስወገድ ተነስቶ ነበር፡፡ የቀደሙ ሥርዓቶችም ደርግም ይሁን አሁን ያለው መንግሥት ኢትዮጵያ ውስጥ ያላደረጉት ቢኖር ሥልጣንን፣ እንዲሁም ሀብትን ከተለያዩ በአገሪቷ ከሚኖሩ ሕዝቦች ጋር እኩል መከፋፈልን ነው፡፡ አፄ ኃይለ ሥላሴ ይኼንን አላደረጉም፡፡ ማሰብም አልቻሉም፡፡ ደርግም ሥልጣንና ሀብት የመከፋፈሉን ጉዳይ አላሰበበትም፡፡ በዚህም ምክንያት ከአፄው ሥርዓት በባሰ ሁኔታ ደርግ የተለያዩ አመፆችን፣ ቀውሶችንና ጦርነቶች በተለያዩ አካባቢዎች ማስተናገድ ጀመረ፡፡ በአዲሱ መጽሐፌ ‹‹ኢትዮጵያ ዘ ላስት ቱ ፍሮንቲየርስ) የፖለቲካ መስመር (ድንበር) ብዬ የምጠቅሰውም የሥልጣንና የሀብት ክፍፍልን በየአገሪቷ ጥግ (ፔሪፈሪ) ከሚኖሩ ሕዝቦች ጋር ተግባራዊ አለማድረጉን ነው፡፡

ሪፖርተር፡- ሁለቱ መስመሮች (ድንበሮች) (ዘ ላስት ቱ ፍሮንቲየርስ) ምንድን ናቸው?

ጆን ማርካኪስ፡- የመጀመርያ መስመር ፖለቲካዊ ሲሆን፣ ይኼም ከጥንቷ አቢሲኒያ ጀምሮ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው ሥልጣንን በበላይነትና በብቸኝነት መቀራመት  ነው፡፡ ይኼ አስተዳደርም ሕዝቡ በጭቆና እንዲኖር፣ ከሥልጣን ክፍፍልም ሆነ ከሀብት አብዛኛውን የአገሪን ክፍል ያገለለበት ሁኔታ ፈጥሯል፡፡ አገሪቷ ላለችበት አለመረጋጋትና ግጭቶችም መንስዔ ሆኗል፡፡ ሁለተኛው መስመር በአገሪቷ ድንበር አካባቢ የሚገኙት ከፊል በረሃማና ቆላማ ቦታዎች ኢትዮጵያ ከምትባለው አገር ጋር አለመዋሀዳቸውና ላለመዋሀድም የሚያደርጉት ትግል ነው፡፡ የፊውዳሉ የአገዛዝ ሥርዓት ከወደቀ በኋላ የወታደራዊ አገዛዝም በከፍተኛ ደረጃ ማዕከሉን ጠንካራ ያደረገ ነበር፡፡ የነበረው የተጠናከረ የወታደራዊ ኃይል በተለያዩ አካባቢዎች የተነሱትን የሽምቅ ኃይል ተዋጊዎች ለማንበርከክ አልቻለም፡፡ በተለይም የሕወሓትና የሻዕቢያ ትግል ሲፋፋም ወታደራዊውም ሥርዓት መፍረክረክ ጀመረ፡፡ ከነዚህ ሥርዓት መውደቅ በኋላም የኢሕአዴግ መንግሥትም በተለያዩ ሥርዓቶች የተሠሩ ስህተቶች እንዳይደገሙ ከፍተኛ ጥረት አድርጓል፡፡ የኢሕአዴግ መንግሥት ሥልጣን በወሰደበት የመጀመርያዎቹ ዓመታት የተለያዩ የሽምቅ ተዋጊዎች በተለያዩ አካባቢዎች ነበሩ፡፡ ሥልጣንን በመከፋፈልና የተለያዩ ክልሎችን ማዕከል በማድረግ ብሔርን መሠረት ያደረገ ፌዴራሊዝም ሥርዓት ቀረፁ፡፡ ይኼ ትልቅ ነገር ነው፡፡ በአማራነት ማንነት መዋጥን መሠረት ያላደረገ ኢትዮጵያዊነትን ያስተዋወቀ ሥርዓት ነው፡፡ ማኅበረሰቦች ባህላቸውን እምነታቸውንና ማንነታቸውን ጠብቀው ዜጋ የሚሆኑበት አገር ለመፍጠር ተሞክሯል፡፡ ይህ ፌዴራሊዝም የክልል መንግሥታት ራሳቸውን የሚያስተዳድሩበት፣ የራሳቸውን ተወካዮች የሚመርጡበት፣ የራሳቸውን ቋንቋ የሚናገሩበትን፣ ወዘተ መሠረት ያደረገ ነው፡፡ ነገር ግን እንዳለፉት መንግሥታት የፖለቲካ መስመር ጥያቄውን መመለስ አልቻለም፡፡ ሥልጣን አሁንም በማዕከላዊው (በፌዴራል) መንግሥት ቁጥጥር ሥር ነው፡፡ ፌዴራል መንግሥቱ ይወስናል፡፡ የተለያዩ ክልሎች አስፈጻሚ ናቸው፡፡ ፌዴራል መንግሥቱ ሥልጣንንም ሆነ ሀብትን በቁጥጥሩ ሥር አድርጎ ለመከፋፈልም ሆነ በጋራ ለመጠቀም ዝግጁ አይደለም፡፡ ይኼ አካሄድ ደግሞ ለሥርዓቱ ትልቅ ጠንቅ ነው፡፡ የአንድን አገር ህልውና ለመጠበቅ ኃይል ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ እንደ ቀድሞዎቹ መንግሥታት ኢሕአዴግም ተመሳሳይ ቀውስ ገጥሞታል፡፡ እንደ ቀደሙት መንግሥታትም እነዚህን ጥያቄዎች ከመመለስ ሠራዊቱን ችግሮቹን ለመፍታት ማሳተፍን መርጧል፡፡

ሪፖርተር፡- ብዙዎቹ የደቡብ ግዛቶች ከ16ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በነበሩ ነገሥታት ይተዳደሩ ነበር፡፡ እነዚህን ግዛቶች የኢትዮጵያ አካል የማድረግ ስህተቶች ምንድን ናቸው?

ጆን ማርካሲስ፡- አቢሲኒያ ጥንታዊ፣ ተመሳሳይ ሕዝብና እሴት የነበራት አገር (ኔሽን ስቴት) ናት፡፡ ጥንታዊ እንደመሆኗ መጠን ለረዥም ዓመታት ደጋግሞ ከመታረስና ከአየር ንብረት ጋር ተያይዞ ከፍተኛ የእርሻ መሬት ችግር አጋጠማት፡፡ ከፍተኛ የመሬት ፍላጎት የመኖር ጥያቄ ሆነ፡፡ በዚህም ምክንያት በጠንካራ ወታደራዊ ኃይል በመታገዝ ወደ ተለያዩ አገሪቷ አካባቢዎች መስፋፋት ተጀመረ፡፡ ወደ ደቡብ የኢትዮጵያ ክፍል የነበረው የመስፋፋት ዘመቻ ተጠናክሮ ቀጠለ፡፡ የሰሜኑ ክፍል ሕዝብ በተለምዶ ነፍጠኛ ተብለው በሚጠሩት የተለያዩ የደቡባዊ የአገሪቷን ክፍል መቆጣጠር ቀጠለ፡፡ በነፍጣቸው (በመሣሪያቸው) እየታገዙ ሕዝቡን በኃይል ከመሬቱ አፈናቀሉት፡፡ መሬት ብቻ በቂ አልሆነም፡፡ ይኼ የመስፋፋት ተግባር የሠራተኛ ኃይል አስፈላጊው ነበር፡፡ በእዚህም ኢትዮጵያ የተለያዩ ግዛቶችና ሕዝቦች አገር (ኔሽን ስቴት) መሆን አቆመች፡፡ አቢሲኒያ የተስፋፋባቸው የተለያዩ ግዛቶች አቢሲኒያ አልነበሩም፡፡ አቢሲኒያውን አንድ እምነትና ተመሳሳይ ማኅበራዊ እሴቶች ያሉባት አገር ነበረች፡፡ የተለያዩ ሕዝቦች በኢትዮጵያ ውስጥ ሲካተቱ ኔሽን (ስቴት) የመሆኑም ሁኔታ ቆመ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በኃይል የተቀላቀሉት ሕዝቦች ደስተኛ ሊሆኑ አልቻሉም፡፡ የኢትዮጵያም ኅብረ ብሔራዊ ጉዞም በዚህ ተጀመረ፡፡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ ጊዜ የማዕከላዊ ሥርዓት አስተዳደር የተለያዩ ፖሊሲዎችን ያወጣል፡፡ ባላባቶቹ አስፈጻሚ ነበሩ፡፡ በደርግም ጊዜ በአካባቢ የነበሩ ካድሬዎቹ ከማዕከላዊ መንግሥት የሚመጣውን ማንኛውንም ውሳኔ አስፈጻሚ ሆኑ፡፡ ሥርዓቶች ቢቀያየሩም ሥልጣን የሚፈጸምበት መዋቅር አንድ ነው፡፡ የማዕከላዊው መንግሥት በተለያዩ አካባቢ የሚኖሩ ካድሬዎችን የሥርዓቱ አካል ያደረገውም ለብቻቸው ማስተዳደር ስላልቻለ ነው፡፡ በአካባቢው ያሉ ካድሬዎችም የሥርዓቱ ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ የኢሕአዴግ ሥርዓትም በአካባቢው ያሉ አስተዳዳሪዎችን የሥርዓቱ ተጠቃሚ በማድረግ ፖሊሲውን ለማስፈጸም ችሏል፡፡ በእኔ አስተያየት ይኼ የተረጋጋ ሥርዓት አይደለም፡፡

ሪፖርተር፡- በትክክለኛው መንገድ ውህደት የለም?

ጆን መርካኪስ፡- ፖለቲካዊ ውህደት በፍፁም የለም፡፡ በአገሪቷ በተለያዩ አካባቢዎች የሚኖሩ ሕዝቦች እርስ በርስ ተዋህደዋል፡፡ ጋብቻ በመፍጠርና እርስ በርስ በመነጋገር በባህል ደረጃ ውህደት ተፈጥሯል፡፡ አሁን የሚያስፈልገው ፖለቲካዊ ውህደትና መፍትሔ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- የፖለቲካ መፍትሔው ምንድነው?

ጆን ማርካኪስ፡- የፌዴራሉ (የማዕከላዊ) መንግሥት ሥልጣንና ሀብትን በተለያዩ አካባቢዎች ለሚኖሩ ሕዝቦች እኩል ማጋራት መቻል አለበት፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ ቁጥር ያላቸውን ብሔሮችን መንግሥት ከሥልጣንና ከሀብት ማጋራት ውጪ ሊያደርግ አይችልም፡፡ ይኼ ምናልባት ከአምስት ክፍለ ዘመናት በፊት ሊደረግ ይችል ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን አይቻልም፡፡ ስለዴሞክራሲ አይደለም የማወራው፡፡ ነገር ግን ሕዝቦች ተወካዮቻቸውን የሚመርጡበት፣ ድምፃቸው የሚሰማበት የፖለቲካ ሥርዓት ሊዘረጋ ይገባል፡፡ ሕዝቦች ራሳቸውን የሚያስተዳድሩበት፣ ሥልጣንንና ሀብትን የሚጋሩበት ሥርዓት መፍጠር ግዴታ ነው፡፡ ምንም እንኳን ይኼ መንግሥት ካቢኔውን በአዳዲስ ባለሥልጣናት ቢሞላም ሥልጣንና ሀብት ማጋራት ማለት ይኼ አይደለም፡፡

ሪፖርተር፡- የብሔርና የመደብ ጭቆናን ጥያቄ አስመልክቶ ማዕከላዊው አስተዳደር ሰሜኑን የኢትዮጵያን ክፍል ይመርጠዋል የሚሉ አካላት ሲኖሩ፣ ከዚህ በተቃራኒ ገዢው መደብ ሁሉንም የማኅበረሰብ ክፍል እኩል የመጨቆን ከሥልጣንም ሆነ ከሀብት ማጋራት ሁሉንም ሳይለይ በእኩል የነጠለ ነው ተብሎም ይታመናል፡፡ ስለዚህ ጉዳይ ምን ይላሉ?

ጆን ማርካኪስ፡- የማዕከላዊ አገዛዝ ጭቆና የባህል የበላይነትን የማስፈን ሁኔታ የተተገበረው አስተዳደሩን በተቆጣጠረው የሐበሻው የገዢው የመደብ ክፍል ነበር፡፡ የሰሜኑ ጭቁን ገበሬ ከዚህ የበላይነት የሚጋራው በሐሳብ ወይም በመንፈስ ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን የኢኮኖሚያዊ ሁኔታውን ብናይ የሰሜኑ ገበሬ ደሃ ነው፡፡ በተለይም ከደቡብ አካባቢ ካለው ገበሬ ጋር ሲነገፃፀር የነጣ ደሃ ነው፡፡ የደቡብ አካባቢ መሬት ለም ሲሆን፣ የሰሜኑ መሬት አስቸጋሪና ለብዙ ጊዜ የታረሰ በመሆኑ ለገበሬው አስቸጋሪ ነው፡፡ በተለይም በባለፉት አሥርት ዓመታት ወደኋላ ብንሄድ ጎጃም ወይም ትግራይ አካባቢ ምንም ዓይነት መሠረተ ልማቶች አልነበሩም፡፡ ስለዚህ ገበሬው ከነበሩት ሥርዓቶች ተጠቃሚ አልነበረም፡፡ ለዚህም ነው የተለያዩ ችግሮች እየተፈጠሩ ያሉት ትግራይን እንደ ምሳሌ መውሰድ እንችላለን፡፡ አሁን የትግራይ ሕዝብ ምን እያለ ነው? ሕዝቡ ከዚህ ሥርዓት ተጠቃሚ ናቸው እያለ ይወቅሰዋል፡፡ እውነታው ግን ምንም የለውም፡፡ ለዚህም ነው በሥርዓቶች ተጠቃሚ የሚሆን ለሥርዓቱ ታማኝ የሆነው የገዢው መደብ ነው የምንለው፡፡ በኦሮሚያ ክልል ለሥርዓቱ ታማኝ የሆኑ የኢሕዴድ (ኢሕአዴግ) አባላት ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ እነዚህ ግን ሰፊውን የኦሮሞ ሕዝብ አይወክሉም፡፡

ሪፖርተር፡- ስለዚህ ከየትም አካባቢ ቢመጡ ለሥርዓቱ ታማኝ የሆኑትን ሥርዓቱ ጠቅሟቸዋል ማለት ይቻላል?

ጆን ማርካኪስ፡- አዎ ማለት ይቻላል፡፡

ሪፖርተር፡- ከሰሜኑ ወይም ከቆላው ዝቅተኛ ቦታዎች የሚመጡ ቢሆኑም?

ጆን ማርካኪስ፡ የቆላማው ከፊል በረሃማ ዝቅተኛ አካባቢዎች በተለየ ዓይን መታየት ያለባቸው ናቸው፡፡ የዘውዳዊ የአገዛዝ ሥርዓት አካባቢውን ለመቆጣጠር ምንም ዓይነት ጫና አላደረገም፡፡ ምክንያቱም ይህ አካባቢ ምንም ዓይነት ተፈጥሯዊ ሀብት የለውም ተብሎ ስለታሰበ ነው፡፡  መሬቱም ከፊልና ሙሉ በሙሉ በረሃማ የሆነ አካባቢ ነው፡፡ ይኼ አካባቢ በዋነኝነት አርብቶ አደር የሚኖርበት ሲሆን፣ በገንዘብ ስለማይገበያይ ለረዥም ዘመናት ግብር አይከፍልም፡፡ በከፍተኛ ደረጃ የታጠቁ፣ ከቦታ ቦታ ድንበርን ጭምር አቋርጠው የሚሻገሩ አርብቶ አደሮች ናቸው፡፡ የሚተዳደሩት በራሳቸው ሕግ ሲሆን፣ የአካባቢው መሪዎችም ከማዕከላዊው መንግሥት ውጪ ያስተዳድሯቸዋል፡፡ ከአርብቶ አደሮቹም በተጨማሪም ከእጅ ወደ አፍ ግብርና የሚተዳደሩም ነዋሪዎች መሥፈሪያ ነው፡፡ እነዚህም መሬቱን አጥፍተው ቁጥቋጦዎቹን ቆርጠው አትክልቶች ይተክላሉ፡፡ መሬቱ ለም መሆኑን ሲያቆም ወደ ሌላ አካባቢ ይሰደዳሉ፡፡ የተውት መሬት ላይ እንደገና ተመልሰው መሬቱን ለማረስ ይሞክራሉ፡፡ ከቦታ ቦታ እየተመላለሱ ለዘመናት የተለያዩ መንግሥታት በራሳቸው እንዲንቀሳቀሱ ትተዋቸዋል፡፡ የደርግ መንግሥት በተወሰነ መልኩ ይኼንን ሕዝብ ከማዕከላዊው አስተዳደር ጋር ለማዋሀድ ሞክሯል፡፡ ነገር ግን በቂ ጊዜ አልነበረውም፡፡ በፖለቲካዊም ሆነ በኢኮኖሚያዊ መንገድ ከማዕከላዊ መንግሥት ጋር ለማዋሀድ አሥራ ሰባት ዓመት በቂ አልነበረም፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች ተጠናክሮ ይካሄድ የነበረው የመሠረተ ትምህርት ዘመቻ በእነዚህ አካባቢ አልነበረም፡፡ በአጠቃላይ መንግሥት የሚቆጣጠረው አካባቢ አልነበረም፡፡ ለመጀመርያ ጊዜም የኢሕአዴግ መንግሥት ይኼንን አካባቢ ለማዋሀድ እየሞከረ ነው፡፡ የተለያዩ የመንግሥት መዋቅሮች ፍርድ ቤቶች፣ የመሠረተ ልማት ማዕከላት፣ እንደ ትምህርት ቤት፣ የጤና ኬላዎች ተቋቁመው እየሠሩ ነው፡፡ ይኼ አካባቢ በከፍተኛ ሁኔታ ለግጭት የተጋለጠ በመሆኑ የተረጋጋ አይደለም፡፡ በዚህም በመንግሥት እየተደረጉ ያሉ የማዋሀድ ሙከራዎች ሙሉ በሙሉ አልተሳኩም፡፡ የፌዴራል መንግሥት እነዚህን አካባቢዎች አልተቆጣጠረም፡፡ አሁንም ግብር አይከፍሉም፡፡ ትክክለኛ ውህደት እንዲመጣ ሥልጣንና ሀብትን የሚጋሩበት ሥርዓት መዘርጋት አለበት፡፡

ሪፖርተር፡- በብሔር ላይ የተመሠረተው የፌዴራሊዝም ሥርዓት ስህተት አለበት ወይ? ስህተቶቹስ ምንድን ናቸው? ሲጀመርስ ለኢትዮጵያ ትክክለኛ የአስተዳደር ሥርዓት ነው ወይ? የኢሕአዴግ መንግሥት እንደሚለው የተለያዩ ሕዝቦች ቋንቋና ባህል የሚከበርበትና እንደ አገር የሚዋሀዱበት ሥርዓት መፍጠር ነው ወይ? ይኼ ውህደት መጥቷል ብለው ያስባሉ?

ጆን ማርካኪስ፡- ኢሕአዴግ የተለያዩ ሕዝቦችን ዕውቅና በመስጠት ለማዋሀድ ሞክሯል፡፡ ጥያቄው የሚነሳው ማዕከላዊ መንግሥት ይወክለናል በሚሉ ሰሜነኞች ነው፡፡ ይኼ የኅብረተሰብ ክፍል ፌዴራሊዝም በአገሪቷ አንድነት ላይ ጥላሸት አጥልቷል ብለው ያምናል፡፡ እኔ ከኢትዮጵያ መገንጠል የሚፈልግ ማኅበረሰብ (ቡድን) አለ ብዬ አላምንም፡፡ ከኢትዮጵያ ተገንጥለው ወደ የት ሊሄዱ? የመገንጠል ጥያቄ ወይም የተለያዩ የብሔር ጥያቄዎችን እያነሱ ያሉ ማኅበረሰቦች ሥልጣንንና ሀብትን መጋራት፣ በመረጧቸው ሕዝብ መተዳደርን የመሳሰሉ ናቸው፡፡ ስለዚህ እነዚህ ጥያቄዎች ፖለቲካዊ መልስ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ኢትዮጵያን የብዙ ብሔር ብሔረሰቦች አገር ያደረጋት ኢሕአዴግ አይደለም፡፡ ኢሕአዴግ ያደረገው ነገር ቢኖር ለእነዚህ ሕዝቦች ዕውቅና መስጠትና በባህላቸው እንዲኮሩ ማበረታታት ነው፡፡ ይኼ የመገነጣጠል ፍራቻ የሚያቆመው ሥልጣንንና ሀብትን የመጋራት ጥያቄ ሲመለስ ነው፡፡

ሪፖርተር፡-በመጽሐፍዎ ማጠቃለያ ላይ የገበያው ሁኔታ የመሬትን ተፈላጊነት ዋጋ እየወሰነ የመጣ ኃይል እንደሆነ ተጠቅሷል፡፡ ይኼ ደግሞ መሬት የመንግሥት ነው ከሚለው ሐሳብ ጋር ይጣረሳል፡፡ ይኼ እንዴት ሊሆን ቻለ?

ጆን ማርካኪስ፡- ወደኋላ ሄደን ታሪክን በምንመረምርበት ወቅት መሬት በጣም ጠቃሚና የሀብት እንዲሁም የተለያዩ እሴቶች አመንጪ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ጥያቄው የመሬት ተቆጣጣሪ ማን ነው? ከጥንት ጊዜ ጀምሮ መሬትን የሚቆጣጠረው መንግሥት ቢሆንም፣ የሰሜን አካባቢ ነዋሪዎች በመሬታቸው ላይ ጠንካራ መብት ነበራቸው፡፡ መሬትን ከአቢሲኒያ ገበሬዎች በጭራሽ መውሰድ አይቻልም፡፡ መሬታቸው የሚወሰደው ሲያምፁ ወይም ግብር መክፈል ሲያቆሙ ነው፡፡ መሬት በቤተሰብ ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፍ ርስት ነው፡፡ ለዚህም ነው ‹‹አፅመ ርስት›› ተብሎ የሚጠራው፡፡ በዚህም ምክንያት መሬት ምንም ዓይነት ገበያ አልነበረውም፡፡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ አገዛዝ የመጨረሻዎቹ ዓመታት የዓለም ባንክና የዓለም የገንዘብ ድርጅት የመሳሰሉ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች መሬት ወደ ግል ይዞታ እንዲዞር ከፍተኛ ጫና እያሳደሩ ነበር፡፡ አንዳንድ ሙከራዎችም በደቡብ ኢትዮጵያ አካባቢ ታይተዋል፡፡ ደርግ መሬትን በአዋጅ በመንግሥት ቁጥጥር ሥር አዋለው፡፡ ይኼ ማለት ገበሬዎቹ ማከራየት፣ መሸጥ ወይም ሰው መቅጠር አይችሉም ነበር፡፡ የገጠርን መሬት ለሕዝብ ለማድረግ የወጣው አዋጅ መንግሥት መሬትን በበላይነት እንዲቆጣጠር ያቀደ ባይሆንም፣ በተቃራኒው ደርግ ከዚህ የተለየ ሐሳብ ነበረው፡፡ በኢሕአዴግ አገዛዝ በጽንሰ ሐሳብ ደረጃ መሬት የመንግሥት ነው፡፡ በደርግ ከነበረው ሥርዓት የተቀየረ ነገር የለም፡፡ መሬትን መቆጣጠር ማለት ገበሬውን መቆጣጠር ማለት ነው፡፡ ይኼ ሐሳብ በተለያዩ መንግሥታት ባልተገባ ሁኔታ ተግባር ላይ ውሏል፡፡ የደርግ መንግሥት የተለያዩ የገበሬ ማኅበራትን፣ የመንግሥት እርሻዎችን በማቋቋም ገበሬውን አሰቃይቶታል፡፡ በኢሕአዴግም መንግሥት መሬት የመንግሥት ነው፡፡ በተለያዩ ልሂቃን አማካይነት መሬት ወደ ግል ይዞታ እንዲዘዋወር የሚያደርጉ ጫናዎች አሉ፡፡ መሬትን ወደ ግል ይዞታ ማዛወር ማለት በአገሪቷ ላይ ከፍተኛ ቀውስ እንዲመጣ መፍቀድ ነው፡፡ ምክንያቱም ከመሬታቸው ሊፈናቀሉ የሚችሉ ገበሬዎችን የሚሸከም የከተማ የኢኮኖሚ አቅም የለም፡፡ ትልልቅ ዘመናዊ እርሻዎች በተለያዩ የአገሪቷ ክፍሎች እየተስፋፉ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት የሚፈናቀሉ ገበሬዎች ወዴት ሊሄዱ ነው? የሚሉ ጥያቄዎች እየተነሱ ነው፡፡ ተቃዋሚዎች ወይም የቀድሞ ተቃዋሚዎች የሚጋጩ ሐሳቦችን ያነሱ ነበር፡፡ አንደኛው ቡድን ኢትዮጵያዊነትን ማዕከል ያደረገው የሐበሻው ቡድን፣ ፌዴራሊዝምን በፅኑ በመቃወም የጥንቱ ሥርዓት እንዲመጣ የሚፈልግ ነው፡፡ በሌላ በኩል እንደነ ዶ/ር መራራ ጉዲና፣ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስና የመሳሰሉት የሚወክሉት ማኅበረሰብ የበለጠ ፌዴራሊዝምና ሥልጣን መጋራትን ይፈልጋል፡፡ ሁለቱ ቡድኖች ፍፁም ተቃራኒ ጉዳይ ነው የሚያወሱት፡፡ ለእነ ዶ/ር መረራ  መሬት ወደ ግል ይዞታ መዞር ያስፈራቸዋል፡፡ መሬት ወደ ግል ይዞታ መዞር የመጨረሻው መጥፎ ነገር ነው፡፡ ይኼም ሆነ ያ መሬት ወደ ግል ይዞታ መዞሩ አሁን በከፍተኛ ፍጥነት እየተካሄደ ነው፡፡፡ መሬት እየተሸጠና እየለወጠ ነው፡፡ የገበያውም ሁኔታ ለመሬት ሽያጩ ወሳኝ ሆኗል፡፡ በኦሮሚያ ያሉ ገበሬዎችም በከፍተኛ ሁኔታ እያማረሩ ያሉት ጥቂት ሺሕ ብሮች ካሳ ተከፍሏቸው፣ የተፈናቀሉበት መሬት አሁን በሚሊዮኖች ብር እየተቸበቸበ መሆኑ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በኢትዮጵያ ውስጥ ሁለት የማይታረቁ ሐሳቦች ያሏቸው ቡድኖች አሉ፡፡ አንደኛው ቡድን ፌዴራሊዝሙን የሚቃወም ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ የተለያዩ የነፃ አውጪ ቡድኖችን የሚወክለውና ፌዴራሊዝሙ ትክክለኛውን የሥልጣን መጋራት እንዳልሰጣቸው የሚናገሩ ቡድን ናቸው፡፡ እነዚህን ሁለት የማይታረቁ ሐሳብ ያላቸውን ቡድኖች እንዴት አንድ ላይ ማምጣት ይቻላል?

ጆን ማርካኪስ፡- ኢሕአዴግ ኢትዮጵያን የመከፋፈልና የመገነጣጠል ሐሳብ አለው ብዬ አላምንም፡፡ በብሔር የተመሠረተ ፌዴራላዊዝምን ሲያመጡ አገሪቷን በአንድ ላይ የሚያስተዳደሩበት መንገድ ነው የቀየሱት፡፡ የተለያዩ ባህሎችን አንድ ላይ በማምጣት ቀድሞ የነበረውን የዜግነት ሐሳብ በመቀየር የማስተዳደሩን ሥልጣን በተለያዩ ክልሎች ለሚገኙ ሕዝቦች ሰጥተዋል፡፡ ይኼ ሁሉ ግን የተደረገው ሕዝቡን ፀጥ ለማስባል እንጂ ሥልጣንን ለማጋራት አይደለም፡፡ ፌዴራሊዝሙ በኢሕአዴግ የተሰላ ጥረት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አስተዳደሩ ከሰሜን ክፍል የተውጣጣ ነው፡፡ ይኼ ሕዝብ ኢትዮጵያን ሊበታትን ነው የሚል ሐሳብ ማሰብም በጭራሽ አይቻልም፡፡ ይኼ ተልካሻ ሐሳብ ነው፡፡ እንዴት ነው የትግራይ ሰው ኢትዮጵያን ለመገንጠል የሚነሳው? በእኔ አስተሳሳብ ትግራዋይ አክራሪ ሐበሻና ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡ ስለዚህ ፌዴራሊዝሙ በተለያዩ የአገሪቷ ክልሎች ተነስተው የነበሩ ግጭቶችን ለማብረድና ማዕከላዊ አስተዳደር የተጠናከረበት፣ የተለያዩ ክልሎች ተንጠልጣይ ሆነው ፀጥ ብለው የሚጓዙበት ሥርዓት ለመገንባት ነው፡፡ ይኼንን ለመረዳት የተለያዩ ቡድኖች ጊዜ አልፈጀባቸውም፡፡ የተለያዩ ነፃ አውጪ ቡድኖች የመጡትም ይኼንን በመረዳት ነው፡፡ አሁን ዋናው ጥያቄ ይኼ የፖለቲካ ጥያቄ እንዴት ዕልባት ማግኘት ይችላል? የሚለው ነው፡፡ ኢሕአዴግ ከዚህ ማጥ እንዴት መውጣት ይችላል? ወደፊት ቢቀጥል አገሪቷን ለመገነጣጠል ነው የሚለው ኃይል ያይልበታል፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ ወደ ኋላ መመለስ አትችልም፡፡ ስለዚህ አጣብቂኝ ሁኔታ ላይ ነው ያለው ኢሕአዴግ፡፡ ችግሮቹን ከመፍታት በዘለለ የተለያዩ የውጭ ኃይሎች ጥያቄ ነው ማለት አያዋጣውም፡፡ ዘላቂ የሆነ መፍትሔ ለማምጣት ጥረት እያደረገ እንዳልሆነ ሊወሰድ ይችላል፡፡

 

 

Standard (Image)

በናይል ተፋሰስ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶች ላይ እየጎለበቱ ያሉ ሥጋቶች

$
0
0

በላይኛው ተፋሰስ አገሮችና በሱዳን በምግብ፣ በባዮ ፊውልና ከፍተኛ ገንዘብ በሚያስገኙ አዝርዕቶች ላይ ያተኮሩ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶች የናይል ኃይድሮ ፖለቲካ ገጽታ ላይ ምን ተፅዕኖ ይኖራቸዋል? ይህ እየጎለበተ የመጣ አዝማሚያ ውጤታማ ትብብርና የጋራ የዓባይ ውኃ አስተዳደርን ለመፍጠር ይገፉ ይሆን? ውኃውን በተመለከተ የቀጣናው አገሮች የሚኖራቸው ግንኙነት ምን ገጽታ ይሰጠዋል? በቀጣናው የሚሠሩ ተቋማትስ ምን ሚና ይኖራቸዋል? ‹‹Land and Hydro Politics in the Nile River Basin – Challenges and New Investments›› በሚል ርዕስ የወጣውና ባለፈው ነሐሴ ወር 2008 ዓ.ም. የተመረቀው መጽሐፍ እነዚህንና መሰል ጥያቄዎችን ለመመለስ ይሞክራል፡፡

ይኼው መጽሐፍ በቅርቡ እ.ኤ.አ. ከዲሴምበር 3 እስከ 5 ቀን 2016 በሱዳን በዋድ መዳኒ በተካሄደ ዓውደ ጥናት በድጋሚ የተመረቀ ሲሆን፣ ለመጽሐፉ አስተዋጽኦ ያደረጉ በርካታ አጥኚዎች ዓውደ ጥናቱን ታድመዋል፡፡ ዓውደ ጥናቱ በስቶክሆልም ዓለም አቀፍ የውኃ ኢንስቲትዩት (ሲዊ)፣ በዓለም አቀፍ የውኃ ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት (ኢውሚ) እና በሱዳን ኃይድሮሊክ ጥናት ማዕከል (ኤችአርሲ) በጋራ የተዘጋጀ ነው፡፡ ተመሪማሪዎች፣ ኤክስፐርቶች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ የግሉ ዘርፍና ሚዲያንም ያሰባሰበ ነበር፡፡ መጽሐፉም ሆነ ዓውደ ጥናቱ ዋነኛ ጭብጥ ያደረጉት በናይል ተፋሰስ በተለይም በምሥራቃዊ ናይል የሚካሄዱ ግዙፍ የውኃና የመሬት ኢንቨስትመንቶችን ነው፡፡

ኤሚል ሳንድስትሮም ከመጽሐፉ ሦስት አርታኢዎች አንዱ ሲሆኑ፣ በመጽሐፉ ከተካተቱ ምዕራፎች በአንዱ እየተስፋፉ የመጡ የመሬት ኢንቨስትመንቶች በናይል ኃይድሮ ፖለቲካ ላይ ስለሚኖራቸው ተፅዕኖ በስፋት ይተነትናሉ፡፡ እንደ ሳንድስትሮም ገለጻ፣ ለመሬትና ለሠራተኛ በአንፃራዊነት ርካሽ ዋጋ የሚጠይቁ አገሮች በግብርና ዘርፍ መሰማራት ለሚፈልጉ የውጭ ኢንቨስትመንቶች የሚስቡ መዳረሻዎች ሆነዋል፡፡ ምንም እንኳን በአካባቢው የሚከናወኑ የመሬት ኢንቨስትመንት ስምምነቶችና በድንበር ዘለል ውኃ ማኔጅመንትና የውኃ አቅርቦት ላይ ስለሚኖራቸው ተፅዕኖ ያለው ትክክለኛ መረጃ ውስንነት ያለበት ቢሆንም፣ የኢንቨስትመንቶቹ ቁጥር ግን በፍጥነት እየተመነደገ ስለመሆኑ ጥርጣሬ የለም ይላሉ፡፡ 

በእንግሊዝ በሚገኘው ሱሴክስ ዩኒቨርሲቲ በዴቨሎፕመንታል ስተዲስ ኢንስቲትዩት የዶክትሬት ተመራማሪ ራሚ ሎትፊ ሃና ከመሬትና ከውኃ ጋር የተያያዙ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶችን ለአራት ይከፍሏቸዋል፡፡ እነዚህም በቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት (በግል)፣ በቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት (በመንግሥት)፣ በሁለት መንግሥታት ድርድርና በአገሮቹ የግል ባለሀብቶች የሚካሄዱ ናቸው፡፡

ከእነዚህ መንገዶች በአንዱ ወይም በሌላው በናይል ተፋሰስ በቅርብ ዓመታት ግዙፍ የመሬት ኢንቨስትመንቶች ተከናውነዋል፡፡ በተለይ ኢትዮጵያን፣ ግብፅን፣ ሱዳንንና ደቡብ ሱዳንን ባቀፈው የምሥራቅ ዓባይ ተፋሰስ አገሮች ይህ ይበልጥ ተጧጡፎ ቀጥሏል፡፡ የስንድስትሮም ጥናት እንደሚጠቁመው፣ እ.ኤ.አ. ከ2008 እስከ 2013 ባለው ጊዜ ውስጥ ብቻ በምሥራቅ ዓባይ ተፋሰስ አገሮችና በኡጋንዳ የተከናወኑት ግዙፍ የመሬት ኢንቨስትመንቶች 4.3 ሚሊዮን ሔክታር መሬት ሸፍነዋል፡፡ በተመሳሳይ ጊዜ ውስጥ የግብፅ መንግሥት ብቻውን በላይኛው ተፋሰስ አገሮች የፈጸማቸው ግዙፍ የመሬት ኢንቨስትመንት ስምምነቶች 1.7 ሚሊዮን ሔክታር መሬት የሸፈኑ ናቸው፡፡

ለእነዚህ የግብርና ሥራዎች የውኃ አቅርቦት እጅግ ወሳኝ ጉዳይ ቢሆንም፣ በእነዚህ ኢንቨስትመንቶች ድርድር የውኃ ጉዳይ ሙሉ በሙሉ ችላ የተባለ እንደሆነ የሳንድስትሮም ጥናት ያሳያል፡፡ በውሎቹ ለመሬቶቹ ስለሚቀርበው ውኃ ምንም የተባለ ነገር እንደሌለ አመልክተዋል፡፡ ‹‹ይኼ በናይል ዙሪያ ባለው የውኃ ሀብት ጥያቄ ላይ ተጨማሪ ውስብስብ የሚያክል ነው፤›› ብለዋል፡፡

በተመሳሳይ በዋድ መዳኒው ዓውደ ጥናት የቀረቡት ጥናቶች በአሁኑ ወቅት በተፋሰሱ እየተከናወኑ ያሉ የውኃ፣ የመሬትና የኢነርጂ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶችና ዘላቂነታቸው ላይ ያለው አለመመጣጠን የናይል ጉዳይን ይበልጥ እንዳያወሳስበው ሥጋታቸውን አንፀባርቀዋል፡፡ የናይል ተፋሰስ አገሮችን እየፈተኗቸው ያሉ ችግሮች ላይ ተጨማሪ ፈተና ሆኖ እንዳይቀጥል፣ እነዚህ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶች በከፍተኛ ጥንቃቄ መመራት እንዳለባቸውም አሳስበዋል፡፡ ጥናቶቹ እንደ ደመደሙት፣ ከእነዚህ ኢንቨስትመንቶች አስቀድሞም ቢሆን የውኃው መጠንና ጥራት እየቀነሰ ነበር፡፡ በዚህ ላይ የአየር ንብረት ለውጥና የሕዝብ ብዛት መጨመር ሲታከልበት ፈተናውን ይበልጥ ያወሳስበዋል፡፡

በሌላ በኩል በአካባቢው ለሚገኙ ጥቂት አገሮች የምግብ ዋስትና ሌላ አንገብጋቢ አጀንዳ ነው፡፡ የቀጣናው ደሃ አገሮች ዜጎቻቸውን ለመመገብና በሕይወት ለማቆየት በግብርና ላይ በከፍተኛ ሁኔታ ጥገኛ ናቸው፡፡ በተለይ የምሥራቅ ናይል ተፋሰስ አገሮች ሕዝብ ከእጅ ወደ አፍ በሆነ ግብርና፣ የመስኖ ግብርናና በኃይድሮ ፓወር ላይ ጥገኛ ነው፡፡ ከዘርፉ ብዙ የግብርና ጠቀሜታዎች መካከል የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ቁልፍ ሚና የሚጫወት መሆኑ፣ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የሥራ ዕድል የሚፈጥርና የመሬት ዋጋን የሚጨምር መሆኑ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የውጭ ንግድን ለማስፋፋትና ለአካባቢ ጥበቃ ምቹ የሆነ ቢዝነስ ለማከናወን ያለው ቁልፍ ሚናም ቀላል አይደለም፡፡

እነዚህን የግብርና ሥራዎች ለማከናወን የሚያስፈልገው ውኃ ሁሌም ከዝናብ አይገኝም፡፡ በመስኖ የሚከናወነው የግብርና ሥራ ቁጥሩ ከፍተኛ ነው፡፡ ከውኃ አቅርቦት ጥናቱ አንፃር ሥጋት የሆነው በመስኖ የሚካሄደው ግብርና ነው፡፡ ለመስኖ ግብርና የሚውለው የውኃ መጠን ከፍተኛ በመሆኑ፣ በታችኛው ተፋሰስ አገሮች የሚፈሰውን መጠን ይቀንሳል በሚል ነው ሥጋቱ የሚመነጨው፡፡ በዓባይ ተፋሰስ አገሮች መካከል ባለው ድርድር የውኃ መጠን መቀነስ ከዋነኛ አጀንዳዎች መካከል ተጠቃሽ ነው፡፡ የናይል የማዕቀፍ ስምምነት እንዳይፈረም ያደናቀፈው ጉዳይ የውኃ ደኅንነት መሆኑ ለዚህ ምስክር ነው፡፡

እንዲሁም ተጨማሪ የውኃ አቅርቦት ጥያቄ እየጨመረ እንደሚመጣ ይጠበቃል፡፡ ስለወደፊቱ ጊዜ ያሉ ትንበያዎች ይህ ጥያቄ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ እንደሚመጣ ያሳያሉ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የውኃና የመሬት ሀብቶች ጥናት ማዕከል ዳይሬክተር ዶ/ር ጌጤ ዘለቀ፣ ‹‹እ.ኤ.አ. በ2050 የተፋሰሱ አገሮች የሕዝብ ቁጥር አንድ ቢሊዮን እንደሚደርስ ትንበያ አለ፡፡ ከእዚህ ሕዝብ መሀል 70 በመቶ የሚሆነው በከተማ አካባቢ እንደሚኖር ይጠበቃል፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ለውኃ፣ ለምግብና ለኢነርጂ አቅርቦት ጥያቄ እ.ኤ.አ. በ2035 ወደ 1,170,328 ጊጋ ዋት በሰዓት እንደሚያድግ ይጠበቃል፤›› ብለዋል፡፡

ከውኃ እጥረትና ከጥራት መቀነስ ጋር ለተያያዘው ችግር ከፊል መፍትሔ ተደርጎ የሚወሰደው የኢንቨስትመንቶቹ ዘላቂነት ነው፡፡ ዶ/ር ጌጤ በተፈጥሮ ሀብቶች ማኔጅመንት ላይ የሚደረጉ ኢንቨስትመንቶች ዘላቂ እንዲሆኑ ለማድረግ ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጥ እንደሚገባ ይከራከራሉ፡፡ ‹‹ባለፉት አራት አሠርት የተፈጥሮ ሀብቶች ዘላቂ እንዲሆኑ ለማድረግ ከፍተኛ ወጪ ቢወጣም፣ የመሬት መሸርሸር አሁንም በምሥራቅ ናይል ከፍተኛ ተግዳሮት ነው፤›› ብለዋል፡፡ የተገኘው ውጤት ግን ከተደረጉ ጥረቶች ጋር የማይጣጣም እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ የናይል ቤዚን ኢንሼቲቭ ዋና ዳይሬክተር ኢኖሰንት ንታካናና የኢንትሮ ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈቅ አህመድ ነጋሽ ግን፣ ተቋሞቻቸው የተፈጥሮ ሀብቶች በዘላቂነት ማገልገላቸውን እንዲቀጥሉ ለማድረግ በርካታ ሥራዎችን እያከናወኑ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

ዶ/ር ጌጤ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶች ዘላቂ እንዲሆኑ ለማድረግ ሥራው መጀመር ያለበት በዕቅድ ዝግጅት ወቅት መሆን እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ የአካባቢው ማኅበረሰብና ባለሥልጣናት የፕሮጀክቶቹ ባለቤት እንዲሆኑ ማድረግ ለዚህ ስኬት ወሳኝ መሆኑንም አመልክተዋል፡፡

በኤክስፐርቶቹ ዕይታ የዘላቂነት ጉዳይ በአገሮቹ በተናጠል ከሚሠራ ይልቅ፣ በትብብር ቢሠራ ተመራጭ የሚያደርጉ በርካታ ምክንያቶች አሉ፡፡ ለአብነትም ያህል ዶ/ር ጌጤ የመሬት መራቆት ምርታማነትን ከመቀነስ ባሻገር፣ የተፋሰሱን ባዮ ፊዚካል ጤንነት ስለሚጎዳ አገሮቹ በትብብር ሊሠሩ ይገባል ይላሉ፡፡ ዶ/ር ጌጤ በአንድ የዓውደ ጥናቱ ተሳታፊ የታችኛው ተፋሰስ አገሮች፣ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ የላይኛው ተፋሰስ አገሮች የመሬት ዘላቂነት ለማረጋገጥ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ተጠይቀው ነበር፡፡ ‹‹ለምሳሌ ሱዳን ንፁህ ውኃን ከደለል ለመለየት በሚሊዮን ዶላሮች እንደምታወጣ እናውቃለን፡፡ ለፅዳት ይህን ሁሉ ወጪ ከማውጣት ለመሬት ዘላቂነት ይህን ገንዘብ በኢትዮጵያ ከፍታማ ቦታዎች ላይ ማውጣት ይቻላል፡፡ ይህ ምርታማነትን ያሳድጋል፣ አፈሩንም እዚያው ያስቀራል፤›› ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

የዋድ መዳኒ ዓውደ ጥናት ተሳታፊዎች በሱዳን የሚገኙ ሁለቱን ትልልቅ የመስኖ ግብርና ኢንቨስትመንቶች ማለትም ረሃድ የግብርና ኮርፖሬሽንንና ዳል የመስኖ እርሻን ሲጎበኙ እንደተነገራቸው፣ ኢንቨስትመንቶችን ለማንቀሳቀስ ከሚያውሉት ወጪ ውስጥ 60 በመቶ ያህሉ ለካናል ፅዳት የሚውል ነው፡፡ የሱዳን ሲናርና ሮሰሪስ ግድቦች የመያዝ አቅም በከፍተኛ ሁኔታ የቀነሰው በመሬት መራቆትና በደለል ምክንያት ነው፡፡

ይህ ቢሆንም ሱዳን በመስኖ የሚካሄድ ግብርናን ለማስፋፋት ያላት አቅም ግዙፍ ነው፡፡ በሲዊ የወሰን ተሻጋሪ ውኃ ማኔጅመንት ክፍል ፕሮግራም ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር አና ኤሊሳ ካስካዮ፣ እ.ኤ.አ. በ1990ዎቹ የመስኖ ግብርና በሱዳን ትኩረት ተነፍጎት እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ይህ ደግሞ ነዳጅ ከመገኘቱ ጋር ተያይዞ ነበር፡፡ ነገር ግን ደቡብ ሱዳን ከሱዳን ተነጥላ ራሷን ከቻለች በኋላ ከነዳጅ የሚገኘው ገቢ በመቀነሱ አሁን ደግሞ ትኩረት ተሰጥቶታል፡፡

ዶ/ር አና ከዚሁ ጎን ለጎን በዓለም ፖለቲካዊ ኢኮኖሚ ላይ እ.ኤ.አ. ከ2008 በኋላ የተከሰተው ለውጥና በግብርና ዘርፍ መሰማራት የሚፈልጉ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንቶች መበራከት፣ ሱዳንን ዋነኛ መዳረሻ ማድረጉን ይጠቁማሉ፡፡ አሁን በሱዳን በመስኖ የለማው መሬት ከ1.2 ሚሊዮን እስከ 2.2 ሚሊዮን ሔክታር የሚገመት ሲሆን፣ ከአጠቃላይ መታረስ ከሚችለው መሬቷ አንድ በመቶ አካባቢ ብቻ የሚሆን ነው፡፡

የሱዳን የውኃ ሀብቶች ቴክኒካል ክፍል ሊቀመንበርና የቀድሞው የውኃ ሀብት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ሰይፈልዲን አብደላ፣ ሱዳን ገና ጥቅም ላይ ያልዋለ የውኃና የመሬት ሀብቶች ባለቤት እንደሆነች ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን የሀብቶች አጠቃቀምና አስተዳደር ላይ በርካታ ክፍተት ያለባቸው ጉዳዮች እንዳሉ ይቀበላሉ፡፡

ዶ/ር አናም በዚህ ሐሳብ ይስማማሉ፡፡ ሱዳን በመስኖ ለማልማት ያሰበችው የግብርና ሥራ ሙሉ በሙሉ ተግባር ላይ ቢውል ቢያንስ በዓመት ተጨማሪ አሥር ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውኃ እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል፡፡ እንደ ዶ/ር አና ገለጻ የሱዳን የመስኖ ግብርና የማስፋፋት ዕቅድ ሙሉ በሙሉ ሊተገበር የሚችለው፣ የላይኛው ተፋሰስ አገሮች የውኃ ማጠራቀሚያ መሠረተ ልማት ሲሳካ ነው፡፡ ምናልባትም ሱዳን ለታላቁ ህዳሴ ግድብ የምትሰጠው ድጋፍ ከዚሁ ዓላማዋ ጋር የተያያዘ ነው፡፡

ጥቂት የማይባሉ የሱዳን ባለሥልጣናት ታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ በሱዳን የሚከናወነውን የመስኖ እርሻ በእጥፍ ለማሳደግ እንደሚጠቅማቸው ያምናሉ፡፡ ግድቡ የውኃውን ፍሰት ለመቆጣጠርና ለመስኖ ግብርናው የውኃ አቅርቦት እንዲጨምር በማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ሳይንሳዊ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡

በተመሳሳይ ዶ/ር አና ግድቡ ሱዳን ውኃ ከመልቀቅና ከማከፋፈል አንፃር የምትወስዳቸው ውሳኔዎች የተሻሉ እንዲሆኑ በማስቻልም ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት ጠቅሰዋል፡፡ ያልተጠበቀ እጥረት ቢፈጠር መፍትሔ የሚሰጥም እንደሆነ አክለዋል፡፡

ከሱዳን በተቃራኒ በኢትዮጵያ የመስኖ እርሻ በገበሬዎች የተወሰነ እንደሆነ፣ በኖርዲክ አፍሪካ ኢንስቲትዩት ተመራማሪ የሆኑት ዶ/ር አታክልት በየነ ይገልጻሉ፡፡ ይሁንና ከኢትዮጵያ መሬት ውስጥ 74.3 ሚሊዮን ሔክታር የሚሆነው ለግብርና የተመቸ እንደሆነ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡ ከዚህ ውስጥ አነስተኛ ገበሬዎች 14.6 ሚሊዮን ሔክታር የሚሆነውን ብቻ እንዳለሙም መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የመንግሥት ይፋዊ መረጃ እንደሚያሳየው 4.3 ሚሊዮን ሔክታር መሬት በመስኖ መልማት የሚችል ነው፡፡ አሁን የለማው አንድ ሚሊዮን ሔክታር ብቻ ነው፡፡ ዶ/ር አታክልት የመስኖ ማኔጅመንት ሽግግር የግብርና ፖሊሲው አካል የሆነውና ወደ ተግባር የገባው በቅርቡ እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡

አዲሱ ስትራቴጂ የሚበረታታባቸው በርካታ ምክንያቶች እንዳሉ ዶ/ር አትክልት ያስረዳሉ፡፡ ለአብነትም ለድህነት ቅነሳ፣ ለኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለአረንጓዴ ልማትና የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም ቁልፍ መሣሪያ በመሆን ሊያገለግል እንደሚችል ይጠቁማሉ፡፡ የከተማ ነዋሪና የኢንዱስትሪ ፍላጎቶችን በአግባቡ የሚረዳ አምራች ለመፍጠርም ትልቅ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸዋል፡፡ ዶ/ር አትክልት በጣና ሐይቅ ተፋሰስ የሚገኘው የቆጋ ግድብና ግዙፍ የመስኖ እርሻ 10,000 የሚጠጉ አነስተኛ አርሶ አደሮችን እንደሚያሳትፍ አመልክተዋል፡፡

ከዚህ በተቃራኒ በጋምቤላ ግዙፍ የእርሻ ኢንቨስትመንቶች ከፍተኛ ችግር ውስጥ መዘፈቃቸው ይነገራል፡፡ በሊንድ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ ትምህርት ክፍል የፒኤችዲ ተማሪ የሆኑት አቶ ወንድወሰን ሚጫጎ፣ ሁሉም ማለት በሚቻል ሁኔታ ውጤታማ መሆን እንዳልቻሉ ገልጸዋል፡፡ በጋምቤላ 11 ዓለም አቀፍ ኢንቨስተሮች፣ በርካታ የኢትዮጵያ ዜጎችና በውጭ አገር ነዋሪ የሆኑ ኢትዮጵያዊያን የተሰማሩ ቢሆንም የአካባቢው ተወላጆች በባለሀብትነት እንዳልተመዘገቡ አቶ ወንድወሰን ጠቅሰዋል፡፡

አቶ ወንደወሰን ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር ምክክር አለመደረጉና በውሳኔ አሰጣጡ ተሳታፊ አለመሆናቸው፣ የአካባቢው ነዋሪዎች እንዲማሩና እንዲሠለጥኑ በቂ ዕድል አለመሰጠቱ፣ የተፈጠረው የሥራ ዕድል እጅግ አነስተኛ መሆን፣ የኢንቨስትመንት ፈቃዳቸውን ከባንክ ብድር ለማግኘት ብቻ የተጠቀሙ ሐሰተኛ ባለሀብቶች መገኘት፣ ጣውላ በማምረትና በመሸጥ ሲሳተፉ የተገኙ ሕገወጥ ባለሀብቶች መገኘት በጋምቤላ ግዙፍ የግብርና ኢንቨስትመንቶችን ስኬት እንቆቅልሽ እንዳደረገው አቶ ወንድወሰን ዘርዝረዋል፡፡

በዓውደ ጥናቱ የቀረቡ በርካታ ጥናቶች እንዳመለከቱት በምሥራቅ ናይል የሚገኙ የመሬት፣ የውኃና ኢነርጂ ኢንቨስትመንቶች መፃኢ ዕድል የተፋሰሱ አገሮች የትብብር አቅጣጫን የሚወስን ነው፡፡ የተሻለ ውሳኔ በመወሰን የአካባቢውን ሕዝቦች ኑሮ ለማሻሻል ሳይንሳዊ ዕውቀትና ጠንካራ ማስረጃ እጅግ አስፈላጊ ጉዳይ እንደሆነም አስምረውበታል፡፡ ይህን ለማሳካትም አገሮቹ ዕቅድ ሲያወጡም ሆነ ሲፈጽሙ ቀጣይነት ያለው ምክክር ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡

ፕሮፌሰር ሰይፈልዲን አገሮቹ በተናጠል ፕሮጀክቶችን ማቀድና መፈጸም ከቀጠሉ፣ ያለው ውኃ በስኬት ፕሮጀክቶችን ለመፈጸም እንደማያስችልም አስጠንቅቀዋል፡፡ እንደ እሳቸው እምነት ናይል በኃይድሮ ፓወር፣ በመስኖ፣ በትራንስፖርቴሽንና በቱሪዝም የአገሮቹን ራዕይ ማሳካት የሚችለው በትብብር ከተመራ ብቻ ነው፡፡

‹‹የናይል ውኃ በአጭር፣ በመካከለኛና በረጅም ጊዜ ምን እንደሚሆን በአጠቃላይ መረዳት ካልቻልንና የትኛውም ዕርምጃ በናይል ላይ የማይቀለበስ ጉዳት እንደሚያስከትል ካልተረዳን ትልቅ ችግር ላይ እንወድቃለን፡፡ የናይል ወንዝ ሳይንስን በአግባቡ አልተረዳነውም፤›› ሲሉ ፕሮፌሰር ሰይፈልዲን በጋራ የመሥራት ጊዜው ለነገ የሚባል ሳይሆን አጣዳፊ እንደሆነ አስጠንቅቀዋል፡፡        

 

Standard (Image)

የመንግሥትን ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት የሚጠይቀው የውኃ አጠቃቀም ስትራቴጂ

$
0
0

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከማስተማር በተጨማሪ የመመረቂያ ጽሑፍ በማዘጋጀት ላይ የነበሩ የኬሚስትሪ ተማሪዎች አማካሪ ሆነው ያጋጠማቸውን ልምድ አቶ አመሐ በቀለ ያስረዳሉ፡፡ ‹‹የመመረቂያ ጽሑፋቸውን እየሠሩ ከነበሩ ተማሪዎች ለአንዱ አማካሪ ሆኜ በማግዝበት ወቅት፣ ለጥናቱ ግብዓት ሲሰበሰብ ካገኛቸውና ካነጋገራቸው ግለሰቦች መካከል በአቃቂ አካባቢ ያነጋገረው ወጣት ታሪክ አስደንጋጭ ነበር፤›› ይላሉ፡፡ ከአዲስ አበባ በአቃቂ በኩል አድርጎ ወደ አባ ሳሙኤል በሚፈሰው ወንዝ ዳር በአትክልትና ፍራፍሬ ምርት ራሳቸውን ስለሚያስተዳድሩ አርሶ አደሮች የአንዱን ታሪክ ይገልጻሉ፡፡ ይህ የተመራቂው ተማሪ የጥናት አካል የሆነው ወጣት አርሶ አደር ውኃውን አትክልት ለማጠጣት ሲሞክር ሰውነቱን እንደሚያሳክከው፣ ሌላ ጊዜ በቆዳው ላይ መሰነጣጠቅ እያስከተለበት መሆኑን የጥናት ሥራውን በሚያማክሩበት ወቅት መታዘባቸውን ይገልጻሉ፡፡

አቶ አመሐ በቤተ ሙከራ አማካሪነት የሚያገለግሉ የኬሚስትሪ ባለሙያ ናቸው፡፡ ይህን ልምዳቸውን ያካፈሉት ከታኅሳስ 15 እስከ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. በአዳማ ከተማ የኢትዮጵያ ውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ባዘጋጀው የሁለት ቀናት የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ ላይ ነበር፡፡ በዚሁ መድረክ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት አቶ አመሐ፣ ኢትዮጵያ ያላት የውኃ ሀብት ከፍተኛ ቢሆንም ውኃው በቴክኖሎጂ በታገዘ የአጠቃቀም ዘዴ ካልተያዘ፣ ከሀብትነቱ ይልቅ ጉዳት ሊያስከትል እንደሚችል አስረድተዋል፡፡

ለበርካታ ዓመታት ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ታድላለች ተብሎ ከሚነሱ የተፈጥሮ ሀብቶች ውስጥ የውኃ ሀብት ይጠቀሳል፡፡ አንዳንዴም አገሪቱን ‹‹የምሥራቅ አፍሪካ የውኃ ማማ›› በማድረግም ስሟ ሲነሳ መስማት የተለመደ ነው፡፡ በአንፃሩ ደግሞ በተለይ ከዓለም የከባቢ አየር ሙቀት መጨመር በተያያዘና ከአካባቢ መራቆት ጋር በተገናኘ፣ የአገሪቱ የውኃ ሀብት መቀነሱንና አደጋ ላይ መውደቁም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ሲነገር ይሰማል፡፡

በቅርቡ የተሾሙት የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስትሩ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ፣ በአዳማው የምክክር ጉባዔ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ባደጉበት ወቅት የአገሪቱን ውኃ ሀብት በዝርዝር ገልጸው ነበር፡፡

‹‹አገራችን እንደሚታወቀው ሰፋፊ የተፈጥሮ ፀጋዎች ያላት ውብ አገር ናት፤›› ያሉት ሚኒስትሩ፣ ‹‹በውኃ ዘርፍ ብቻ ያሏት የተፈጥሮ ፀጋዎች ማንኛውንም ዓይነት የኢኮኖሚ እመርታ ለማስመዝገብ፣ በዚያው መጠን የሕዝቦችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል የሚያስችል መሠረታዊ ዕድገት የሚፈጥሩ ስትራቴጂካዊ የተፈጥሮ ሀብት ናቸው፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

በየተፋሰሶቹ በተደረገ ጥናት የአገሪቱ አለኝታ የሆነው ውኃ 123 ቢሊዮን ሜትር ኪዩቢክ ሜትር የሚደርስ ሲሆን፣ ከዝናብ የሚገኘው ውኃ ወደ አንድ ትሪሊዮን ኪዩቢክ ሜትር እንደሚደርስም ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ ከእነዚህም ከጠቀሷቸው ሁለቱ የውኃ መገኛዎች ውስጥ 12 በመቶ የሚሆነው በገጸ ምድር ላይ የሚገኘው እንደሆነ፣ በትክክል የማይታወቅ በማለት ሚኒስትሩ የገለጹት ወደ 36 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር የሚገመት የከርሰ ምድር ውኃ አገሪቷ እንዳላት አክለዋል፡፡ እንዲሁም ቅሪተ አካል በሚገኝበት የመሬት ጥልቅ ክፍል ያለው የውኃ መጠንም በትክክል እንደማይታወቅ ጠቁመዋል፡፡

ይህ ሁሉ የሚገመተው በአንፃሩ በተፋሰሶች አማካይነት ወደ ሌላ አገር ከሚሄደው በተጨማሪ፣ አብዛኛው ውኃ በትነት መልክ እንደሚባክንም ሳይገልጹ አላለፉም፡፡ ነገር ግን፣ ‹‹በአገሪቱ ያለንን ሀብት በአግባቡ ይዘን ወደ ጠቃሚ ሀብት ልንለውጥ ይገባናል፤›› ያሉት ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ፣ ‹‹ይህን ማድረግ ስላልቻልን የተለዋዋጭ የተፈጥሮ አደጋና ድርቅ ተጋልጠናል፤›› ሲሉም አስረድተዋል፡፡

በተጨማሪም አለ የተባለውን ከፍተኛ የውኃ ሀብት ተጠቅሞ የሕዝቡን ኑሮ በአግባቡ መለወጥ እንዳይቻል ያደረጉ ምክንያቶችን ሚኒስትሩ የዘረዘሩ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ ‹‹የውኃ ሀብታችንን እንዳንጠቀም የተረጋጋ የፖለቲካ ሁኔታ እንዳይኖረን ያደረጉን ያለፉት ሥርዓቶች፤›› ይገኙበታል ብለዋል፡፡ እንዲሁም ወጥ የሆነ የውኃ አጠቃቀም ፖሊሲ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ አለመኖሩ ሌላው ችግር እንደነበርም አክለው ገልጸዋል፡፡

የውኃ ሀብቱን በመጠቀም ረገድ መንግሥት አበረታች የልማት ሥራዎችን እየተገበረና መልካም ውጤት እየተገኘበት መሆኑን ያወሱት ሚኒስትሩ፣ በዚህ ወቅት ያለው ሳይንሳዊ አጠቃቀምና በቂ የሠለጠነ የሰው ኃይል ውሱንነትን ጨምሮ የውኃ ሀብት መጠኑን ማስተካከል የሚችል የቴክኖሎጂ ባለቤት መሆን አለመቻሉ ትልቁ ተግዳሮት እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡

የውኃ ዘርፍን በአግባቡ መጠቀምና ወደ ተሻለ የልማት ምንጭነት ለማሳደግ ከሚንቀሳቀሱ መንግሥታዊ ተቋማት ዋነኛውን ኃላፊነት ወስዶ እንዲንቀሳቀስ በአዋጅ የተቋቋመው፣ የኢትዮጵያ ውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ነው፡፡ ተቋሙ በኢንስቲትዩትነት በ2005 ዓ.ም. በአዋጅ ከመቋቋሙ በፊት በፕሮጀክት ደረጃ በጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (JICA) ድጋፍ፣ ለ15 ዓመታት ያህል የኢትዮጵያ ውኃ ምርምር ማዕከል በመሆን አገልግሏል፡፡

የኢትዮጵያ ውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ዘነበ ጋረደው፣ ኢንስቲትዩቱ የውኃ ዘርፍን የማስፈጸም አቅም ለማሳደግ በሰው ኃይል ልማትና በምርምር ቴክኖሎጂ ሽግግር የበኩሉን አስተዋፅኦ እንዲያበረክት ታስቦ በመንግሥት መቋቋሙን ገልጸዋል።

ኢንስቲትዩቱ በዋናነት በሰው ኃይል ልማትና በውኃ ሀብት ዙሪያ ችግር ፈቺ ምርምር ማካሄድ፣ ተስማሚ ቴክኖሎጂዎችን ማላመድ፣ ማስተላለፍና  በሌሎችም ተያያዥ ዘርፎች ላይ የምርምር አገልግሎት የመስጠት ኃላፊነት ተሰጥቶት እየሠራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ችግር ሊፈቱና ጠቃሚ የፖሊሲ ሐሳቦች ለማመንጨት፣ የሥራ አፈጻጸምን ለመገምገምና የወደፊት አቅጣጫ ለማስቀመጥ ታስቦ መድረኩ መዘጋጀቱን ዋና ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል።

አቶ ዘነበ ተቋማቸው ልዩ የቤተ ሙከራ አገልግሎት መስጠት አንዱ ተልዕኮው መሆኑን ነው የሚናገሩት፡፡ በአገር ውስጥ ያለ የከርሰ ምድርም ሆነ የገጸ ምድር ውኃ የተለያዩ ፍተሻዎች እንደሚደረግላቸውም ይጠቁማሉ፡፡

በአሁኑ ወቅት በአገር ውስጥ የተለያዩ ኢንቨስትመንቶችና ኢንዱስትሪዎች እያደጉ እንደሚገኙ የሚጠቁሙት ዋና ዳይሬክተሩ፣ የሚለቅቁት ፍሳሽ ፍተሻ ሊደረግለት እንደሚገባ ይናገራሉ፡፡ ለመጠጥነት የሚውለው ውኃም ለጤና ተስማሚ ስለመሆኑ አስፈላጊው ፍተሻ ሊደረግለት ይገባል ሲሉ ያሳስባሉ፡፡ ይህንን ፍተሻ ለማከናወን የሚውሉ ቤተ ሙከራዎች በጣም ጥቂት እንደሆኑም አስረድተዋል፡፡ ፍተሻውን በአገር ውስጥ በማከናወን የውጭ ምንዛሪን ማዳን ይገባልም ሲሉ ይገልጻሉ፡፡

እንደ ዋና ዳይሬክተሩ ገለጻ፣ ልዩ ቤተ ሙከራውን ለማደራጀት ኢንስቲትዩቱ እየሠራ ነው፡፡ ‹‹ቤተ ሙከራውን ለማደራጀት ከፍተኛ በጀት ያስፈልጋል፡፡ የገንዘብ እጥረትም አለ፡፡ ችግሩን ለመፍታት መንግሥት ልዩ ትኩረት ሊሰጥ ይገባል፡፡ ለቤተ ሙከራው አገልግሎት የሚውሉ ኬሚካሎችም በተመሳሳይ ከፍተኛ ገንዘብ የሚጠይቁ ናቸው፤›› በማለት ከሚያበረክተው አገልግሎት አንፃር ተመዝኖ መንግሥት ልዩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡

ቤተ ሙከራውን ገንብቶ አስፈላጊዎቹን የመመርመሪያና የመፈተሻ መሣሪያዎች ለማሟላት፣ በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ እንደሚያስፈልግ የሚጠበቅ መሆኑን፣ የተቋሙ ኃላፊዎች አጠቃላይ የፋይናንስ ፍላጎቱን ለማጠናቀቅ የዳሰሳ ጥናት እያካሄዱ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ኃላፊዎቹ ቢያንስ አንድ የመፈተሻ መሣሪያ ከ200 እስከ 300 ሚሊዮን ብር እንደሚያወጣ ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡

‹‹መሣሪያዎቹ ባላቸው የገበያ ተፈጥሮአዊ ሁኔታ ስንመለከት ውድና ከፍተኛ ፋይናንስ የሚፈልጉ ናቸው፤›› በማለት ለሪፖርተር ያስረዱት አቶ ዘነበ፣ ፋይናንሱ በመንግሥት ብቻ የሚሸፈን ነው ለማለት ስለሚያስቸግር አማራጭ የገቢ ምንጮች የሚገኙበትን መንገዶች መንግሥት ሊያስብበት እንደሚባ አክለዋል፡፡

የፋይናንስ አቅሙ አገርን የሚፈታተን መስሎ ቢታይም ውኃ ሕይወት በመሆኑ የግድ ቤተ ሙከራውን ማቋቋም እንደሚያስፈልግ ይከራከራሉ፡፡ ‹‹ውኃ ማግኘት ሕይወት ነው፡፡ ሰብዓዊ መብት ነው፡፡ ሕይወት የሆነ ጉዳይ ላይ ደግሞ ልዩ ትኩረት ያስፈልጋል፡፡ አንዳንድ አገሮች ለምሳሌ ኬንያን ብንመለከት ውኃ ሰብዓዊ መብት ነው ብለው እየሠሩ ነው፡፡ እኛም አገር ለሕይወት ከዚህ የሚበልጥ ሥራ ስለሌለ ንፁህና የተጣራ ውኃ ለማግኘት ደረጃውን የጠበቀ ቤተ ሙከራ የግድ ያስፈልጋል፤›› ሲሉ ያስረዳሉ፡፡

በቤተ ሙከራ አገልግሎት ዘርፍ የማማከር ሥራ የሚሠሩት የኬሚስትሪ ባለሙያው አቶ አመሐ በበኩላቸው የክህሎት ክፍተት፣ የባለሙያዎች  እጥረት፣  ፍተሻ የሚደረግባቸው መሣሪያዎችና ኬሚካሎች አለመሟላት ዘርፉን ፈተና ውስጥ  እንደከተተው ይጠቁማሉ። ቴክኖሎጂን በበቂ ሁኔታ አለመጠቀምም ጉድለት መሆኑን በመጥቀስም የሚኒስትሩን ሐሳብ ያጠናክራሉ። ለአብነት ኢንዱስትሪዎች የሚለቁት ፍሳሽ ተገቢውን የአሠራር ሥርዓት አልፎ አለመወገዱና ለውኃ መበከል ምክንያት መሆኑን በማውሳት፣ ከተፋሰሱ በታች ያሉ የኅብረሰብ ክፍሎች የሚጠቀሙት በመሆኑ ለተለያዩ ጉዳቶች ሊዳርጋቸው እንደሚችልም ይገልጻሉ፡፡

እንደ አቶ አመሐ ገለጻ፣ የውኃና ፍሳሽ አገልግሎትም ለኅብረተሰቡ የሚያከፋፍለው ውኃ በአግባቡ ፍተሻ እየተደረገለት ስለመሆኑ በእርግጠኝነት መናገር አይቻልም። ተቋሙ ባደራጀው ቤተ ሙከራ ሥራውን በአግባቡ መምራት ፈታኝ ሆኖበታል። ይህ እጥረት እንደ አተት ላሉ የውኃ ወለድ በሽታዎች ምክንያት ነው፡፡ የታሸገ ውኃ የሚያቀርቡ የንግድ ተቋማት የአገሪቱን አስገዳጅ ደረጃ አሟልተው ስለማቅረባቸው ተገቢው ክትትል መደረግ አለበት። በሌላ በኩል ለሌሎች የልማት ዓይነቶች የኬሚካል ግብዓቶች በራሳችሁ በውኃ ሀብት ጤናማነት ላይ ችግር እየፈጠሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ ለአብነትም ያህል በዓለም የጤና ድርጅት (WHO) የተከለከለው የዲዲቲ ምርት በስፋት ኢትዮጵያ ውስጥ በወባ ማጥፊያነት ስለሚውል፣ የአገሪቱ የውኃ ሀብት ጥራት ጥያቄና ሥጋት ማስነሳቱ እንዳልቀረ አስረድተዋል፡፡

በዘርፉ የሚታየውን ችግር ለማቃለል በአቶ አመሐ የሚሰነዘሩ የመፍትሔ ሐሳቦች አሉ። የቤተ ሙከራ አደረጃጀትን በአግባቡ በመተግበር እየቀረበ ያለው ለጤና ተስማሚ ውኃ ስለመሆኑ ማረጋገጥ ይገባል። ይህንን ማድረግ ካልተቻለ በቀጣይም ተመሳሳይ ችግሮች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ በኢንዱስትሪ ዘርፉ የተሰማሩ አካላትም ኃላፊነት በተሞላበት መንገድ የቆሻሻ ፍሳሽ አወጋገዳቸውን ሊያስተካክሉ ይገባል፡፡ ፍሳሻቸውን በአግባቡ ካላስወገዱ በውኃ ሀብት አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 197/2000 መሠረት ተጠያቂ እንደሚሆኑ ተደንግጓል። በዚህ መሠረት የሚመለከተው አካል ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ ተጠያቂነትን የማስፈን ሥራ መሥራት አለበት። የምክክሩ ተሳታፊዎችም በዚህ ጉዳይ ላይ ከመንግሥት ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት ሊኖር ይገባል ሲሉም አሳስበዋል፡፡

የታሸገ ውኃ የሚያቀርቡ የንግድ ተቋማት የአገሪቱን አስገዳጅ ደረጃ ስለማሟላታቸው የጥራት ፍተሻ ለማድረግ፣ እንዲሁም ኢንዱስትሪዎች ወደ ወንዝ የሚለቁት ፍሳሽ ጉዳት ያለው መሆኑን ለመፈተሽ በልዩ ሁኔታ የተደራጀ ቤተ ሙከራ መገንባት እንደሚያስፈልግ ያሳስባሉ፡፡

በጉባዔው ላይ የተገኙት የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስትሩ የባለሙያዎቹን ጥያቄ መገንዘባቸውን ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን ሚኒስቴሩም ሆነ መንግሥት ለዚህ ጉዳይ መቼ ምላሽ እንደሚሰጡ የገለጹት ነገር የለም፡፡ ሆኖም የኢንስቲትዩቱ ኃላፊዎች ቀደም ሲል ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የተቋሙን የሥራ እንቅስቃሴ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹ሥራችሁ የፈለገ አበረታች ቢሆን እንኳ ደረጃውን የጠበቀ ልዩ ቤተ ሙከራ መገንባት ካልቻላችሁ የትም አትደርሱም፤›› እንዳሏቸው በማስታወስ፣ ከመንግሥት በጎ ምላሽ እንደሚያገኙ ተስፋ አድርገዋል፡፡

የልዩ ቤተ ሙከራው መገንባት በአገሪቱ ውስጥ ያለውን መጠነ ሰፊ የውኃ ሀብት ካጋጠመው መበከልና ሥጋት ሊያላቅቅ እንደሚችልም እያሳሰቡ ነው፡፡  

Standard (Image)

በመንታ መንገድ ላይ የሚገኘው የእርሻ ኢንቨስትመንት

$
0
0

ኢትዮጵያ ለእርሻ ሥራ አመቺ የሆነ በሚሊዮን ሔክታር የሚቆጠር መሬት ባለቤት ናት፡፡ አብዛኛው ጠፍ መሬት የሚገኘው ግን በዝቅተኛው የኢትዮጵያ አካባቢ በመሆኑ ሳይደፈር ቆይቷል፡፡

ነገር ግን በተለይ ከኢትዮጵያ ሚሊኒየም ወዲህ ለሰውና ለእንስሳት ሕይወት አደገኛ የሆኑ በሽታዎች ባሉባቸው በእነዚህ በረሃማ አካባቢዎች፣ በርካታ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ኢንቨስተሮች በመግባታቸው ታሪክ በመቀየር ላይ ይገኛል፡፡

ከአሥር ዓመታት በፊት በእርሻ መስክ ብዙም ስማቸው የማይጠራው ጋምቤላ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ ደቡብ ኦሞ፣ አፋርና ሶማሌ የበርካታ ባለሀብቶችን ትኩረት ስበዋል፡፡

ጥናቶች እንደሚያመለክቱት ከኢትዮጵያ ሚሊኒየም ወዲህ 134 የአገር ውስጥና የውጭ ባለሀብቶች በፌዴራል ደረጃ ተመዝግበው ከ500 ሺሕ ሔክታር በላይ መሬት ወስደዋል፡፡

በክልል ደረጃ ደግሞ የኢንቨስትመንት ፈቃድ በማውጣት 5,240 ባለሀብቶች ከ1.95 ሚሊዮን ሔክታር መሬት ወስደዋል፡፡ ነገር ግን እነዚህ ባለሀብቶች የተመቻቸ ሁኔታ ገጥሟቸዋል ማለት አይቻልም፡፡ ከመጀመሪያው አንስቶ አዲሱ የኢትዮጵያ የሜካናይዝድ እርሻ ስሙ ያማረ አልነበረም፡፡

በተለይ በርካታ የውጭና የአገር ውስጥ ባለሀብቶች መሬት መውሰድ በጀመሩበት ወቅት፣ ‹‹የመሬት ቅርምት›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶ ብዙ ተብሎበታል፡፡ ጉዳዩ የሚመለከታቸውን የመንግሥት ተቋማት በቂ ድጋፍ፣ ክትትል የመሬት ቅርምት ተብሎ ለተከፈተው ዘመቻም በበቂ ሁኔታ አፀፋዊ ምላሽ ባለመሰጠቱ፣ ዘርፉ መድረስ ባለበት ደረጃ እንዳልተጓዘ የሚናገሩ አሉ፡፡

በተለይ በቅርቡ የእርሻ ኢንቨስትመንት በበርካታ ችግሮች በመተብተቡ፣ ችግሮቹን ለይቶ ምላሽ ለመስጠት ያስችላል የተባለ ጥናት ተዘጋጅቷል፡፡

በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ ሚኒስትር አቶ ዓለማየሁ ተገኑ የሚመራ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች የተካተቱበት ቡድን ተቋቁሞ ጥናት አካሂዷል፡፡

ይህ ጥናት ከየካቲት 14 ቀን እስከ ግንቦት 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ድረስ የተካሄደ ሲሆን፣ በአጠቃላይ 63 ገጾች አሉት፡፡

ጥናቱ ሰባት ጉዳዮች ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ ከእነዚህ ነጥቦች መካከል የባለሀብቶች የቀረጥ ነፃ ታክስ ተጠቃሚነት፣ የባንክ ብድር አሰጣጥ፣ መሬት ማዘጋጀትና ማስተላለፍ፣ መልካም አስተዳደርና ኪራይ ሰብሳቢነት የሚሉት ይገኙበታል፡፡

ጥናቱ በፌዴራል ደረጃ እንዲሁም ለብቻው በጋምቤላ ክልል ላይ ያተኮረ ነው፡፡ በተለይ የችግሮች ሁሉ ማጠንጠኛ የሆነው የጋምቤላ ክልል ሲሆን፣ በርካታ የአገር ውስጥና የውጭ ኩባንያዎችም በዚሁ ክልል የሚገኙ ናቸው፡፡ ችግሮቹም ውስብስብና ለመፍታትም ጊዜና  ጥናት የሚፈልጉ ናቸው ተብሎ ለዘርፉ የሚቀርበው ብድር እንዲቆም መደረጉም ይታወሳል፡፡

ጥናቱ ቅዳሜ ታኅሳስ 15 ቀን 2009 ዓ.ም. በግዮን ሆቴል ለውይይት ቀርቦ ነበር፡፡ በዚህ ጥናት በርካታ የእርሻ ዘርፍ ኢንቨስተሮች ደስተኞች አልነበሩም፡፡ ለውይይት በቀረበው በዚህ ጥናት ከተበሳጩ ባለሀብቶች መካከል አቶ ኪሮስ በርሄ፣ አቶ ሙላይ አዲሱና አቶ አብረሃሌ ይህደግ ይገኙበታል፡፡

እነዚህ ሦስት ባለሀብቶች በጋምቤላ ክልል በእርሻ ሥራና በተለያዩ ኢንቨስትመንት መስክ የተሰማሩ ናቸው፡፡ ሁለቱ ባለሀብቶች በጥናቱ ውስጥ ባልተገባ ሁኔታ ስማችን ተነስቷል በሚል ተቃውመዋል፡፡ ባለሀብቶቹ የጥናቱን ውጤትም እንደማይቀበሉት ገልጸዋል፡፡ አቶ አብረሃሌ በበኩላቸው ለሠሩት ሥራ ሽልማት ሲጠብቁ የጅምላ ወቀሳ መቅረብ አግባብ አለመሆኑን ይተቻሉ፡፡      

አቶ ኪሮስ በ2001 ዓ.ም. በጋምቤላ ክልል ፒኝዶ ወረዳ ጎግ ቀበሌ 1,000 ሔክታር መሬት ተረክበው ወደ ሥራ እንዲገቡ፣ ለዚህ እርሻ ሥራ 12.5 ሚሊዮን ብር ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በትግራይ ክልል የሚገኙ ንብረቶቻቸውን በማስያዝ መበደራቸውን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

አቶ ኪሮስ በጥናቱ ስማቸው የተነሳው ከብድር ጋር አይደለም፡፡ ገንዘቡን የራሳቸውን ንብረት አስይዘው የተበደሩት በመሆኑና እስካሁንም ዕዳቸውን እየከፈሉ መሆኑን ይናገራሉ፡፡

አቶ ኪሮስ በጥናቱ ስማቸው የተነሳው ከቀረጥ ነፃ መብት ተጠቅመው መጠኑ ያልተገለጸ (ሪፖርተር ባለው መረጃ 498.7 ሜትሪክ ቶን) የአርማታ ብረት አስገብተዋል፡፡ ነገር ግን ጥናቱ በሚካሄድበት ወቅት በእርሻ ቦታው ብረቱ የለም የሚል ነው፡፡

አቶ ኪሮስ ለሪፖርተር እንደሚገልጹት፣ እሳቸው በአድዋ ከተማ ባለአራት ኮከብ ሆቴል እየገነቡ ይገኛሉ፡፡ ብረቱን ያስገቡት በሆቴል ዘርፍ የሚሰማሩ ድርጅቶች የቀረጥ ነፃ መብት የሚሰጣቸው በመሆኑ፣ ይህንን መብታቸውን ተጠቅመው ብረት ማስገባታቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹ለእርሻ ሥራ ብረት አላስገባሁም፡፡ መንግሥትስ ለእርሻ ሥራ ብረት ከቀረጥ ነፃ ይፈቅዳል ወይ?›› ሲሉ አቶ ኪሮስ ጥናቱ ሆን ተብሎ መንግሥትን ከግለሰብ ጋር ለማጋጨት ያለመ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ሥራዬን የማከናውነው በአንድ የግብር ከፋይ ቁጥር ነው፡፡ ጉዳዩን ለያይተው ማየት አለባቸው፤›› ሲሉ አቶ ኪሮስ ይናገራሉ፡፡

‹‹ብረቱ በእርሻ ስም የገባ ነው የተባለው ሐሰት ነው፡፡ ብረቱ ለሆቴል ሥራ ያስገባሁት መሆኑ መታወቅ አለበት፤›› ሲሉ አቶ ኪሮስ ተከራክረዋል፡፡

አቶ ሙላይም በተመሳሳይ ስማቸው በጥናቱ ውስጥ ተጠቅሷል፡፡ በጥናቱ ውስጥ አቶ ሙላይ አዲሱ በኢታንግ ልዩ ወረዳ 54 ፒክአፕ ተሽከርካሪዎች፣ አራት ሎደሮችና ስድስት ሲኖትራኮች ከቀረጥ ነፃ ማስገባታቸውን ጥናቱ ገልጾ፣ በመስክ ላይ የተገኘው ግን አንድ ፒክአፕ ብቻ መሆኑን አክሏል፡፡

ነገር ግን አቶ ሙላይ ይህን አይቀበሉትም፡፡ አቶ ሙላይ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ሙላይ አዲሱ አስመጪና ላኪ በሚል የንግድ ስያሜ ሥር በአራት ዘርፎች ሥራዎችን ይሠራሉ፡፡ እነዚህም እርሻ፣ የተለያዩ ተሽከርካሪዎችንና የኮንስትራክሽን መሣሪያዎችን ከውጭ ማስገባት፣ የተለያዩ የቅባት እህሎች፣ ጥራጥሬዎችና ቅመማ ቅመሞችን ወደ ውጭ መላክና የኮንስትራክሽን ዘርፎች ናቸው፡፡

አቶ ሙላይ ጨምረው እንደገለጹት፣ በርካታ ፒክአፖችን ወደ አገር ያስመጡት ʻቦንድድ ዌርሃውስʼ በመጠቀም ነው፡፡ የቀረጥ ነፃ መብት ያላቸው ባለሀብቶች ሙሉ መረጃ ሲያቀርቡ ይህን ግብይት ይፈጽማሉ ይላሉ፡፡

‹‹ነገር ግን አጥኚው ቡድን በቂ መረጃ ሳይዝ ስማችንን በአደባባይ ማንሳቱ አግባብ አይደለም፡፡ መልካም ስምን የሚያጎድፍ ነው፤›› ሲሉ የተናገሩት አቶ ሙላይ፣ ‹‹ጥናቱም ጥያቄ ውስጥ ይጥላል፤›› ሲሉ አክለዋል፡፡

‹‹የእርሻ ሥራውንም አስመጪነቱንም በአንድ የግብር ከፋይ ነው የምንሠራው፡፡ ተለያይቶ መቅረብ ነበረበት፤›› ሲሉ አቶ ሙላይ ተናግረዋል፡፡

በጋምቤላ ክልል ያሉ ወረዳዎች ለግብርና ኢንቨስትመንት ሜካናይዜሽን በእጅጉ ምቹ መሆናቸውን ጥናቱ ይገልጻል፡፡ ነገር ግን ወረዳዎች ምቹ የመሆናቸውን ያህል ከጥቂቶች በስተቀር ባለሀብቶቹ ከወሰዱት መሬት ጋር ተመጣጣኝ የሆነ የእርሻ መሣሪያዎች እንደሌለው ጥናቱ ጨምሮ ይገልጻል፡፡

ከዚህ በመነሳት መንግሥት ባለሀብቶቹን ለማበረታታት የተለያዩ የማበረታች ፖሊሲዎች ያዘጋጀ ሲሆን፣ በተለይ የቀረጥ ነፃ መብት በመፍቀዱ የተለያዩ የእርሻ መሣሪያዎችንና ተሽከርካሪዎችን እንዲያስገቡ ፈቅዷል፡፡

‹‹የታክስ ቀረጥ ማበረታቻ ደንብ ላይ በግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ለሚሰማሩ አልሚዎች ምን ምን እንደሚያስገቡ የሚያመላክት ሲሆን፣ ከተሽከርካሪ በስተቀር አፈጻጸም የተዘጋጀለት ባለመሆኑ ለኪራይ ሰብሳቢነት የተመቻቸ ሁኔታ እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል፤›› ሲል ጥናቱ የቀረጥ ነፃ መብት ላልተገባ ድርጊት ምቹ ሁኔታ እንዲፈጠር ማድረጉን አመልክቷል፡፡

በጋምቤላ ክልል ከሚገኙ 623 ባለሀብቶች ውስጥ 200 ለሚሆኑት የባንክ ብድር ተፈቅዷል፡፡ ለመሬት ልማት፣ ለካምፕ ግንባታ፣ ለተሽከርካሪ፣ ለማሽነሪ፣ ለሥራ ማስኬጃና ለሌሎች ወጪዎች በድምሩ 4.96 ቢሊዮን ብር ብድር ተፈቅዷል፡፡

ከዚህ ውስጥ ለተሽከርካሪና ለማሽነሪ 784,147 ሚሊዮን ብር መለቀቁን ጥናቱ አመልክቷል፡፡ ‹‹ነገር ግን የተለቀቀው ገንዘብ ሙሉ ለሙሉ ለታለመለት ዓላማ አልዋለም፤›› ሲል ይገልጻል፡፡  

‹‹በጋምቤላ ክልል 623 ባለሀብቶች 630,518 ሔክታር መሬት ተረክበዋል፡፡ ከዚህ ውስጥ እስካሁን ማልማት የሚጠበቅባቸው 405,572.84 ሔክታር ነበር፡፡ ʻነገር ግን የለማው መሬት መጠን 64,010,62 ሔክታር ብቻ (15.78 በመቶ) ነው፤›› ሲል ጥናቱ ገልጿል፡፡

369 ባሀብቶች ማልማት ያልጀመሩ መሆናቸውን፣ ከእነዚህ ውስጥ 140 ምንጣሮ መጀመራቸውን ይገልጻል፡፡ ወደ ልማት ከገቡት 254 ባለሀብቶች ውስጥ 216 በውላቸው፣ 38 ከውል ውጪ ያለሙ እንደሆኑ በመግለጽ ጥናቱ በዘርፉ የሥራ አፈጻጸም ደካማነት እንደሚታይ አስረድቷል፡፡

ነገር ግን አቶ አብረሃሌ ይህን አይቀበሉትም፡፡ አቶ አብረሃሌና ወንድሞቹ እርሻ ልማት ኩባንያ በጋምቤላ ክልል ኢታንግ ልዩ ወረዳ 2,000 ሔክታር መሬት በ2001 ዓ.ም. እንደተረከበ ይገልጻሉ፡፡

አቶ አብረሃሌ በስማቸው በ2002 ዓ.ም. 1,000 ሔክታር መሬትም ተረክበዋል፡፡ ‹‹በተረከብነው መሬት ላይ ጥጥ፣ ሰሊጥ፣ ማሾ፣ ማሽላ፣ በርበሬና በቆሎ አልምተናል፡፡ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የተረከብነውን መሬት ብናለማም አጥኚ ቡድኑ በእርሻችን ተገኝቶ የሰጠን ደረጃ ቢ ነው፡፡ ይህ እንዴት ይሆናል? ደረጃ ከመስጠቱ በፊት እኔ የእርሻዎቹ ባለቤት ልጠየቅ አይገባም ወይ?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ 

አቶ አብረሃሌ ጨምረው እንደገለጹት፣ 13 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን መስክ በማልማታቸው የጋምቤላ ክልልና ሕዝብ ተባባሪዎች ነበሩ፡፡ የጋምቤላ ክልል አመራሮችም ደስተኞች እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡

የጋምቤላ ክልል የእርሻ ኢንቨስተሮች ኅብረት ሥራ ማኅበር ፕሬዚዳንት አቶ የማነ ሴፉ ጥናቱ ችግር ያለበት እንደሆነ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

‹‹ከጅምሩ የጥናቱ ቡድን ሲዋቀር የባለሀብቶች ወኪል ባለመካተቱና የአንድ ወገን ጥናት በመሆኑ የተሟላ ጥናት ነው ብሎ ለመውሰድ እንደማይቻል ሊታወቅ ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

‹‹በጥናት ቡድኑ መካተት አለብን ብለን ተደጋጋሚ ጥያቄ ለሚመለከተው አካል በተለይ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ደብዳቤ ብናስገባም ሰሚ አላገኘንም፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡

‹‹ጥናቱ ማተኮር የነበረበት የውጭና የአገር ውስጥ ባለሀብቶች የወሰዱትን የመሬት መጠን፣ የብድር መጠን፣ ያለሙትን መጠን፣ ብድር የወሰዱና ያልወሰዱትን ለይቶ ማቅረብ ላይ ነበር፤›› ሲሉ የገለጹት የማኅበሩ ፕሬዚዳንት አቶ የማነ፣ ‹‹ገና ወደ ሥራ ያልገቡ አንድ ዓመት ካልሞላቸው አዳዲስ አልሚዎች ጋር ቀላቅሎ ማቅረብ ተገቢ አይደለም፡፡ ካሉት 623 ባለሀብቶች 194 የአገር ውስጥ ባለሀብቶች ብቻ ብድር መውሰዳቸው ተለይቶ መቅረብ ይገባው ነበር፤›› ሲሉም አስረድተዋል፡፡

ልማት ባንክ ከሰጠው 4.9 ቢሊዮን ብር ብድር ውስጥ የአገር ውስጥ ባለሀብቶች የወሰዱት 1.9 ቢሊዮን ብር መሆኑን፣ ከዚህ ውስጥ 30 በመቶ የባለሀብቱ የግል መዋጮ እንደሆነ ጥናቱ ሊያሳይ ይገባ እንደነበር አቶ የማነ ይናገራሉ፡፡ የተቀረው ሦስት ቢሊዮን ብር በጋምቤላ ያሉ ስድስት የውጭ ባለሀብቶች ድርሻ መሆኑን ጥናቱ ሊያረጋግጥ ይገባ እንደነበርም ገልጸዋል፡፡

የልማት ባንክ ተበዳሪ የሆኑ 194 የአገር ውስጥ ባለሀብቶች ማልማት የሚጠበቅባቸው 54,179 ሔክታር ሆኖ እያለ፣ ብድር ያልወሰዱትንና በረዥም ጊዜ ሊያለሙ የተረከቡትን መሬት በጅምላ በማስላት አላለሙም ብሎ ማቅረብ አደናጋሪ ጥናት ሊያስብል እንደሚችልም አቶ የማነ ገልጸዋል፡፡

ብድር ከወሰዱት መልማት ያለበት 54,179 ሔክታር መሬት ከ51,000 ሔክታር በላይ መልማቱን የኢትዮጵያ ልማት ባንክ መረጃ ጠቅሰው ገልጸዋል፡፡ ‹‹ይህም ከ94 በመቶ በላይ መልማቱን ያሳያል፡፡ ይህን ሀቅ መደበቅም አይገባም ነበር፤›› ሲሉ የተናገሩት አቶ የማነ፣ የጋምቤላ የእርሻ ኢንቨስተሮች በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሆነውም ጥሩ የሥራ አፈጻጸም ማስመዝገብ መቻላቸውን ተከራክረዋል፡፡

ስድስት የውጭ ባለሀብቶች የያዙት ከ240,000 ሔክታር መሬት በላይ መሆኑን፣ የወሰዱትም ብድር ከሦስት ቢሊዮን ብር በላይ ነው፡፡ ከስድስቱ ሁለቱ ካሩቱሪና ቢኤችኤ ፈቃዳቸው መሰረዙን፣ የአብዛኛዎቹም የሥራ አፈጻጸም ደካማ እንደሆነ፣ እነዚህን የውጭ ድርጅቶች ከአገር ውስጥ ባለሀብቶች ጋር ቀላቅሎ ማቅረብ እንደማይገባ የጋምቤላ ኢንቨስተሮች ተናግረዋል፡፡

አቶ የማነ ከቀረጥ ነፃ የገቡ ተሽከርካሪዎችን በሚመለከት እንደገለጹት በብድርና ከቀረጥ ነፃ የገቡ ተሽከርካሪዎች ሰነድ (ሊብሬ) በባንክ ኮላተራል የሚያዝ መሆኑ እየታወቀ ለሦስተኛ ወገን ተላልፏል መባሉ ስህተት ነው ይላሉ፡፡

በአገሪቱ በተለይም በጋምቤላ ክልል እርሻ ኢንቨስትመንት ላይ በርካታ ችግሮች እንዳሉ በጥናቱም ታምኖበታል፡፡ ወጥ የሆነ አሠራር አለመኖር፣ አገልግሎቶች በግለሰቦች መልካም ፈቃድ ላይ የተሠረቱ መሆናቸው፣ የአንድን ባለሀብት ይዞታ ለሌላ ባለሀብት መስጠት (መሬት መደራረብ)፣ የፀጥታ ችግር፣ የፍትሕ ተቋማት አድሏዊ አሠራር፣ የአመራሮች ድጋፍ አነስተኛ መሆን፣ የመሠረተ ልማት አቅርቦት፣ የገበያ ትስስር ችግር፣ ተጠያቂነት አለመኖርና የመሳሰሉት ተጠቃሾች ናቸው፡፡  

ታኅሳስ 15 ቀን 2009 ዓ.ም. በተካሄደው ውይይት የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጋትሉዋክ ቱት እንደገለጹት፣ በአመራሩና በባለሀብቱ መካከል ያለውን ችግር ለመፍታት ጥናት ወሳኝ ድርሻ አለው፡፡

‹‹ችግሮቻችንን ሲነገረን ካልተቀበልን ችግርን መፍታት አንችልም፡፡ የጥናት ሰነዱን እንቀበላለን፤›› ሲሉ አቶ ጋትሉዋክ ገልጸዋል፡፡

‹‹የጋምቤላ የእርሻ ኢንቨስትመንት አስጨንቆናል፡፡ ትልቁ የዘርፉ ችግር የአመራሩ ነው፡፡ አመራሩ ሥራውን በአግባቡ አልሠራም፡፡ በአግባቡ ቢሠራ የመሬት መደራረብ ችግር አይፈጠርም ነበር፤›› ሲሉ አቶ ጋትሉዋክ ተናግረዋል፡፡

‹‹ጥናቱንና በጥናቱ ውስጥ የተጠቀሱትን ችግሮች በጠቅላይ ሚኒስትሩ ፊት ተቀብለናል፡፡ የመሬት ካርታ በቢሮ አይሠራም፡፡ የሚሠራው በኔትወርክ ከቢሮ ውጪ ነው፡፡ የአቅም ችግር አለ፡፡ የሙስና አመለካከት አለ፤›› ሲሉ የተናገሩት አቶ ጋትሉዋክ፣ ‹‹በዘርፉ ችግር እየፈጠሩ ያሉ አካላትን እየለየን ዕርምጃ መውሰድ ጀምረናል፤›› ብለዋል፡፡

አቶ ጋትሉዋክ ክልሉ በሕገ መንግሥቱ መሠረት ራሱን የሚያስተዳድር መሆኑን በመግለጽ፣ የእርሻ ባለሀብቶች ለክልሉ በርካታ ቁም ነገሮችን መፈጸማቸውን ዘርዝረዋል፡፡ ‹‹በፀጥታ ማስከበር፣ በመሠረተ ልማት ግንባታና በሥራ ፈጠራ ባለሀብቶች ብዙ ድጋፍ አድርገዋል፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

በተካሄደው ጥናትም ቀደም ሲል መሬት በውክልና በመግባቢያ ሰነድ ከክልሎች ተወስዶ በፌዴራል ደረጃ ለባለሀብቶች የሚሰጥበትና የሚተዳደርበት አካሄድ እንዲቀር መደረጉም ተገልጿል፡፡

በሕገ መንግሥት ከተደነገጉ መሠረታዊ ጉዳዮችና አሁን በክልሉ ካለው ተጨባጭ ሁኔታ ጋር ተያይዞ፣ የፌዴራል መንግሥት መሬት በውክልና ማስተዳደሩ በኅብረተሰቡ ዘንድ ብዥታ እየፈጠረ በመሆኑ መሬት የማስተዳደርና ለባለሀብቶች የማስተላለፍ ተግባር በክልሎች ባለቤትነት እንዲፈጸም ተወስኗል፡፡ በዚህ መነሻነት የፌዴራል መንግሥት በዚህ ረገድ የክልሎችን አቅም የመገንባት ተቀናጅቶና ተባብሮ ኢንቨስትመንቱ የተሳለጠ የማድረግ ሥራ እንዲሠራ፣ የክልሉ መንግሥት በክልሉ ውስጥ ያለው የተዘበራረቀ፣ ግልጽነት የጎደለውና ተጠያቂነት በሌለበት ሁኔታ የሚፈጸመውን የመሬት ማስተላለፍና የይዞታ ካርታ አሰጣጥ ሁኔታ ከሚመለከታቸው የፌዴራል መሥሪያ ቤቶች ጋር በመቀናጀት ጠንካራ የአሠራር ሥርዓት እንዲዘረጋ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ባሉበት በተካሄደ ስብሰባ ላይ መወሰኑ ታውቋል፡፡

መሬት የማስተዳደር ሥራ ከፌዴራል መንግሥት ወደ ክልሎች እንዲሸጋገር መደረጉ ባለሀብቶችን ያስደሰተ ሲሆን፣ የተዘጋጀው ጥናት የአንድ ወገን በመሆኑ ማሻሻያ እንዲደረግበት ባለሀብቶቹ ጠይቀዋል፡፡

የጥናት ሰነዱ በቋሚነት የሚያገለግል በመሆኑ፣ ባለሀብቶች የሚያነሷቸው ጠቃሚ ሐሳቦች ቢካተቱ ችግሮችን ፈትቶ የሚፈለገውን ልማት ለማምጣት አመቺ ሁኔታ እንደሚፈጥር አቶ የማነ ገልጸዋል፡፡

በእርሻ ኢንቨስትመንት ዘርፍ ያሉ ችግሮች አገሪቱን ዋጋ እያስከፈሉ እንደመሆናቸው፣ ችግሮቹን በመፍታት የግብርና ዘርፍን ማሳደግ የፌዴራል መንግሥትን ቁርጠኝነት እንደሚፈልግ እየተገለጸ ነው፡፡                  

 

Standard (Image)

የቀዝቃዛው ፖለቲካ ቀዝቃዛ ተቃውሞ

$
0
0

የዛሬ 25 ዓመት ኢሕአዴግ ሥልጣን ላይ ከወጣ ጊዜ ጀምሮ የመቃወም መብት በመርህ ደረጃ የተከለከለ አይደለም፡፡ በተግባር ግን መቃወም ያለ ብዙ ዋጋ የሚፈጸም እንዳልሆነ በርካታ አብነቶች ይቀርባሉ፡፡

የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት በ1987 ዓ.ም. ሲረቀቅ ለመቃወም ዋና የመሠረት ድንጋይ የጣለው በነፃነት የማሰብ፣ የተለየ ሐሳብ የመያዝ፣ የተለየን ሐሳብ በነፃነት የማራመድ፣ የመደራጀትና መብትና ተያያዥነት ላላቸው ሌሎች መብቶች ዋስትና የሚሰጥ ነው፡፡

በዚህም መሠረት የተቃውሞ ሐሳቦች በተለይ በተለያዩ የግል ሚዲያዎች ከመግለጽ ጀምሮ፣ በ1997 ዓ.ም. በመንግሥት ሥልጣን ለውጥ ለማምጣት ተቃርበው ነበር፡፡ የምርጫው እንቅስቃሴና የሕዝብ ተሳትፎ እንዲሁም የምርጫው ቅስቀሳ የፈጠረው ትኩሳት፣ የኢትዮጵያ የሩብ ዓመት ፖለቲካ ማነፃፀሪያ ሲሆን ይስተዋላል፡፡

ከምርጫው በፊት በቁጥር በርከት ያሉ ተቃዋሚዎች በርካታ ኅብረቶችና ጥምረቶች ሲፈጥሩና ሲፈረከሱ ተስተውሏል፡፡ ቢሆንም እንደ 1997 ዓ.ም. ተቃዋሚዎች ሁለት ጎራ ለይተው ኢሕአዴግን የፈተኑበት ጊዜ አልነበረም ለማለት ያስደፍራል፡፡ በወቅቱ ፌዴራላዊ አስተሳሰብ አራማጆች ሊሰኙ የሚችሉት ተቃዋሚ ፓርቲዎች የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ኅብረት በሚል ስያሜ በአንድ ጥላ የተቀናጁ ሲሆን፣ በአብዛኛው አሃዳዊ መንግሥት (አንድነት) አራማጆች የሚባሉ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ደግሞ ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ (ቅንጅት) በሚባል ስያሜ መሰባሰባቸው ይታወሳል፡፡ ሁለቱም የተቃዋሚ ጥምረቶች ሁለት ጎራ ከመፍጠራቸውም ባሻገር፣ የጋራ ትብብር ሲያደርጉና የአንዱን ድምፅ ሌላው እንዳይሻማ ለማድረግ ትብብር ሁሉ ፈጽመው ነበር፡፡

በአንዳንዶች በአሉታዊነት የሚነሱ መጠነኛ ችግሮች የታዩበት ቢሆንም፣ በምርጫው ውጤት ላይ ውዝግብ እስከተነሳ ጊዜ ድረስ ክስተቱ ለፖለቲካ አቅም የደረሰና የኢትዮጵያን ሕዝብ ከጫፍ እስከ ጫፍ በአገሩ ፖለቲካ ላይ በይገባኛል ስሜት እንዲሳተፍ ያነሳሳ ነበር፡፡ በእርግጥ በምርጫው ማግሥት ጥያቄ ቢነሳበትም በኢሕአዴግ በኩል የነበረው ምርጫውን ነፃና ፍትሐዊ የማድረግ ተግባራዊ ዝግጅትም የክስተቱ ዋና መሠረት ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ሆኖም የምርጫ ውጤትን መነሻ አድርጎ የተነሳው ውዝግብና ይህንን ተከትሎም በመሪዎች ላይ የተወሰደው የማሰር ዕርምጃ፣ በተለይ የቅንጅት ተወካዮች ፓርላማ አለመግባትና የአዲስ አበባ አስተዳደርን አለመረከብ ተፈጥሮ በነበረው የዴሞክራሲ ጭላንጭል ላይ አሉታዊ ጥላ አጥልቶበታል፡፡

ነገሩ በይቅርታ ያለቀ ቢመስልም፣ በዚሁ አወዛጋቢ ምርጫ ማግሥት የተወሰዱ አስተዳደራዊና ሕጋዊ ዕርምጃዎች በብዙ ዘንድ ሁኔታው ወደኋላ የሚመለስ እንዳይሆን ተሰግቶ ነበር፡፡   

በኢትዮጵያ የተቃውሞ ፖለቲካ ተሳትፎና ትንታኔ ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የኢዴፓ እንዲሁም የቅንጅት መሥራች አቶ ልደቱ አያሌው በተለያዩ ጊዜያት በሰጧቸው አስተያየቶች፣ የኢትዮጵያ የተቃውሞ ፖለቲካ በውስጠ ዴሞክራሲ ዕጦት የተተበተበና የሐሳብ ልዩነት የማይስተናገድበት፣ እንዲሁም በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዕርዳታ ላይ የተመሠረተና በራሱ የአገር ውስጥ አቅም ላይ ያልተመሠረተ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡

የመገናኛ ብዙኃንና የመረጃ ነፃነት አዋጅ፣ የማኅበራትና የበጎ አድራጎት ድርጅቶች አዋጅ፣ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅና የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ በከፍተኛ ሁኔታ ይተቻሉ፡፡ የማኅበራትና የበጎ አድራጎት ድርጅቶች አዋጅና የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ በተለይ የኢትዮጵያን የተቃውሞ ፖለቲካን በገንዘብም ሆነ በሐሳብ ጽንፈኛ ተብሎ ከሚፈረጀው ዳያስፖራ ለማላቀቅ የረዳ ቢመስልም፣ በራሱ በሁለት እግሩ የሚቆም ሕጋዊ የተቃዋሚዎች ኅብረትና ጥምረት እንዳይኖር ከፍተኛ ድርሻ መጫወቱን ብዙዎች ብዙ ብለውበታል፡፡

የመከለስ አዝማሚያ

በግንቦት ወር 2007 ዓ.ም. የተካሄደው አምስተኛ ጠቅላላ ምርጫ ሁለት ተቃራኒ ውጤቶች አስከትሏል፡፡ ኢሕአዴግ ሥልጣን ከያዘ ጀምሮ ባለፉት 25 ዓመታት፣ የፓርላማ ውክልና ሙሉ ለሙሉ ማግኘቱ የተገለጸበት የመጀመርያው ክስተት ነው፡፡ በኢሕአዴግ ትንታኔ መሠረት ውጤቱ የተገኘው አስተሳሰቡ በሕዝቡ ውስጥ በመስረፁ ነው፡፡ የምርጫው ውጤት ይፋ ሆኖ ኢሕአዴግ መንግሥት በመሠረተ በጥቂት ወራት ውስጥ ግን በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ተቃውሞና አመፅ ተቀስቅሷል፡፡

የአዲስ አበባ ዙሪያና ኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላንን መሠረት ያደረገው በኦሮሚያ አካባቢ የተነሳው ተቃውሞ ለአንድ ዓመት የዘለቀ ሲሆን፣ ወደኋላም በአገሪቱ ሁለተኛው ትልቁ ክልል ወደሆነው አማራ ክልል ቀጥሏል፡፡ ከዚህ በፊት የ1997 ዓ.ም. ምርጫ ውጤት ተከትሎ የተነሳው ተቃውሞን ጨምሮ መንግሥት አንዳንድ ተመሳሳይ ተቃውሞዎችን ያስተናገደ ቢሆንም፣ ይኼኛው አመፅ የተነሳበት አካባቢ ብዛትና የቆየበት ጊዜ ግን ከሌላው ወቅት የተለየ ነበር፡፡

በአገር ውስጥ በሕጋዊነት የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚዎች የዳር ታዛቢ የሆኑበት ይህ አመፅ፣ በአብዛኛው በመንግሥት በአክራሪነት የሚፈረጁ የውጭ ኃይሎች የተቆጣጠሩት ነበር፡፡ እንደ መሣሪያ ሆኖ በዋናነት ያገለገለውም ማኅበራዊ ሚዲያ በተለይም ደግሞ ፌስቡክ ነበር፡፡ የአገር ውስጥ ተቃዋሚዎች ተቃውሞው በሰላማዊ መንገድና በሰከነ መንፈስ እንዲፈታ ጥያቄ ከማቅረብ ውጪ ተሳትፎአቸው እስከዚህም ነበር፡፡ አመፁ ያስከተለው ቁሳዊ ውድመትና የሕይወት መጥፋት ግን ከመቼውም ጊዜ በላይ ከፍተኛ ነበር፡፡ በዚህም ደረጃ ኢሕአዴግ ሁኔታውን እንደገመገመ የገለጸ ሲሆን፣ በመንግሥትም በድርጅትም ደረጃ ራሱን ለመፈተሽ ቃል መግባቱም ይታወሳል፡፡

ከዚህ አንፃር የሕዝብን ቀልብ የሳበው የፕሬዚዳንቱ የመስከረም 30 ቀን 2009 ዓ.ም. የሁለቱ ምክር ቤቶች የሥራ ዘመን መጀመሪያ የጋራ ጉባዔ የመክፈቻ ንግግር ሲሆን፣ መንግሥት ዘርፈ ብዙ የፖለቲካ ማሻሻያዎች ለማድረግ መወሰኑን ያበሰረ ነበር፡፡ በተለይ ደግሞ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በፓርላማው ለማሳተፍ የምርጫ ሥርዓቱን ለመከለስ የተገባው ቃል በይበልጥ የሕዝቡን ቀልብ የሳበ ነበር፡፡ ኢሕአዴግ ምርጫው ችግር እንደነበረበት በግልጽ ባያምንም፣ ተቃውሞው የኢኮኖሚ ጥያቄ ብቻ ሳይሆን የሥርዓት ተቃውሞም ጭምር እንደሆነ አምኗል፡፡

በኢሕአዴግ ንድፈ ሐሳብ መተንተኛ መጽሔት አዲስ ራዕይ የመስከረም - ጥቅምት 2009 ዓ.ም. ዕትም ላይ ለቀውሱ መነሻ ሦስት መሠረታዊ ነገሮችን በመነሻነት ያስቀምጣል፡፡ እነዚህም የውስጥ ዴሞክራሲ መላላትና በአድርባይነት እየተተካ መምጣት፣ ሥልጣን የሕዝብ ማገልገያ መሆኑ ቀርቶ ለግለሰብ ጥቅም መዋሉ፣ እንዲሁም ዕድገቱን ተከትሎ የሕዝቡ በተለይ ደግሞ የወጣቶች ፍላጎት መጨመር ናቸው፡፡

‹‹በመናናቅና በጥላቻ ላይ የተመሠረተ አስተሳሰብ ቀላል በማይባል ደረጃ ጉዳት ሲያደርስ ተመልክተናል፤›› ይላል፡፡ ቀጥሎም ‹‹ለጽንፈኛ አፍራሽ ፖለቲካ ዘመቻ ምቹ ሁኔታ የተፈጠረው በሌላ ሳይሆን ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ጉዟችን ካጋጠመው መደነቃቀፍ ጋር ተያይዞ ነው፤›› በማለት ʻአፍራሽና ጽንፈኛʼ የተባለው የውጭ ኃይል የራሱ ድርጅት በፈጠረለት ምቹ አጋጣሚ የተነሳ በድል አድራጊነት ስሜት መወረሩን ይገልጻል፡፡

ተቃውሞውን ተከትሎ የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ መንግሥት ካቢኔ እንደ አዲስ የተዋቀረ ሲሆን፣ ቀደም ሲል በተቃዋሚዎች ሲቀነቀን የነበረው በምሁራን የመመራት ጥያቄ ተቀባይነት ያገኘ ይመስላል፡፡ የዶ/ር እና የፕሮፌሰር ማዕረግ ያላቸው የተወሰኑ የዩኒቨርሲቲ ምሁራንን በሚኒስትርነት ሾሟል፡፡ በድርጅቶቹም ውስጥ ራሱን እየፈተሸ ይመስላል፡፡

በተቃዋሚዎችና በአንዳንድ ምሁራን ለቀውሱ እንደ ዋና መነሻ ተደርጎ የሚነሳው የልማታዊ መንግሥት ርዕዮተ ዓለም ወይም የልማት ሞዴል፣ እንዲሁም የአውራ ፓርቲ ሥርዓትን ግን ከፕሮግራሙ ያስወጣው አይመስልም፡፡ ቀውሱንም ድርጅቱ ሲተነትነው ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መንግሥት በትክክል ባለመፈጸሙ ምክንያት እንጂ፣ የመስመር ችግር ተደርጎ አልተወሰደም፡፡ በተደጋጋሚ ጊዜያት እንደሚያቀርበው ‹‹የአፈጻጸም ችግር››ን ከመጥቀስ ባሻገር ገዥው ፓርቲ የሚያራምደው መስመር አገር ውስጥ በሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚዎች ላይ ያስከተለውን ጉዳት የተመለከተ ወይም ለመመልከት ፍላጎት ያለው አይመስልም፡፡ የምርጫ ሥርዓቱን ለማሻሻል የተነሳበት ምክንያትና ተቃዋሚዎችን በፓርላማ ለማሳተፍ ድርጅቱ የወሰነበት ምክንያትም በዚህ ሰፊ ትንታኔው ላይ አልተካተተም፡፡

ተቃዋሚዎች ምን ይሠራሉ? 

በምርጫ ቦርድ የተመዘገቡ ሕጋዊ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ቁጥር ወደ 60 የሚጠጋ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ድምፃቸው የሚሰማውና በተለይ በምርጫ ወቅት በንቃት የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚዎች ግን ጥቂቶች ናቸው፡፡ በቅርቡ በተነሳው ተቃውሞና አመፅም የዳር ተመልካች መሆናቸው በግልጽ ታይቷል፡፡ በአገሪቱ ያሉ ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከምርጫ ውጪ በውስጣዊ ልዩነት ሲወዛገቡ መታየታቸው፣ አልያም አምስት ዓመት ሙሉ ድምፃቸውን አጥፍተው ለምርጫ ብቅ ማለታቸው አዲስ ነገር አይደለም፡፡

‹‹ምርጫ የአምስት ዓመት እንቅስቃሴ የሚቋጭበት ወቅት ነው፤›› የሚሉት የአረና ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ ገብሩ አሥራት ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በነፃነት እንዳይንቀሳቀሱ እክል የፈጠረባቸው ቢሆንም አባላቶቻቸውን በማደራጀት፣ ገንዘብ በማሰባሰብና የተለያዩ ውይይቶችን በማድረግ እንደሚያሳልፉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በአገሪቱ የተከሰተው ቀውስ የሥርዓቱ ውጤት መሆኑን የሚያምኑት አቶ ገብሩ፣ ምኅዳሩን የሚያሻሽሉ ዕርምጃዎች ቢወሰዱ በተቃዋሚዎች እንቅስቃሴ ላይ የሚታየውን ክፍተት መሙላት ይችላል የሚል ሐሳብ አላቸው፡፡ ኢሕአዴግ ከተቃዋሚዎች ጋር አብሮ ለመሥራት ያነሳው ሐሳብም ከዚህ በፊት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምክር ቤት አባል የሆኑና ያልሆኑ የሚለውን ቅድመ ሁኔታ ያስቀራል የሚል ተስፋ አላቸው፡፡

ከሦስት ዓመታት በፊት ከአንድነት ፓርቲ ለቀው የወጡት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ከፓርቲ ፖለቲካ ራሳቸውን ካገለሉ ቆይተዋል፡፡ እሳቸው በአንድነት ፓርቲ ውስጥ ሳሉ የውስጥ ውይይት ይደረግ ነበር፡፡ ነገር ግን አዳራሽ ለማግኘት፣ ሰላማዊ ሠልፍ ለማድረግና የድርጅቱን ልሳን ለማሳተም ይደረግ የነበረው እንቅስቃሴ ከመንግሥት በሚመጣ ጫና ከባድ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡

ያም ሆነ ይህ መንግሥት ከተቃዋሚዎች ጋር በጋራ ለመሥራት ያቀረበው ጥሪ አፍዓዊ ሆኖ እንዳይቀር ያሳስባሉ፡፡ ተቃዋሚዎች በተለይ ከመንግሥት ጋር አብረው ቢሠሩ አገሪቱ የተሻለ እንደምትጠቀምም ይገልጻሉ፡፡ መንግሥት ለማሻሻል ያቀደው የምርጫ ሕግ ላይ የራሳቸውን ሐሳብ እንዲያንፀባርቁ፣ እንዲሳተፉና የባለቤትነት ስሜት እንዲሰማቸው ሊደረግ ይገባል ይላሉ፡፡ ‹‹የምርጫ ሥርዓቱ ችግር ምን እንደሆነ ከተቃዋሚዎች በላይ የሚያውቀው የለም፤›› ያሉት ዶ/ር ነጋሶ፣ ጥሪው ለይስሙላ ሳይሆን የተቃዋሚዎች ድምፅ በግልጽ በሚዲያ ለሕዝብ እንዲቀርብና በገዥው ፓርቲም ሐሳባቸው እንዲደመጥ ይጠይቃሉ፡፡ ምናልባትም በቀጣዩ ምርጫ ትርጉም ያለው ተሳትፎ እንዲያደርጉ ይረዳቸዋል የሚል አቋም አላቸው፡፡

‹‹ሥርዓቱ ከአገዛዝ ወደ ዴሞክራሲ አልተሸጋገረም፤›› የሚል አቋም ያላቸው የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት በበኩላቸው፣ ተቃዋሚዎች በምርጫ ወቅት ብቻ እንዲንቀሳቀሱ የሚያደርጋቸው ኢሕአዴግ ራሱ እንደሆነ ይከራከራሉ፡፡ በተለይ ሚዲያን በእኩልነት ለመጠቀም እንዳይችሉ መንግሥት ገደብ ማድረጉ ትልቅ ችግር እንደፈጠረ ያስገነዝባሉ፡፡ እንደ እሳቸው እምነት ኢሕአዴግ ተቃዋሚዎች እንዲኖሩ የሚፈልጋቸው በምርጫ እንዲያጅቡትና ቅቡልነትን እንዲያገኝ ብቻ ነው፡፡

የኢትዮጵያ የፖለቲካ ባህል ቀኖናዊ (የሃይማኖት መልክ ያለው) እንደሆነና አጀማመሩም በማርክሳዊ አስተሳሰብ በጠላትነትና በወዳጅነት ላይ የተመሠረተ እንደሆነ ያምናሉ፡፡ ‹‹እኛም ከዚህ ሕዝብ ነው የተቀዳነው፤›› የሚሉት ኢንጂነር ይልቃል፣ መከፋፈልና የውስጥ ዴሞክራሲ ችግር የተቃዋሚዎች ባህሪ ብቻ እንዳልሆነ ይሞግታሉ፡፡ ኢሕአዴግም ውስጥ ችግሩ እንዳለ ነገር ግን በሥልጣንና በጉልበት ስለሚፈታው እምብዛም አይታይም ይላሉ፡፡ ከሌሎች ጋር አብሮ የመሥራትና የመተባበር መንፈስ የአንድ ፓርቲ ዋና ዓላማ አለመሆኑንና የጎንዮሽ ሥራ እንደሆነ ያምናሉ፡፡

የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሁኔታ በ‹‹ጠላት››ና በ‹‹ወዳጅ››፣ በ‹‹እኛ›› እና በ‹‹እነሱ›› ጎራዎች የሚገለጽ መሆኑን የሚናገሩት ኢንጂነሩ፣ ከዚህ ባህል በመውጣት የሠለጠነ ፖለቲካ ለማራመድ ፓርቲያቸው አዲስ አስተሳሰብና ወጣቶችን ማዕከል ያደረገ አካሄድ እንደሚከተል ይናገራሉ፡፡ ‹‹የተለየ ሐሳብ የያዘ ሰው የማጥፋት ባህል መቅረት አለበት፤›› ሲሉም ያጠቃልላሉ፡፡

ቀዝቃዛ ተቃውሞ

የ1997 ዓ.ም. ምርጫን ተከትሎ በተወሰዱ ዕርምጃዎችና በራሳቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎች የውስጥ ችግር ምክንያት የተቃውሞው ኃይል ከ1998 ዓ.ም. ጀምሮ መቀዛቀዝ ታይቶበታል፡፡ ʻፖለቲካን እንደ ኮረንቲʼ የመፍራት ባህልም ደግሞ እንዳገረሸ የሚያምኑ በርካቶች ናቸው፡፡

የቅንጅት መሪዎችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ከታሰሩ በኋላ የተፈጠረው አስፈሪ ድባብ፣ ታሳሪዎች በይቅርታ በመፈታታቸው ያሻሽለዋል ተብሎ ተገምቶ ነበር፡፡ የሆነው ግን ተቃራኒው ነበር፡፡ ብዙዎች ከአገር የተሰደዱ ሲሆን፣ አንዳንዶቹ ነፍጥ ማንሳታቸውን አውጀዋል፡፡ እንደ እነ ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ያሉት ፖለቲከኞች ደግሞ ከፖለቲካ ራሳቸውን አግለዋል፡፡ የተቀሩት ኃይሎችም በተለይ አንድነት፣ መኢአድና ኢዴፓ ወደ ቀድሞ ፓርቲያቸው ተመልሰው እንቅስቃሴ ቢያደርጉም ጥረታቸው ፍሬ ሲያፈራ አይስተዋልም፡፡

በምርጫ 2002 ዋዜማ ተቃዋሚ ኃይሎችን ወደ አንድ የጋራ መድረክ ለማምጣት ለአንድ ዓመት ያህል የውይይት መድረክ ተዘጋጅቶ ነበር፡፡ በእነ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ አቶ ገብሩ አሥራትና አቶ ስዬ አብረሃ የቀረቡ ጥናታዊ ጽሑፎች የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎችን ድክመቶች በግልጽ ያሳዩ ነበሩ፡፡ እርስ በእርስ መጠላለፍ፣ በጠላቴ ጠላት መርህ መተባበርና በኢሕአዴግ ጥላቻ ላይ ብቻ መቆም፣ እንዲሁም የጠራ የፖለቲካ ፕሮግራም በአማራጭነት ይዞ ያለመቅረብ የሚሉ ድክመቶች በዋነኛነት ተለይተው ነበር፡፡ እነዚህን ድክመቶች ለማረም ቆርጦ የተነሳው ስምንት የፖለቲካ ፓርቲዎችን የያዘና በብሔርና በኅብረ ብሔር የተመሠረቱ ድርጅቶች አንድ ላይ ያሰባሰበው መድረክ ግን ብዙም ሳይቆይ ውዝግብ ውስጥ መግባቱ ይታወሳል፡፡

በ2002 ምርጫ በአንድነት ፓርቲ ተወካይ መድረክ ካገኘው የአዲስ አበባ አንድ ወንበር ውጪ የተቃዋሚዎቹ ጥረት በምርጫ ውጤት አልታየም፡፡ በምክንያትነትም የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምኅዳር አላፈናፍን ማለቱ ተጠቅሶ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ በ2007 በተካሄደው ምርጫም ተቃዋሚዎች ጨርሰው ከፓርላማ የወጡ ሲሆን፣ ብዙዎቹ በኢትዮጵያ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት የመፍጠር ዕድል አደጋ ላይ መውደቁን ገልጸው ነበር፡፡ በኢሕአዴግ በኩል ግን ተቀባይነት ያለው አልነበረም፡፡

በተለያዩ የመንግሥት ባለሥልጣናት እንደሚገለጸው፣ ሁኔታው በተቃዋሚዎች ድክመት የተነሳ እንደሆነ በመተቸት ኢሕአዴግ አውራ ፓርቲ ሆኖ ለመቀጠል የቀረፀው ስትራቴጂ ድል ተደርጎ በድርጅቱ ንድፈ ሐሳብ መጽሔት ተተንትኗል፡፡ ተቃዋሚዎች ይህንን አይቀበሉም፡፡ ይልቅ ሁኔታውን በውጭ ሆነው ሥርዓቱን በነፍጥ ለመታገል ለወሰኑ ድርጅቶች መልካም ዜና እንደሆነ ተደርጎ ነበር የተገለጸው፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌዴራሊዝም ጥናት ማዕከል መምህር አቶ ናሁሰናይ በላይ የፒኤችዲ ዲግሪ ማሟያቸውን በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ተግዳሮቶች ላይ እየሠሩ ይገኛሉ፡፡ አቶ ናሁሰናይ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በአገር ውስጥ የሚገኙ ሕጋዊ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በነፃነት ለመንቀሳቀስ የሚችሉበት ምቹ ሁኔታ የለም፡፡

‹‹አብዛኞቹ በጠራ ሐሳብ ላይ የመሰባሰብና የውስጥ ዴሞክራሲ ችግር ያለባቸው ቢሆንም፣ በዋናነት ከገዥው ፓርቲ የሚደርስባቸውን ጫና መቋቋም የሚችሉት አይደለም፡፡ የፖለቲካና የገንዘብ አቅምም የላቸውም፤›› ብለዋል፡፡ በመሆኑም በአገር ውስጥ ፖለቲከኞች ቁጥጥር ሥር መሆን የነበረበት የተቃውሞ ፖለቲካ ውጭ ባሉ ሰዎች እጅ እንዲዛወር በር ከፍቷል ይላሉ፡፡ እንደ ተመራማሪው እምነት በውጭ የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች የሚዲያና የገንዘብ አቅም ያላቸው ቢሆኑም፣ የሚያራምዱት ፖለቲካ ኃላፊነት የጎደለውና በአገር ህልውና ላይ አደጋ ሊያደርስ የሚችል ነው፡፡ በዚህም ምክንያት በጫና ከሕጋዊ ተቃዋሚዎች እጅ እንዲወጣ የተደረገው የተቃውሞ ፖለቲካ ተመልሶ ወደሚመለከተው ሕዝብና በሕግና በኃላፊነት ወደሚንቀሳቀሱ የአገር ውስጥ ኃይሎች የሚመለስበት መንገድ በገዥው ፓርቲ ሊታሰብበት እንደሚገባ ዶ/ር አቶ ናሁሰናይ ያሳስባሉ፡፡

 

 

Standard (Image)

ናይል በሚዲያዎች ዕይታ

$
0
0

‹‹እ.ኤ.አ. በ2040 በውኃ እጦት የሚሰቃዩ አሥር ተቀዳሚ አገሮች የትኞቹ ናቸው?››

ጋዜጠኛና ጸሐፊው ዳንኤል ካሊናኪ ይህን ጥያቄ ያቀረበው ናይል ቤዚን ኢንሺየቲቭ (ኤንቢአይ) እ.ኤ.አ. ከታኅሳስ 12 እስከ 16 ቀን 2016 በሩዋንዳ ኪጋሊ አዘጋጅቶት ለነበረው ክልላዊ የሚዲያ ሥልጠና ተሳታፊዎች ነው፡፡ ከኤርትራ በስተቀር የኢንሺየቲቩ አባል አገሮችን የወከሉ የሚዲያ ባለሙያዎች በዝርዝሩ ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ ያሏቸውን አገሮች መጥቀስ ጀመሩ፡፡ በተለይ የግብፅና የሱዳን ጋዜጠኞች አገሮቻቸው በዝርዝሩ ውስጥ እንዳሉ እርግጠኛ የነበሩ ይመስላሉ፡፡ በኋላ ላይ ካሊናኪ ሙሉውን ዝርዝር ሲያቀርብ አንድም አፍሪካዊ አገር በዝርዝሩ አልተካተተም፡፡ ዝርዝሩ ውስጥ ያሉት አገሮች ባህሬን፣ ኩዌት፣ ፍልስጤም፣ ኳታር፣ የተባበሩት የዓረብ ኤምሬቶች፣ እስራኤል፣ ሳዑዲ ዓረቢያ፣ ኦማንና ሊባኖስ ናቸው፡፡

ከዚህ እውነታ በተቃራኒ የናይል ተፋሰስ አገሮች የሚዲያ ውጤቶችን በግርድፉ ያየ ሰው፣ በውኃ እጥረትና የናይል ውኃን በጋራ ለመጠቀም ስምምነት ባለመኖሩ የተነሳ አገሮቹ ወደ ጦርነት የማምራት ዕድላቸው ሰፊ እንደሆነ እንዲያስብ ሊገደድ ይችላል፡፡

ለዳንኤል ካሊናኪ ይህ የእውነታና የምልከታ ልዩነት መነሻ የናይል ጉዳይን ከመጠን ያለፈ የፖለቲካ ጉዳይ አድርጎ ማየትና አሉታዊ የሚዲያ ዘገባዎች ናቸው፡፡ ካሊናኪ በእነዚህ ዘገባዎች ግጭት ላይ ትኩረት እንደሚደረግ የጠቆመ ሲሆን፣ ከኤክስፐርቶች ይልቅ በርካታ ባለሥልጣናት ሽፋን እንደሚያገኙ፣ የመንጋነት ባህሪ እንደሚስተጋባ፣ እነዚህ ሚዲያዎች ወገንተኝነት የሚንፀባረቅባቸውና እውነታውን በሚያጣምሙ ጋዜጠኞች እንደሚመሩ አስገንዝቧል፡፡

በካርቱም ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ ተባባሪ ፕሮፌሰር ዶ/ር አታ ባታይኒ ከዳንኤል ካሊናኪ ጋር ተመሳሳይ የሆነ አቋም አላቸው፡፡ በቅርቡ በሱዳን ዋድ መዳኒ በናይል ላይ ተደርጎ በነበረ ዓውደ ጥናት እንደገለጹት፣ የናይል ጉዳይ ከመጠን ባለፈ የፖለቲካ ጉዳይ ሆኗል፡፡ ዶ/ር ባይታኒ፣ ‹‹ተመራማሪዎችና ምሁራን የፖለቲካ መደቡ በናይል ላይ ያለው ግንዛቤ እንዲሰፋ ማገዝ ይችላሉ፡፡ በበርካታ አገሮች የአመራር ክፍተት አለ፡፡ ዋነኛው ትኩረት የፖለቲካ መሪነትን ማስቀጠልና የአጭር ጊዜ ጥቅም ሆኗል፤›› ብለዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የውኃና መሬት ሀብት ማዕከል ዳይሬክተር ዶ/ር ጌጤ ዘለቀም በተመሳሳይ፣ ‹‹በተለመደው መንገድ መቀጠል አንችልም፡፡ የሳይንስ ማኅበረሰቡ በመውጣት የተሻሉ መንገዶችን ለፖለቲከኞቹ መንገር አለበት፤›› ብለዋል፡፡

በናይል ላይ የሚደረገው የሐሳብ ልውውጥ በፖለቲካው መደብ የበላይነት መካሄዱ የራሱ ችግር እንዳለው የገለጹት የምሥራቃዊ ናይል ቀጣና የቴክኒክ ጽሕፈት ቤት የማኅበራዊ ልማትና ኮሙዩኒኬሽን ክፍል ኃላፊ ዶ/ር ውባለም ፈቃደ፣ ‹‹የእኛ ጥረት በናይል ላይ የሚደረገውን የሐሳብ ልውውጥ በዋነኝነት ወይም በብቸኝነት የፖለቲካ ወይም የደኅንነት ችግር አድርጎ ከማየት የተፈጥሮ ሀብት ማኔጅመንት ችግር አድርጎ ወደማየት ማሻገር ነው፡፡ ጉዳዩ ከመጠን በላይ የፖለቲካ ገጽታ ሲላበስ ትክክለኛ መረጃ መጣመሙ አይቀርም፡፡ የፖለቲከኞችን መረጃ መሞገትና ስህተት ሲሆን ማስተካከል የብልህ ጋዜጠኛ ግዴታ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ለአንዳንዶች የናይልን ጉዳይ የፖለቲካ ወይም የደኅንነት ጉዳይ አድርጎ ማየት ለጉዳዩ ተገቢ የሆኑ አካላትን ከውሳኔ አሰጣጥ ሒደቱ ያገላል፡፡ በስቶኮልም ዓለም አቀፍ የውኃ ኢንስቲትዩት የድንበር ተሻጋሪ ውኃ ማኔጅመንት ክፍል ፕሮግራም ማናጀር ዶ/ር አና ካስካዎ ከእነዚህ አስተያየት ሰጪዎች የሚካተቱ ናቸው፡፡ ዶ/ር ካስካዎ፣ ‹‹የናይል ጉዳይ የፖለቲካ ጉዳይም መሆኑን መካድ አይቻልም፡፡ ነገር ግን ከዚህ የባሰው ጉዳይ የደኅንነት ጉዳይ ተደርጎ መካለሉ ነው፡፡ ይኼ ትልቅ ችግር ነው፡፡ ምክንያቱም በውሳኔ አሰጣጡ ሊሳተፉ የሚገባቸውን አካላት ይቀንሳል፤›› ብለዋል፡፡

በግብፅ የካይሮ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስና የፖለቲካ ሳይንስ ፋኩልቲ ሌክቸረር ዶ/ር ራውያ ቶፊቅ ግን በዚህ ግምገማ አይስማሙም፡፡ ዶ/ር ቶፊቅ፣ ‹‹የናይልን ጉዳይ የፖለቲካ ጉዳይ አድርጎ በማየትና የቴክኒክ ጉዳይ በማድረግ መካከል ግልጽ ልዩነትን ሁሌም ማግኘት አይቻልም፤›› ብለዋል፡፡ ዶክተሯ መንግሥታት በተፈጥሯቸው እንደ ሁኔታው በፖለቲካ ወይም በቴክኒክ ጉዳዮች ሊሳተፉ ከሚችሉ ተቋማትና ግለሰቦች እንደሚዋቀሩም አስታውሰዋል፡፡ ‹‹አንዳንዶች የትብብር አጀንዳው ላይ ለመሥራት ከፍተኛ ፍላጎት ይኖራቸዋል፡፡ ሌሎቹ ግን ያን ያህል ጉጉት ላይኖራቸው ይችላል፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡

ይሁንና ተፋሰሱን የሚገጥመው ችግር ናይልን የፖለቲካ ወይም የደኅንነት ችግር አድርጎ በማየት የተገደበ አይደለም፡፡ እንደ የውኃ ፍላጎት ማደግ፣ የሕዝብ ብዛት መመንደግ፣ የአየር ንብረት ለውጥ ያሉ ችግሮች የናይልን ህልውና ጭምር እየተፈታተኑ ስለመሆኑ የተፋሰሱ ውሳኔ ሰጪዎችና ነዋሪዎች በቂ ትኩረት አለመስጠታቸው፣ እንደ ኤንቢአይ ያሉ ክልላዊ ተቋማትን እያስጨነቀ ይገኛል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1999 ከተቋቋመ ጀምሮ ኤንቢአይ ከሚዲያ ጋር በቅርበት ይሠራል፡፡ የኪጋሊው የሚዲያ ሥልጠናም ኤንቢአይ ሚዲያው ይህን ችግር ተገንዝቦ ለተከታዮቹ ይህንኑ እንዲያሰራጭ ለማንቀሳቀስ የወሰደው የቅርብ ጥረት አካል ነው፡፡

ቁጥራቸው እያደገ ያለና አሳማኝ ማስረጃዎችን የያዙ በርካታ የጥናት ውጤቶች ይህን አደገኛ አዝማሚያ ለመቀልበስ አስቸኳይ የተቀናጀ ዕርምጃ እንደሚያስፈልግ ይደመድማሉ፡፡ በዚህም ሚዲያ ተፋሰሱ በአጭርና በረጅም ጊዜ ሊገጥም ስለሚችለው አደጋ ለሕዝቡ የማስጠንቀቅ ኃላፊነት ተሸክሟል፡፡ ሚዲያው በዚህ ኃላፊነት ለአሁኑ ብቻ ሳይሆን ለቀጣዩ ትውልድ ፍላጎት ጭምር መቆም እንዳለበትም ተመልክቷል፡፡ በሥልጠናው ላይ የቀረቡትን ጨምሮ በርካታ ጥናቶች ናይልን እየገጠሙት ያሉት በርካታ ችግሮች እየተባባሱ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ የኢንትሮ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፈቅአህመድ ነጋሽ፣ ‹‹የአካባቢ ሥነ ምኅዳሩንና የብዝኃ ሕይወት ሀብቶቻችንን በፍጥነት እያጣን ነው፤›› ብለዋል፡፡

በተጨማሪም እያደገ ከመጣውና ናይልን እየፈተኑ ከመጡ ተግዳሮቶች መካከል ከተሜነትና የኢንዱስትሪ መስፋፋት፣ እንዲሁም የድርቅ ተደጋግሞ መከሰት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በከፊል ሕዝቡን በማስተማር እነዚህን ችግሮች አገሮቹ እንዲቋቋሙ ለማድረግ ሚዲያው ኃላፊነት ወድቆበታል፡፡

የኤንቢአይ ሴክሬታሪያት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢኖሰንት ንታባና (ኢንጂነር) እንደሚገልጹት፣ የአምስት ቀናቱ የሚዲያ ሥልጠና ዓላማ የተፋሰሱ አገሮች ጋዜጠኞች ናይልን እየገጠሙ ያሉ ተግዳሮቶችና ስላሉት አቅሞችና ተስፋዎች ጥልቅ መረዳት እንዲኖራቸው ማገዝ ነው፡፡ ንታባና ይህ በተፋሰሱ ዘላቂ ትብብርን ለማስፋፋት ቁልፍ ሚና እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡

በቅርቡም ኢንትሮ ለምሥራቃዊ ናይል ጋዜጠኞች ተመሳሳይ ሥልጠና ሰጥቶ ነበር፡፡ አቶ ፈቅአህመድ ኢንትሮ በርካታ ስኬቶችን ያስመዘገበ ቢሆንም፣ እነዚህ እንቅስቃሴዎች ወደ ሕዝቡ እንዲደርሱ በሚፈለገው ደረጃ ሚዲያው ሽፋን አለመስጠቱን ተናግረዋል፡፡

ንታባናም ሆኑ አቶ ፈቅአህመድ በናይል ጉዳይ ተቀዳሚው የሚዲያ ኃላፊነት የአገሮቹን የጋራ ተጠቃሚነት በማውጣት ትብብርን ማስፋፋት እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ እስካሁን ኤንቢአይ የናይል ውኃ ሁሉንም አባል አገሮች ተጠቃሚ በሚያደርግበት መንገድና አገሮቹ እርስ በርስ መተማመንና መግባባት እንዲኖራቸው ለማድረግ በርካታ ጥረቶችን አድርጓል፡፡ እነዚህ ጥረቶች ሲደረጉ ዋናው ታሳቢ የተደረገው ነገር የናይል ወንዝ የሁሉም አገሮች የጋራ ንብረት መሆኑ ነው፡፡

‹‹የጋራ ኢንቨስትመንት ፕሮግራሞችን አዘጋጅተናል፣ ድንበር የለሽ ትንታኔ ሠርተናል፣ የአየር ንብረት ለውጥ ችግርን ለመቋቋም የሚያስችሉ ፖሊሲዎችና አሠራሮችን አዘጋጅተናል፣ የነገ ውሳኔ ሰጪ ወጣት ኤክስፐርቶችን በማሠልጠን ስለናይል የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው አድርገናል፣ ኤክስፐርቶችና ፖሊሲ አውጪዎች በበርካታ የቴክኒካዊ ጉዳዮች እንዲመክሩና ለስምምነት መሠረት እንዲጥሉ አድርገናል፣ በናይል ላይ የመረጃና የእውቀት ቋት ገንብተናል፤›› በማለት አቶ ፈቅአህመድ ኢንትሮ ከሠራቸው ውጤታማ እንቅስቃሴዎች ውስጥ ከፊሉን ዘርዝረዋል፡፡

ንታባና ኤንቢአይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ትብብር ለመፍጠር በሚያደርገው ጥረት ሚዲያ ቁልፍ አጋሩ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ግንዛቤ ለማሳደግ፣ ትኩረት የሚደረግባቸው አካላትን ተደራሽ ለማድረግና የሕዝቡን አስተያየት ለመቅረጽ ከሚዲያ የተሻለ ሌላ አካል ለማግኘት እንደማይቻልም አስገንዝበዋል፡፡

‹‹ያለሚዲያ እገዛ የናይል ትብብር ግቡን አይመታም፤›› የሚሉት ዶ/ር ውባለም በበኩላቸው፣ ሚዲያው ትብብርን ለማስፋፋት የሚያደርገውን ጥረት በራሱ ወይም ለሌሎች መድረክ በመፍጠር ሊወጣው እንደሚችል አመልክተዋል፡፡ እነዚህ ባለድርሻ አካላት የግል ቢዝነስ ዘርፉ፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ ሲቪል ማኅበራት፣ ሃይማኖታዊ ተቋማትና መሰል አካላትን እንደሚጨምሩም ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡

የሱዳን የውኃ ሀብቶች የቴክኒክ ክፍል ኃላፊና የቀድሞ የውኃ ሀብት ሚኒስትር ሰይፈልዲን አብደላ (ፕሮፌሰር) የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በናይል ላይ ላለው ትብብር የስኬት ተምሳሌት እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ­‹‹ውይይቶችና ድርድሮች በርካታ ጊዜያት መውሰዳቸው እውነት ነው፡፡ ምክንያቱም ከታሪካዊ ጉዳዮች ጋር የተቀላቀሉ በመሆኑ ቀላል አይደለም፡፡ ከባህልና ከፖለቲካ ጋር የሚያያዙ በርካታ ጉዳዮችም ከድርድሩ ጀርባ ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን በኤንቢአይ ትብብር አሁን የተሻለ ቁርጠኝነት በማሳየት ላይ በመሆናችን በትክክለኛ የትብብር አቅጣጫ ላይ እንገኛለን፤›› ሲሉ ለሪፖርተር አብራርተዋል፡፡

ሰይፈልዲን በግድቡ ጉዳይ የሱዳን ዋና ተደራዳሪም ናቸው፡፡ እንደ እሳቸው ግድቡ እንደ ሱዳን ላሉ የታችኛው ተፋሰስ አገሮች በርካታ ጠቀሜታዎች እንዳሉት በሙሉ ስሜትና መተማመን የሚገልጽ ሱዳናዊ ኃላፊ ማግኘት አይቻልም፡፡ ይህ እምነት ከየት እንደመጣ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፣ ‹‹የግድቡን ጥቅም ሁሌም የማወሳው ከቴክኒካዊ የኋላ ታሪኬ በመነሳት ነው፡፡ አብዛኞቹን የዓባይ ገባሮችና የኢትዮጵያን ተዳፋት ቦታዎች መርምሬያለሁ፡፡ ከቴክኒክ አንፃር በሦስቱ አገሮች ፍላጎቶች መካከል ተቃርኖ አላየሁም፡፡ እንዲያውም በተቃራኒው እንደሚደጋገፉ አረጋግጫለሁ፤›› ብለዋል፡፡ ሰይፈልዲን በሙያቸው የግድብ ኢንጂነር ሲሆኑ በሱዳን ግድቦች በተለያዩ ኃላፊነቶች ለበርካታ ዓመታት ሠርተዋል፡፡

የግድቡ ተፅዕኖ ግምገማ ጥናት በሒደት ላይ ይገኛል፡፡ አንዳንዶች የግድቡ ግንባታ በማለቅ ላይ ባለበት በዚህ ወቅት የተፅዕኖ ግምገማ ጥናት ላይ ድርድር የማድረጉ አስፈላጊነት ላይ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡ ይህ ጥያቄ ሰይፈልዲን ከጋዜጠኞች ከሚቀርቡላቸው ጥያቄዎች ውስጥ እጅግ የተደጋገመው ነው፡፡

‹‹በዚህ ጉዳይ ላይ ሚዲያው ያለው ግንዛቤና አረዳድ የተሳሳተ ነው፡፡ በግድቡ አካላዊ ቅርፅና እኛ እየተደራደርን ባለበት ጉዳይ መካከል ልዩነት አለ፡፡ የግድቡን ዲዛይን በተመለከተ ተነጋግረን የመፍትሔ ሐሳብም አቅርበናል፡፡ ኢትዮጵያም በቀና ልቦና ሁሉንም የመፍትሔ ሐሳቦች በተግባር ፈጽማለች፡፡ አሁን እየተደራደርን ያለነው በግድቡ የመጀመሪያ ሙሌትና ግድቡ ሥራ ላይ በሚውልበት ሁኔታ ላይ ነው፤›› ሲሉም አብራርተዋል፡፡

የሥልጠናው ተሳታፊ ኤክስፐርቶች በተፋሰሱ አገሮች መካከል አልፎ አልፎ የሚታየው ውጥረት በአብዛኛው የሚነሳው በተሳሳተ መረጃ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ትክክለኛ መረጃ እውቀት በማይኖርበት ወቅት ክፍተቱ በአላዋቂነት፣ በፍራቻ፣ በሐሜትና በመሳሰለው ሊሸፈን እንደሚችልም ጠቅሰዋል፡፡

የማንኛውም ሚዲያ ዋና ሥራ ትክክለኛ፣ እውነተኛና ተጨባጭ መረጃ መስጠት ነው፡፡ በናይል ጉዳይ ላይ የሚሠራ ሚዲያም ከዚህ አንፃር የተለየ ሚና አይኖረውም፡፡ በናይል ጉዳይ ተገቢ የሆነ ድርሻ ያላቸው አካላት ትርጉም ያለው ተሳትፎ እንዲያደርጉና የሚዲያውን አገልግሎት አጥብቀው ይሻሉ፡፡ ነገር ግን የናይል ጉዳይ ካለው ስስና አሳሳቢ ባህሪ አንፃር ሚዲያው ተጨማሪ ኃላፊነት እንዳለበት ይታመናል፡፡ ከዚህ አንፃር በተለይ ብሔራዊ ሚዲያው ስለናይል በቋሚነት ለሕዝቡ መረጃ የመስጠት፣ የማስተማር፣ የማነሳሳትና የማንቀሳቀስ ተጨማሪ ኃላፊነት እንዳለበት አቶ ፈቅአህመድ ይከራከራሉ፡፡ ዶ/ር ውባለምም በተመሳሳይ የናይል ጉዳይን ሳይንስንና ተጨባጭ ኩነቶችን ተመሥርቶ ለመጻፍ ሚዲያው ተጨማሪ ጥረቶችን ሊያደርግ እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡ ከዚህ አንፃር የኋላ ታሪክና ምርመራ ማድረግ ተፈላጊ ባህሪ እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡

እንደ ዶ/ር ውባለም ገለጻ ሚዲያው የሕዝብ ድጋፍን በማንቀሳቀስ፣ የሕዝቡን አመለካከትና አስተያየት በመቅረጽ አዋቂ፣ ብሩህና ደፋር መሪዎችን ለመፍጠር ትልቅ አስተዋጽኦ አለው፡፡ በተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች የተፋሰሱ አገሮች አንፃራዊ ተጠቃሚነትን በማጉላት ትብብር የመፍጠር ሚናም ሊኖረው እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡ የተለያዩ የናይል ባለድርሻ አካላትን በማገናኘት ድልድይ ሆኖ ሊሠራ እንደሚችልም አስገንዝበዋል፡፡ ‹‹ይሁንና ይህንን የማስተማር ሚና በአብዛኛው ሚዲያው አይወጣውም፤›› ሲሉ ዶ/ር ውባለም ምልከታቸውን አካፍለዋል፡፡

ከዚህ በተቃራኒ ሚዲያው አሉታዊ ሚና ሊጫወት እንደሚችልም ተመልክቷል፡፡ ዶ/ር ውባለም፣ ‹‹ጠባብ በመሆን፣ ልዩነቶች፣ የማይቻሉ ጉዳዮችና ቅሬታዎች ላይ በማተኮር›› ይህን አሉታዊ ሚና ሚዲያው ሲጫወተው ማየት አዲስ ነገር እንዳልሆነ ይከራከራሉ፡፡

የናይልን ጉዳይ በተመለከተ በተለይ ዓለም አቀፍ ሚዲያው ግጭት ላይ ትኩረት አድርጎ ይሠራል፡፡ ‹‹ጎጂ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ፡፡ ኤንቢአይ ከተቋቋመ ጀምሮ በርካታ ሥራዎችን ሠርቷል፡፡ ነገር ግን እነዚህን ስኬቶች የሚሸፍን ኃላፊነት የሚሰማው ዓለም አቀፍ ሚዲያ ማየት አልተቻለም፡፡ ዓለም አቀፍ ሚዲያው የተለየ አጀንዳ ሊኖረው ይችላል፡፡ ምናልባትም እንደ ክልላዊ አልያም ብሔራዊ ሚዲያ ኃላፊነት ላይሰማቸው ይችላል፡፡ አሳዛኙ ነገር ክልላዊና ብሔራዊ ሚዲያውም ግጭት ላይ ሲያተኩር ነው የሚታየው፤›› በማለት ዶ/ር ውባለም የዓለም አቀፍ ሚዲያው ተፅዕኖ ወደ ሌሎች ሚዲያዎች መተላለፉን ይገልጻሉ፡፡ ‹‹በአብዛኛው ዓለም አቀፍ ሚዲያው የናይል ጉዳይን ስሜት ቀስቃሽ ጉዳይ አድርጎ የሚያቀርበው ሲሆን፣ ውስብስቡን የናይል ጉዳይ ከግጭትና ከቀውስ ጋር ብቻ አስተሳስሮ ሲስለው ይስተዋላል፤›› በማለት አቶ ፈቅአህመድ በተመሳሳይ ያክላሉ፡፡

በሌላ በኩል የናይል ጉዳይን የሚሸፍኑ የሚዲያ ተቋማት በብሔራዊ ጥቅም ስም ገለልተኝነታቸውን እያጡ እንደሆነ የሚያስጠነቅቁም አሉ፡፡ በግብፅ ሚኑፊያ ዩኒቨርሲቲ የሶሲዮሎጂ ፕሮፌሰር የሆኑት ዶ/ር ሞሐመድ ሞሄይድን፣ ‹‹ሚዲያውን በንቃት ነው የምከታተለው፡፡ ከልምድ እንዳየነው የናይል ተፋሰስ አገሮች የሚዲያ ተቋማት ለሕዝቡ የሚሰጡት መንግሥት ሕዝቡ እንዲያውቅ የሚፈልገውን ጉዳይ ብቻ ነው፡፡ ዋና ዓላማቸውም ሕዝቡን ወደ አንድ የተወሰነ አቅጣጫ እንዲያስብ ማድረግ ነው፡፡ ተመራጩ መንገድ ግን የሚዲያ ሚና የመንግሥት ይፋዊ መረጃን እንዲሞግትና እንዲጠይቅ ይጠብቃል፤›› ብለዋል፡፡ ንታባና ግን ሚዲያው የኤንቢአይን የትብብር አጀንዳ ለማስፈጸም በአጋርነት ሲንቀሳቀስ የሙያ ደረጃውንና ሥነ ምግባሩን ሳይቀንስ እንዲሆን ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡

‹‹ብሔራዊና ክልላዊ ሚዲያ ሕዝቡን የማስተማር የተለየ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ከናይል ዓውድ አንፃር ገንቢ ጋዜጠኝነት ማለት ጥያቄ የማይቀርብባቸውንና በሳይንስ የተረጋገጡ የናይል አደጋዎችን ለሕዝቡ ማስተማር ማለት ነው፡፡ ይኼ ከወገንተኝነት ጋር አይገናኝም፡፡ ሕዝባዊ አገልግሎት ነው፤›› በማለት ዶ/ር ውባለም ይሞግታሉ፡፡

አቶ ፈቅአህመድ ሚዲያው የናይል ጉዳይን ከውኃ ጉዳይ ጋር ብቻ አቆራኝቶ እንደሚያይም ተችተዋል፡፡ ዶ/ር ውባለም በዚህ ይስማማሉ፡፡ ‹‹ናይል ውኃ ብቻ ማለት አይደለም፡፡ ሕይወት የሚደግፍ ሥርዓት ነው፡፡ ናይል ማለት ምግብ፣ ኢነርጂ፣ ኃይል፣ የውኃ ትራንስፖርት፣ ጂኦፖሊቲክስ፣ የዱር እንስሳት፣ ባህልና ሌላ ሌላም ነገር ማለት ነው፤›› ብለዋል፡፡ በተጨማሪም የተወሰኑ የሚዲያ ባለሙያዎች በ‹‹ናይል ጉዳዮች›› ላይ ስፔሻሊስት መሆን እንዳለባቸው ዶ/ር ውባለም ገልጸዋል፡፡

የሚዲያ ባለሙያዎች ያልዳሰሷቸውና ያልደረሱባቸው በርካታ የናይል ጉዳዮች እንዳሉም አቶ ፈቅአህመድ አስታውሰዋል፡፡ ‹‹ታሪካዊ፣ ባህላዊ፣ ጂኦፖለቲካዊ፣ ጂኦስትራቴጂካዊ፣ ከሕግ ጋር የተያያዙ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና መሰል የናይል ጉዳዮችን ሌሎች ወገኖችን ሳያስቀይም ሚዲያው ሊጽፍና ሊያስተምር ይችላል፤›› ብለዋል፡፡

ኤንቢአይ/ኢንትሮ ናይልን በተመለከተ ላለው መረጃና እውቀት ዋነኛው ማዕከል ሆኖ እያገለገለ ይገኛል፡፡ ሚዲያው በናይል ጉዳይ የተሻለ ግንዛቤና እውቀት እንዲኖረው ሥልጠና ከመስጠት ባሻገር፣ በናይል ጉዳይ የላቀ ዘገባ ላቀረቡ ጋዜጠኞች በየሁለት ዓመቱ የሚሸልምበት የናይል ሚዲያ ሽልማት ፕሮግራምንም እ.ኤ.አ. በ2015 ጀምሯል፡፡                          

Standard (Image)

‹‹ከፍተኛ አመራሩ ተጠያቂ ያልሆነው ማስረጃ ስለሌለ ነው›› ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ

$
0
0

ሰኞ ጥር 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በጽሕፈት ቤታቸው ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ከረጅም ጊዜ በኋላ በተሰጠው በዚህ መግለጫ ጋዜጠኞች አንገብጋቢና በቅድሚያ ምላሽ ያስፈልጋቸዋል ያሉዋቸውን ጥያቄዎች አቅርበዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ በከፍተኛ አመራሩ ላይ ዕርምጃ ያልተወሰደበት ምክንያት፣ የትግራይና የአማራ ክልሎች አመራሮች ጥፋተኛ ከተባሉ በኋላ ለምን ዕርምጃ እንዳልተወሰደባቸው፣ የኦሮሚያ ክልል ልዩ ጥቅምን በዝርዝር የሚደነግገው ሕግ ለምን እንዳልወጣ፣ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ይደረጋል የተባለው ድርድር የት እንደደረሰና የመሳሰሉት ጥያቄዎች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ከቀረቡት ጥያቄዎች መካከል ዋነኛ ፖለቲካዊ አንድምታ ያላቸው ከነምላሻቸው በዮሐንስ አንበርብርእንደሚከተለው ተጠናቅሯል፡፡

ጥያቄ፡- አመራሩ ሥልጣንን ለግል ጥቅም የማዋል ዝንባሌ እንዳለው በፓርቲ ደረጃ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ በተወሰደው ዕርምጃም አንዳንድ የካቢኔ አባላት ተነስተዋል፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ መልሰው ተሹመዋል፡፡ ለምን ተነስተው ለምን መልሰው ተሾሙ?

ጠ/ሚ ኃይለ ማርያም፡- ኢሕአዴግ ብዙ መስዋዕትነት ከፍሎ በኢትዮጵያ የሰላም፣ የዴሞክራሲና የፍትሐዊ አስተዳደር ሥርዓት እንዲሰፍን ለማድረግ የሠራ ድርጅት ነው፡፡ በየጊዜው ራሱን በራሱ እያረመ የዘለቀ ድርጅት ነው፡፡ የሚመራውም መንግሥት እንደዚሁ ራስን በራስ የማረም መርህ ተከትሎ የመጣ መንግሥት ነው፡፡ ስለዚህ በቅርቡ ያካሄደውም ተሃድሶ በዚህ መርህ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ለማንኛውም ድርጅትም ሆነ መንግሥት የአመራር ሥርዓቱ ወሳኝ ነው፡፡ በሒደት የካፒታሊዝም ሥርዓት ለመገንባት ጥረት እየተደረገ እንደመሆኑ ሁሉ፣ ሥርዓቱን የሚያጋጥመው አደጋዎች ምንድናቸው የሚሉትን በውል ለይተናል፡፡ ከእነዚህ አደጋዎች አንዱ በአመራር ላይ ያለ አካል ቀስ በቀስ የራሱን ኑሮ ለማሻሻል የግል ብልፅግናውን የመፈለግ፣ ከዚያም አልፎ የቆመለትን ዓላማ እየሸረሸረ የመሄድ ይህም በመጀመሪያ በአመለካከት ደረጃ በሒደት ደግሞ በተግባር የሚገለጽ ችግር እንደሚያጋጥም ነው፡፡

ኢሕአዴግ በተሃድሶ እንቅስቃሴዎቹ የፓርቲውን መሠረታዊ መርህ የሚሸረሽሩ ነገሮችን ማስተካከል ይገባል በሚል ሲሠራ ነው የቆየነው፡፡ በአሁኑ የተሃድሶ እንቅስቃሴም ያጋጠሙንን ፈተናዎችና ተግዳሮቶች ለይተናል፡፡ ከእነዚህም መካከል ዋናውና በውልም ለይተን የያዝነው የመንግሥትን ሥልጣን የምናይበትን መንገድ ነው፡፡ ይህንን በምንፈትሽበት ጊዜ በሌብነትና በሙስና የሚገለጽ የመጨረሻው ደረጃ ብልሹነት አለ፡፡ ከዚህም ባሻገር የያዘውን ሥልጣን ለሕዝብ አገልግሎት መጠቀም ሲገባ ኑሮውን፣ ቤተሰቡን፣ ሕይወቱን በመምራት ዙሪያና ምቹ ኑሮ ለመኖር የመሞከር ነገር ተስተውሏል፡፡ ባይሰርቅ እንኳ ስርቆት ድረስ የመሄድ አመለካከት ተለይቷል፡፡ ከዚህ በመነሳት እጅግ አብዛኛውን አመራር እያጠቃ ያለው ለሥራ ከመትጋትና መስዋዕትነት ከመክፈል ይልቅ መዝናናትን የመምረጥ፣ ባለጉዳይን ያለማስተናገድ፣ ቢሮ ያለመገኘት ወይም ዝግ መሆን፣ ከሥራ ሰዓት ውጪ ያለመሥራት፣ እንደ ማንኛውም ሲቪል ሠራተኛ 11፡30 ሰዓት ሲሆን ከቢሮ ወጥቶ መሄድ፣ የተለያዩ ጉዞዎችን የማብዛትና የመሳሰሉት ውጤታማ የማያደርጉ ዝንባሌዎች ይታያሉ፡፡ ይህ ደግሞ ሥልጣንን ለኅብረተሰብ ጥቅም ብሎ ለወሰነ ፓርቲ የማይገባ ሥነ ምግባር ነው፡፡

ስለዚህ በቅርቡ ባደረግነው የአመራር ለውጥና ሽግሽግ ውስጥ እንዲካተቱ የተደረጉት ከታች እስከ ላይ በዚህ ችግር ውስጥ ያልገቡትን ነው፡፡ አመራሮች የሕዝብ አገልግሎት ውስጥ ሊሳተፉ ይገባል በሚል መርህ ነው፡፡ አንዳንዱ ደግሞ ከአቅም ማነስ ማለትም ከዕውቀት ወይም ከክህሎት ማነስ ጋር ተያይዞ ነው የተቀነሰው፡፡ ስለዚህ አመራሮቹ ሲነሱ ከእነዚህ በአንዱ ተገምግመው ነው ማለት ነው፡፡ ዝቅ ብሎ የተመደበ ከሆነ በቀደመው ቦታ ላይ አቅም አልነበረውም ተብሎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ በተመሳሳይ ወደ ላይ የተመደበ ወይም ወደ ሌላ አካባቢ የተሸጋገረም ከሆነ በተመሳሳይ የተሻለ አቅም አለው ተብሎ መታየት አለበት፡፡ አንድ ግልጽ ሊሆን የሚገባው ነገር በስርቆት፣ በሌብነት፣ በሙስና ተሳትፎ ማስረጃ የተገኘበት በምንም መልኩ ተጠያቂ ሳይሆን ሊቀር አይችልም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ጥርጣሬዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ወደ ሕግ ተጠያቂነት ለመውሰድ በቂ ማስረጃ ሊኖር ይገባል፡፡ ጥርጣሬዎች በሚኖሩበት ጊዜ ሊወሰዱ የሚችሉ ዕርምጃዎች ሁለት ናቸው፡፡ አንደኛው አስተዳደራዊ በሆነ መንገድ ከሥልጣኑ እንዲወጣ ይደረጋል፡፡ ከሥልጣኑ ከወጣ በኋላ በቂ ማስረጃ ካለ ወደ ሕግ ቀርቦ ይጠየቃል፡፡ በቂ ማስረጃ ሳይኖር ወደ ሕግ አቅርቦ ማሸነፍ ስለማይቻል ትርጉም የለውም ማለት ነው፡፡ ሙስና በጣም ውስብስብ የሆነ ወንጀል ነው፡፡ የተቻለውን ያህል ባገኘነው በቂ ማስረጃ አመራሮችን ተጠያቂ እያደረግን መጥተናል፡፡ ነገር ግን በዚህ ያበቃል ማለት አይደለም፡፡

ሙስና ውስብስብነቱ ታውቆ አሁን ከሥልጣን የወረዱ፣ እንዲሁም በሥልጣን ላይ ያሉና በሙስና የተሳተፉትን በየጊዜው በጥናት ላይ በመመሥረት የማፅዳት ሥራ መከናወን አለበት፡፡ ሁለተኛው በተሃድሶ ንቅናቄው ውስጥ እንደ ሥርዓት ሊቀመጥ ይገባል ብለን ያቀድነው ኅብረተሰቡ በፀረ ሙስና ትግል ውስጥ በስፋትና በጥልቀት የሚሳተፍበትን ሁኔታ ማመቻቸት ማስረጃዎችን ለማግኘት ወሳኝ መሆኑን ነው፡፡ በብዙ አገሮች እንደተለመደው የሙስናን ውስብስብ ባህሪ ታሳቢ አድርገን ኅብረተሰቡ ማስረጃ በማቅረብ የሚሳተፍበትን ሁኔታ ማመቻቸት አለብን፡፡ ከዚህ አኳያ መንግሥት የወሰነው የዴሞክራሲ ግንባታ ማዕከል አቋቁሞ ኅብረተሰቡ ለዚህ ማዕከል በየጊዜው ማስረጃዎችንና መረጃዎችን የሚሰጥበት ሁኔታ ማመቻቸት ነው፡፡ ሌላው የመንግሥት ባለሥልጣናት ሀብትና ንብረት ይፋ የሚሆንበትን ሁኔታ በማመቻቸት፣ ይፋ ከሆነው በተጨማሪ ‘እከሌ የተባለ ባለሥልጣን ንብረት አለው’፣ ‘በራሱ ብቻ ሳይሆን በዘመዶቹ ወይም በወዳጆቹ የተያዘ ሀብት አለው’ በማለት እንዲጠቁሙ ለማድረግ ታቅዷል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የዴሞክራሲ ተቋማትን ማለትም በቅርቡ በተጠናከረ መንገድ ያቋቋምነው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አለ፣ የፀረ ሙስናና ሥነ ምግባር ኮሚሽንም አለ፣ በተጨማሪም በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ውስጥ በተለየ መንገድ በአሜሪካ እንዳለው ኤፍቢአይ ዓይነት የምርመራ ቢሮ አቋቁመናል፡፡ ኅብረተሰቡ ዘመናዊ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂዎችን የሚጠቀምበትን ሁኔታ ማመቻቸት እንደሚገባ በመወሰን እየሠራን ነው፡፡

      ዋናው ጉዳይ ግን አመለካከትን መቀየር ነው፡፡ ሙስናን የሚጠየፍ አመራርና ማኅበረሰብ መገንባት ነው መፍትሔው፡፡ በተሃድሶ ጊዜ ዋነኛው ድል ሆኖ ያገኘነው ማንኛውም ዓይነት የሙስና ዝንባሌ ሐሜት እንኳን ቢሆን ወደ መድረክ ወጥቶ ውይይት ተካሂዶበታል፡፡ በአገራችን ሙስና የማይፈቀድ ተግባር መሆኑ ላይ ግንዛቤ ይወሰዳል፡፡ ስለዚህ ሁሉም ሰው ራሱን የሚገዛበትና የሚጠበቅበት ሁኔታን ያመቻቻል፡፡ ስለዚህ የንፅህና ጉዳይ የሚለካው በተግባራዊ እንቅስቃሴና ኅብረተሰቡ የሚያቀርባቸውን መረጃዎች መሠረት አድርጎ በሚከናወን ትግል ነው፡፡

ጥያቄ፡- [ችግር እንዳለበት የተገመገመው ከፍተኛ አመራር ያልተጠየቀበትን ምክንያት አስመልክቶ የሰጡት ማብራሪያን ያልተዋጣላቸው ጋዜጠኞች ጠቅላይ ሚኒስትሩን በድጋሚ ጠይቀዋል፡፡] ኅብረተሰቡ እያለ የሚገኘው መንግሥት የራሱን አጥፊዎች ሲቀጣ በሁለት ለይቶ የላይኛውና የታችኛው አመራር በሚል ነው፡፡ የላይኛው ከፍተኛ አመራር በሙስናና በኪራይ ሰብሳቢነት አይጠየቅም፡፡ መካከለኛና የታችኛው አመራር ነው እየተጠየቀ ያለው፡፡ ከፍተኛው አመራር ለምን አይጠየቅም? በኪራይ ሰብሳቢነት አልተሳተፈም ቢባል እንኳን እነዚህን ችግሮች ተመልክቶ የማስቆም ኃላፊነት አልነበረበትም ወይ? ከዚህ ቀደም የወልቃይት ፀገዴ ጉዳይን በተመለከተ ሲመልሱ ዋነኞቹ የችግሩ ፈጣሪዎች የሁለቱ ክልሎች አመራሮች እንደሆኑና እጃቸውን ማስገባታቸውን ገልጸው ነበር፡፡ እነዚህ የሁለቱ ክልል አመራሮች መቼ ተጠየቁ? ከዚሁ የወሰን ጥያቄ ጋር ተያይዞ የበርካታ ሰዎች ሕይወት ጠፍቶና ንብረት ወድሞ ሳለ ዋነኛ የችግሩ ባለቤት የተባሉት የሁለቱ ክልሎች አመራሮች ለምንድነው በሕግ ተጠያቂ የማይሆኑት?

ጠ/ሚ ኃይለ ማርያም፡- የመልካም አስተዳደርና የኪራይ ሰብሳቢነት ችግር በዋናነት የአመለካከት ችግር ነው፡፡ የዚህ የአመለካከት ችግር የከፍተኛ አመራሩ ነው፡፡ እንዲያውም ብሶ የሚታየው በከፍተኛ አመራሩ ላይ ነው፡፡ ከፍተኛ አመራሩም በግምገማው ወቅት ይህ ስህተት ነው ብሎ አምኖ ተቀብሏል፡፡ ትክክለኛ ኢሕአዴግአዊ አመለካከቶችን እንዲጨብጡ ተደርጓል፡፡ ትልቁ ድልም ይኼ ነው፡፡ በዚህ ላይ ተመሥርቶም ሕዝቡ የሚፈልገውን መልካም አስተዳደርና ልማት ለማምጣት ቆርጠን መሥራት አለብን የሚል ድምዳሜም ላይ ደርሰናል፡፡ ባገኘነው ማስረጃ ልክ ተጠያቂ መሆን የሚገባቸው ተጠያቂ ሆነዋል፡፡ አሁን ከጥያቄዎቻችሁ እንደገባኝ አንድ ትልቅ ባለሥልጣን እንኳን ቢታሰር በቃ ማሰር ጀምረዋል የሚለውን ማየት የሚፈለግ ይመስለኛል፡፡ ነገር ግን ዝም ተብሎ ተነስቶ ሰው አይታሰርም፡፡ ሰው ለማሰር ማስረጃ ያስፈልጋል፡፡ እኔ ደግሞ መልሼ የምጠይቀው የትኛውን ባለሥልጣን ነው ማስረጃ ኖሮን ያላሰርነው? ይነገረን እያልኩ ነው ያለሁት፡፡ የሚዲያ ባለሙያዎችም ይኼ ማስረጃ እያለኝ አላሰራችሁም የምትሉ ከሆነ ይነገረን፡፡ ፈትኑን፡፡ ይኼ ማስረጃ አለ ነገር ግን በዚህ ላይ ተመሥርታችሁ ዕርምጃ አልወሰዳችሁም ይባልና በዚህ ማስረጃ ላይ ተመሥርተን ዕርምጃ ያልወሰድን ከሆነ ሊነገረን ይገባል፡፡ በዚህ መንገድ ካልተገነዘብነው ብዙ ጊዜ ተራራ የሚያክል ነገር ይወራና ማስረጃ ሲባል አይጥ የማይሸፍን ነገር ይሆናል፡፡ ስለዚህ በወሬ ዕርምጃ አይወሰድም፡፡ ለዚህ ነው ይህንን ውስብስብ ሙስና የማጋለጥ ጉዳይ ኅብረተሰቡን ማሳተፍ ያስፈልጋል ያልኩት፡፡ ስርቆት በግልጽ አይፈጸምም፡፡ ውስብስብ አድርጎ ነው የሚሰረቀው፡፡ ይህ ሊጋለጥ የሚችለው ኅብረተሰባዊ ንቅናቄ ሲኖር ነው፡፡ ባወቅነውና ባለን መረጃ ልክ ዕርምጃ እየተወሰደ ነው የመጣነው፡፡ አሁንም ግን ዝግ ነው ማለት አይደለም፡፡ ማስረጃ ከተገኘ የትም ደረጃ ላይ ያለ አመራር ይሁን መተው የለብንም፡፡ በዚሁ ደረጃ በቁርጠኝነት መሥራት ይገባናል የሚለውን እንደ መተማመኛ ብንይዝ የተሻለ ይሆናል፡፡

ጥያቄ፡- ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ያላት ሕገ መንግሥታዊ ልዩ ጥቅም እስከ ኅዳር ውሳኔ ያገኛል ተብሎ የነበረ ቢሆንም እስካሁን የተወሰነ ነገር የለም፡፡ እንዲሁም በወልቃይት ፀገዴ ከወሰን ለውጥ ጥያቄ ጋር ተያይዞ የሚመለከታቸው የአማራና የትግራይ ብሔራዊ ክልሎች ችግሩን ይፈቱታል ተብሎ ነበር፡፡ ሁለቱ ክልሎች ምን እየሠሩ ነው?

ጠ/ሚ ኃይለ ማርያም፡- ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ያላት ልዩ ጥቅም በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠ ጉዳይ ነው፡፡ ልዩ ጥቅሙን በተመለከተ ሕግ እናወጣለን፡፡ ክቡር ፕሬዚዳንቱ የሁለቱን ምክር ቤቶች የጋራ ስብሰባ በመክፈቻ ንግግራቸው ሲከፍቱ በዚህ ዓመት ሕግ ይወጣለታል ነው እንጂ ያሉት ወር አልጠቀሱም፡፡ ይህ ሕግ የሚወጣው በሩጫ አይደለም፡፡ የሕጉ የመጀመሪያ ረቂቅ ተቀርጿል፡፡ ረቂቁን ከተለያዩ የኅብረተሰብ አካላትና ባለድርሻዎች ጋር ሳይመከርበት ወደ ሥራ እንዲገባ የሚደረግ ከሆነ የራሱን ጣጣ ይዞ ይመጣል፡፡ ስለዚህ የተቀረፀው ረቂቅ ሕግ በአመራር ደረጃ ከታየ በኋላ ባለድርሻዎች እንዲወያዩበት ተደርጎ በመጨረሻም የሕግ አወጣጥ ሒደትን ተከትሎ መፅደቅ አለበት እንጂ በሩጫ የሚሆን ነገር አይደለም፡፡ ይህ ሕገ መንግሥታዊ ጉዳይ ስለሆነ ማንም ሊከራከረው የሚገባ ጉዳይ አይደለም፡፡ ስለዚህ ተግባራዊ የሚሆን ነው፡፡

በተለያዩ አካባቢዎች ከወሰንና ከማንነት ጋር ተያይዞ የተነሱ ጉዳዮችን በተመለከተ በተለይ የማንነት ጉዳይ ከወሰን ጋር የሚያገናኘው ነገር የለውም፡፡ የማንነት ጉዳይ ሕገ መንግሥታዊ ነው፡፡ ማንኛውም የማንነት ጥያቄ አለኝ የሚል አካል ራሱ ነው መጠየቅ ያለበት፡፡ ወክዬህ እጠይቅልሃለሁ የሚል አካል ሊኖረው አይገባም፡፡ ራሱ ሕዝቡ ነው መጠየቅ ያለበት፡፡ ሕዝቡ ደግሞ እንዴት መጠየቅ እንዳለበት የተቀመጡ መሥፈርቶች አሉ፡፡ ስለዚህ በየትኛውም አካባቢ የማንነት ጥያቄ አለኝ የሚል አካል ካለ በዚያው አካባቢ ላለው መስተዳድር አካል ጥያቄውን ያቀርባል፡፡ በዚያ መሥፈርት ይካሄዳል ብለን አስቀምጠናል፡፡ ይህንን የሚገድብ ምንም ነገር የለም፡፡ ሕገ መንግሥታዊ መብት ነው፡፡ ይህንን መብት ለማስፈጸም ትክክለኛ የሕዝብ ጥያቄ መሆኑን ማረጋገጥ የግድ ነው፡፡ ከዚህ አልፎ የወሰን ጉዳዮችን በተመለከተ ሁለት ቦታዎች ላይ በፍጥነት መሥራት ያለብን አለ፡፡

አንደኛው በትግራይ ወልቃይት ፀገዴና በአማራ ወልቃይት ጠገዴ አካባቢ ያለ የወሰን ጉዳይ ነው፡፡ እስካሁን ድረስ ይህ የወሰን ጥያቄ ያልተፈታው ውስብስብ ስለሆነ አይደለም፡፡ ያልተፈታው በአመራሮቻችን ውስጥ ባለ የአመለካከት ችግር የተፈጠረ ነው በሚል በተሃድሷችን ውስጥ በዝርዝር አይተናል፡፡ አሁን በቅርቡ ባደረግነው ግምገማ መሠረት ይህ የአመለካከት መዛነፍ ተስተካክሎ ከላይ እስከ ታች እስከ ቀበሌ ድረስ ይህንን የወሰን ጥያቄ ለመመለስ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለን ገምግመናል፡፡ ስለዚህ የወሰኑን ጉዳይ መወሰን ብዙም ከባድ አይደለም፡፡ በዚያ አካባቢ ያሉ ሕዝቦች ከማናችንም በላይ የሚተዋወቁ ናቸው፡፡ ወሰንህን ራስህ ወስን ብለን ብንተወውና ሌላ ከውጭ የሚገፋ ኃይል ባይኖር በራሳቸው መወሰን ይችላሉ፡፡ ውስብስብ ያደረገው የእኛ አመራር እጅ በረጅሙ ስለሚገባበት ነው፡፡

ሁለተኛው የወሰን ችግር ያለው በሱማሌና በኦሮሚያ በተለይም በምዕራብና በምሥራቅ ሐረርጌና ከዚህ ጋር አጎራባች የሆኑ የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ዞኖችና ቀበሌዎች ነው፡፡ ከዚህ በፊት ሕዝበ ውሳኔ ተካሂዶ የነበረ ሲሆን፣ ይህንን ሕዝበ ውሳኔ ተግባራዊ በማድረግ ዙሪያ በሁለቱም አካባቢዎች መዋቅሮች ያለ ችግር ያወሳሰበው ጉዳይ ነው፡፡ ይህም የተወሰኑ የኅብረተሰብ ክፍሎች ሕይወት እንዲጠፋ ያደረገ ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን ከመሠረቱ ለመፍታት የሚያስችል አመለካከት ተፈጥሯል፡፡ ሁለቱን ክልሎች ለመርዳት የፌዴራል ጉዳዮችና አርብቶ አደር ልማት ሚኒስቴር እያስተባበራቸው ጉዳዩን እንደሚፈቱት ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡

ጥያቄ፡- የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በአገሪቱ የተከሰተውን ግጭት መቀልበስ መቻሉን ተከትሎ ከተያዘለት የስድስት ወራት ጊዜ ቀደም ብሎ ሊነሳ ይችላል ወይ? ገዥው ፓርቲም ሆነ መንግሥት የሁሉንም ኅብረተሰብ ክፍል ድምፅ የሚሰማበት የፖለቲካ ሥርዓት ለማስፈን ቃል መግባታቸው ይታወሳል፡፡ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለመነጋገር ፈቃደኛ መሆናቸውም ተገልጿል፡፡ ይህ በምን ሁኔታ ላይ ይገኛል?

ጠ/ሚ ኃይለ ማርያም፡- የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መነሳትን በተመለከተ ሊታይ የሚገባው አንደኛውና የመጀመሪያው ጉዳይ ያገኘነው ሰላምና መረጋጋት መሠረታዊ መሆኑን ማረጋገጥ ነው፡፡ ከዚህም አልፎ የሕዝቡን አስተያየት ማግኘት ይገባናል፡፡ ሕዝቡ አስተማማኝ ሰላም አግኝቻለሁ ስለዚህ አዋጁ ቢነሳ ችግር የለብንም የሚል አስተያየት ከሰጠ፣ አዋጁ በመሠረታዊነት ዘላቂ ሰላምን እንደሚያመጣ ስናረጋግጥ የምናነሳው ይሆናል፡፡ ከሕዝቡ ጋር ተወያይተንና መተማመን ፈጥረን በዚህ ላይ የተመሠረተ ውሳኔ ነው የሚሆነው፡፡ እስካሁን ባለው አፈጻጸም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የተጠበቀውን ግብ አሳክቷል፡፡ ይህ ስኬት ዘላቂ መሆኑን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ ይህንን ስናረጋግጥ በማንኛውም ጊዜ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሊነሳ ይችላል፡፡ ይህ ካልተረጋገጠ ደግሞ ሊራዘም የሚችልበት ሁኔታ ይኖራል፡፡ የሚያጣድፈን ነገር የለም፡፡ ምክንያቱም በኢኮኖሚያችን ላይ ያመጣው ተፅዕኖ የለም፡፡ በዲፕሎማሲያችን ላይም ያመጣው ተፅዕኖ የለም፡፡

ከተቃዋሚዎች ጋር የሚደረግ ግንኙነትና እንደዚሁም ደግሞ ድርድርና ውይይትን በተመለከተ መንግሥትና ገዢው ፓርቲ የወሰኑት ነው፡፡ ዴሞክራሲን የማስፋትና ጥልቀት እንዲኖረው የማድረግ ጉዳይ ተወስኗል፡፡ ከዚህ ውስጥ አንደኛው ከተቃዋሚዎች ጋር የመገናኘት ጉዳይ ነው፡፡ በመንግሥት በኩል የዴሞክራሲ ግንባታን የሚከታተል ማዕከል በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ውስጥ ተቋቁሟል፡፡ ይህ ማዕከል ዕቅዱን አውጥቷል፡፡ አንደኛው የዕቅዱ አካል ከተቃዋሚዎች ጋር የመደራደርና የመነጋገር ጉዳይ ነው፡፡ የሚያነሷቸው ጉዳዮች ምን እንደሆኑ አናውቅም፡፡ ነገር ግን መድረኮችን የምናዘጋጅ ይሆናል፡፡ ከዚህ አኳያ ኢሕአዴግን የሚወክል ኮሚቴ ተዋቅሯል፡፡ በድርጅቱ ምክትል ሊቀመንበር [አቶ ደመቀ መኮንን] የሚመራና ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች ያሉበት ኮሚቴ ተዋቅሯል፡፡ ይህ ኮሚቴም የራሱን ዕቅድ አዘጋጅቶ በሒደት ከተቃዋሚዎች ጋር መነጋገርን ይጀምራል፡፡

እንግዲህ ድርድሩ ሳይጀመር በፊት ድርድሩ ምን ሊሆን ይችላል ብሎ መወሰን አይቻልም፡፡ ስለዚህ ውይይቱ በቅርቡ ይጀመራል ብለን እናምናለን፡፡ ነገር ግን በእኛ ዕይታ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የራሳቸውን አማራጭ ፖሊሲ ለሕዝብ በማቅረብ ሚናቸውን እንዲወጡ በመርህ ደረጃ እንፈልጋለን፡፡ ነገር ግን በእኛ አገር ይህ ነው የእኔ አማራጭ ፖሊሲ ብሎ የሚያቀርብ አልታደልንም፡፡ የኢሕአዴግን አፈጻጸምና የኢሕአዴግን ፖሊሲ መተቸት፣ ማብጠልጠል እንጂ አማራጭህ ምንድነው ተብሎ ቢጠየቅ የሚቀርብ ምላሽ እስካሁን አላየንም፡፡ የተወሰኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚሞክሩ አሉ፡፡ እነዚህ መበረታታት ይገባቸዋል፡፡ የድርድር አጀንዳዎችን አብረን ከተቃዋሚዎች ጋር የምንወስን ይሆናል፡፡ 

Standard (Image)

ሚኒስትሮች በዘፈቀደ የውጭ ጉዞ ማድረግ ይችላሉ?

$
0
0

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ባለፈው ዓመት ተፈጥሮ ከነበረው ፖለቲካዊ ቀውስ በኋላ፣ ለመጀመርያ ጊዜ ሰኞ ጥር 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ወደ ሚዲያ ብቅ ብለዋል፡፡

በዕለቱ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለመጠየቅና ማብራሪያ ለመስጠት ብቻ መቅረባቸውን ያሳወቁት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የሚመሩት ፓርቲና መንግሥት እያደረጉት ነው ስለተባለው በጥልቀት መታደስ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

‹‹ኢሕአዴግ እንደ ድርጅት ብዙ መስዋዕትነት ከፍሎ በአገራችን ልማታዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሐዊ የአስተዳደር ሥርዓት እንዲሰፍን ለማድረግ ብዙ ሥራዎችን የሠራ ድርጀት ነው፤›› በማለት የተናገሩት አቶ ኃይለ ማርያም፣ ‹‹በየጊዜውም ይኼንኑ ዓላማ ለማሳካት ራሱን በራሱ እያረመና እያስተካከለ ከራሱ አፈጻጸሞች እየተማረ የዘለቀ ድርጅት ነው፤›› ብለዋል፡፡

የሚመራውም መንግሥት ራስን በራስ የማረም መርህን ተከትሎ እየሠራ የሚገኝ መሆኑን፣ በቅርቡ የተካሄደውም የተሃድሶ እንቅስቃሴ በዚሁ መርህ ላይ የተመሠረተ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ለአንድ የፖለቲካ ድርጅትና ራሱ ለሚመራው መንግሥት ወሳኝ ነገር የአመራር ሥርዓቱ መሆኑን በማመን፣ በቅርቡ በተደረገው በጥልቅ የመታደስ እንቅስቃሴ ትልቅ ትኩረት እንደተሰጠው አብራርተዋል፡፡

የአገሪቱ ጥረት በሒደት የካፒታሊስት ሥርዓትን መገንባት መሆኑን ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም፣ ይኼንኑ መሠረት በማድረግም ሥርዓቱን የሚያጋግሙ አደጋዎች ምን ሊሆኑ እንደሚችሉ በዚህ የመታደስ ሒደት መለየቱን ጠቁመዋል፡፡

ከሚያጋጥሙ አደጋዎች አንዱ የሚመራው አካል ቀስ በቀስ የራስን ሕይወትና ኑሮ የማሻሻል፣ የግል ብልፅግናውን የመፈለግ እንዲሁም የቆመለትን ዓላማ እየሸረሸረ መሄድ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

ይኼ መጣመም በፍጥነት እስካልተቃና ድረስ በሒደት በተግባር የሚገለጽ ሌብነት ውስጥ እንደሚገባ፣ ይህም አገሪቱን አደጋ ውስጥ ሊከት እንደሚችል ገልጸዋል፡፡

በገዢው ፓርቲና በመንግሥት ደረጃ ከፍተኛ አመራሩ ራሱን የገመገመው የመንግሥትን ሥልጣን ለሕዝብ አገልግሎት ማዋል ሲገባውና ሌት ተቀን ተረባርቦ ውጤት ማምጣት ሲገባው ኑሮውን፣ ቤተሰቡንና ሕይወቱን በመምራት ዙሪያ እንደተጠመደ በይፋ አምነዋል፡፡

የሚያገኙትን ሕጋዊ ጥቅማ ጥቅሞች በመጠቀም አመራሩ በስንፍና መቀመጡን፣ ከዚህ አንስቶ እስከ ስርቆት ድረስ የመሄድ አዝማሚያ በግምገማው ወቅት እንደተጋለጠና ውይይት እንደተደረገበት ገልጸዋል፡፡

መስዋዕትነት ከመፈለግና ሕዝብን ከማገልገል ይልቅ መዝናናትን የመምረጥ፣ ቢሮ አለመገኘት፣ ከሥራ ሰዓት ውጪ አለመሥራት፣ እንዲሁም የተለያዩ ጉዞዎችን የማብዛት በከፍተኛ ችግርነት መለየታቸውን ተናግረዋል፡፡

‹‹የመንግሥት ሥልጣንን ለኅብረተሰብ ለውጥ ብሎ ለወሰነ ፓርቲ የማይገቡ ሥነ ምግባሮች ናቸው፤›› ብለዋል፡፡

በእነዚህ ችግሮች ላይ በጥልቀት ውይይት እንደተካሄደ፣ ከዚህ በኋላ ፓርቲው የማይታገሳቸው ጉዳዮች መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ተናግረዋል፡፡

በፓርቲው በጥልቀት የመታደስ ሒደት በዋነኝነት ከተነሱት ችግሮች መካከል፣ አንዱ የአመራሩ መዝናናት ላይ መጠመድና የውጭ ጉዞ ማብዛት ይገኝበታል፡፡

የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት የውጭ ጉዞ የሚያደርጉት እንዴት ነው? ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስለሚኒስትሮችና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጉዞ የማወቅ ኃላፊነት የለባቸውም? የሚኒስትሮቹ ሕጋዊ ተጠያቂነት እስከምን ነው? የሚሉት ጥያቄዎች ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር በኋላ መንሸራሸር ጀምረዋል፡፡

የውጭ ጉዞ ለምን ዓላማ?

ይኼንኑ በተመለከተ የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአሠራር ሥነ ሥርዓት መመርያ፣ ስለሚኒስትሮች የውጭ ጉዞ ዝርዝር ድንጋጌዎቸችን አስቀምጧል፡፡

መመርያው ሚኒስትሮች ከመንግሥታዊ ኃላፊነታቸው ጋር በተያያዘ ከኢትዮጵያ ውጪ የሚያደርጉት ጉዞ ለአገር ጠቀሜታ ያለው መሆኑ የተረጋገጠና በአግባቡ ለመምራትና ሥርዓት ለመከተል የሚያገለግል መሆን እንዳለበት ያስረዳል፡፡ ሚኒስትሮች ማለትም በሁሉም ደረጃ ያሉትን እንደሚያጠቃልል ያስቀምጣል፡፡

በዚህም መሠረት ማንኛውም ሚኒስትር የውጭ ጉዞ የሚያደርግበት ዓላማ የአገርንና የመንግሥትን ተልዕኮ ለመፈጸም፣ አገርን በመወከል የአገርን ጥቅምና ስም የሚያስጠብቁ ተግባራትን ለማከናወን፣ ለአገርና ለወገን ጠቀሜታ የሚውል ልምድና ተሞክሮ ለማግኘት መሆኑን የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአሠራር መመርያ ያብራራል፡፡

ሚኒስትሮች ከላይ ለተገለጸው ዓላማ ብቻ በመንግሥት አገልግሎት ስም የውጭ ጉዞ ማድረግ እንዳለባቸው ብቻ ሳይሆን፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ፈቃድ ማግኘት እንዲሁም ተፈቅዶላቸው ከተጓዙ በኋላ አጭር፣ ግልጽና በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሪፖርት ማቅረብ እንዳለባቸው መመርያው ይደነግጋል፡፡

የጉዞ ፈቃድ

ማንኛውም ሚኒስትር የውጭ ጉዞ ለማድረግ ሲያስብ አስቀድሞ የጠቅላይ ሚኒትሩን ፈቃድ በጽሑፍ ማግኘት እንዳለበት ይገልጻል፡፡ በመሆኑም ጉዞ ለማድረግ የሚፈልግ ሚኒስትር ከጉዞው መነሻ ቀደም ብሎ ስለጉዞው ዓላማና አስፈላጊነት፣ ለጉዞው የሚያስፈልገው ጊዜ፣ አብረው የሚጓዙትን የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ከነሥራ ኃላፊነታቸው በማቅረብ ማስፈቀድ እንዳለበት ይገልጻል፡፡

ጉዞው የሚደረግበት አገር የጉዞውን ሙሉ ወጪ የሚሸፍን መሆኑን ወይም አለመሆኑን በመግለጽ የጉዞ ፈቃድ እንዲሰጠው ማስፈቀድ ይኖርበታል፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትሩ ፈቃድ ከተገኘ በኋላም በቀረበው የጉዞ ዕቅድ ላይ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ተወያይቶ አስፈላጊውን መመርያ እንደሚሰጥ በመመርያው ተደንግጓል፡፡

የሚኒስትሮች የዓመት ጉዞን አስመልክቶ ከሚያስነሳቸው ጥያቄዎች መካከል ጉዞ የሚደረግባቸውም ከተሞች ዝርዝር፣ በጉዞው ወቅት በምን ጉዳዮች ከነማን ጋር ውይይት ለማድረግ እንደታቀደ፣ ወጪውን የሚሸፍነው ሦስተኛ ወገን ከሆነ ማን እንደሆነና በምን ሁኔታ እንደሚሸፈን ማሳወቅ የሚሉት ይገኙበታል፡፡

የሚኒስትሮች የግል ጉዞ

ሚኒስትሮች ግለሰባዊ መብቶች ያሏቸው ቢሆንም፣ ከሕዝብና መንግሥት አገልጋይነታቸው የመነጨ ገደቦች ሊጣልባቸው ይችላል፡፡ ከእነዚህም አንዱ በዘፈቀደ የውጭ ጉዞ ማድረግ ይገኝበታል፡፡

በዚህም የተነሳ ሚኒስትሮች ለግል ጉዳዮቻቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩን በቅድሚያ በማስፈቀድና የተመደቡበት የመንግሥት ሥራ እንዳይበደል አስፈላጊውን ሁሉ በማመቻቸት፣ በራሳቸው ወጪ የውጭ ጉዞ ማድረግ እንደሚችሉ ይገልጻል፡፡

በሌላ በኩል በጠቅላይ ሚኒስትሩ ፈቃድ ለመንግሥታዊ የሥራ ዓላማ ወደ ውጭ የተጓዘ ሚኒስትር፣ የተጓዘበትን የመንግሥት ሥራ በተግባር ካጠናቀቀ በኃላ የግል ጉዳዩን ለማከናወን ጠቅላይ ሚኒስትሩን በቅድሚያ በማስፈቃድ የመመለሻ ጊዜን ማራዘም ይችላል፡፡ ይሁን እንጂ ለተራዘመው ኃላፊነት ተጨማሪ ጊዜ ወጪውን በራሱ የመሸፈን ኃላፊነት እንዳለበት ይገልጻል፡፡

ከሚኒስትሮች ጋር ስለሚጓዙ ቤተሰቦች

ከሚኒስትሮች ጋር ወደ ውጭ የሚጓዙ የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች አብረው ሄደው አብረው መመለስ እንዳለባቸው መመርያው ይገልጻል፡፡

ሚኒስትሮች ወደ ውጭ በሚጓዙበት ጊዜ የሚከፈሏቸው አበልና ሌሎች ወጪዎች በየጊዜው እየተጠና በመንግሥት እንደሚሸፈን ተቀምጧል፡፡

ከሚኒስትሮች ጋር ስለሚጓዙ የቤተሰብ አባላት አስመልክቶ በሚገልጸው ክፍል፣ አሁንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ መፍቀድ እንዳለባቸው መመርያው ይገልጻል፡፡

‹‹ሚኒስትሮች የቤተሰብ አባላት አብረዋቸው እንደሚጓዙ የሚያቀርቡትን ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሁኔታው እያየ ሊፈቅድ ይችላል፡፡ ወጪውም እንደ አግባቡ እየታየ በመንግሥት እንዲሸፈን ሊፈቅድ ይችላል፤›› በማለት ይደነግጋል፡፡

አጠቃላይ የውጭ ጉዞ ዓላማና መንፈሱ የተገለጸው ቢሆንም፣ በተለምዶ አጋጣሚዎች ሚኒስትሮች በዘፈቀደ ከመጓዝ እንዳልታቀቡ እንዲሁም ለምን ዓላማ እየተጓዙ እንደሆኑ እንደማያሳውቁ ይነገራል፡፡

ከላይ የተገለጸው መመርያ በ1996 ዓ.ም. የወጣና አሁንም ድረስ የሚኒስትሮች የምክር ቤት አሠራር የሚመራበት ቢሆንም፣ የውጭ ጉዞን በተመለከተ የተደነገገውን ማንም እየተጠቀመበት አለመሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡

የሚኒስትሮችን ጉዞ በተመለከተ የመጨረሻውን ውሳኔ የሚሰጠውን ጠቅላይ ሚኒስትሩን እያስፈቀዱ መጓዝ የሚገባቸው ቢሆንም፣ በዚህ መሠረት ነገሮች እየተፈጸሙ አለመሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰሞኑ መግለጫቸው በግልጽ ተናግረዋል፡፡         

 

 

 

Standard (Image)
Viewing all 475 articles
Browse latest View live