Quantcast
Channel: እኔ የምለዉ
Viewing all 475 articles
Browse latest View live

‹‹የኢንተርኔት መዘጋት ኢትዮጵያን ባይገልጽም ለደኅንነት ሲባል ከዚህም የባሰ ውሳኔ ሊወሰን ይችላል››

$
0
0

የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትር፣ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር)

ለማኅበራዊ መስተጋብር ዋነኛ መሣሪያ ትምህርት እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ አሪስ ጣጣሊስ የተባለው ታዋቂ ፈላስፋ ትምህርት የሁሉም ነገር መሠረት እንደሆነ ተናግሯል፡፡ ለማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዕድገት ትልቁ መሰላል ትምህርት እንደሆነ ገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ የትምህርት ሥርዓት ከተጀመረ ብዙ ዓመታት ቢያስቆጥርም፣ የዘመናዊነት መልክ የያዘው ግን በአፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት እንደሆነ የታሪክ ድርሳናት ያወሳሉ፡፡ ከዚህ በፊት የነበረው የትምህርት ሥርዓት ዋነኛ ዓላማ ሃይማኖትን ለማስፋፋት የሚሰጥ እንደነበረም ይነገራል፡፡ ዜጎች ሃይማኖታቸውን ጠንቀቀው እንዲያውቁ፣ ካወቁ በኋላም ሃይማኖቱ በሚያዘው አስተምህሮ መሠረት እንዲያልፉና ለሌሎች እንዲያስተምሩ በማሰብ የትምህርት ሥርዓት ይቀረፅና ይሰጥ እንደነበር ይነገራል፡፡

የተለያዩ አገሮችን ተሞክሮ በመቀመር የአገሪቱን የትምህርት ሥርዓት ከመንፈሳዊ ወደ ዓለማዊ በመቀየር፣ ዘመናዊ ትምህርት በኢትዮጵያ መሰጠት ከተጀመረ ከመቶ ዓመታት በላይ ዕድሜ አስቆጥሯል፡፡

ከንጉሠ ነገሥቱ እስከ ደርግ ሥርዓት የነበረው የትምህርት ፖሊሲ ብዙ ኢትዮጵያዊያን ምሁራንን እንዳፈራ ቢነገርም፣ የኢሕአዴግ መንግሥት አገሪቱን ከተቆጣጠረበት 1983 ዓ.ም. ወዲህ ግን ‹‹ጥራት ያለው ትምህርት ለሁሉም›› በሚለው መፈክር በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊንን በማስተባበር የአገሪቱን ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ችግሮች የሚፈታ ዜጋ በመፍጠርና በመቅረፅ ረገድ የተጓዘው መንገድ አበረታች እንደነበረ ምሁራን ሲናገሩ ይደመጣል፡፡ ‹‹ጥራት ያለው ትምህርት ለሁሉም›› የትምህርት ፖሊሲ በአገሪቱ ከተቀረፀ ወዲህ በአገሪቱ በአራቱም አቅጣጫ ክልሎች፣ ዞኖች፣ ወረዳዎችና ቀበሌዎች ትምህርት ቤቶችን በመገንባት ዜጎች የመማር ዕድል እንዲያገኙ በማድረግ ረገድ የተካሄደው መንገድ አበረታች እንደሆነ የተለያዩ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡

ለትምህርት ጥራቱ አጋዥ የሆኑ የላብራቶሪ፣ የቤተ ሙከራ፣ የአይሲቲና ሌሎች መሠረተ ልማቶችን አሟልቶ ትምህርቱን ከመስጠት አንፃር ያሉ ክፍተቶች ወይም ጉድለቶች እንዳሉ ግን አይካድም፡፡ ለትምህርት ጥራት ወሳኝ ናቸው ተብለው የሚጠቀሱ እነዚህ ግብዓቶች ተሟልተው በአገሪቱ ውስጥ ባሉ የመጀመርያም ሆነ ሁለተኛና መሰናዶ ትምህርት ቤቶች አለመገኘት፣ በትምህርት ጥራቱ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እያሳደሩ እንደሆነ የተለያዩ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ የኢንፎርሜሽን ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ማዕከሎች በተገቢው ሁኔታ የተደራጁ አለመሆን ትልቁ ፈተና መሆኑም ተጠቃሽ ነው፡፡

‹‹ጥራት ያለው የትምህርት ለሁሉም›› በሚለው የአገሪቱ የትምህርት ፖሊሲ የተነሳ በአሁኑ ወቅት በየዓመቱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተማሪዎች አሥረኛና አሥራ ሁለተኛ ክፍል በመድረስ ለብሔራዊ ፈተና እንደሚቀርቡ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ካለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት ወዲህ በአገሪቱ በብሔራዊ ደረጃ ለፈተና የሚቀርቡትና ወደ መሰናዶና ዩኒቨርሲቲ የሚገቡት ተማሪዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻቀበ መጥቷል፡፡ በአንድ ዓመት ብቻ ወደ መሰናዶ ትምህርት ለመግባት ፈተና የሚወስዱ የተማሪዎች ቁጥር በሚሊዮን የሚቆጠር ሆኗል፡፡

ወደ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት የአሥራ ሁለተኛ ክፍልን ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና የሚወስዱ ተማሪዎች ቁጥርም በመቶ ሺሕዎች ደርሷል፡፡ ባለፈው ዓመት የአሥራ ሁለተኛ ክፍል ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት ለፈተና ሲቀርቡ ያጋጠመው ችግር ግን በአገሪቱ የትምህርት ሥርዓትና ፖሊሲ ላይ ትልቁ ፈተና ሆኖ እንዳለፈ ይታወቃል፡፡ ተማሪዎቹ በተፈጠረላቸው አጋጣሚም ሆነ ግሎባላይዜሽን ባመጣው ጫና ማኅበራዊ ሚድያዎችን የመጠቀም ዕድል አግኝተዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት የዓለምን ሕዝብ በፍጥነት እያግባባና መረጃ እያለዋወጠ የሚገኘው ማኅበራዊ ሚድያ በተለይም ፌስቡክ፣ ዓለም ወደ ሥልጣኔ እየገሰገሰች መሆኗን ማሳያ እንደሆነ የፌስቡክ መሥራቹ ማርክ ዙከርበርግ ከዓመት በፊት ተናግሯል፡፡ እነዚህ ማኅበራዊ ሚድያዎች ለአንድ አገር የትምህርት ሥርዓት መሻሻል የራሳቸው አዎንታዊ ጎን እንዳላቸው ምሁራን ሲናገሩ ይደመጣል፡፡

የአንድ አገር የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ የደረሰበትን ደረጃ በፍጥነት ከማሳወቅ ባሻገር የፖለቲካ ሥርዓቱና ተሞክሮው ምን እንዳሚመስል በመጠቆም ማኅበራዊ ሚድያ እየተጫወተ ያለው ሚና ከፍተኛ ነው፡፡ በዓለም ላይ ታዋቂ የሆኑ የፖለቲካ መሪዎች፣ የአሠራርና የአመራር ጥበባቸውን እንዲሁም በምን ሁኔታ አገራቸውን ወደ ዕድገት ደረጃ ማሸጋገር እንደቻሉ፣ መረጃዎችን ተደራሽ በሆነ ዘዴ በፍጥነት በማስተላለፍ ማኅበራዊ ሚድያ የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ እንደሆነ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡

በሌላ በኩል እነዚህ ማኅበራዊ ሚድያዎች ለሁሉም ተደራሽ ከመሆናቸው አንፃር አገርን በማፍረስና የፖለቲካ ኢኮኖሚ ሥርዓቱን በመናድ በኩል ከፍተኛ አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳላቸው የሚከራከሩ አሉ፡፡ የጀርመን መራሒተ መንግሥት አንገላ መርከል ባለፈው ዓመት ለሕዝብ እንደራሴዎች የተናገሩትም ይኼንኑ ነው፡፡

ከዓመታት በፊት የግብፅ መሪዎች ከሥልጣናቸው መነሳት ማኅበራዊ ሚድያዎች ከፍተኛ ተፅዕኖ እንደነበራቸው ‹‹አህራም ኦንላይን›› የተሰኘው የሚድያ አውታር ከወራት በፊት ዘግቧል፡፡ የግብፅ መሪ የነበሩትን ሆስኒ ሙባረክ ከሥልጣናቸው እንዲነሱ ከማቀጣጠል ጀምሮ፣ በሙስሊም ወንድማማቾች የፖለቲካ ፓርቲ ላይ ሕዝቡ እንዲያምፅና መሐመድ ሙርሲ ከሥልጣናቸው እንዲወርዱ ማኅበራዊ ሚድያ ዋነኛውን ድርሻ እንደተወጣ፣ በተለያዩ ጊዜያት የወጡ መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡

በአገራችን ኢትዮጵያም ከ2008 ዓ.ም. ጀምሮ ተቀስቅሶ በነበረው አገራዊ አመፅ፣ ተቃውሞና ሁከት ማኅበራዊ ሚድያዎች ዋነኛ መሣሪያ ሆነው ያገለግሉ እንደነበር መንግሥት በተደጋጋሚ ጊዜ ሲናገር ተደምጧል፡፡ ከጎንደር እስከ ባህር ዳር፣ ከወለጋ እስከ ሱሉልታ፣ ከጌዴኦ እስከ አርሲ በነበረው አለመረጋጋት ማኅበራዊ ሚድያ በተለይም ፌስቡክ የራሱን ሚና እንደተጫወተ ተነግሯል፡፡ በዚህ የተነሳ መንግሥት ማኅበራዊ ሚድያውን በተለይም ፌስቡክን በተለያዩ ጊዜያት ሲዘጋና ሲከፍት ተስተውሏል፡፡

ባለፈው ዓመት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፣ ማኅበራዊ ሚድያው ለአንድ አገር ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ዕድገት የራሱን አስተዋፅኦ እየተጫወተ ቢሆንም፣ አገርን በማፍረስ በኩልም ያለው ሚና ከፍተኛ በመሆኑ በዚህ ረገድ ሊታሰብበት እንደሚገባ መግለጻቸው ይታወሳል፡፡ ማኅበራዊ ሚድያው በተለይም ፌስቡክ ለታዳጊ አገሮች የራሱን አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ ቢሆንም፣ በዚያው ልክ ያለውን አሉታዊ ተፅዕኖ አጽንኦት ሰጥተው መናገራቸው ይታወቃል፡፡ በዚህም ረገድ በተመድ በኩል የተለያዩ ዕርምጃዎች መወሰድ እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡

በኢትዮጵያ ለብዙ ወራት ለነበረው አለመረጋጋት እንደ ዋነኛ የመግባቢያ መሣሪያ ሆኖ ሲያገለግል እንደቆየ የሚገለጸው ማኅበራዊ ሚድያ፣ ከዚያ ወዲህም በአገሪቱ የትምህርት ሒደትና ሥርዓት ላይ እንቅፋት ፈጥሮ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

ባለፈው ዓመት ወደ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት ሲዘጋጁ በነበሩ ተማሪዎች፣ ወላጆችና የአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አስከትሎ ነበር፡፡ ባለፈው ዓመት ፈተናው ተሰርቆ በፌስቡክ በመውጣቱ ዓመቱን ሙሉ አንገታቸውን ደፍተው ሲማሩና ሲያጠኑ በቆዩ ተማሪዎች ላይ አድርሶት ያለፈው የሞራል ኪሳራ ከባድ እንደነበር፣ ተማሪዎች ዛሬም ድረስ ሲናገሩ ይደመጣል፡፡

በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ተበጅቶለት የሚሰጠው ይኼ ፈተና በአገሪቱ ላይ አስከትሎት ያለፈው ኪሳራ በቀላሉ የሚታይ እንዳልሆነ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ ለአንድ ተማሪ የሚሆን የፈተና ወረቀት ከማዘጋጀት አንስቶ እስከ መልስ መስጫው፣ እንዲሁም የፈተና ወረቀቱን ከማጓጓዝ እስከ ፈታኝ መምህራን የቀን አበል መክፈል ድረስ ያለው ወጪ ከባድ ነው፡፡ የወረቀት ዋጋ ሰማይ በደረሰበት፣ የማተሚያ ቀለም በተወደደበት በዚህ ጊዜ ፈተናውን እንደገና አዘጋጅቶ፣ እንደገና አባዝቶ፣ እንዲሁም እንደገና ወደየትምህርት ቤቶች አሠራጭቶ ሒደቱን በማከናወን ወቅት የጠየቀው ጊዜና ገንዘብ አገሪቱን በከፍተኛ ሁኔታ ጉድቷት እንዳለፈ ማሳያ ነው፡፡ ጉዳዩ በጊዜና በገንዘብ ላይ ጭምርም ጉዳት እንዳደረሰ ባለሙያዎች ሲናገሩ ተደምጧል፡፡

የአሥራ ሁለተኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና ተሰርቆ በማኅበራዊ ሚድያዎች በመውጣቱ በአገሪቱ ኢኮኖሚም ብቻ ሳይሆን በፖለቲካዊ ሒደቱም ላይ ተፅዕኖ አሳርፎ እንዳለፈ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የአገሪቱን መረጃ በጥብቅና በሚስጥር በመያዝና በማስተዳደር ረገድ ጉድለት እንዳለ ማሳያ ሆኖ እንዳለፈ ተነግሯል፡፡ አገር አቀፍ ፈተናን ለዘራፊዎች አጋልጦ መስጠት በትምህርት ሥርዓቱ ላይ ያለውን ክፍተት እንደሚያሳይ ባለሙያዎች ሲናገሩ ተደምጧል፡፡ ለዚህ ሁሉ የጊዜና የገንዘብ መባከን፣ እንዲሁም የተማሪዎችና የወላጆች ሞራል ውድቀት መነሻ ምክንያት የሆነው ፈተናው ተሰርቆ በማኅበራዊ ሚድያ በተለይም በፌስቡክ  መውጣቱ እንደሆነ ይታወቃል፡፡

በዚህ ዓመት ባለፈው ተከስቶ የነበረውን ችግር መልሶ ላለማስተናግድ ሲባል ማኅበራዊ ሚድያው በተለይም ፌስቡክ ተዘግቶ የሰነበተ ቢሆንም፣ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትር ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) ግን፣ ጉዳዩ ከፈተናው መሰረቅ ጋር የተያያዘ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡

ሰኞ ግንቦት 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ሚኒስትሩ በጽሕፈት ቤታቸው ተገኝተው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ2 ‹‹የኢንተርኔት መዘጋት ኢትዮጵያን የሚገልጽ ጉዳይ ባይሆንም ለደኅንነት ሲባል ከዚህም የባሰ ውሳኔ ሊወሰን ይችላል፤›› ብለዋል፡፡ ኢንተርኔት በአጠቃላይ እንዳልተቋረጠ የሚገልጹት ሚኒስትሩ፣ ትኩረት የተደረገበት በተለይም ሶሻል ሚድያው እንዲዘጋ የተወሰነበት ዋነኛው ምክንያት፣ አገር ተረካቢ የሆነው አዲሱ ትውልድ ለብዙ ዓመታት ሲለፋበት የነበረውንና አሁን ፈተና በመፈተን ውጤቱን ለማግኘት በሚጥርበትና በጉጉት በሚጠብቅበት ጊዜ በመሆኑ፣ የተፈታኙን ሞራል ለመጠበቅ ሲባል እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በማኅበራዊ ሚድያዎች የሚለቀቁት አሉባልታዎችና የሐሰት ወሬዎች በሥነ ልቦናቸው ላይ ተፅዕኖ እንዳያሳርፍ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡

ይኼ ዘመን አመጣሽ ማኅበራዊ ሚድያ ለአዎንታዊም ሆነ ለአሉታዊ ጉዳዮች ክፍት እንደሆነ የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ የሐሰት አሉባልታዎችን በመንዛት ሕዝብን የማደናገር አቅም እንዳለው አስታውቀዋል፡፡ አሁን ጥያቄው ኢንተርኔት መዘጋቱና አለመዘጋቱ ሳይሆን፣ ተማሪዎች ተረጋግተውና ምንም ዓይነት ሥነ ልቦናዊ ጫና ሳይደርስባቸው ትኩረታቸውን በጥናታቸው ላይ ብቻ አድርገው ፈተናቸውን እንዲወስዱ የማድረግ ጉዳይ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

‹‹የኢንተርኔት መቋረጥ ምንም መጉላላት አያደርስም ብለን አናስብም፤›› ያሉት ሚኒስትሩ፣ ጉዳቱ ታይቶና ተመዝኖ ትውልድ መጎዳት ስለሌለበት መወሰኑን አስረድተዋል፡፡ በአገር ውስጥ ያሉ የውጭ ተቋማትና ድርጅቶች የመንግሥት ተቋማትን ጨምሮ በዚህ ችግር መጉላላትና ኪሳራ እንደሚደረስባቸው ጠቁመዋል፡፡

በየጊዜው ለሚፈጠረው የኢንተርኔት መቆራረጥና መዘጋት ኃላፊነቱን ማን እንደሚወስድ ለተጠየቁት ጥያቄ ሚኒስትሩ ምላሽ ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡ ከኢንተርኔት መቆራረጥና መዘጋት ጋር ተያይዞ አገሪቱ ምን ያህል ገንዘብ በዓመት እንዳጣች ከጋዜጠኞች የተጠየቁት ሚኒስትሩ በተመሳሳይ መልስ ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ ባለፈው ዓመት ለፈተናው መሰረቅ ዋነኛ ተዋናይ በሆኑ ግለሰቦችና ባለሙያዎች ላይ የተወሰደ ዕርምጃ ካለ እንዲገልጹ ሲጠየቁ፣ ወደፊት በሚመለከተው አካል ይፋ ይደረጋል ብለዋል፡፡ ዘንድሮ ኢንተርኔት የተቋረጠው እንደ ባለፈው ዓመት ፈተናው ይሰረቃል ተብሎ እንዳልሆነም አክለው አብራርተዋል፡፡ ‹‹የተለያዩ ሰዎች ፈተናው እንዳይሰረቅ በማሰብ ነው መንግሥት ኢንተርኔት የዘጋው የሚሉት ውሸት ነው፤›› ብለዋል፡፡ ምንም ሳይፈጠር ሆን ብለው ሥነ ልቦናዊ ጫና ለማሳደር የሚፈልጉ አካላት ያንን ዕድል እንዳያገኙ በማሰብ እንደሆነ ሞግተዋል፡፡

በፈተና ወቅት ኢንተርኔት መዝጋት ዘንድሮም የተከሰተ ሲሆን፣ ይኼንን ችግር በዘላቂነት በመፍታት ረገድ መንግሥት ምን እየሠራ እንደሆነ ሚኒስትሩ ከመግለጽ ተቆጥበዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ሳዑዲ ዓረቢያ የሚኖሩ ሰነድ አልባ ኢትዮጵያዊያንን የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ እንደቀጠለ ዶ/ር ነገሪ ተናግረዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በየዕለቱ ከአንድ ሺሕ በላይ ዜጎች የጉዞ ሰነድ በመውሰድ ላይ እንደሆኑና እስካሁን ባለው ሒደትም ከ50 ሺሕ በላይ ዜጎች የጉዞ ሰነድ መውሰዳቸውን አስረድተዋል፡፡ የጉዞ ሰነዱን ከወሰዱ መካከልም 74.4 በመቶ ያህሉ ሴቶችና ሕፃናት መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ እስከ ዓርብ ግንቦት 25 ቀን 2009 ዓ.ም ድረስ 20 ሺሕ የሚጠጉ ዜጎች ወደ አገራቸው እንደተመለሱና ይኼም በራሳቸው ጊዜ የሚመለሱትን እንደማያካትት አስረድተዋል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ ብሔራዊ የዜጎች አስመላሽ ግብረ ኃይልና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተቀናጅተው በመንቀሳቀስ ላይ እንደሆኑ፣ በቀን ውስጥ የሚደረገውን የበረራ ቁጥርም ለማሳደግ ከሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት ጋር በመነጋገር ተጨማሪ የበረራ ፈቃድ ተጠይቆ ምላሽ እየተጠበቀ መሆኑን ሪፖርተር መዘገቡ ይታወቃል፡፡

ከሳዑዲ ለሚመለሱ ሰነድ አልባ ዜጎች አገር ውስጥ ሲመጡ ምን ድጋፍ ለማድረግ ታቅዷል? ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ፣ መንግሥት በሦስቱ ክልሎች በአማራ፣ በደቡብና በኢትዮጵያ ሶማሌ እንዲሁም አዲስ አበባን ጨምሮ ተመላሾች ሲመጡ በሚቋቋሙበትና በሚደራጁበት ሁኔታ ላይ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ሳዑዲ ዓረቢያ የሚኖሩ ሕጋዊ የመኖሪያ ፍቃድ የሌላቸው ዜጎችን በተመለከተ እንደነ ፊሊፒንስና ፓኪስታን ያሉ አገሮች ዜጎቻቸውን የአየር ትራንስፖርት እያቀረቡ እየወሰዷቸው እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሳምንታዊ በረራውን ከሃያ አንድ ወደ አርባ ሁለት ከማድረሱ ባሻገር የዋጋ ቅናሽ ስለማድረጉ አልተነገረም፡፡ ለአንድ በረራ ከሚያስከፍለው ከ800 እስከ 1,000 ሪያድ ከፍለው ከሳዑዲ መምጣት ያልቻሉ ሰነድ አልባ ዜጎች በተመለከተ እየተሠራ ያለውን ሥራ እንዲያብራሩ የተጠየቁት ሚኒስትሩ፣ በገንዘብ እጥረት ሳዑዲ የሚቀሩ ሰነድ አልባ ኢትዮጵያዊያን እንደማይኖሩ ተናግረዋል፡፡

ሚኒስትሩ በጋዜጣዊ መግለጫቸው ወቅት እንደተናገሩት፣ በአገሪቱ ተከስቶ የነበረውን ድርቅ የመከላከሉ ሥራም ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ካለፈው ዓመት ወዲህ በኢትዮጵያ ሶማሌ፣ በኦሮሚያ ክልል ቦረና፣ በባሌ፣ በጉጂ፣ በምዕራብና ምሥራቅ ሐረርጌ፣ በደቡብ ክልል፣ ደቡብ ኦሞ፣ ሰገን ሕዝቦችና ጋሞጎፋ በዝናብ እጥረት ወገኖችን ለመታደግ የምግብና የውኃ አቅርቦት፣ እንዲሁም የጤናና የትምህርት አገልግሎት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል፡፡

ዕርዳታ ለሚያስፈልጋቸው 7.8 ሚሊዮን ወገኖች በዋናነት በኢትዮጵያ መንግሥት፣ እንዲሁም ቀሪው በዓለም ምግብ ፕሮግራምና መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች ጥምረት 98,587 ሜትሪክ ቶን እህል መሠራጨቱን አስረድተዋል፡፡ በ173 ወረዳዎች በሚገኙ 3,012 ትምህርት ቤቶች ትምህርታቸውን ለሚከታተሉ ከ1.1 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች ምገባ እየተከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል ከፓሪስ የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት ጋር በተያያዘ አሜሪካ ከአባልነቷ መውጣቷ ይታወቃል፡፡ የተለያዩ የዓለም አገሮችም የአሜሪካን ድርጊት እየኮነኑና እየተቃወሙ እንደሚገኙ ሰሞኑን የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በዚህ የተነሳም በአሁኑ ወቅት ፈጣን የኢኮኖሚው ዕድገት እያስመዘገበች ያለችው ቻይና ከአውሮፓ ኅብረት ጋር አዲስ የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት አድርጋለች፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያ መንግሥት ያለውን አቋም እንዲገልጹ የተጠየቁት ሚኒስትሩ፣ ‹‹ይኼ የአሜሪካ መንግሥት ውሳኔ ስለሆነ ውሳኔውን እናከብራለን፡፡ የተለያዩ አገሮች ይኼንን እያወገዙ እንደሆነም እንሰማለን፡፡ በእኛ በኩል ማውገዙ ተገቢ ሆኖ አይታየንም፡፡ ድርሻችንን መወጣቱ ላይ ነው ትኩረት የምናደርገው፤›› ብለዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት በየዓመቱ ሪፖርት በሚያቀርብበት ወቅት የተለያዩ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በሚሊዮን የሚቆጠር የጥሬ ገንዘብ ጉድለት እንደሚገኝባቸው፣ በዘንድሮው ሪፖርቱ ላይም ይኼ ጉዳይ እንዳልተሻሻለ ሪፖርተርን ጨምሮ በተለያዩ የሚድያ ውጤቶች መገለጹ ይታወሳል፡፡  መንግሥት ደግሞ ለእስካሁን ድረስ ዕርምጃ ሲወስድ አይታይምና ይኼ ጉዳይ እስከ መቼ ነው በዚህ ሁኔታ የሚዘልቀው ተብለው ለተጠየቁት፣ ‹‹እነዚህ የበጀት ጉድለት ያሳዩ መሥሪያ ቤቶች ተመርምረው በዚህ ችግር እጃቸው ያለበት የመንግሥት የአመራር አካላት ዕርምጃ እንዲወስድባቸው፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ከአሥር ቀናት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ በፌዴራል ፖሊስና በጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የመንግሥትና የሕዝብን ገንዘብ ባጎደሉ አካላት ላይ ምርመራ ይጀመራል፤›› ብለዋል፡፡ የፌዴራል ዋና ኦዲተር ኦዲት በተደረጉ 113 መሥሪያ ቤቶች 5.2 ቢሊዮን ብር ያልተወራረደ መሆኑን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማቅረቡ ይታወሳል፡፡

በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ከወራት በፊት በአገሪቱ ተከስቶ ስለነበረው አለመረጋጋት ባቀረበው ሪፖርት ተጠያቂ ሊሆኑ ይገባቸዋል የተባሉ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች እስከ ዛሬ ምን ዕርምጃ ተወስዷል ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ፣ ክልሎች የወሰዱትን ዕርምጃ በተመለከተ ኮሚሽኑ በሚቀጥለው ሳምንት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሪፖርት እንደሚያቀርብ ጠቁመዋል፡፡       

 

Standard (Image)

‹‹ጥናታችን በመጠኑም ቢሆን ጽንፈኝነት እንዳለ የሚያሳይ ቢሆንም መንግሥት ኢንተርኔት ለመዝጋት ሰበብ ሊሆነው አይችልም››

$
0
0

 

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር)፣ የሚዲያ ኤክስፐርት

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር) መቀመጫቸውን በደቡብ አፍሪካው ዊትዋተርስራንድ ዩኒቨርሲቲ ያደረጉ የሚዲያ ኤክስፐርት ናቸው፡፡ ኢጂኒዮ ተነፃፃሪ የሚዲያ ሕግና ፖሊሲ ላይ በማተኮር ይሰሩበት ከነበረው የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ሴንተር ፎር ሶሽዮ-ሌጋል ስተዲስ ለቀው ዊትስ ዩኒቨርሲቲን የተቀላቀሉት እ.አ.አ. በ2016 ነው፡፡ ይሁንና አሁንም የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ አሶሼት ሪሰርች ፌሎው ናቸው፡፡ ከለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ ፒኤችዲ ዲግሪያቸውን ካገኙ በኋላ ከኦክስፎርድ በፊት በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካና ዓለም አቀፍ ጥናቶች የትምህርት ክፍል ሠርተዋል፡፡ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በአዲስ አበባ፣ እንዲሁም ለጣሊያን ኢኖቬሽን ሚኒስቴር በሮም ይሠሩ ነበር፡፡ የኢጂኒዮ የጥናትና ምርምር ሥራዎች በተለይ ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ አገሮችን የተመለከቱ የሚዲያና የፖለቲካ ለውጥ ጉዳዮች፣ እንዲሁም በመላው ዓለም እየተመነደጉ ያሉ ልዩ የሆኑ የኢንፎርሜሽን ማኅበረሰብ ሞዴሎች ላይ ትኩረት ያደርጋሉ፡፡ ኢጂኒዮ በርካታ የጥናት ፕሮጀክቶችን የመሩ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል ኢንፎርሜሽንና ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ በምሥራቅ አፍሪካ፣ የሰላም ግንባታና በአገር ግንባታ ላይ ያለውን ሚና የሚገመግመው፣ እንደ ቻይና ያሉ በመመንደግ ላይ የሚገኙ ኃይሎች በአፍሪካ ሚዲያና ቴሌኮሙዩኒኬሽን ዘርፍ እየጨመረ የመጣውን ሚናቸውን ለመረዳት የተካሄደው፣ እንዲሁም ከምርጫ በፊት በኢንተርኔት አማካይነት የሚሠራጩ የጥላቻ ንግግሮች ባህሪና ተፅዕኖን ለመተንተን የተካሄደው ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የኢጂኒዮ የፒኤችዲ ጥናት በኢትዮጵያ ልማትና አለመረጋጋት ያላቸውን ግንኙነት የሚመረምር ሲሆን፣ በአገሪቱ ላይ ከ12 ዓመታት በላይ የተለያዩ ሥራዎችን ሠርተዋል፡፡ ኢጂኒዮ በቅርቡ በግብፅ ካይሮ የናይል ቤዚን ካፓሲቲ ቢዩልዲንግ ኔትወርክና የዩኔስኮ ወተር ኤዱኬሽን ኢንስቲትዩት በመተባበር አዘጋጅተውት በነበረ ሥልጠና ላይ በአሠልጣኝነት ተሳትፈው ነበር፡፡ ሥልጠናው በናይል ላይ የሚሠሩ ሳይንቲስቶችና ጋዜጠኞች እየተመጋገቡ በሚሠሩበት መንገድ ላይ ግንዛቤ ለመስጠት ያለመ ነበር፡፡ በሥልጠናው የተሳተፈው ሰለሞን ጐሹ በኢትዮጵያ ስላለው የሚዲያ ነፃነትና የሥልጠናውን ጭብጥ በተመለከተ ኢጂኒዮን አነጋግሯቸዋል፡፡

ሪፖርተር፡-በአፍሪካ ስላለው ወቅታዊ የሚዲያ ይዞታና የትኞቹ አገሮች የተሻለ አፈጻጸም እያሳዩ ስለመሆኑ ምን ይላሉ? ኢትዮጵያስ በአንፃራዊነት የት ትገኛለች?

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር)፡- አንዱን አገር ከሌላው አገር ጋር በማነፃፀር ደረጃ በማውጣት አላምንም፡፡ በኢትዮጵያ፣ በኬንያ፣ በሶማሊላንድ፣ በሩዋንዳና በተለያዩ አገሮች ካካሄድኩት ጥናቶች መረዳት የቻልኩት እነዚህ አገሮች ኮሙዩኒኬሽንን በተመለከተ የራሳቸው በጎ ጎን ያላቸው ቢሆንም፣ ይህን በዓለም ላይ ካለ የትኛውም አገር ኮሙኒኬሽን መዋቅር ጋር በቀላሉ ማነፃፀር እንደማይቻል ነው፡፡ በኬንያ ላይ በሠራሁት አንድ ጥናት ከታዘብኳቸው ጉዳዮች አንዱ በአገሪቱ የራዲዮ ቶክሾውስ በጣም ተወዳጅ መሆናቸው ነው፡፡ ይህ ደግሞ የመጣው እንደ ጣሊያንና እንግሊዝ በመሳሰሉ ሌሎች ቦታዎች ባልተለመደ ሁኔታ በፕሮግራሞቹ በሚስተናገዱ በንቁ ተሳትፎ የታጀቡ ክርክሮች የተነሳ ነው፡፡ ንቁ ተሳትፎው ደግሞ የመጣው በፕሮግራሞቹ የግለሰቦች ድምፅ ብቻ ሳይሆን የማኅበረሰቡም መሰማት አለበት ከሚለው እምነት ነው፡፡ ሁሌም ግንዛቤ ውስጥ የማንከተው አንዱ ነገር በሚዲያ የሚነገሩ ነገሮች በመንግሥት ዝቅተኛ መዋቅር የሚገኙ አካባቢዎች ላይ ለውጥ ሊያመጡ የመቻላቸውን ዕድል ነው፡፡ በአፍሪካ እንዳየሁት  በብሔራዊ ደረጃ በአብዛኛው ተግዳሮትና ክፍተት ነው የሚሰማው፡፡ ነገር ግን በተዋረድ መዋቅሮች የሚዲያ ለውጥ የማምጣት ኃይል ይታያል፡፡

የአፍሪካ ሚዲያ ምን እንደሚመስልና ምን መምሰል እንዳለበት፣ እንዲሁም ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብትን ጨምሮ በሕግ ማዕቀፍና በተግባራዊ አፈጻጸም መካከል ያለውን ተቃርኖ በተመለከተ ትልቅ ክርክር ይደረጋል፡፡ ለምሳሌ የካሜሩናዊው ምሁር ፍራንሲስ ንያምኖህ ሥራዎች የአፍሪካ ሚዲያ ልዩ ባህሪያት ምን እንደሚመስሉ ለማስገንዘብ የሚጥሩ ናቸው፡፡ ሌላኛው ደቡብ አፍሪካዊ ምሁር ኸርማን ዋሰርማን በኢንተርኔት ምንነት ላይ ተፈጥሯል ከሚባለው ዓለም አቀፋዊ ስምምነት በተቃራኒ፣ የአፍሪካን የኢንተርኔት ታሪክ ለመገንባት መጠየቅ ያሉብንን ጥያቄዎች ለማሳየት ይሞክራል፡፡ ስለዚህ አገሮቹን ከማነፃፀር ይልቅ በተጫባጭ በየአገሮቹ ያለውን ሁኔታ ማሳየት ይመረጣል፡፡

ወደ ኢትዮጵያ ስንመጣ አስደናቂ ለውጥ በማምጣት ላይ ብትሆንም፣ ለክርክር ምኅዳር ከመፍጠርና ሁሉም ወገን የሚያርፍበት መካከል ላይ ያለ ከባቢ ሁኔታ ከመፍጠር አንፃር ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ውስጥ ነች፡፡ ሚዲያው ከረጅም ጊዜ ጀምሮ እጅግ ጽንፍ የያዘ ነው፡፡ ከጋዜጠኝነትና ከተለያዩ ሙያዎች የመጡ ግለሰቦች በአገሪቱ ተቃራኒ ጫፍ ላይ የሚገኙ አካላት ተገናኝተው የሚያወሩበት አማካይ ሥፍራ ለመፍጠር በርካታ ሙከራዎች ሲያደርጉ አይቻለሁ፡፡ ይኼ በጣም ቅር የሚያሰኝ ነገር ነው፡፡ እርግጥ ነው ጉዳዩ አወዛጋቢ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ መንግሥትም ሆነ በውስጡ ያሉ ግለሰቦች ይኼ አማካይ ሥፍራ እንዲኖር ዕድል የሰጡ መስለው ሁኔታው ለጊዜው እንዲኖር ካደረጉ በኋላ መልሰው በከፍተኛ ሁኔታ ሲዘጉት ይታያል፡፡ ሰዎች ማንም ጋዜጠኛ ወደ እስር ቤት ሊገባ አይገባም ሲሉ እሰማለሁ፡፡ እኔ በግሌ የምቃወመው እስሩን ሳይሆን ዓላማውን ነው፡፡ ማንም ቢሆን ባይታሰር ደስ ይለኛል፡፡ ነገር ግን ጽንፍ የያዙ ጋዜጠኞች ላይ መንግሥት የሆነ ዕርምጃ ቢወስድ እረዳለሁ፡፡ ሆኖም ለእኔ ልብ የሚሰብር ሆኖ ያገኘሁት ድልድይ የሚገነቡና ከኅብረ ብሔራዊ ፌዴራሊዝም እስከ አብዮታዊ ዴሞክራሲ፣ እንዲሁም የመንግሥትን ልማታዊ መንግሥት ነኝ ጨምሮ የአገሪቱን ተቋማዊ አደረጃጀት የሚያከብሩትንም ጭምር ሲዘጋ ማየቴ ነው፡፡ ይኼ አገሪቱን ወደ ኋላ የሚያስቀር ነው፡፡ ምክንያቱም የአገሪቱን ጥቂት ባለ ብሩህ አዕምሮና ምርጥ ወንድና ሴቶች ልጆችን እየተከታተሉ ዕርምጃ መውሰድ ለረጅም ጊዜ ዘላቂ አይሆንም፡፡      

ሪፖርተር፡- ከኢንተርኔት መስፋፋት ጋር በተያያዘ በኢትዮጵያ ላይ በሠሩት አንድ ጥናትዎ በከፍተኛ ወጪ የሚገነባው የኢንተርኔት መሠረተ ልማት የፖለቲካ መሣሪያ እንደሆነ ተከራክረዋል፡፡ ይኼ ከኢትዮጵያ ጋር በተለይ የተያያዘ ችግር ነው? ወይስ በአኅጉሩ በስፋት የተለመደ ጉዳይ ነው? 

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር)፡- በአኅጉሩ ቴሌኮሙዩኒኬሽንን በሞኖፖሊ የያዙ አገሮች ኢትዮጵያና ጂቡቲ ብቻ ናቸው፡፡ የኢትዮዽያ ፖሊሲ በጣም ግልጽ ነው፡፡ ቢያንስ በአጭር ጊዜ የመቀየር ሐሳብ የለም፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት መሞገስ ያለበት አንድ ጉዳይ ቢኖር ዜጎችን እስከ መጨረሻው ተዋረድ ዘልቆ ለመድረስ ያለው ቁርጠኝነት ነው፡፡ ከተሜና መካከለኛ ገቢ ያላቸውን ብቻ ሳይሆን የተገለሉ ማኅበረሰቦችንም ለማካተት ይሞክራል፡፡ በአገሪቱ ካለው ብዝኃነትና አስቸጋሪ መልክዓ ምድር አንፃር ይህን ማድረግ ቀላል አይደለም፡፡ ነገር ግን ወደዚህ ግብ ለመድረስ የተመረጠው ስትራቴጂ በሞኖፖል የሚፈጸም በመሆኑ ማንንም አሸናፊ የሚያደርግ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት የሥራ ኃላፊዎችን፣ የኢትዮ ቴሌኮም የቴክኒክ ተቀጣሪዎችን፣ እንዲሁም ፈንድ ያደረገውንና ሥራው ላይ ያሉ የቻይና ኩባንያዎች ተወካዮችና ሌሎች ሰዎችን ቃለ ምልልስ በማድረግ እንደተረዳሁት የትኛውም ወገን ደስተኛ አይደለም፡፡ ውድድር ባለመኖሩና ጫና ስለሌለ የቴሌኮም አገልግሎትን የማሻሻል ፍላጎት የለም፡፡ የአገልግሎት ጥራቱ እጅግ የወረደ በመሆኑ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ሕዝብ ግን ቅሬታውን እያቀረበ ነው፡፡ ይህ አገልግሎት እንዲሻሻል በተለይ ከቴክኒክ አንፃር ሁሉም አካል የበኩሉን እንዲወጣ ዕድል ሊሰጠው ይገባል፡፡ ውድቀትንም ሆነ ስኬትን በታማኝነት መግለጽና መወያየት ያስፈልጋል፡፡ ዘርፉን ለግሉ ዘርፍ ክፍት ማድረግ የማድረግ ዕቅድ ከሌለ ቢያንስ ባለው ሥርዓት ውስጥ አማራጮችንና ማትጊያዎችን በማምጣት፣ ሁሉም ወገኖች እንዲወዳደሩ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ እስካሁን ይኼ እየሠራ አይደለም፡፡   

ሪፖርተር፡- መንግሥት ኢንተርኔት የምዘጋው በዚሁ አማካይነት የሚንሸራሸሩ ጽንፍ የረገጡ ሐሳቦች የአገሪቱን የትራንስፎርሜሽን አጀንዳ አደጋ ላይ የሚጥሉ ናቸው በሚል ምክንያት ነው፡፡ አንዱ የምርምር ሥራዎ በኢንተርኔት የሚሠራጩ የጥላቻ ንግግሮችን የተመለከተ ነው፡፡ የጥናቱ ግኝቶች ምንድን ናቸው? የባለድርሻ አካላትስ አስተያየት ምን ይመስላል?

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር)፡- ጥናታችን በሌሎች አገሮች እንዳለው ሁሉ በኢትዮጵያም የጥላቻ ንግግርና የጽንፈኝነት መገለጫዎች እንዳሉ ያሳያል፡፡ ይህ ‹‹መቻቻል››የሚል ርዕስ የሰጠነው ጥናት በዓይነቱ ለየት ያለ ስለሆን እንኮራለን፡፡ አማርኛ በአገር ውስጥና በውጭ አገር ባሉ ኢትዮጵያዊያን የሚነገር በመሆኑ በፌስቡክ የሚንሸራሸሩ አደገኛ ንግግሮችን በቁጥር መግለጽ መቻላችን፣ በኢትዮጵያም ሆን በመላው ዓለም የተለየ ጥናት አድርጎታል፡፡ ውጤቱ ለሁሉም በግልጽ ተደራሽ እንዲሆን የተደረገ ሲሆን፣ በዚህም የተገኘው ቁጥር 0.7 በመቶ እንደሆነ ማየት ይቻላል፡፡ ጥናታችን በመጠኑም ቢሆን ጽንፈኝነት እንዳለ የሚያሳይ ቢሆንም መንግሥት ኢንተርኔት ለመዝጋት ሰበብ ሊሆነው አይችልም፡፡ ሌላው በጥናቱ ይፋ የሆነው ነገር ግጭት ቀስቃሽ ንግግሮች በአብዛኛው የሚመጡት ከተፅዕኖ ፈጣሪ ሰዎች አለመሆኑን ነው፡፡ በተቃራኒው ጥቂት ተከታይ ሰዎች ናቸው ይህ አዝማሚያ ያላቸው፡፡ ለዚህ በሰጠነው ትርጉም መሠረት ይህን የሚያደርጉት የመገለል ስሜት ካላቸው የማኅበረሰብ ክፍሎች የመጡ ናቸው፡፡ በአገሪቱ መፃኢ ዕድልና በሕይወታቸው ላይ ተፅዕኖ ባላቸው ፖሊሲዎች ላይ የመካተት ስሜት የላቸውም፡፡

ስለዚህ ኢንተርኔት የጥላቻ ንግግርን ከማንሸራሸር በላይ ሌሎች ንቅናቄዎችን ለመፍጠር ጥቅም ላይ ሊውል ይችላል፡፡ የተለየ የፖለቲካ አቅጣጫ ላላቸውና አገሪቱ በምን መንገድ መሄድ እንዳለባት የተለየ ሐሳብ ላላቸው ሰዎች መድረክ ሆኖም ያገለግላል፡፡ ይኼ አግባብነት ያለው አጀንዳ በመሆኑ በመንግሥት ተቀባይነት ሊኖረው ይገባል፡፡ አንዳንድ ድምፆች ጽንፈኛ ቢሆኑም ሌሎች ድምፆች ተገቢ ጥያቄ ያላቸው በመሆኑ ሊሰሙ ይገባል፡፡ በዚህ ሒደት የትውልድ ለውጥ ግንዛቤ ውስጥ መግባት አለበት፡፡ በተማሪዎች ንቅናቄ ጊዜ የተፈጠረው ጽንፍ የያዘ ልዩነት ሳቢያ ከዚያ በኋላ ባሉት ዓመታት ተገቢ የሆኑ ክርክሮች እንዳይደረጉ እንቅፋት ሆኗል፡፡ በጥናታችንም የዚያ ትውልድ አባላት የፖለቲካ ሐሳባቸውን ሲገልጹ የጠብ አጫሪነት አዝማሚያ እንደሚታይባቸው ተገንዝበናል፡፡ በተቃራኒው የአዲሱ ትውልድ አባላት ከመንግሥት ጋር ወይም ሥልጣን ላይ ካለው ኃይል ጋር አተካሮ ውስጥ ከመግባት ይልቅ፣ ለውይይት ክፍት በመሆን አማራጭ ሐሳቦችን በማቅረብ ላይ እንደሚያተኩሩ ነው ያየነው፡፡

ሪፖርተር፡- የናይል ቤዚን አገሮች ሚዲያ የናይል ጉዳይን ከፍተኛ ትኩረት ይሰጠዋል፡፡ እንደ ሚዲያ ባለሙያ የናይል ጉዳይ የሚዲያ ሽፋንን እንዴት ያዩታል?

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር)፡-በአንፃራዊነት ለናይል ጉዳይ አዲስ ነኝ፡፡ ስለዚህ የምሰጠው አስተያየት በመማር ላይ ያለ ሰው አስተያየት ነው የሚሆነው፡፡ በአብዛኛው በሚዲያ እንደተለመደው ለናይል ጉዳይ የሚሰጠው ሽፋን ከግጭት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ግጭት እስካለ ድረስ ለግጭት ሽፋን መሰጠቱ በራሱ ችግር አይደለም፡፡ ነገር ግን ግጭት ለመኖሩ ዕውቅና ከሰጠን በኋላ እሱን የምንሸፍንበት የተለያየ መንገድ ይኖራል፡፡ ግጭቱ ምን ያህል የተወሳሰበ እንደሆነ ለማብራራት የተለያዩ አካላትን ድምፅ ማካተት ይቻላል፡፡ የ21ኛው ክፍለ ዘመን በፈጠረው ዕድል በመጠቀም በማኅበራዊ ሚዲያ የሚንፀባረቁ የግለሰብ አስተያየቶችን በሚዲያ ዘገባዎች ማካተት ይቻላል፡፡ ይህ ግን በአብዛኛው ተግባር ላይ ሲውል አይታይም፡፡

ሪፖርተር፡- ጋዜጠኞች የናይል ጉዳይ ላይ ሚዛናዊ ዘገባ መሥራትና በተመሳሳይ ብሔራዊ ጥቅማቸውን እንደ ዜጋ እንዴት ማስከበር ይችላሉ?

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር)፡- ይኼ ብሔራዊ ጥቅም የሚባል ጽንሰ ሐሳብ በግሌ ያበሳጨኛል፡፡ በአጠቃላይ በአፍሪካና በመላው ዓለም ከተንሰራፋው የብሔርና ብሔርተኝነት ጽንሰ ሐሳብ ጋር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተጋጨሁ ነው፡፡ ቀደም ብሎ የጠራ ርዕዮተ ዓለም በመቅረፅና እሱንም በመግለጽ፣ እንዲሁም የፓን አፍሪካኒዝም ስሜትን በማቀንቀን የሚታወቁት የመለስ ዜናዊ አንዳንድ ሐሳቦችን አደንቅ ነበር፡፡ እርግጥ ነው ማንም ጠቅላይ ሚኒስትር ወይም ፕሬዚዳንት እንደሚያደርገው የኢትዮጵያን ያስቀደመ እንቅስቃሴ ነበር የሚያደርጉት፡፡ እ.ኤ.አ. በ1950ዎቹ፣ በ1960ዎቹ እና በ1970ዎቹ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆኑ የሚዲያ ውጤቶች ነበሩ፡፡ በወቅቱም የቀድሞ ጋዜጠኞች የነበሩት ክዋሜ ንክሩማህንና ጆሞ ኬንያታን የመሳሰሉ ሰዎች ከአገር የዘለለ ርዕይ አስፈላጊነትን ይሰብኩ የነበረ ቢሆንም፣ ብሔራዊ ንቅናቄዎችን በሚያገለግል መንገድ የተቃኘ መሆኑ ግን አልቀረም፡፡ የተለያዩ አገሮችን ለሚያካልለው ናይል የፓን አፍሪካኒዝም ስሜት ሊጠቅም ይችላል፡፡ በብሔርተኝነት ዘመን የፓን አፍሪካኒዝም ስሜት ጥቅም ላይ የማይውል ከሆነ ምናልባትም ጋዜጠኞች መልሰው ሊያመጡት ይገባል፡፡ ጋዜጠኞች አንዱ መጠየቅ ያለባቸው ጥያቄ ከአፍሪካ አኅጉር በቀላሉ መውጣት የማይችለው ውኃ ይህን ሁሉ ግጭት ሲፈጥር፣ ከአፍሪካ እየወጡ ሌሎች አገሮችን የሚጠቅሙ ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶች ለምን ተመሳሳይ ችግር እንደማይፈጥሩ ነው፡፡     

ሪፖርተር፡- ሥልጠናው አንዱ ትኩረት ያደረገበት ጉዳይ ጋዜጠኞች በናይል ጉዳይ ላይ ከሚሠሩ ባለድርሻ አካላት ጋር እንዴት ተቀናጅተው እንደሚሠሩ ነው፡፡ ጋዜጠኞች ሚዛናዊ ሆነው ሙያቸውን አክብረው መሥራትና በተመሳሳይ የራሳቸው አጀንዳ ሊኖራቸው ከሚችለው እነዚህ አካላት ጋር በትብብር ሊሠሩ የሚችሉት እንዴት ነው?

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር)፡- በዚህ ጉዳይ ላይ ለጋዜጠኞች ሐዘን ይሰማኛል፡፡ በተለይ የኅትመት ጋዜጠኞች በኢንተርኔት በነፃ ከተለያዩ ምንጮች ከሚገኝ መረጃ በሚገጥማቸው ውድድር የተነሳ ከፍተኛ ጫና ውስጥ ናቸው፡፡ በዚህ ጫና ላይ ጋዜጠኞች በናይልና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ኤክስፐርት እንዲሆኑ መጠበቅ ከባድ ነው፡፡ ጋዜጠኞች አንዳንድ ጉዳዮች አከራካሪ መሆናቸውን ለመረዳት የግድ ዝርዝር ዕውቀት አያስፈልጋቸውም፡፡ በብሔራዊና በዓለም አቀፍ ሚዲያ ላይ በሚሰጡ አስተያየቶች ሐሰተኛ የሳይንስ መረጃ እንደሚሰጥም አስተውለናል፡፡ እነዚህ ሐሰተኛ ቁጥሮች እንዲታረሙና ውይይት እንዲደረግባቸው ጋዜጠኞች ትልቅ ሚና ይጫወታሉ፡፡  

ሪፖርተር፡- እንደ ሚዲያ ባለሙያነትዎ በናይል ጉዳይ ላይ ሚዲያው የትብብርንም ሆነ የግጭት አቅጣጫን ተከትሎ ሽፋን ሲሰጥ እንዳዩ አምናለሁ፡፡ ይህን የተፈጥሮ ሀብት ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ለማስተዳደርና ለመጠቀም እንዲቻል፣ ከዚህ አንፃር ሊቀየሩ የሚገባቸው ተጋዳሮቶች ምንድን ናቸው?  

ኢጂኒዮ ጋግሊያርዶኔ (ዶ/ር)፡- እንደዚህ ዓይነት ሥልጠናዎች ላይ ጋዜጠኞች እርስ በርስ ሲከባበሩና ለሌሎች ሰዎች ሐሳብም አክብሮታቸው የሚታይ ቢሆንም፣ ጋዜጠኞች ወደ አገራቸው ሲመለሱ በሥራዎቻቸው ይህ ስሜት አይታይም፡፡ ለዚህ ከላይም ሆነ ከታች የሚመጣው ጫና አስተዋጽኦ እንዳለው እረዳለሁ፡፡ ነገር ግን ጋዜጠኞቹ ለብሔራዊ ታዳሚዎቻቸው ሲጽፉ ከዚህ ስሜት ውስጥ ጥቂቱን እንኳን ይዘው ቢቆዩ ትልቅ መሻሻል ያመጣ ነበር፡፡ አንዳንዴ ጋዜጠኞች ሚዛናዊና ገለልተኛ ናቸው የሚል አስተሳሰብ ሲንፀባረቅ አያለሁ፡፡ ነገር ግን አንዳንዴ ጋዜጠኛው የራሱን ስሜት ሲያካፍል ብቻ ነው ሁሉንም መረጃ በዓውድ በዓውዱ ማሳየት የሚችለው፡፡ ከናይል ጉዳይ አንፃር ይኼ አስፈላጊ ነው፡፡ ግጭቶች በአግባቡ ከተያዙ ብዙ ልንማርባቸው እንችላለን፡፡ ከግጭት በኋላ ሰዎች ቅድሚያ የሚሰጧቸው ዋጋዎች ላይ ዳግም ግምገማ ሊያደርጉና የተፈጠሩትን ስህተቶች ሊያዩ ይችላሉ፡፡

 

Standard (Image)

በክልሎች መካከል አስተዳደራዊ ወሰን የማካለል ችግርና የኦሮሚያ ክልል አዲሱ ተሞክሮ

$
0
0

በኢትዮጵያ ውስጥ በአሁኑ ወቅት በተወሰኑ ክልሎች መካከል ያለው  አስተዳደራዊ ወሰን በቅጡ የተካለለ ባለመሆኑ፣ የተለያዩ ግጭቶች የተከሰቱ መሆናቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ አንዱ ክልል ከሌላው ክልል የሚለይበት አስተዳደራዊ ወሰን በግልጽ የተካለለና የተወሰነ ስላልሆነ፣ በክልሎች መካከል ባሉ አጎራባች ነዋሪዎች መካከል ደም አፋሳሽ ግጭት ተከስቶ ያለፈበት ጊዜ ሩቅ አይደለም፡፡ ለአብነት ያህል በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል መካከል ተፈጥሮ በነበረው አስተዳደራዊ የወሰን ይገባኛል ጥያቄ የብዙ ሰዎች ሕይወትና ንብረት መጥፋቱ ይታወሳል፡፡ በዚህ ግጭት የተነሳ ዜጎች ከቀያቸው ተሰደዋል፣ ንብረታቸው ወድሟል፡፡ ይህ ችግር ከክልሎች አልፎ አገራዊ በመሆን በአገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ የሚባል የፖለቲካ አለመረጋጋት ፈጥሮ እንደነበርም አይዘነጋም፡፡

በ1997 ዓ.ም. በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች መካከል ተካሂዶ የነበረው ሪፈርንደም የተሟላ ባለመሆኑ፣ በሁለቱ ክልሎች መካከል የሚኖሩ ዜጎች ደም አፋሳሽ ጦርነት ውስጥ ገብተው እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

በአማራና በትግራይ ክልሎች መካከል የነበረው የአስተዳደራዊ ወሰን ችግር አሁንም ድረስ የራስ ምታት እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የአማራ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሡ ጥላሁን በአንድ ወቅት ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በአማራ ክልል ውስጥ በሚገኘው ጠገዴና በትግራይ ክልል ውስጥ በሚገኘው ፀገዴ መካከል ያለው አስተዳደራዊ ወሰን  ያልተካለለ በመሆኑ፣ በእነዚህ አካባቢዎች በሚኖሩ ወገኖችና በሁለቱ ክልሎች ከፍተኛ አመራሮች መካከል ቅሬታ እንዳለ ገልጸው ነበር፡፡ ይህ ችግር የሁለቱ ክልሎች ከፍተኛ አመራሮች በጥልቅ ተሃድሶ ውስጥ እያለፉ በመሆኑ በቅርብ እንደሚፈታ ቢናገሩም፣ እስከ ዛሬ  ድረስ መፍትሔ አላገኘም፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ ከአንድ ዓመት በፊት ተከስቶ ለነበረው ሁከትና ብጥብጥ እንደ መነሻ ምክንያት ከተወሰዱ ጉዳዮች አንዱ በክልሎች መካከል ያለው አስተዳደራዊ ወሰን ያልተካለለ በመሆኑና ከዚህ ጋር ተያይዘው በመጡ ሌሎች ጉዳዮች እንደነበር ማስታወስ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ በኦሮሚያ ክልል ተፈጥሮ የነበረው ብጥብጥ ለወራት የቀጠለና በኋላ ላይም መሠረቱን አስፍቶ አገራዊ ቀውስ አስከትሎ እንዳለፈ አይዘነጋም፡፡ የአዲስ አበባ ከተማን ለማስፋፋት በተደረገው እንቅስቃሴ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ጋር ያላት አስተዳደራዊ ወሰን እንደተካለለ መረጃዎች ቢጠቁሙም፣ ከተማዋን ወደ ጎን ለማስፋፋት በተደረገው ሙከራ በሕዝቡ ዘንድ ተቃውሞ በማስነሳቱ ውጤታማ ሳይሆን መቅረቱ ይታወቃል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ አዲስ አበባ በአብዛኛው ከኦሮሚያ ክልል ጋር የምትዋሰን በመሆኑ፣ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ልታገኝ የሚገባው ጥቅም መረጋገጥ እንዳለበት ለብዙ ጊዜ በክልሉ ተወላጆች ሲጠየቅ ቆይቷል፡፡ ጥያቄው ከቀረበ ብዙ ዓመት ቢያስቆጥርም ባለፈው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ከክልሉ ነዋሪዎች ጋር ባካሄዱት ውይይት፣ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ልታገኝ ስለሚገባት ጥቅም በሚመለከት በሚቀጥለው ሳምንት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ እንደሚፀድቅ ተናግረዋል፡፡

ኦሮሚያ ክልል ከትግራይ ክልል በስተቀር በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉ ክልሎችና የከተማ መስተዳደሮች ጋር ይዋሰናል፡፡ በአገሪቱ ውስጥ ካሉ ክልሎች መካከል በቆዳ ስፋትም ሆነ በሕዝብ ብዛት አብላጫ ያለው የኦሮሚያ ክልል፣ በአስተዳደራዊ ወሰን ምክንያት በተለያዩ ጊዜያት ከተለያዩ ክልሎች ጋር ግጭት ውስጥ ገብቶ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ለምሳሌ በ2000 ዓ.ም ከጋምቤላ ክልል ጋር በነበረው የአስተዳደራዊ ወሰን ችግር ምክንያት በሁለቱ ክልሎች መካከል በሚኖሩ ዜጎች በተቀሰቀሰ ግጭት ንብረት መውደሙ ይታወቃል፡፡ በወቅቱ በሁለቱ ክልሎች መካከል ያለው አስተዳደራዊ ወሰን በቅጡ ያልተካለለና ያልተወሰነ በመሆኑ፣ በሁለቱ ክልሎች መካከል ቅራኔ እንደነበር ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ አንድ የኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ አመራር ተናግረዋል፡፡

ከአፋር ክልል ጋር ባለው ሰፊ አስተዳደራዊ ወሰን ምክንያትም ችግሮች ሲፈጠሩ እንደቆዩ ተናግረዋል፡፡ ሁለቱን ክልሎች በሚያዋስኑዋው የአርብቶ አደር አካባቢዎች ለግጦሽና ለእርሻ ሲሉ በአጎራባች ክልሎች መካከል በተደጋጋሚ ጊዜ  ግጭቶች ሲፈጠሩ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

በአፋርና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል መካከል ያለው አስተዳደራዊ ወሰንም በግልጽ የተካለለ ባለመሆኑ፣ በሁለቱ ክልሎች አጎራባች ነዋሪዎች መካከል ተደጋጋሚ የሆነ ግጭትና ሁከት ሲከሰትና የሰው ሕወት ሲጠፋ ቆይቷል፡፡ ምንም እንኳ  የሁለቱ ክልል ነዋሪዎች አርብቶ አደሮች ቢሆኑም፣ ለፍየሎቻቸውና ለግመሎቻቸው ግጦሽ እርስ በእርሳቸው ሲጠፋፉና ሲገዳደሉ እንደቆዩ ይነገራል፡፡

አማራና ኦሮሚያ ክልሎች በበኩላቸው ሰፊ የሆነ መሬት የሚጋሩ ሲሆን፣ በእነሱም መካከል የአስተዳደራዊ ወሰን ችግር በመኖሩ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ግጭቶች ሲፈጠሩ ይስተዋላል፡፡ ለምሳሌ ሁለቱን ክልሎች በሚያዋስነው ምንጃር አካባቢ በተደጋጋሚ ጊዜ በነዋሪዎች መካከል ግጭቶች ሲፈጠሩ ነበር፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ ክልሎችና የከተማ መስተዳደሮች መካከል ግልጽ የሆነ አስተዳደራዊ ወሰን ባለመካለሉ የተነሳ፣ በዜጎች መካከል በተደጋጋሚ ጊዜ ግጭትና ንትርክ ሲካሄድ ቆይቷል፡፡ በተወሰኑ አካባቢዎች ላይ ይህ ግጭትና ንትርክ አሁንም ድረስ እንዳለ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

ኢትዮጵያ በዘጠኝ ክልሎችና በሁለት የከተማ አስተዳደሮች የተዋቀረች ፌዴራላዊ አገር ነች፡፡ እነዚህ ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች የራሳቸው የሆነ አስተዳደራዊ ወሰንና  የአስተዳደር ሥርዓት ተበጅቶላቸው መተዳደር ከጀመሩ ከ20 ዓመታት በላይ ተቆጥሯል፡፡ ክልሎች የፌዴራሊዝም ሥርዓቱ በሰጣቸው መብት ራሳቸውን በራሳቸው ከማስተዳደር አልፈው እስከ መገንጠል የሚደርስ መብት አላቸው፡፡

ዘጠኙ ክልሎችና ሁለቱ የከተማ መስተዳድሮች በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌድሪ) አስተዳደር ጥላ ሥር ሆነውና ራሳቸውን በማስተዳደርና በመምራት ከሌሎች ክልሎች ጋር የተለያዩ ግንኙነቶችን በመፍጠር እንደሚኖሩ በሕገ መንግሥቱ ላይ ተደንግጓል፡፡ ክልሎች በሚያመሳስላቸው ጉዳዮች ላይ አብረው በመሥራትና አብረው በማደግ ራሳቸውን የመለወጥ ሕገ መንግሥታዊ መብት ተሰጥቷቸዋል፡፡ አንዳንድ ክልሎች በማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ተባብረውና ተጋግዘው ሲሠሩ ይታያሉ፡፡ ክልሎች እርስ በራሳቸው አብረው ከመሥራታቸው ባሻገር፣ በመካከላቸው ልዩነቶች ሲፈጠሩና ግፋ ሲልም ለፀብና ለተለያዩ ጉዳዮች ሲዳረጉ ይታያል፡፡ በመካከላቸው ያለው አስተዳደራዊ የወሰን ይገባኛል ጥያቄ ደግሞ በክልሎች መካከል ቅራኔ በመፍጠር ዋነኛው ጉዳይ እንደሆነ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡

በክልሎች መካከል ያለው የወሰን  ይገባኛል ጥያቄ በተደጋጋሚ ጊዜ በተለያዩ ክልሎች መካከል ሲፈጠር የቆየና በሕዝቦች መካከል ቅሬታን ፈጥሯል የሚሉ ወገኖች  አሉ፡፡ እነዚህ ቅሬታዎች ደግሞ አድገውና ከፍ ብለው በአገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ የሆነ ብጥብጥና ሁከት አስከትለው እንዳለፉ በማስታወስ፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉ ክልሎች በቆዳ ስፋትም ሆነ  በሕዝብ ቁጥር አብላጫ ያለው የኦሮሚያ ክልል ሲሆን፣ በአብዛኛው ከክልሎች ጋር ወሰን በመጋራትም ትልቁን ሥፍራ ይይዛል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ተከስቶ በነበረው ሁከትና ብጥብጥ የተነሳ የመልካም አስተዳደር ችግር መፈጠሩን የክልሉ መንግሥት በማመኑ በክልሉ አመራሮች ላይ ሹም ሽር አድርጓል፡፡ በአገሪቱ ሰፊ የቆዳ ስፋት ያለውን ክልል ማስተዳደር ከባድና አቅም የሚጠይቅ ጉዳይ እንደሆነ ባለሙያዎች ሲገልጹ ቢሰማም፣ ይህን ጥያቄ ለመመለስ በክልሉ በወጣት ኃይል የሚመራ ከፍተኛ አመራር ተቋቁሟል፡፡ ይህ አብዛኛው ወጣት የሆነው የክልሉ ከፍተኛ አመራር፣ ለዘመናት ሲንከባለሉ የመጡ ችግሮችን ለመፍታት ላይ ታች ሲል ታይቷል፡፡

በክልሉ ከፍተኛ ችግር ሆኖ የነበረውን የወጣቱን የሥራ ዕድል ከመፍጠር አንስቶ ከክልሎችና ከአዲስ አበባ ጋር ያለውን የወሰን ጥያቄ፣ እንዲሁም ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚከሰቱ ግጭቶችንና ብጥብጦችን ለመፍታት በመንቀሳቀስ ላይ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ወደ ሥልጣን ከመጣ ከዓመት ያልበለጠው የአቶ ለማ መገርሳ አዲሱ ካቢኔ የክልሉን ሁለንተናዊ ችግር ለመፍታት እያደረገ ባለው እንቅስቃሴ ሲሞካሽ እየተሰማ ነው፡፡

በኦሮሚያ ክልል የኢኮኖሚ አብዮትን ከማቀጣጠል ጀምሮ ከተለያዩ ክልሎች ጋር ያለውን የወሰን ችግር ለመፍታት ሌት ከቀን እየሠራ መሆኑን፣ በቅርብ እየወጡ ያሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይህ አዲሱ የክልሉ ካቢኔ ወደ ሥልጣን ከመጣ ወዲህ በአብዛኛው የክልሉ ወጣቶች ዘንድ አድናቆትን እየተቸረው እንደሆነም  የሚናገሩ ወገኖች አሉ፡፡ ኦሮሚያን የኢንዱስትሪ ማዕከል ከማድረግ ባለፈ ሰላም የሰፈነበት ክልል ለማድረግ አሁንም  እንቅልፍ ሳይወስደው እየሠራ ነው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡

ከወራት በፊት ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ጋር ተፈጥሮ የነበረውን የወሰን ችግር የፈታ ሲሆን፣ በአሁኑ ጊዜ ደግሞ ከጋምቤላና ከቤንሻንጉል ጉምዝ ክልሎች ጋር ያለውን የወሰንና ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚከሰቱ ችግሮችን ለመፍታት በእንቅስቃሴ ላይ ነው፡፡ ባለፈው ሳምንት በተለያዩ ጊዜያት ከጋምቤላና ከቤንሻንጉል ጉምዝ ክልሎች ከፍተኛ አመራሮችና በክልሎች መካከል ከሚኖሩ ነዋሪዎች ጋር የስምምነትና የሰላም ኮንፈረንስ አካሂዷል፡፡ በዚህም ለዓመታት ያህል በድንበር አካባቢ ይኖሩ በነበሩ ነዋሪዎች መካከል ይፈጠር የነበረውን ውዝግብና ብጥብጥ በመፍታት ረገድ የተጓዘው ጉዞ ይበል የሚያሰኝ እንደሆነ ነዋሪዎች ሲናገሩ ተደምጧል፡፡

በፌዴራልና አርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስቴር አደራዳሪነት የተካሄደው ይህ አስተዳዳራዊ ወሰንን የማካለል ሥራ፣ ኦሮሚያ ክልልን ከሚያዋስኑ ክልሎች ጋር ከዚህ በፊት የነበሩትን ችግሮች እንደሚፈታ ታምኖበታል፡፡

አስተዳደራዊ የወሰን ችግሮች መኖራቸውን አምኖ ይህንን ችግር ለመፍታት ወደ ሥራ የገባው የኦሮሚያ ክልል አዲሱ ካቢኔ፣ ከአጎራባች ክልሎች ጋር ያለውን አስተዳዳራዊ ወሰን ለመፍታት ዛሬም ድረስ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን፣ አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የክልሉ ባለሥልጣን ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

 ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ጋር የነበረውን የረጅም ጊዜ ችግር በሰላም ከተፈታ ወዲህ፣ በሁለቱ ክልሎች አጎራባች አካባቢዎች በሚኖሩ ወገኖች መካከል ምንም ዓይነት ግጭት አለመፈጠሩን ባለሥልጣኑ ተናግረዋል፡፡

በአቶ ለማ መገርሳ የሚመራው የኦሮሚያ ክልል አዲሱ ካቢኔ በአሁኑ ወቅት ከጎረቤት  ክልሎች ጋር ያለውን አስተዳደራዊ ወሰን በማካለልና በክልሉ ፀጥታ እንዲሰፍን በማድረግ ረገድ እየሠራ ያለው ሥራ፣ በክልሉ ነዋሪዎች ዘንድ ከፍተኛ አድናቆትን እያገኘ መምጣቱን የሚናገሩ አሉ፡፡

የክልሉ ባለሥልጣን እንደሚሉት፣ አዲሱ የክልሉ ካቢኔ የ2009 ዋነኛ ዕቅዱ ኦሮሚያን በሚያዋስኑ ክልሎች መካከል ያለውን አስተዳደራዊ ወሰን በግልጽ መለየት ነው፡፡ በክልሉ ብሎም በአዋሳኝ ድንበሮች መካከል የሚኖሩ ዜጎች ዋስትናቸውን ማረጋገጥ እንደሆነም ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ ከወራት በፊት ስምምነት ላይ የተደረሰባቸውን የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልልና የአፋር ክልል አስተዳደራዊ ወሰኖችን ጨምሮ፣ ከጋምቤላና ከቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ጋር የወሰን ማካለል መደረጉን ባለሥልጣኑ አስረድተዋል፡፡

ግንቦት 29 ቀን 2009 ዓ.ም. ከቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ጋር የተደረገው  የአስተዳደራዊ ወሰን የማካለል ስምምነትም በይዘቱ ከጋምቤላ ክልል ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ የሚናገሩት ባለሥልጣኑ፣ በሁለቱ ክልሎች ወሰን አካባቢ የሚኖሩ ወገኖችን ያካተተ አጠቃላይ ስምምነት መደረጉን ገልጸዋል፡፡ አጠቃላይ አስተዳዳራዊ ወሰኑን የማካለል ሥራም በቅርብ ቀን  እንደሚጠናቀቅ ጠቁመዋል፡፡

ከአስተዳደራዊ ወሰን ጋር በተያያዘ ኦሮሚያ ክልል በአሁኑ ጊዜ በክልሉ ብሎም በአገር ደረጃ ግጭትን ለማስቀረት የሚያችል እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን ባለሥልጣኑ ተናግረዋል፡፡ ከዓመታትና ከወራት በፊት በወሰን ምክንያት የጠፋው የሰው ሕይወትና ንብረት ሁለተኛ እንዳይደገም፣ የኦሮሚያ ክልል አዲሱ ካቢኔ የቤት ሥራው አድርጎ እየሠራ እንደሆነ አክለዋል፡፡

ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አንድ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር ደግሞ፣ በክልሎች መካከል ያለው ግጭት ሊወገድ የሚችለው ሁሉም ክልሎች እንደ ኦሮሚያ ክልል የቤት ሥራቸውን በተገቢው ሁኔታ ሲሠሩ ብቻ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡

መምህሩ እንደሚሉት በኦሮሚያ ክልል ለወራት የዘለቀው ግጭትና ሁከት መነሻ ምክንያት ከነበሩት ጉዳዮች መካከል አንዱ በክልሎች፣ በተለይም ኦሮሚያ ክልል በሚያዋስናቸው ሌሎች ክልሎች ጋር የነበረው የወሰን ጉዳይ እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ ይህንን ተገንዝቦ ወደ ሥራ የገባው አዲሱ የኦሮሚያ አስተዳደር ካቢኔም ምሳሌ ሊሆን እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

የግጭትና የሁከት መነሻ የነበረውን የኦሮሚያ ክልል ሰላም የሰፈነበትና ወጣቶች የሥራ ዕድል ባለቤቶች እንዲሆኑ ከማድረግ አንፃር እየተጫወተ ያለውን ሚና ያደነቁት መምህሩ፣ ሌሎች ክልሎችም በመካከላቸው ያለውን አስተዳደራዊ ወሰን መፍታት እንደሚገባቸውም ጠቁመዋል፡፡

የፌዴራልና አርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች  ሚኒስቴር  ይህንን ጉዳይ አጠናክሮ በመያዝ፣ በሌሎች ክልሎች መካከል ያለውን አስተዳደራዊ ወሰን መፍታት እንደሚገባውም ገልጸዋል፡፡

ግሎባላይዜሽን እንደ ሰደድ እሳት እየተቀጣጠለና ዓለም አንድ መንደር ሆና ሳይንስና ቴክኖሎጂ እየረቀቀ በመጣበት በዚህ በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን፣ ኢትዮጵያ ገና በአስተዳደራዊ ወሰን ማካለል ችግር ውስጥ ገብታ ደፋ ቀና ማለት እንደሌለባት ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ ሥልጣኔ ከአንድ ጫፍ ወደ ሌላኛው ጫፍ ሴኮንድ ባልሞላ ጊዜ እየተቀጣጠለ ባለበት በዚህ ዘመን፣ የዓለም አገሮች ከሌላው ኃያል የሚሆኑበትን ዘዴ ለመቀየስ ደፋ ቀና በሚሉበት በዚህ ዘመን፣ ኢትዮጵያ ገና ዳዴ ማለት እንደሌለባት ያስረዳሉ፡፡

በአገሪቱ ውስጥ ያለው የአስተዳደራዊ ወሰን ችግር ከኦሮሚያ ክልል ተሞክሮ በመውሰድ ሊፈታ እንደሚገባ ያሳስባሉ፡፡

በ2009 ዓ.ም የኦሮሚያ ክልል አዲሱ ካቢኔ ዓላማ የሆነውን የወሰን ማካል ችግሮችን በመፍታት የክልሉን ፀጥታ ማስፈን እንደሆነና በ2010 ዓ.ም. ደግሞ ፊቱን ወደ ሌሎች ጉዳዮች እንደሚያዞር የኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣን ተናግረዋል፡፡ ከአማራ ክልል ጋር ያለውን አስተዳደራዊ የወሰን ችግር ለመፍታት ደግሞ የኦሮሚያ ክልል ኃላፊነቱን ወስዶ በመንቀሳቀስ ላይ እንዳለ የሚናገሩት ባለሥልጣኑ፣ በቀሪዎቹ ሦስት ወራትም ችግሮችን ሙሉ በሙሉ እንደሚፈታ ገልጸዋል፡፡

በክልሉ ውስጥ ካሉ የአንዱ ቢሮ ኃላፊ የሆኑት ይህ ግለሰብ የኦሮሚያ ክልል ከጋምቤላና ከቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ጋር ያደረገውን የአስተዳደራዊ ወሰን ይዘትና ሌሎች ዝርዝር ስምምነቶችን ከመግለጽ ተቆጥበዋል፡፡ ከዚህ በፊት የኦሮሚያ ክልልና የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ደርሰውበት የነበረውን አስተዳደራዊ የወሰን ማካለል ስምምነት ይዘትና ዝርዝር ጉዳዮች ለሚዲያዎች ይፋ አድርገው የነበረ ቢሆንም፣ ይህንን ግን ባለሥልጣኑ ከመግለጽ ተቆጥበዋል፡፡ ወደፊት ከሁሉም ክልሎች ጋር ስምምነት ከተደረገ በኋላ ዝርዝር  የስምምነት ይዘቶችን ይፋ እንደሚደረግ ቃል ገብተዋል፡፡

Standard (Image)

‹‹አሁን ያለውን የዕርዳታና የብድር አሰጣጥ አዝማሚያ ብዙም ተስፋ ባናደርግበት መልካም ነው››

$
0
0

 

ሰዒድ ኑሩ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ባለሙያዎች

ማኅበር የማክሮ ኢኮኖሚ ዘርፍ ኃላፊ

የቀድሞው የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር አቶ ሱፍያን አህመድ ሰኔ 8 ቀን 1999 ዓ.ም. የአገሪቱን የ2000 ዓ.ም. በጀት በሚሊኒየም ክብረ በዓል ዋዜማ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቅርበው ነበር፡፡ አቶ ሱፊያን ባቀረቡት የበጀት ሰነድ 43.9 ቢሊዮን ብር እንዲፀድቅላቸው ጠይቀዋል፡፡ በዚህ ወቅት በጀቱ ግዙፍ ነው ተብሎ መነጋገሪያ ሆኖ ነበር፡፡ በወቅቱ ይህ በጀት ሰባት ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ጉድለት ነበረው፡፡ ከአሥር ዓመታት ቆይታ በኋላ የወቅቱ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ትብብር ሚኒስትር አብርሃም ተከስተ (ዶ/ር) ሰሞኑን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት የ2010 ዓ.ም. በጀት፣ ክብረ ወሰን የሰበረ የበጀት ረቂቅ አቅርበዋል፡፡ ሚኒስትሩ ባቀረቡት ሰነድ እንደተመለከተው፣ ለቀጣዩ በጀት ዓመት 320.8 ቢሊዮን ብር እንዲፈቀድ የጠየቁ ሲሆን፣ ይህ ግዙፍ በጀት የ53.9 ቢሊዮን ብር ጉድለት አሳይቷል፡፡ የበጀቱን ከፍተኛ ድርሻ የሚይዘው ለክልሎች በድጎማ የሚሰጠው በጀት፣ የካፒታል በጀት፣ የመደበኛ በጀትና የድህነት ቅነሳ በጀት ነው፡፡ በወቅታዊው የበጀት ቀመር ጉዳይ ውድነህ ዘነበ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ባለሙያዎች ማኅበር የማክሮ ኢኮኖሚ ዘርፍ ኃላፊ ሰዒድ ኑሩን (ዶ/ር) አነጋግሯቸዋል፡፡

ሪፖርተር፡- የዛሬ አሥር ዓመት በኢትዮጵያ ሚሊንየም ክብረ በዓል ዋዜማ የቀድሞው የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር አቶ ሱፍያን አህመድ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 43.9 ቢሊዮን ብር በጀት እንዲያፀድቅላቸው ሲያቀርቡ፣ በጀቱ እጅግ ከፍተኛ ነው ተብሎ ነበር፡፡ ከአሥር ዓመት በኋላ የአሁኑ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ትብብር ሚኒስትሩ አብርሃም ተከስተ (ዶ/ር) 320.8 ቢሊዮን ብር ሲያቀርቡ በድጋሚ ክብረ ወሰን የሰበረ ነው ተብሎ ነበር፡፡ በሁለቱ በጀቶች መካከል ያለው የመግዛት አቅም ምን ይመስላል? አንድነትና ልዩነታቸውስ?

ዶ/ር ሰዒድ፡-ሁለት ነገሮችን ማየት ጠቃሚ ነው፡፡ የመጀመሪያው ኢኮኖሚው በምን ያህል ፍጥነት እያደገ ነው የሚለው ነው፡፡ ሁለተኛው የዋጋ ግሽበቱ ነው፡፡ የምትመድበው በጀት የመግዛት አቅሙ ምን ያህል ነው? ምን ያህል የማስፈጸም አቅም አለው? አንደኛው ኢኮኖሚው በአሥር ዓመት ጊዜ ውስጥ በ10 እና በ11 በመቶ እያደገ ነው፡፡ በዚያው ልክ የሚሰበሰበው የታክስ ገቢ ይጨምራል፡፡ አሥር ዓመት ቀላል አይደለም፡፡ ሁለተኛው በኢትዮጵያ ሁኔታ ትልቁ ምክንያት የዛሬ አሥር ዓመት ምናልባት በአሥር ብር እንገዛቸው የነበሩ ዕቃዎች ዛሬ አንድ መቶ ብር ገብተዋል፡፡ ምናልባት ወደ አሥር እጥፍ ማለት ነው ዕድገቱ፡፡ በተለይ በዚያን ጊዜ አካባቢ የዋጋ ንረት ከፍተኛ ነበር፡፡ ትልቅ መሟሟቅ ነበር፡፡ በአብዛኛው መንግሥት የሚመራው የመሠረተ ልማት ግንባታ ነበር፡፡ ምንም መሠረተ ልማት ለሌላት አገር ኮብልስቶን፣ ኮንስትራክሽን፣ የመንገድ ሥራ፣ የዩኒቨርሲቲዎች ግንባታ፣ የቤቶች ልማት በሙሉ ትልልቅ የመሠረተ ልማት እንቅስቃሴዎች ናቸው፡፡ ይህን ስታደርግ ወጪ ይጨምራል፡፡  እነዚህ ግንባታዎች ለምርት ያላቸው አስተዋጽኦ ዘግይቶ ነው የሚታየው፡፡ እንደምታስታውሰው ከፍተኛ የዋጋ ንረት ነበር፡፡ በአሥር ዓመት ጊዜ ውስጥ ዋጋ በብዙ እጥፍ ጨምሯል፡፡ ካሰላነው በጊዜ ዋጋ መሆን አለበት፡፡

የዛሬውን በጀት በሚሊኒየም ከነበረው ዋጋ ጋር ብታሰላው ትልቅ አይደልም፡፡ የሚሊኒየሙ በጀት 43,947,669,337 ብር ነበር፡፡ የአሁኑ በጀት 320.8 ቢሊዮን ብር ነወ፡፡ አሁን የተያዘው 320.8 ቢሊዮን ብር በጀት በ2000 ዓ.ም. በነበረው ዋጋ 110 ቢሊዮን ብር ብቻ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው በዋጋ ንረት የመጣ ነው፡፡ በአማካይ ዋጋ በሦስት እጥፍ አድጓል፡፡ በዚያ ወቅት በመቶ ብር ትገዛ የነበረው ዕቃ አሁን ሦስት መቶ ብር ነው እንደ ማለት ነው፡፡ ከመፈጸም አንፃር፣ ሥራ ከመሥራት አንፃር የምታየው የገበያ ዋጋን የሚያንፀባርቅ አይደለም፡፡ መነሻችን ይኼ ነው፡፡ በ2000 ዓ.ም. በሚሊኒየም ወቅት 43.9 ቢሊዮን ብር በጀት ሲቀርብ ጉድ ተብሏል፡፡ አሁን 320.8 ቢሊዮን ብር ደርሷል አሁን ይኼም ትልቅ ይመስላል፡፡ ነገር ግን በ650 በመቶ ዕድገት አለው፣ ነገር ግን በትክክለኛ ዋጋ ብታሰላው 155 በመቶ ብቻ ነው ሥራ የመፈጸም አቅሙ፡፡ ሌላው የተቀረው የዋጋ ንረት ነው፡፡

ሪፖርተር፡- የዘንድሮው በጀት ከ2009 በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀር ምን ገጽታ አለው?

ዶ/ር ሰዒድ፡-የ2010 ዓ.ም. በጀት ከ2009 ዓ.ም. በጀት ጋር ሲነፃፀር 17 በመቶ ያህል ዕድገት አሳይቷል፡፡ የ2009 በጀት ከ2008 በጀት ጋር ሲነፃፀር ዕድገቱ ተመሳሳይ ነው፡፡ የዋጋ ንረቱ ስምንት በመቶ ቢሆን፣ እስከ ዛሬም ስምንት በመቶ ስለነበር የተጣራ የስምንት በመቶ ዕድገት ይኖራል፡፡ በሁለት ከፍለን እንየው፡፡ ባለፈው ዓመት ተጨማሪ በጀት ነበር፡፡ መሀል ላይ ተጨምሯል፡፡ አሁን የምናወዳድረው በጀትን ከበጀት ጋር ነው፡፡ በጊዜው ዋጋ የይስሙላ ዋጋ (ኖሚናል) 17 በመቶ ዕድገት አሳይቷል፡፡ ነገር ግን ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር፣ የዋጋ ጭማሪም ስለሚኖር በጀቱ በመፈጸም አቅሙ የዋጋ ንረት ይደግማል ብለን ብናስብና ስምንት በመቶ ይሆናል ብንል፣ ዕድገቱ ስምንት በመቶ ይሆናል፡፡ መንግሥት ያቀዳቸውን ዕቅዶች ከማስፈጸም አንፃር ዕድገት አለ፡፡ ገንዘቡ ዕድገት አለው፡፡ ከመፈጸም አቅም አንፃር በስምንት በመቶ አድጓል፡፡

ሪፖርተር፡- ለ2010 ዓ.ም. የቀረበው በጀት ካለፉት ዓመታት ጋር ሲነፃፀር ከፍተኛ የበጀት ጉድለት አለበት፡፡ ይህንን የበጀት ጉድለት ከአገር ውስጥ ምንጮች ለመሸፈን ታቅዷል፡፡ የውጭ ብድርና ዕርዳታ የመቀነስ አዝማሚያ እያሳየ በመምጣቱ ከዋጋ ንረት አንፃር ኢኮኖሚው ላይ የሚኖረው ተፅዕኖ እንዴት ይታያል?

ዶ/ር ሰዒድ፡-የበጀት ጉድለቱ 53.9 ቢሊዮን ብር ነው፡፡ ይህን ስናወዳድር ሁለት ነገሮችን ማየት ይኖርብናል፡፡ አንደኛ ጉድለቱ በ2010 ዓ.ም. በሚኖረው ዋጋ ብታስበው የስምንት በመቶ ወይም የአሥር በመቶ የዋጋ ልዩነት ስለሚኖር ከዚህ አንፃር መታየት አለበት፡፡ ሁለተኛው ማየት ያለብን ከኢኮኖሚው አንፃር ሲታይ ይህ የዋጋ ጉድለት ምን ያህል ነው? ይህንን የበጀት ጉድለት የሚሸከም የኢኮኖሚ ዕድገት አለን ወይ? ባለፈው ዓመት በበጀት ተይዞ የነበረው የበጀት ክፍተት ወይም ጉድለት በአጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) በዕቅድ ተይዞ የነበረው ሁለት በመቶ ነው፡፡ ይኼ ዕቅድ ተተግብሯል ወይ የሚለውን የምናየው ይሆናል፡፡ በ2006 ዓ.ም. የበጀት ጉድለቱ ከአጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት 1.8 በመቶ ነው፡፡ በ2008 ዓ.ም. ደግሞ 2.9 በመቶ ነበር፡፡ አሁን ያለው የበጀት ጉድለት የፈለገውን ያህል ትልቅ ይምሰል እንጂ ከጂዲፒው ጋር ማየት ያስፈልጋል፡፡ መለኪያችን እሱ ነው፡፡

በ2010 ዓ.ም. በጀት ላይ በጊዜው ዋጋ 19 በመቶ ሊያድግ ይችላል፡፡ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ በተቀመጠው ጂዲፒ 11 በመቶ ያድጋል ቢባል፣ እዚህ ላይ የዋጋ ንረቱን ስምንት በመቶ ስትደምርበት 19 በመቶ የጂዲፒ ዕድገት ይኖራል፡፡ የአገር ውስጥ ምርት በጊዜው ዋጋ ሲሰላ በ19 በመቶ ዕድገት ይኖራል፡፡ እንደዚህ ከሆነ የአሪቱ ኢኮኖሚ ከ1.5 ትሪሊዮን ብር በላይ ነው፡፡ ስለዚህ ይኼንን 53.9 ቢሊዮን ብር የበጀት ጉድለት ስታሰላው 3.5 በመቶ ያህል ነው፡፡ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ከተያዘው አንፃር ሲትይ ትንሽ ሞቅ ብሏል፡፡ የ0.5 በመቶ ጭማሪ አለው፡፡ ይኼ ምንም ማለት አይደለም፡፡ ኢኮኖሚው ከዚህም በላይ ሊያድግ ይችላል፡፡ ትልቁ ነገር ጉድለቱን የምንሸፍንበት መንገድ ነው፡፡ በአገር ውስጥ አቅም መሸፈን ስንችል ትልቅ ነገር ሊሆን ይችላል፡፡ ክፍተቱን በሁለት ከፍለን እንየው፡፡ አንዱ በዋጋ ንረት ሁለተኛው አጠቃላይ ያሰብናቸውን ዕቅዶች ከማሳካት አንፃር እንየው፡፡ እንግዲህ ክፍተቱን ለመሙላት ገንዘብ ማተም ሊሆን ይችላል፡፡ ቦንድ መሸጥ ሊሆን ይችላል፡፡ በእነዚህ በምንሸፍንበት ጊዜ ከዋጋ ንረት በተጨማሪ ሌላ ችግር ሊፈጥር ይችላል፡፡

የዋጋ ንረትን ለመቋቋም አንድ መውጪያ አለን፡፡ የግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ ምርታማ ከሆነ ንረቱን የማረጋጋት ድርሻው ከፍተኛ ይሆናል፡፡ ከባድ የሚሆነው ግን ጂቲፒ የሚያስበው መዋቅራዊ ለውጥ እንዲመጣ ነው፡፡ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ በተለይም ወደ ማኑፋክቸሪንግ መዋቅራዊ ለውጥ እንዲመጣ ይፈልጋል፡፡ ግብርና በተፈጥሮው ከውጭ የሚገቡ ግብዓቶችን አይፈልግም፣ ቢበዛ ማዳበሪያ ይፈልጋል፣ ግብርና ያለማዳበሪያ ሊሠራም ይችላል፡፡ ምን ማለት ነው? ግብርና ብዙ ካፒታል ሳይሆን ብዙ ሠራተኛ የሚፈልግ ነው፡፡ ወደ ማኑፋክቸሪንግ ለመግባት ሲታሰብ ግን ለሚኖሩት ግብዓቶች ካፒታልና ቴክኖሎጂ ያስፈልጋሉ፡፡ ጥሬ ዕቃ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህ ስለሌሉን ከውጭ ነው የምናስገባው፡፡ ጥሬ ዕቃ ከማስመጣት ገና አልተላቀቅንም፡፡ ቆርቆሮ እንኳ ለማምረት የምንጨምረው እሴት ቆርቆሮ ማጠፍ በሆነበት መሠረታዊ ግብዓቱን ከውጭ ማስገባት ይጠይቃል፡፡ ጥጥ እንኳ ከውጭ እናስገባለን፡፡ ጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ ላይ እየተረባረብን ባለንበት ወቅት ጥጥ ከውጭ ይገባል፡፡ የጥጥ ምርት ስለሌለ ማለት ነው፡፡ ቢኖርም ዘለቄታዊ አይደለም ይቆራረጣል፡፡ ሁሉንም በአገር ውስጥ ማምረት እስክንጀምር ከውጭ ማስገባታችንን እንቀጥላለን፡፡ ከውጭ የምናስገባው ደግሞ በብር አይደለም፣ በውጭ ምንዛሪ ነው፡፡ በውጭ ምንዛሪ በሚሆንበት ጊዜ የቱንም ያህል ገቢ በአገር ውስጥ ብታሰባስብም እነዚህን ግብዓቶች በብር ልታስገባ አትችልም፣ የውጭ ምንዛሪ ያስፈልጋል፡፡

የውጭ ምንዛሪ የሚገኙባቸው የታወቁ ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ከኤክስፖርት፣ ከውጭ በዕርዳታና በብድር፣ በውጭ የሚኖሩ ሰዎች የሚልኩት ነው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ በእጃችን ላይ ያለው ኤክስፖርት ነው፡፡ ኤክስፖርት ደግሞ ያለው አፈጻጸም ደካማ ነው፡፡ የውጭ ዕርዳታ እየቀነሰ ነው፡፡ ለምግብ ዕርዳታ እንኳ እየቀነሰ ነው፡፡ ብድር አስቸጋሪ ነው፡፡ የውጭ ብድር የሚመሠረተው በኤክስፖርት አፈጻጸም ጥንካሬ ነው፡፡ የአበዳሪዎች ዋነኛው ጥያቄ መክፈል ይችላሉ ወይ ነው፡፡ እንዲህ ከሆነ የበጀት ጉድለት ባይኖር እንኳ በጀቱ በአገር ውስጥ ቢሸፈን እንኳ፣ ይኼን 320.8 ቢሊዮን ብር እዚሁ ብንሸፍን በብር አሁን ባለንበት ሁኔታ ትራንስፎርሜሽኑ ያቀደቸውን ከማሳካት  አንፃር የውጭ ምንዛሪ የግድ ነው፡፡ ስለዚህ ትርጉም ባለውና ከአጠቃላይ በጀቱ ውስጥ ጎላ ባለ ደረጃ በውጭ ምንዛሪ መገኘት አለበት፡፡

ሪፖርተር፡- በ2010 በጀት ዓመት ከአገር ውስጥ 221 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዷል፡፡ በ2009 ዓ.ም. ይሰበሰባል የተባለው ሁሉ ካለመሰብሰቡ አንፃር የሚሰካ ይመስልዎታል?

ዶ/ር ሰዒድ፡-ማሳካት ይቻላል፡፡ ምናልባት ካለፈው ዓመት ዕቅድ ጋር ሲወዳደር ጥናቶች እንደሚያመለክቱት ዕቅዱን ማሳካት ይቻላል፡፡ በ2009 ዓ.ም. መንግሥት በአብዛኛው በሌሎች ሥራዎች በተለይም በፖለቲካ ተጠምዶ ነበር፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ወቅቶች መንግሥት ሠራም አልሠራም የሰዎች አስተሳሰብ ለወጥ ይላል፡፡ አንዳንዴም ማባበል ይኖራል፡፡ ነገር ግን በሌሎች ሥራዎች መወጠር ሲኖር ያልታዩ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ጥናቶች እንደሚያመለክቱት ገና አልተነካም፡፡ ወደፊት እንደ ኢኮኖሚው ይወሰናል፡፡ ጥያቄው እንዲያውም ኢኮኖሚው ያመነጫል ሳይሆን፣ መሰብሰብ ያለበት ገቢ እየተሰበሰበ አይደለም ነው ቁም ነገሩ፡፡

ሪፖርተር፡- ከአጠቃላይ በጀቱ ውስጥ 45 ቢሊዮን ብር ያህል ከውጭ በሚገኝ ገንዘብ ለመሸፈን ታቅዷል፡፡ አገሪቱ ብዙ ብድር ያለበት እንደመሆኑ ተፅዕኖ አይፈጥርም?

ዶ/ር ሰዒድ፡-አንፃራዊ ነው፡፡ አሁን ባለው ብድር ላይ ባናበዛ ጥሩ ነው፡፡ አሁን ያለውን የኤክስፖርት አፈጻጸም ማስተካከል ያስፈልጋል፡፡ አሁን ያለውን የዕርዳታና የብድር አሰጣጥ አዝማሚያ ብዙም ተስፋ ባናደርግበት መልካም ነው፡፡ አንድ ነገር ግን ማድረግ ይቻላል፡፡ ቅድሚያ የሚሰጠው፣ ለኤክስፖርት ነው፡፡ ኤክስፖርቱ ላይ መረባረብ ያስፈልጋል፡፡ ከኤክስፖርት የሚገኘው ገቢ በዋጋ ቀንሷል? አዎ ቀንሷል፡፡ ዓለም አቀፍ አንድምታ አለው፡፡ ይህን የምናካክሰው በምንድነው? የምንልከውን ምርት መጠን በመጨመር ነው፡፡ ጥራቱን ማረጋገጥ አለብን፡፡ ለኤክስፖርት ታስበው የነበሩ ፕሮጀክቶችን የሞት ሽረት ትግል አድርጎ መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ሌላኛው ሬሚታንስ ነው፡፡ በይፋ የገባ ሬሚታንስ ይፋ ባልሆነ መንገድ ይወጣል፡፡ እዚህ ላይ መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን ዋናው ከውጭ የምናስገባውን እዚህ ማምረት መቻል ይኖርብናል፡፡

ሪፖርተር፡- የአገሪቱን የውጭ ምንዛሪ ግኝት በሰፊው ያሻሽላሉ የተባሉ መንግሥታዊ ፕሮጀክቶች ይጠናቀቃሉ ከተባለበት ጊዜ እጅግ የዘገዩ አሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል ስኳርና ከስኳር ተረፈ ምርት ይገኛል የተባለው ኢታኖል፣ የማዳበሪያ ፋብሪካ ፕሮጀክቶች፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ እነዚህ በወቅቱ መድረስ ባለመቻላቸው ኢኮኖሚውን መደገፍ አልቻሉምና ተፅዕኖው እንዴት ይገለጻል?

ዶ/ር ሰዒድ፡- እንዲህ ዓይነት ፕሮጀክቶች ትልቅ ጥንቃቄ ይፈልጋሉ፡፡ አርበኛ መሆን ይጠይቃል፡፡ እያንዳንዳቸው የሚያማልሉ ዕቅዶች አገርን የሚያሳድጉ፣ ከልመና የመውጣት ልዕልና የማጎናፀፍ አቅም ያላቸው ፕሮጀክቶች ናቸው፡፡ ምክንያቱን አላውቅም የሙስናውን ነገርና ሌላ ሌላውን ተወውና አንደኛ ስናቅድ ለዕድገት ከመጓጓታችን የተነሳ በአገር ውስጥ አቅም መሥራት ፈልገን ይሆናል፡፡ አንዱ ችግር ይኼ ነው፡፡ ግብርና የእኛ ባህል ነው፡፡ እንጀራ መጋገርና ወጥ መሥራት እንችላለን፡፡ ከቴክኖሎጂና ከብረት ጋር መታገል የእኛ ባህል አይደለም፡፡ በአንድ ሌሊት ሊመጣ አይችልም፡፡ ጥርስህን ልትነቅልበት ይገባል፡፡ እኛ ምንም በማናውቀው ነገር ሌሎች ባህል ባደረጉት ሥራ ላይ ስንገባ አርበኝነት አንግበን ብቻ ሊሆን አይገባም፡፡ ቴክኖሎጂውን ለመማር ጊዜ ያስፈልጋል፡፡ ቴክኖሎጂውን እስክንማር ድረስ ጊዜው ስለማይጠብቀን ኮንትራት ሰጥተን ልናሠራ ይገባል፡፡ ይኼ ሲሆን ከፕሮጀክቱ እዚህና እዚያ የሚቆነጠር ነገር ላይኖር ይችላል፡፡ ስለዚህ ስህተት የሠራን ይመስለኛል፡፡

ሪፖርተር፡- የአገሪቱ ኢኮኖሚ እያደገ ቢሆንም የዚያኑ ያህል የሕዝብ ቁጥር ዕድገቱ ከፍተኛ በመሆኑ፣ የሚገነቡ የመሠረተ ልማት አውታሮች እየተዋጡ ነው የሚል ሐሳብ ይደመጣል፡፡ ከዚህ አንፃር የሕዝብ ቁጥር ከኢኮኖሚው ጋር ያለው አንድምታ ምን ይመስላል?

ዶ/ር ሰዒድ፡- ሕዝብን ምንም አታደርገውም፡፡ በመጀመርያ ደረጃ የኢትዮጵያ ሕዝብ ብዙ ነው፡፡ መሠረቱም ሰፊ ነው፡፡ ምንም አታደርገውም፡፡ ምንም ከማታደርጋቸው ነገሮች አንዱ የሕዝብ ቁጥር ነው፡፡ ቀጥሎ ያለው የምታቅደው ዕድገት ነው፡፡ የሕዝብ ቁጥራችን ለእኔ መባረክ ነው፡፡ ጥሩ ጎኑን ማየት ያስፈልጋል፡፡ በሌላ ጎኑ ችግር አለው፡፡ የሕዝብ ቁጥር ዕድገት ለደካማ አገር ችግር ነው፡፡ እኛ የኢትዮጵያ ሕዝብ በዛ የምንለው አቅማችን ዝቅተኛ ስለሆነ ነው፡፡ ሰፊ አገርና ሰፊ ሀብት ይዘን የሕዝብ ቁጥራችን ጥንካሬ ሊሆነን ይገባል፡፡ 

 

 

Standard (Image)

የኤርትራና ጂቡቲ ሰሞነኛው ጉዳይና የኢትዮጵያ አሠላለፍ

$
0
0

 

ኤርትራና ጂቡቲ በመካከላቸው ባለውና ዱሜራ እየተባለ በሚጠራው ተራራማ ደሴት ላይ ለዘመናት ሲወዛገቡ ቆይተዋል፡፡ ይህ በቀይ ባህር ጠረፍ ዳርቻ የሚገኘው ተራራማ አካባቢ ለወታደራዊ ዓላማ ካለው ፋይዳ የተነሳ፣ ሁለቱ አገሮች በተለያዩ ጊዜያት ሲነታረኩበት ቆይተዋል፡፡ ዱሜራ ወይም ራስ ዱሜራ እየተባለ የሚጠራው ሥፍራ ከቀይ ባህር የሚነሳና ዙሪያውን በውኃ የተሸፈነ ደሴት እንደሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ኤርትራና ጁቡቲ በዚህ የድንበር አካባቢ አማካይነት ከሁለት ጊዜ በላይ ደም አፋሳሽ ጦርነት ውስጥ ማሳለፋቸውን የሁለቱ አገሮች የታሪክ ማኅደር ያስረዳል፡፡

እጅግ አነስተኛ የሆነ የሕዝብ ቁጥር ያላቸው ሁለቱ አገሮች የወደብ ባለቤቶች ናቸው፡፡ ኤርትራ የምፅዋና የአሰብ ወደቦች ባለቤት ነች፡፡ ጂቡቲ ደግሞ የዶራሌ፣ የጂቡቲና የታጁራ ወደብ ባለቤት ነች፡፡ ሁለቱ አገሮች ተፈጥሮ ከሰጣቸው አቀማመጥ የተነሳ ለወታደራዊ ዓላማና ለንግድ ሥራ ተፈላጊ ናቸው፡፡ የሁለቱ አገሮች ከቀይ ባህር ጋር በቀጥታ መገናኘት ደግሞ የተፈላጊነታቸውን መጠን ከፍ ያደርገዋል፡፡ ይህ አካባቢ የዓለም ሕዝብ በተለይም የዓረብና የአውሮፓ አገሮች ዓይን ማረፊያ ነው፡፡

አውሮፓውያን አፍሪካን በቀኝ ግዛት ለመከፋፈል ዕቅድ ሲወጥኑ በጂቡቲና በኤርትራ በኩል ያለውን አካባቢ ለመቆጣጠር የነበራቸው ፍላጎትና የእርስ በርስ ሽኩቻ፣ የሁለቱ አገሮች ተፈላጊነት ከፍ ያለ መሆኑን ማሳያ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ጣሊያን ቀይ ባህር የሚያዋስነውን አካባቢ ለመያዝ ያደረገችው እሽቅድምድም ከፍተኛ እንደነበር ታሪክ ይናገራል፡፡ አውሮፓዊቷ አገር ፈረንሣይ ደግሞ በምሥራቅ አፍሪካ በተለይም በጂቡቲ በኩል ያለውን አካባቢ ለመቆጣጠር ወታደራዊ ቤዟን በዚህ አካባቢ በማሥፈርና መሠረት በመያዝ ወደ ሌሎች የአፍሪካ አገሮች ግዛቷን ለማስፋፋት ያደረገችው ሙከራ፣ ለዚህ ቦታ ተፈላጊነት ማሳያ ተደርጎ ይቆጠራል፡፡ እነዚህ አውሮፓዊ አገሮች በኤርትራና በጂቡቲ መካከል የሚያዋስነውን ግዛት በተመለከተ እ.ኤ.አ. በ1935 ስምምነት አድርገዋል፡፡ በስምምነቱ መሠረትም ይህንን አካባቢ ከወታደራዊ ቀጣና ነፃ ለማድረግ ጥረት ተደርጓል፡፡

እ.ኤ.አ. በ1996 ኤርትራ ዱሜራ አካባቢ ጦሯን በማሠለፍ ከጂቡቲ ጋር ወደ ጦርነት ገብታለች፡፡ ጉዳዩን ጂቡቲ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የፀጥታው ምክር ቤት ብታቀርብም ዘላቂ መፍትሔ ሳይሰጥ እንደቀረ ይነገራል፡፡ በወቅቱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ ጉዳዩ ለአፍሪካ ቀንድ አገሮች ከፍተኛ ሥጋት እንደሆነ አመልክተው በአስቸኳይ መፈታት እንዳለበት አሳስበው ነበር፡፡ እ.ኤ.አ. በ2004 በሁለቱ አገሮች መካከል በነበረው ግጭት 44 ያህል የጂቡቲ ወታደሮች ሲገደሉ ከ55 በላይ የሚሆኑት ደግሞ እንደቆሰሉ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በኤርትራ በኩል ደግሞ 100 ያህል ወታደሮች ተገድለዋል፣ 100 ወታደሮች ተማርከዋል፣ 21 ያህሉ ደግሞ ቆስለዋል፡፡ በወቅቱም የጂቡቲ ፕሬዚዳንት እስማኤል ኦማር ጊሌ፣ ‹‹ሁሌም ወዳጆች ነበርን፡፡ አሁን የራሳችንን መሬት በጉልበታቸው ለመውረር መጡ፡፡ እኛ ደግሞ ተገቢውን ዕርምጃ ወስደናል፤›› ብለው ተናግረው ነበር፡፡ በወቅቱ የአሜሪካ የመከላከያ ኃይል ደኅንነት ኤጀንሲ ይፋ ባደረገው መረጃ መሠረት ጂቡቲ 18,000 ያህል ወታደሮቿን ለጦርነቱ ዝግጁ ስታደርግ፣ ኤርትራ በበኩሏ ከ200,000 በላይ አዘጋጅታ ነበር፡፡

ለብዙ ዓመታት ያህል በፈረንሣይ እጅ የቆየችው ጂቡቲ በኤርትራ ጦርነት ሲታወጅባት ቅድሚያ ከጎኗ ከተሠለፉ አገሮች መካከል ፈረንሣይ አንዷ እንደነበረች ተጠቁሟል፡፡ የፈረንሣይ መንግሥት ለጂቡቲ ማንኛውንም ድጋፍ ለማድረግ ቃል ገብቶ ነበር፡፡

የኤርትራ መንግሥትን የጂቡቲ ወረራ ለማስቆም ጣልቃ ከገቡ የዓለም አቀፍ ተቋማት መካከል ቀዳሚው የዓረብ ሊግ ነው፡፡ ኤርትራ ከአውሮፓ አገሮች ጋር ባላት የቆየ ጥላቻ በሁለቱ አገሮች መካከል ሊካሄድ ታስቦ የነበረውን የድንበር ግልግል አውሮፓውያን እንዳያዩት ኤርትራ ያደረገችው ጥረት ከፍተኛ እንደነበር የተለያዩ ሚዲያዎች ዘግበውታል፡፡

በመርህና በፖሊሲ ደረጃ ከአውሮፓና ከአሜሪካ የተለየ አቋም ይዞ ብቅ ያለው የኢሳያስ አፈወርቂ መንግሥት ኤርትራንና ሕዝቦቿን፣ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከተለያዩ አገሮች ጋር ያለውን ግንኙነት አቋርጧል፡፡ በዚህም የተነሳ ፊቱን ወደ ዓረብ አገሮች በማዞር ሳዑዲ ዓረቢያ በምትዘውረው የገልፍ አገሮች ስብስብ ታዛቢ አባል ከመሆን ባሻገር፣ በአገሪቱ የዓረብኛ ቋንቋ ትምህርት እንዲሰጥ አድርጓል፡፡

ኢሳያስ አፈወርቂ መራሹ የኤርትራ መንግሥት፣ በአገሪቱ አንድም ቀን ምርጫ ሳያካሂድ ከሃያ ዓመታት በላይ በሥልጣን ላይ ቆይቷል፡፡ የቀይ ባህርን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ፊታቸውን ወደ ኤርትራ ካዞሩ የዓረብ አገሮች መካከል ሳዑዲ ዓረቢያ፣ ግብፅና ኳታር ይገኙበታል፡፡ እነዚህ የዓረብ አገሮች በቀጣናው ለመስፋፋትና ወታደራዊ ይዞታ ለማግኘት ሲሉ ኤርትራን በአንድም ሆነ በሌላ ሲረዷትና ሲደግፏት እንደቆዩ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ከዓባይ ወንዝ ጋር ለብዙ ዘመናት እሰጥ አገባ ውስጥ የቆየችው ኢትዮጵያም ጉዳዩን በአንክሮ ስትከታተለው እንደቆየችና አሁንም ድረስ እየከታተለችው ለመሆኑ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

ኢትዮጵያና ኤርትራ ከደርግ መንግሥት መውደቅ በኋላ ራሳቸውን የቻሉ ሉዓላዊ አገሮች ቢሆኑም፣ በወዳጅነት መዝለቅ የቻሉት ግን ለጥቂት ዓመታት ብቻ ነው፡፡ ኤርትራ በዱሜራ ግዛት ላይ በተደጋጋሚ ጊዜ ወረራ እንደምታካሂደው ሁሉ፣ የኢትዮጵያ ግዛት በሆኑት በባድሜና ሽራሮ ላይም ወረራ በማካሄድ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለመድፈር ሞክራለች፡፡

በ1990 ዓ.ም. የተጀመረው የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት በሁለቱ አገሮች መካከል በብዙ ሺሕ የሚቆጠር የሰው ሕይወትና በሚሊዮን የሚቆጠር ንብረት መውደም ምክንያት ሆኗል፡፡ የኤርትራ ጠብ አጫሪነትን በተለይም በምሥራቅ አፍሪካ አገሮች መካከል ሁከትና ብጥብጥ እንዲኖር እየሠራች ነው ሲል፣ የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ሳይቀር ወንጅሏታል፡፡ ድርጅቱ ከውንጀላም አልፎ ማዕቀብ ጥሎባታል፡፡ ማዕቀቡ እስከዛሬ ድረስ ያልተነሳለት በመሆኑ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ኪሳራ እያደረሰባት ነው የሚሉ መረጃዎች እየወጡ ባለበት ጊዜ፣ ከጂቡቲ ጋር ወደ ሌላ ጦርነት ለመግባት እየተዘጋጀች እንደሆነ ሰሞኑን ተነግሯል፡፡  

በጂቡቲና በኤርትራ መካከል የነበረውን የድንበር ውዝግብ ለመፍታት በቦታው ተሰይመው የነበሩ የኳታር ወታደሮች ከሳምንት በፊት አካባቢውን ለቀው ሲወጡ፣ ኤርትራ ወታደሮቿን በአካባቢው እንዳሠለፈች የጂቡቲ መንግሥት አስታውቋል፡፡

የዓረብ ባህረ ሰላጤ አገሮች ከኳታር ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ካቋረጡ በኋላ፣ ኳታር ወታደሮቿን ከጂቡቲና ኤርትራ ድንበር አስወጥታለች፡፡ የኳታር መንግሥት አሸባሪዎችን ይረዳል ተብሎ ሲወነጀልና ሲከሰስ ቆይቶ ኢራን ከገልፍ አገሮች ስብስብ እንዲወጣ ተደርጓል፡፡ በዚህም የተነሳ የኳታር መንግሥት በመገለሉ ከወሰዳቸው ዕርምጃዎች መካከል ዋነኛው ጉዳይ ወታደሮቹን ከሁለቱ አገሮች ድንበር ማስወጣቱ እንደሆነ በመገናኛ ብዙኃን ተዘግቧል፡፡ ወታደሮቹን ለማስወጣት የወሰነው ደግሞ የኤርትራ መንግሥት ከሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት ጎን መሠለፉን ባስታወቀ ማግሥት እንደሆነ አስረድቷል፡፡

ኢትዮጵያን በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ለመጉዳትና የተለመደ የጠብ አጫሪነት አባዜውን ለመወጣት ሁሌም ሳዑዲ ዓረቢያንና ግብፅን ተከትሎ እንደሚሄድ የሚነገርለት የኤርትራ መንግሥት፣ በቀጣናው የበላይ ሆኖ ለመታየትና የተለመደ የማተራመስ አጀንዳውን ለማራመድ ሲል የአሰብ ወደብን ለሳዑዲ መራሹ ኃይል ከማከራየት ጀምሮ የግብፅ መንግሥት በወደቡ አካባቢ ወታደራዊ ቀጣና እንዲኖረው እያደረገ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ፡፡

እ.ኤ.አ. ሰኔ 24 ቀን 2008 የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት በኒውዮርክ የጂቡቲው ጠቅላይ ሚኒስትር መሐመድ ዳይሌታና የኤርትራው አምባሳደር በተገኙበት ሁለቱን አገሮች በሚያወዛግባቸው ዱሜራ ጉዳይ ላይ ስብሰባ አካሂዶ ነበር፡፡ ከወራት በፊት ጉዳዩን እንዲያጠራ ተልኮ የነበረው የፀጥታው ምክር ቤት አጣሪ ኮሚቴም በዱሜራ አካባቢ ለጦርነት ዝግጁ የሆነው የኤርትራ ጦር ለቀጣናው ብሎም ለአፍሪካ ከፍተኛ ሥጋት እንደሆነ ሪፖርት አቅርቧል፡፡ የፀጥታው ምክር ቤት ባስቀመጠው መሥፈርት መሠረት ጅቡቲ ወታደሮቿን ከአካባቢው ብታስወጣም፣ የኤርትራ መንግሥት እንቢ እንዳለ ለምክር ቤቱ ቀረበ፡፡ የፀጥታው ምክር ቤት እ.ኤ.አ. ጥር 14 ቀን 2009 ባካሄደው ስብሰባ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡ ይህ ውሳኔ የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ውሳኔ ‹‹ቁጥር 1862›› እየተባለ የሚጠራ ሲሆን፣ የኤርትራ መንግሥት በአምስት ሳምንታት ውስጥ ጦሩን ከአካባቢው እንዲያስወጣ ውሳኔ የሰጠ ነው፡፡

ከፀጥታው ምክር ቤት ጋር ብዙም የማትጣጣመው ኤርትራ ውሳኔውን ወደኋላ በመግፋት ለጦርነት ዝግጁ ሆና እንደነበርም በወቅቱ ተገልጿል፡፡ በአሜሪካና በአውሮፓ አገሮች ዘዋሪነት ይንቀሳቀሳል በማለት የምትወነጅለው የፀጥታውን ምክር ቤት ውሳኔ ኤርትራ ሳትቀበለው ቀርታለች፡፡ ገና ወደ ሥልጣን ሲመጣ ጀምሮ ለአሜሪካና አውሮፓ አገሮች ብዙም ፊት ያልሰጠው የኤርትራ መንግሥት፣ ራሱን ለተሻለ ጦርነት ዝግጁ ለማድረግ ሲንቀሳቀስ እንደነበር የጂቡቲ መንግሥት በወቅቱ አስታውቋል፡፡

የኋላ ኋላ የአፍሪካ ኅብረትን ይሁኝታ አግኝቶ ወደ አደራዳሪነት የመጣው የኳታር መንግሥት በኤርትራ በኩል ተቀባይነት ለማግኘት ችሏል፡፡ ተፈጥሮ በነበረው ውዝግብ ከስምንት ዓመት በላይ በኤርትራ ታስረው የነበሩ የጂቡቲ ወታደሮችን በማስለቀቅ እርቀ ሰላም ማምጣት የቻለው የኳታር መንግሥት፣ እ.ኤ.አ ከ2010 ጀምሮ በሁለቱ አገሮች ድንበር መካከል 400 ያህል ወታደሮቹን አሰማርቶ ቆይቷል፡፡

ለዓረብ አገሮች ጆሮው እንደሚከፈት የሚነገረው የኤርትራ መንግሥትም በጉዳዩ ላይ በመስማማት ጦሩን ከአካባቢው ለማስወጣት ስምምነት ላይ ደርሶ ነበር፡፡ እ.ኤ.አ. ከሰኔ 10 ቀን 2010 ጀምሮ በሥፍራው የነበረው የኳታር ጦር ግን ባለፈው ሳምንት አካባቢውን ለቆ ወጥቷል፡፡

አልሸባብንና ሌሎች አሸባሪ ቡድኖችን እንደሚረዳ ተደርሶበት ማዕቀብ የተጣለበት የኤርትራ መንግሥት፣ ከኳታር ጋር የነበረውን የሁለትዮሽ ግንኑነት እንዳቋረጠ ሰሞኑን የሚወጡ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ከሳዑዲ ዓረቢያና ከግብፅ መንግሥታት ሁለንተናዊ ድጋፍ እንደሚያገኝ የሚነገርለት የኤርትራ መንግሥት፣ ከኳታር ጋር ገንብቶት የነበረውን የሁለትዮሽ ግንኙነት መቋረጡን ኳታር ይፋ አድርጋለች፡፡

በአፍሪካ በተለይም በምሥራቅ አፍሪካ ሥጋት እየሆነ የመጣውን አልሸባብ በመደገፍና በማስታጠቅ ቀጣናውን በተለይም ኢትዮጵያንና ጎረቤት አገሮችን ለማተራመስ ሌት ከቀን እንደሚሠራ የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) በተደጋጋሚ ጊዜ ሪፖርት አቅርቧል፡፡ አሁንም ድረስ ከድርጊቱ መቆጠብ እንዳልቻለ የሚነገርለት የኤርትራ መንግሥት፣ ከጂቡቲ ጋር ተፋልሞ የግዛት ማስፋፋት ምኞቱን ለማሳካት እየሠራ እንደሆነ ሚስተር ፓወፒ ራውኒ የተባሉ በኡጋንዳ የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ለፍራንስ 24 የእንግሊዝኛው ጣቢያ ተናግረዋል፡፡ ፓወፒ እንደሚሉት የኤርትራ መንግሥት የማተራመስ ተግባሩን የጀመረው ከኢትዮጵያ ነው፡፡ ይህ ድርጊቱን በማስፋፋት አልሻባብን እየረዳና እየደገፈ ለአቅም አዳም እንዳደረሰው ይናገራሉ፡፡ ዛሬ ደግሞ ለሌላ ጦርነት ከጂቡቲ ጋር እንደተጫጨ ገልጸዋል፡፡

ከስድስት ሚሊዮን የማይበልጥ የሕዝብ ቁጥር ይዞ የግዛት ማስፋፋት ምኞት ያለው የኤርትራ መንግሥት መከታ የሚያደርገው የባህረ ሰላጤው አገሮችን እንደሆነ በቅርቡ እየወጡ ያሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ከወታደራዊ ሎጂስቲክስ ጀምሮ ሌሎች መሠረታዊ ጉዳዮችን ከዓረብ አገሮች እንደሚያገኝ በተለያዩ ጊዜያት የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ሳዑዲ ዓረቢያን ከፊቱ፣ ግብፅን ደግሞ ከጎኑ አድርጎ እንደሚንቀሳቀስ እየተነገረ ያለው የኢሳያስ አፈወርቂ መንግሥት፣ እነሱ በጉንፋን ከተያዙ እሱም ተይዞ ያድራል የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡    

ኢትዮጵያና ኤርትራ ጦርነትም ሆነ ሰላም በሌለበት ቀጣና ውስጥ መኖር ከጀመሩ በርካታ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ የኤርትራ መንግሥት በተለያዩ ጊዜያት ድንበር አካባቢ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን አፍኖ በመውሰድ የጉልበት ሥራ ከማሠራት ባሻገር፣ በእስር እያንገላታ መሆኑን በተለያዩ ጊዜያት ተገልጿል፡፡ ባለፈው ዓመት በትግራይ ክልል በማዕድን ቁፋሮ ተሰማርተው የነበሩ ኢትዮጵያውያንን አፍኖ በመውሰድ ከፍተኛ የሆነ ብዝበዛ አድርሶባቸው እንደነበር ታፍነው ተወስደው የተመለሱ ዜጎች ተናግረዋል፡፡

በ2009 ዓ.ም. ደግሞ ወደ ኢትዮጵያ ክልል ገብቶ በድንበር አካባቢ የሚኖሩ ዜጎችን አፍኖ ለመያዝና ጥቃት ለማድረስ ያደረገው ሙከራ ይታወሳል፡፡ በዚህም የተነሳ ለአንድ ሳምንት ያክል በሁለቱ አገሮች መካከል ከፍተኛ ውጥረት ነበር፡፡ ከኢትዮጵያ ጋር ይህን የመሰለ ግንኙነት ያላት ኤርትራ ሰሞኑን ደግሞ ፊቷን ወደ ጂቡቲ አዙራለች፡፡ የጂቡቲን ሉዓላዊነት በመድፈር በቀይ ባህር አካባቢ ወሳኝ የሆነውን የባቤል መንደብ ለመቆጣጠር ሙከራ እያደረገች እንደሆነ የጂቡቲ መንግሥት አስታውቋል፡፡

በዚህ አካባቢ ተፅዕኖ ፈጣሪ መስሎ መታየት የኤርትራ ባህሪ ነው የሚሉት የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ይልቃል ጌትነት (ኢንጂነር)፣ በአገሩ ሕዝብ ላይ ድንበሩ እንደተወረረ ወሬ በመንዛት ለረጅም ጊዜ በሥልጣን ላይ መቆየት የሚፈልግ መንግሥት እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ የኤርትራ በጂቡቲ ግዛት ላይ አዲስ ወረራ ማካሄድ ለኢትዮጵያ ቀጥተኛ የሆነ ተፅዕኖ እንደሌለው የሚናገሩት ይልቃል፣ ‹‹የኤርትራ መንግሥት የሚለው በአልጀርሱ ይግባኝ የለሽ ውሳኔ ያገኘሁትን መሬትን ኢትዮጵያ ቀምታኛለች፡፡ ይህንን ደግሞ ያደረገችው ምዕራባውያን ከኢትዮጵያ ጎን በመሆናቸው ነው የሚል እምነት አለው፤›› ብለዋል፡፡

የዲስኮርስ መጽሔት ዋና አዘጋጅ የሆኑት አቶ ዳደ ደስታ ግን የኤርትራ በጂቡቲ ግዛት ወረራ ማካሄድ ለኢትዮጵያ ቀጥተኛ ተፅዕኖ እንዳለው ይገልጻሉ፡፡ አቶ ዳደ ሲያብራሩ የኢትዮጵያና ኤርትራ የሁለትዮሽ ግንኙነት ከቆመ ወዲህ ኢትዮጵያ የጂቡቲን ወደብ እንደምትጠቀም፣ ይህ ወደብ በተለይም ፖታሽ ይመረትበታል ከተባለው የታጁራ ወደብ ጋር በቅርብ ርቀት ያለ በመሆኑ በኢትዮጵያ የወጪና ገቢ ንግድ ላይ ቀጥተኛ ግንኙነት እንዳለው ይገልጻሉ፡፡ ሰሞኑን ኤርትራ እንደያዘችው የሚጠቀሰው የባቤል መንደብ ደግሞ ለእነዚህ ወደቦች ቅርብ በመሆኑ ለኢትዮጵያ ያለውን ቀጥተኛ ተፅዕኖ አስረድተዋል፡፡

‹‹ይህ አካባቢ በጣም ከፍተኛ ቦታ ከመሆኑ ባሻገር ወደ ቀይ ባህር አካባቢ አሻግረን ስናይ በዙሪያው ያሉ ብዙ ቦታዎችን ለማየት የሚያስችል ስፍራ ነው፤›› ያሉት አቶ ዳደ፣ ይህንን አካባቢ መያዝ ማለት ክፉ ዓላማ ላለው ኃይል በጣም ወሳኝ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ አካባቢው በጣም ብዙ የንግድ መርከቦች የሚተላለፉበት ነው፡፡ ኢትዮጵያ የባህር በር ባይኖራትም የቀይ ባህር ኃይል እየተባለች የምትጠራ አገር ነች፡፡ በአፍሪካ በተለይም በምሥራቅ አፍሪካ ያላት ተሰሚነትና ኃያልነት ዘላቂ ሊሆንና ሊረጋገጥ የሚችለው በቀይ ባህር አካባቢ ያለውን መዳረሻ ለሌሎች አገሮች መናኸሪያ እንዳይሆን ስትጠብቅና ስትከላከል እንደሆነ ይነገራል፡፡ ይህ ስትራቴጂካዊ አካባቢ ወደ እንደዚህ ዓይነት የሥጋት ቀጣና መሸጋገሩ ለኢትዮጵያ እንቅልፍ የሚነሳና የሚያናድድ ጉዳይ እንደሆነ አቶ ዳደ ተናግረዋል፡፡

በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳዮች ስትራቴጂ ጥናት ተቋም ውስጥ የጂኦ ፖለቲካዊ ጉዳዮች የሥራ ክፍል ኃላፊ አቶ አበበ ዓይነቴ በበኩላቸው፣ ጉዳዩን የአፍሪካ ኅብረት የያዘው ከመሆኑ ባሻገር የኤርትራ መንግሥት እንደከዚህ ቀደሙ በማናለብኝነት ስሜት የሄደበት ባለመሆኑና ጉዳዩን ለማጥናት ፈቃደኝነቱን በማሳየቱ፣ የዚያን ያህል የከፋ ጉዳት በኢትዮጵያም ሆነ በኤርትራ ሊያስከትል እንደማይችል ይገልጻሉ፡፡

የተለያዩ ባለሙያዎችና አስተያየት ሰጪዎች የኤርትራ በጂቡቲ ግዛት ወረራ ማካሄድ ለኢትዮጵያ መልካም አጋጣሚ እንደሆነ ሲናገሩ ተደምጧል፡፡ ለብዙ ዓመታት ለኢትዮጵያ ጋሬጣ ሆና ስታስቸግር የነበረውን የኤርትራ መንግሥት ከጂቡቲ ጋር በመተባበር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሥልጣን ማስወገድ ተገቢነት ላይ ሲከራከሩ ተደምጧል፡፡ አስተያየት ሰጪዎች ይህንን ይበሉ እንጂ፣ ኢትዮጵያ የባህር በር የሌላት አገር ብትሆንም በአገር ውስጥ ያልተረጋጋ ነገር ያላት በመሆኑ ወደዚህ ጉዳይ የምትገባ ከሆነ ብዙ ጣጣ ይዞባት ሊመጣ እንደሚችል ኢንጂነር ይልቃል ያስረዳሉ፡፡ አቶ ዳደ በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ ከጂቡቲ ጋር አብራ ኤርትራን ወደ መውጋት ከመግባቷ በፊት የተለያዩ ጥናቶች መሥራት እንደሚገባት ይናገራሉ፡፡ ኢትዮጵያ ወደዚህ ብትገባ ልታገኘውና ልታጣው የምትችለው ጉዳይ፣ ዓለም አቀፍ ሕጎች፣ በቀጣናው ያለው አሠላለፍና ሌሎች ዝርዝር ነገሮች መታየት እንደሚገባቸው ይገልጻሉ፡፡ አቶ አበበ ደግሞ ጉዳዩ ወደዚህ የሚያስገባ እንደማይሆን ያምናሉ፡፡ የአፍሪካ ኅብረትና የፀጥታው ምክር ቤት ጉዳዩን የያዙት ከመሆኑ በተጨማሪ፣ የኤርትራ የተለሳለሰ አቋም መኖር ችግሩ በሰላማዊ መንገድ ሊፈታ እንደሚችል እምነት እንዳላቸው ይገልጻሉ፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ መሠረት ሁለቱ አገሮች ተቀራርበው ችግሩን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ መፍታት እንዳለባቸው ይፋ አድርጓል፡፡ ችግሩንም ኢትዮጵያ በቅርብ እየተከታተለች እንደሆነ ይፋ አድርጓል፡፡ ይህንን ጉዳይ በቅርበት ለመከታተልና ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት ሲባል ኮማንድ ፖስት እንደተቋቋመ በተለያዩ ማኅበራዊ ሚዲያዎች እየተገለጸ ቢሆንም፣ ከኢትዮጵያ መንግሥት የተሰጠ መግለጫም ሆነ አስተያየት እስካሁን የለም፡፡ የአፍሪካ ኅብረት በበኩሉ ችግሩን ለመፍታት የልዑካን ቡድን በሚቀጥለው ሳምንት ወደ ሥፍራው እንደሚልክ አስታውቋል፡፡ ሁለቱ አገሮች ተቀራርበው በመነጋገር መፍታት እንደሚባቸው ተናግሯል፡፡ ጉዳዩን አስመልክቶ የፀጥታው ምክር ቤት ማክሰኞ ሰኔ 13 ቀን 2009 ዓ.ም. በዝግ ስብሰባ እንደሚመክርበት ለማወቅ ተችሏል፡፡

የኳታር ከቀጣናው መውጣት ማግሥት ጀምሮ ከሰሜን ኮሪያ ጋር ወዳጅነት ለመመሥረት ደፋ ቀና ሲል እንደታየ የሚነገርለት የኤርትራ መንግሥት ፀረ ምዕራባዊያን አቋሙን አሁንም እንዳላቆመ እየተነገረ ነው፡፡ የሰሜን ኮሪያ ፀረ ምዕራባዊ አመለካከት ከኤርትራ ጋር ወዳጅ እንዲሆኑ ከማድረግ ባሻገር ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ለማግኘት እንደሚረዳው ተነግሯል፡፡

ኳታር ጦሯን ከቀጣናው ማስወጣትና ጂቡቲ በኤርትራ ተወርሬያለሁ የማለቷን ውንጀላ በተመለከተ የኤርትራ መንግሥት ባወጣው መግለጫ መሠረት፣ እስካሁን ድረስ ኳታር ከቀጣናው ለምን እንደወጣች ለማወቅ እንዳልቻለና የጂቡቲን ወቀሳም ረጋ ብሎ በማጥናት ምላሽ እንደሚሰጥ ገልጿል፡፡

ኤርትራና ኢትዮጵያ በባህል፣ በቋንቋ፣ በሃይማኖትና በሌሎች ጉዳዮች ተመሳሳይነት ያላቸው በመሆኑ የሁለቱን አገሮች ችግር ለመፍታት ከባድ እንደማይሆን ኢንጂነር ይልቃል ይገልጻሉ፡፡ በሁለቱ አገሮች ላይ ሕዝቡ የመወሰን መብት ኖሮት ዴሞክራሲያዊ መንግሥት በሁለቱም አገሮች ከተመሠረተ ያለውን ችግር መፍታት እንደሚቻል ቢገልጹም፣ አቶ ዳደ ግን በኤርትራ በኩል ያለው የሰላም አማራጭ ዝግ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ የኤርትራ መንግሥት ከአሁን በኋላ ወደ ሰላማዊ መንገድ መጥቶ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ችግር ለመፍታት የሚችልበት ደረጃ ላይ አይደለም ይላሉ፡፡ መፍትሔው ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያ እጅ እንዳለም ይጠቁማሉ፡፡

ኢትዮጵያ የባህር በር የሌላት በመሆኗ፣ ጂቡቲ ደግሞ በሕዝብ ቁጥርም ሆነ በቆዳ ስፋት ትንሽ በመሆኗ ሁለቱን አገሮች የመነካካት፣ የማጨናነቅና አሸንፋለሁ የሚል ስሜት በኤርትራ በኩል እንዳለ አቶ ዳደ ይገልጻሉ፡፡ ይህንን ዓይነት የኤርትራ ሐሳብ ግን ኢትዮጵያ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መዝጋት እንዳለባት ያሳስባሉ፡፡

ሰሞኑን እየወጡ ያሉ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ደግሞ ኳታር የለቀቀችውን ሥፍራ የግብፅ ወታደሮች ሊይዙት ይችላሉ፡፡ ይህንን ጉዳይ ጂቡቲ ልትቀበለውም ላትቀበለውም እንደምትችል የገለጹት አቶ ዳደ፣ ግብፅ በጣም ጠባብ የሆነውንና ከሜድትራኒያን ወደ ቀይ ባህር የሚሻገረውን የስዊዝ ካናል የምታስተዳድር ከመሆኗ ጋር ተያይዞ ይህንን አካባቢ የማስተዳደር ዕድል ካገኘች ልትፈጥረው የምትችለው ወታደራዊ ኃይልና ሊኖራት የሚችለው ስትራቴጂካዊ ቦታ ኃያል ሊያደርጋት እንደሚችል አቶ ዳደ ይናገራሉ፡፡ ግብፅ ይህንን ማድረግ ቻለች ማለት ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ሥጋት ከማስወገድ ባሻገር፣ ኢትዮጵያ የቀይ ባህር ኃያልነቷን ልታጣ እንደምትችል አቶ ዳደ ይስማማሉ፡፡

ኢትዮጵያና ኤርትራ ወዳጅ በነበሩበት ጊዜ ኤርትራ ከሁለቱ ወደቦች በዓመት ከሁለት ቢሊዮን ዶላር በላይ ከኢትዮጵያ ገቢ ታገኝ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይህንን ያህል ፀጋ አጥታ ከኢትዮጵያ ጋር ወደ ጦርነት የገባችው ኤርትራ፣ ከአሁን በኋላ ግማሽ መንገድ መጥታ ልትደራደር እንደማትችል እየተገለጸ ነው፡፡

በአፍሪካ በተለይም በምሥራቅ አፍሪካ የማተራመስ ተልዕኮ እንዳለው የሚነገርለት የኢሳያስ አፈወርቂ መንግሥት፣ የአገሬውን ሕዝብ ከጎረቤት አገሮች ጋር በማቆራረጥና በማለያየት እየሠራ ካለው ባሻገር እጁን ለሰላም የማይዘረጋ በመሆኑ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በኃይል መነሳት እንዳለበት የሚናገሩ ወገኖች አሉ፡፡ ይህንን ከግምት ውስጥ አስገብቶ ዘላቂ መፍትሔ ያመጣል ተብሎ የሚጠበቀው የኢትዮጵያ መንግሥት በኤርትራ ላይ ሊከተለው የሚችል አዲሱ ፖሊሲ እየተጠበቀ ነው፡፡

የኳታር ጦር ከአካባቢው መውጣት ተከትሎ በጂቡቲ ግዛት ጦሩን እንዳሰፈረ የሚነገረው የኤርትራ መንግሥት፣ በአንድም በሌላም የኢትዮጵያን መንግሥት ለማዳከም ብሎ የወሰደው እንደሆነ ይነገራል፡፡ በጂቡቲና በታጁራ በወደብ የሚጠቀመው የኢትዮጵያ መንግሥት ይህንን ዕድል እንዲያጣ በማድረግ ኢኮኖሚያዊ አቅሙን ለማዳከም ዕርምጃውን እንደወሰደ ግምታቸውን የሚናገሩ አሉ፡፡

ግንኙነታቸውን ያቋረጡት የባህረ ሰላጤውን አገሮች በማደራደር ኩዌት እየተንቀሳቀሰች መሆኑን ሰኔ 12 ቀን 2009 ዓ.ም. ወደ ኩዌት ያቀኑት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) አድንቀዋል፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ የበኩሏን ማበርከት እንደምትፈልግ አስረድተዋል፡፡ የኩዌት አሚር በበኩላቸው የባህረ ሰላጤው አገሮች ልዩነት ከአገሮቹ አልፎ በሌሎች አገሮች ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥር በመሆኑ፣ በቶሎ ሊፈታ እንደሚገባውና ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አገሮች ቀዳሚ ሆና እየተንቀሳቀሰች መሆኗን አድንቀዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ለኩዌት አሚር የላኩትን መልዕክት አስረክበዋል፡፡

ሰሞነኛው የኤርትራና የጂቡቲ ጉዳይ ተፅዕኖው ከሁለቱ አገሮች ባለፈ በሌሎች ጎረቤት አገሮች በተለይም ለኢትዮጵያ ከፍተኛ የሆነ ተፅዕኖ ያለው በመሆኑ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ በብዙዎች እየተነገረ ነው፡፡ ኢትዮጵያም በሁለቱ አገሮች መካከል የተፈጠረውን ሰሞነኛ እሰጥ አገባ በአንክሮ በመከታተልና አሠላለፏን በማሳመር፣ ውጤታማ ሥራ ማከናወን እንደሚገባት አስተያየት ሰጪዎች ይስማማሉ፡፡

 

Standard (Image)

የተዳከሙ ሲቪል ማኅበራትን መልሶ የማጠናከር አንገብጋቢነት

$
0
0

 

‹‹ሲቪል ማኅበራት›› የሚለው ቃል የተለያየ የሕይወት ተሞክሮ ላላቸው ሰዎች ጭምር በጣም የተለመደ ነው፡፡ ይሁንና የቃሉ ትክክለኛ ትርጉምና በውስጡ የሚካተቱ ወይም የማይካተቱ ጉዳዮችን በተመለከተ የተለያዩ አረዳዶች አሉ፡፡

ሲሳይ ዓለማሁ (ዶ/ር) “CSO Law in Ethiopia: Considering its Constraints and Consequences” በሚል ርዕስ ባሳተሙት የምርምር ሥራ፣ ሲቪል ማኅበራት በቤተሰብና በአገር መካከል ያለውን ቦታ ለመድፈን የሚችሉ በርካታ ጉዳዮችን እንደሚያካትቱ ገልጸዋል፡፡ በዚህም በጎ አድራጎትና የውትወታ ድርጅቶች፣ የባህልና ሃይማኖታዊ ማኅበረሰቦች፣ መደበኛ ያልሆኑ ማኅበረሰባዊ ቡድኖች፣ የወጣትና የሴት ድርጅቶች፣ የሠራተኛ ማኅበራት፣ የንግድና የሙያ ማኅበራትና ሚዲያ እንደሚካተቱ ዘርዝረዋል፡፡

አቶ ደበበ ኃይለ ገብርኤል ዕውቅ የሕግ ባለሙያ ሲሆኑ፣ ብዙዎች በኢቲቪ/ኢቢሲ በሚያቀርቡት ‹‹ችሎት›› ፕሮግራም ያውቋቸዋል፡፡ አቶ ደበበ በሲቪል ማኅበራት አመራርነት ልምድ ያላቸው ናቸው፡፡ የበጎ አድራጎትና ማኅበራት ረቂቅ አዋጅ ላይ የሚመለከታቸው አካላት ከመንግሥት ጋር ለመነጋገር ባደረጉት ጥረት ንቁ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ለአቶ ደበበ ሲቪል ማኅበራት ማለት መንግሥት ፍላጎት በማጣት ወይም በአቅም ማነስ ሊደርስባቸው የማይፈልጋቸው ወይም የማይችላቸውን ነገሮች፣ እንዲሁም የግሉ ዘርፍ ትርፍ የማያገኝባቸው ጉዳዮች ላይ የሚሠሩ ተቋማት ናቸው፡፡

አንዳንድ ጥናቶች በሲቪል ማኅበራትና በመንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች መካከል ልዩነት ይፈጥራሉ፡፡ በ1999 ®.ም. የወጣው ‹‹የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታና አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› የሚል ርዕስ የተሰጠው የኢሕአዴግ ሰነድ፣ በሲቪል ማኅበራት ላይ ገዥው ፓርቲ ያለውን አቋም ይተነትናል፡፡ በኢሕአዴግም አረዳድ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች በአብዛኛው የገንዘብ ምንጫቸው ከውጭ የሚገኝ ዕርዳታ በመሆኑ ድርጅቶቹ የጥቅም ትስስሮችን የሚፈጥሩና የኪራይ ሰብሳቢ መንግሥት ግልባጭ ናቸው፡፡ ‹‹መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች (NGOs) በምንም ተዓምር ዜጎች የራሳቸውን መብትና ጥቅም ለማስጠበቅ በአባልነት ተሰባስበው የሚፈጥሯቸው ድርጅቶች አይደሉም፡፡ የተወሰኑ ዜጎች ራሳቸውን አደራጅተው ፕሮጀክት እየቀረፁ ለዕርዳታ ሰጭዎች በማቅረብ የራሳቸውን ኑሮ በማሻሻል እግረ መንገዳቸውን ዕርዳታ በተገኘበት ጉዳይ ዙሪያ የሚንቀሳቀሱባቸው አካላት ናቸው፡፡ አጀንዳቸውን የሚወስኑት ዕርዳታ ሰጭዎች እንጂ ድርጅቶች አይደሉም፡፡ ስለሆነም የዴሞክራሲያዊ አሠራር ባህሪና ሚና ያላቸው ተቋሞች ሊሆኑ አይችሉም፤›› ሲልም የገዥው ፓርቲ ሰነድ ያትታል፡፡

ከዚህ በተቃራኒ የብዙኃን ማኅበራት የዜጎችና የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች መብትና ጥቅምን ለማሰባሰብና የተወሰኑ አማራጮች በፖለቲካ መድረክ እንዲቀርቡ የማድረግ ድርሻ እንዳላቸው፣ ዜጎች በመብትና በጥቅማቸው ዙሪያ እየተወያዩና እየተከራከሩ፣ መሪያቸውን እየሾሙና እየሻሩ ዴሞክራሲን የሚማሩባቸው መድረኮች መሆን እንደሚችሉ፣ እንዲሁም አባሎቻቸውን ወክለው ከመንግሥት ጋር በመደራደር መንግሥት ለሕዝቡ ተጠያቂ እንዲሆን ማድረግ እንደሚችሉ ያስገነዝባል፡፡ ‹‹በውጭ ዕርዳታ ላይ የተመሠረቱ፣ መንግሥት አስፈላጊና ጠቃሚ ናቸው ብሎ ሲያምንባቸው ወይም ቢያንስ ከፍተኛ ጉዳት አያስከትሉም ብሎ ሲያምን የሚፈቅድላቸው፣ በተለያዩ ሥራዎች ሊሰማሩ ቢችሉም በዴሞክራሲ መድረክነት ዕውቅና የማይሰጣቸው እንዲሆኑ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ በአባላት የገንዘብና የጊዜ መዋጮ የሚሠሩት ግን የዜጎች የመደራጀት መብት መገለጫ በመሆናቸው መንግሥት ሲፈልግ የሚዘጋቸው ሳይሆኑ፣ በወንጀል ተግባር ላይ መሰማራታቸው በፍርድ ቤት ተረጋግጦ ካልተዘጉ በስተቀር ህልውናቸው የተረጋገጠ ማኅበራት እንዲሆኑና በዴሞክራሲ መድረክነትም እንዲታወቁ ማድረግ አለበት፤›› ሲልም ሰነዱ አቅጣጫ አመልክቶ ነበር፡፡

የመንግሥትና የገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ ሰነዶች ሲቪል ማኅበራት ለአንድ አገር የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካና የማኅበራዊ ሕይወት እምርታ ማሳየት ትልቅ ሚና እንዳላቸው ይገልጻሉ፡፡ ለአብነት ያህል በመርህ ደረጃ ሲቪል ማኅበራት የዴሞክራሲ ሥርዓት እንዲፈጠርና እንዲጠናከር በማድረግ ረገድ ወሳኝ ሚና ሊጫወቱ እንደሚችሉ ከምዕራባዊያን ታሪክ መገንዘብ እንደሚቻል ይጠቅሳል፡፡ ይኼው ሰነድ ማኅበራቱ፣ ‹‹መንግሥት የሚያወጣቸውን ፖሊሲዎችና ተግባራት፣ ወዘተ ተከታትለው ከእነሱ መብትና ጥቅም አኳያ ይወያያሉ፣ መሻሻል መስተካከል አለበት የሚሉትን ለይተው ያቀርባሉ፣ ከመንግሥትና ከሌሎች አካላትም ጋር ይደራደሩበታል፣ ይታገሉበታል፡፡ የብዙኃን ማኅበራት መንግሥት በሕዝቡ ተጠያቂ እንዲሆን በማድረግ ረገድም ሆነ በተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች መካከል የሚታዩ የጥቅም ግጭቶችን የራሳቸውን ጥቅም አሳልፎ በማይሰጥና ጥቅሞችን ለማጣጣም በሚያግዝ መልኩ ለመፍታት ያገለግላሉ፤›› ሲል ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታቸውን ይዘረዝራል፡፡

ይሁንና ማኅበራቱ እነዚህን ጠቀሜታዎች ለመስጠት የሚችሉት ዜጎች መብትና ጥቅማቸውን ለማስከበር በራሳቸው ተነሳሽነት የሚፈጥሯቸው፣ በአባላት መዋጮና ተሳትፎ የሚንቀሳቀሱ፣ በዴሞክራሲያዊ አኳኋን የሚንቀሳቀሱና መሪዎቻቸውን ራሳቸው መርጠው የሚያንቀሳቀሱ ማኅበራት ሲሆኑ ብቻ እንደሆነም ያሰምርበታል፡፡ ከዚህ አኳያ በኢትዮጵያ የሚገኙ ሲቪል ማኅበራት የዴሞክራሲ ሥርዓት ለመገንባት ወሳኝ ድርሻ መጫወት እንዳልጀመሩ ይደመድማል፡፡

ይህ ሰነድ የዛሬ አሥር ዓመት ይፋ የሆነውና የገዥው ፓርቲ አባላት የመከሩበት ከምርጫ 97 በኋላና የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኅበራት አዋጅ ከመውጣቱ በፊት ነው፡፡ በሰነዱ የሠፈሩት አብዛኛዎቹ ሐሳቦችም የሕጉ አካል ሆነዋል፡፡

የሲቪል ማኅበራት ጉዳይ ከ1997 ®.ም. በፊት ያን ያህል ትኩረት የሚሰጠው አልነበረም፡፡ ዘርፉን የሚመራ የሕግ ማዕቀፍም አልነበረም፡፡ በመሠረቱ በአገሪቱ ታሪክ ሲቪል ማኅበራት ጠንካራ መሠረት ያላቸው ተቋማትም አይደሉም፡፡ እንደ ሲሳይ (ዶ/ር) ገለጻ በአገሪቱ ረሃብ በ1960ዎቹና 70ዎቹ ሲከሰት እሱን ለመቋቋም መንግሥት ሲያቅተው ዕርዳታ ለመስጠት የመጡ የልማት መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ናቸው፣ እንደ መጀመሪያ ሲቪል ማኅበራት በአገሪቱ የተቋቋሙት፡፡

ይሁንና ከ1983 ®.ም. በኋላ በኢሕአዴግ አመራር በአገሪቱ የተፈጠረው የሕግና የፖለቲካ ሁኔታ ለሲቪል ማኅበራት ዘርፍ መስፋፋት በአንፃራዊነት ምቹ የሆነ ነው፡፡ በ1987 ®.ም. ወደ ሥራ የገባው የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥትም የመደራጀት መብትን ጨምሮ የሰብዓዊና የዴሞክራሲ መብቶችን በስፋት ያቀፈ መሆኑ ተጨማሪ ማትጊያ ሆኗል፡፡ ሲሳይ (ዶ/ር) እነዚህ ሁኔታዎች መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን ጨምሮ ሲቪል ማኅበራት፣ የሙያ ማኅበራት፣ የንግድ ምክር ቤቶችና ጥቂት ውትወታ ላይ የተሰማሩ ድርጅቶች እንዲቋቋሙ ማስቻላቸውን ይጠቅሳሉ፡፡ ለምሳሌ በ1992 ®.ም. 310 የተመዘገቡ አገር በቀል ሲቪል ማኅበራት ነበሩ፡፡ ይሁንና አብዛኛዎቹ በአገልግሎት አሰጣጥና በልማት ፕሮጀክቶች ላይ የተሰማሩ ነበሩ፡፡ በሰብዓዊ መብትና በአስተዳደር ውትወታ ላይ የተሰማሩት በጣም ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ሲሳይ (ዶ/ር)፣ ‹‹ይህ የሆነው መንግሥት በዚህ ዓይነት ሥራዎች ላይ መሰማራታቸውን ስለሚጠላ ነው፤›› ብለዋል፡፡

የ1997 ምርጫ እስኪመጣ ድረስ የሲቪል ማኅበራት በአንፃራዊ ሁኔታ የነቃ እንቅስቃሴ ያደርጉ ነበር፡፡ ሪፖርተር ያነጋገራቸውና ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ የፖለቲካ ተንታኝ ከ1983 ®.ም. እስከ 1997 ®.ም. ድረስ በኢትዮዽያ በሥራ ላይ የነበሩ ሲቪል ማኅበራት ቁጥራቸው ብዙ የሚባል እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ‹‹የነበራቸውም የገንዘብ አቅምና የሰው ኃይል የተሻለ ነበር፡፡ በአንፃራዊነት የሚያሠራ ከባቢ ሁኔታ ነበር፡፡ ለአንዳንድ ልዩ ጉዳዮች በመቆምና በሕግና በፖሊሲ ላይ ለውጥ ለማምጣት ጫና የመፍጠር ትልቅ ሚና ነበራቸው፤›› ብለዋል፡፡

በከፊል የነበረውን የሕግ ማዕቀፍ እጦት ለመቅረፍ በ2001 ®.ም. የበጎ አድራጎትና የሲቪል ማኅበራት አዋጅ ወጣ፡፡ ይሁንና በሥራ ላይ ያለው ሕግ እንዲወጣ ለመንግሥት መነሻ ሆነዋል ከሚባሉት ምክንያቶች አንዱ፣ በምርጫ 97 ብዙዎቹ መብት ላይ የሚሠሩ ሲቪል ማኅበራት ለተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች በተለይም ለቅንጅት ድጋፍ ሰጥተዋል ተብሎ መታመኑ እንደሆነ የፖለቲካ ተንታኞችና የተለያዩ የጥናት ሥራዎች ያመለክታሉ፡፡

ፖለቲከኛ ማኅበራት

በሲቪል ማኅበራቱ ውስጥ ቁልፍ ሚና የነበራቸው ግለሰቦች በምርጫው ዕጩ ሆነው መቅረባቸው መንግሥትን ይበልጥ እንዳስከፋው በበርካታ ሪፖርቶች ተጠቅሷል፡፡ በወቅቱ ገዥው ፓርቲ ቅሬታውን ሲገልጽላቸው፣ ‹‹ሥልጣን ለመያዝ አንታገልም እንጂ አንድ ፓርቲን መደገፍ አንችልም ማለት አይደለም፤›› ብለው እንደመለሱለትም ይነገራል፡፡

አቶ ደበበ በአፍሪካ ብዙዎቹ ሲቪል ማኅበራት ሲፈጠሩ አፈጣጠራቸው ከመብት ሥራ ጋር የተያያዘ እንደነበር ያስገነዝባሉ፡፡ በኢትዮጵያ ግን ከንጉሡ ጊዜ ጀምሮ አፈጣጠራቸው ከዕርዳታና ከበጎ አድራጎት ጋር የተያያዘ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ‹‹በኢትዮዽያ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች (ኤንጂኦስ) ከስንዴና ከዘይት ጋር ተያይዘው ነው የሚታወሱት፡፡ መብትን ከማስከበርና ከሥነ ዜጋ እንቅስቃሴዎች ጋር የተያያዙ አይደሉም፡፡ አንዱ መሠረታዊ ችግርም ይኼው ነው፤›› ብለዋል፡፡ 

በኢትዮጵያ መብት ላይ የሚሠሩ እንደ ኢሰመጉ፣ አፓፕና ኢውላ የመሳሰሉ ሲቪል ማኅበራት ብቅ ማለት የጀመሩትም ሆነ መብዛት የጀመሩት ከ1983 ®.ም. በኋላ ነው፡፡ ‹‹ቁጥራቸው ብዙ አልነበረም፡፡ አዋጁ በወጣበት በ2001 ®.ም. ላይ ከመብት ሥራ ጋር ተያይዞ በሰብዓዊ መብት ላይ ትምህርት ለመስጠት፣ በምርጫ፣ በሴቶችና ሕፃናት መብት ላይ ለመሥራት ተመዝግበው የነበሩት ወደ 125 የሚሆኑ ነበሩ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ጠንካራ የሚባሉት ከአሥር አይበልጡም ነበር፡፡ አጠቃላይ የኤንጂኦዎች ቁጥር ግን ከ4000 በላይ ይገመት ነበር፤›› ብለዋል፡፡   

ሲቪል ማኅበራት የፖለቲካ አቋም ሊኖራቸው አይገባም በማለት የሚቀርበውን ክርክር የማይደግፉ ምሁራን አሉ፡፡ የፖለቲካ ተንታኙ ሲቪል ማኅበራት በቀጥታ በፓርቲ ተቀጥላነትና በፓርቲ መዋቅር አመራር ሥር አይገቡም ማለት ነው እንጂ፣ ሙሉ በሙሉ ከፖለቲካ የፀዱ ናቸው ማለት እንዳልሆነ ይሞግታሉ፡፡ 

በእርግጥም ከ1997 ®.ም. በኋላ መንግሥት ሲቪል ማኅበራትን ከተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች  ለይቶ ለማየት እንዳዳገተው የፖለቲካ ተንታኞች ይገልጻሉ፡፡ ከዚያ በኃላ በሰብዓዊ መብትና በዴሞክራሲ ላይ እየሠሩ የቀጠሉት ጥቂት ማኅበራት ብቻ ናቸው፡፡ የተፈጠረው ከባቢ ሁኔታ እንደ ተቋም መቀጠላቸውን ራሱ እንደ ተዓምር እንዲታይ እንዳደረገው አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ፡፡ ሕጉ በዋነኛነት የጎዳውም እነዚህኑ ማኅበራት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ በመንግሥት ኃላፊዎች የሚነገረው ሕጉ የአብዛኛውን ሲቪል ማኅበራት ጥቅም እንደማይነካ ነው፡፡ እርግጥ አብዛኛዎቹ እንደ ትምህርት፣ ጤና፣ እርሻ ያሉ የልማት ሥራዎች ላይ ነው ትኩረት የሚያደርጉት፡፡

አቶ ደበበ ሲቪል ማኅበራት ለፖለቲካ ሥልጣን የሚታገሉ ተቋማት እንዳልሆኑ ይቀበላሉ፡፡ ነገር ግን የተደራጁ ሲቪል ማኅበራት ካሉ በማንኛውም ጉዳይ ላይ የዚህና የዚያ ፓርቲ አባል ነኝ ሳይባባሉ፣ እርስ በርስ ለመነጋገርና ሐሳብ ለመለዋወጥ እንደሚያስችል ያስገነዝባሉ፡፡ ‹‹መንግሥት ብዙ ጊዜ ራሱ ተቋም ውስጥ ስላለ የመልካም አስተዳደር ችግር ያነሳል፡፡ የተጠናከረ የሲቪል ማኅበር በሌለበት ሁኔታ ስለመልካም አስተዳደር የፈለግከውን ያህል ብታወራ ለውጥ ልታመጣ አትችልም፡፡ መንግሥት በተቃውሞ የመኖር ባህልን ማወቅ አለበት፡፡ የተለየና የሚቆረቁር ሐሳብ መቀበል መቻል አለብን፡፡ ያን ማድረግ ካልቻልን በወድያኛው ወገን ያለውን ስሜትና ሐሳብ ልናውቅ አንችልም፡፡ ሲፈነዳ አብረን ተያይዘን ነው የምንጠፋው፡፡ ሲቪል ማኅበራት እያንዳንዱ ሰው ምን መብት አለው? ምን ግዴታ አለበት? ሌሎቹንስ ምንድን ነው ማድረግ ያለበት? የሚለውን ማስተማር መቻል አለባቸው፡፡ አሁን ፈሪ የሆነና መብቱን የማያውቅ ማኅበረሰብ እየተፈጠረ ነው፡፡ ይኼ ችግር በአንድ ወይም በሌላ መንገድ ሊፈታ ካልቻለ፣ በዘላቂነት እንደ አንድ ማኅበረሰብ ለመኖር እጅግ ከባድ ነው፤›› ሲሉ ያስረዳሉ፡፡

በሌሎች አገሮች ሲቪል ማኅበራት ሥልጣን የያዙ አካላትን በማግባባት፣ በመሞገት፣ ሕዝባዊ ግፊት በመፍጠር ለሕዝብ ይበጃል የሚሉት ጉዳይ እንዲከናወን፣ ፖሊሲዎች እንዲቀረፁ፣ ሰብዓዊ መብቶች እንዲከበሩ ያደርጋሉ፣ ይታገላሉ፡፡     

የሕጉ ተፅዕኖ

አቶ ደበበ በመንግሥትና በሌሎች አካላት በወቅቱ በርካታ ልዩነቶች ቢንፀባረቁም፣ ሦስት መሠረታዊ ጉዳዮች ግን አንኳር እንደነበሩ ያስታውሳሉ፡፡ አንደኛው መንግሥት የሰብዓዊ መብትና የዴሞክራሲ ሥራ ሊከናወን የሚገባው በዜጎችና በአገር ውስጥ በሚገኝ ገንዘብ ብቻ ነው የሚል አቋም ለመጀመሪያ ጊዜ ማራመድ መጀመሩ ነው፡፡ የአገሪቱ ሕገ መንግሥት በአንቀጽ 31 ላይ፣ ‹‹ማንኛውም ሰው ለማንኛውም ዓላማ በማኅበር የመደራጀት መብት አለው፤›› ሲል ይደነግጋል፡፡ አቶ ደበበ ሕገ መንግሥቱ፣ ‹‹ማንኛውም ሰው›› በሚል ያስቀመጠ በመሆኑ ለዜጎች ብቻ የተተወ መብት ነው ለማለት አዳጋች እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ‹‹አንዱ ትልቁ ልዩነትና ዋና አከራካሪ የነበረው ይኼ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ሌላኛው አከራካሪ ጉዳይ ከማኅበራቱ ለሦስት መከፈል ጋር የተያያዘ ነው፡፡ በአንደኛው ምድብ እዚሁ አገር ውስጥ የተመዘገቡና በአገር ውስጥ በሚገኝ ገንዘብ የሚንቀሳቀሱ ተካተዋል፡፡ በሁለተኛው ምድብ የኢትዮጵያ ነዋሪዎች የሚባሉ ኢትዮጵያ ውስጥ የተመዘገቡ፣ ነገር ግን ከውጭ ገንዘብ የሚቀበሉ ተካተዋል፡፡ በሦስተኛው ምድብ ደግሞ የውጭ በጎ አድራጎት ድርጅቶች ተካተዋል፡፡ አቶ ደበበ፣ ‹‹አዋጁ እኮ ድርጅታቸው ከውጭ ገንዘብ ስለሚቀበል ብቻ ኢትዮጵያዊያንን የኢትዮጵያ ነዋሪዎች በሚል ያስቀምጣቸዋል፡፡ በነዋሪና በዜጋ መካከል ትልቅ ልዩነት አለ፤›› ብለዋል፡፡

የዜጎች ሲቪል ማኅበራትን በገንዘብ የመርዳትም ሆነ ያለመርዳት አዝማሚያ ከአጠቃላይ የአገሪቱ የፖለቲካ ምህዳር መስፋትና መጥበብ ጋር የሚገናኝ ነው፡፡ መንግሥት ፓርቲና መንግሥትን ሳይለያይ ከነጋዴዎች ጭምር ገንዘብ እየሰበሰበ፣ ሲቪል ማኅበራቱ ከ90 በመቶ በላይ ወጪያቸውን ከዜጎች መሰብሰብ አለባቸው ማለት ፍትሐዊ አይደለም የሚል ነጥብም ይነሳል፡፡

የፖለቲካ ተንታኙ ከአገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ በመነሳት የዜጎች የኢኮኖሚ ደረጃ በራሱ መንግሥታዊ ላልሆኑ ተቋማት ገንዘብ ለማዋጣት የሚገፋፋ እንዳልሆነ መረዳት እንደሚቻልም ተከራክረዋል፡፡ 

ሦስተኛው ልዩነት ደግሞ ማኅበራቱ ከሚሠሩት የሥራ ዓይነት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ከአገር ውስጥ ገንዘብ እስካልተገኘ ድረስ ከውጭ በሚገኝ ገንዘብ ከሰብዓዊ መብትና ከዴሞክራሲ ጋር የተገናኘ ሥራ ማከናወን አይቻልም፡፡ አቶ ደበበ፣ ‹‹ሕጉ እያለ ያለው ትምህርት ቤት በመክፈት ወይም ደብተር በመግዛት ትምህርት ቤት እንዲሄድ አድርገው፡፡ ነገር ግን ትምህርት የመማር መብት እንዳለው አትንገረው ነው የሚለው፡፡ የጤና ተቋም መሥርቱ፣ መድኃኒት አቅርቡ፡፡ ነገር ግን ዜጋው የጤና መብት ያለው ስለመሆኑ አትናገሩ ነው የሚለው፡፡ አሁን ያለው አካሄድ ዜጎች የተሰጣቸውን ብቻ ተመፅዋች እንዲሆኑ የሚያደርግ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ሕጉ ማኅበራቱ ላይ ተጨማሪ ችግር ይፈጥራል በሚል ባለድርሻ አካላት ሥጋቶቻቸውን ለመንግሥት ለማሳወቅ ቢጥሩም፣ ይህ ማኅበራቱ ሕጉ ከመውጣቱ በፊት ከራሳቸው የሚመነጭ ችግር የለባቸውም ከሚል እምነት የመነጨ እንዳልሆነ አቶ ደበበ ያስገነዝባሉ፡፡ ነገር ግን የችግሩ መፍቻ መንገድ ሕጉ ብቻ መሆን እንዳልነበረበት ይሞግታሉ፡፡ ‹‹ገንዘብ ከውጭ አታምጡ ከማለት ይልቅ የመጣውን ገንዘብ በዚህ መንገድ ተጠቀሙ ማለት የተሻለ ነበር፤›› ብለዋል፡፡ 

አቶ ደበበ ራሱን የቻለ ዘርፉን የሚያስተዳድር ሕግ መኖሩ ጠቃሚ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ሕጉ በዋናነት ግልጽነትና ተጠያቂነትን እንዳመጣም ያምናሉ፡፡ ማኅበራቱ የሚሰበስቡትን ገንዘብ በእርግጥም ለተጠቃሚዎች እንዲያውሉት ከማስቻል አንፃር፣ ከበፊቱ የተሻለ ውጤት መታየቱም እንደማይካድ ያስረዳሉ፡፡

አቶ ደበበ አብዛኛው ችግር ከአፈጻጸም ጋር የተገናኘ እንደሆነም ያስገነዝባሉ፡፡ ሕጉ በሚረቀቅበት ወቅት ሕጉ በምንም ሁኔታ ማኅበራቱን እንደማይጎዳና ችግር እንደማያስከትል መንግሥት በተደጋጋሚ ቃል ይገባ እንደነበርም አስታውሰዋል፡፡ ‹‹አሁን በተግባር ግን የታየው በመቶዎች የሚቆጠሩ ማኅበራት በየዓመቱ ሲዘጉ ነው፡፡ በዋናነት የሚዘጉትም በገንዘብ እጥረት ምክንያት ነው፤›› ብለዋል፡፡ 

ለአቶ ደበበ ከማኅበራቱ ይዞታ ጋር የተያያዘው ሌላው ችግር የሚያስተዳድራቸው ኤጀንሲ የሕግ አተረጓጎም ችግር ነው፡፡ በኤጀንሲው የወጡ ደንቦችም በጣም የሚገድቡና የሚከለክሉ እንደሆኑ ይገልጻሉ፡፡

በሕጉ የተነሳ ሲቪል ማኅበራቱ ቁጥር እጅግ እንዳይመናመን ተሰግቶ ነበር፡፡ መንግሥት ግን ሕጉ ተግባር ላይ ከዋለ በኋላ እንዲያውም ቁጥራቸው እንደተበራከተ ይከራከራል፡፡ አቶ ደበበ ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ ‹‹ይኼ ሐሰት ነው፡፡ የተለያዩ ጥናቶች እንደሚያሳዩት ሕጉ ከመውጣቱ በፊት ወደ 4,000 የሚጠጉ ሲቪል ማኅበራት ነበሩ፡፡ በቅርብ የወጣ የኤጀንሲው መረጃ የማኅበራቱ ቁጥር 3,300 እንደሆነ ያሳያል፡፡ የሠርተፊኬት ቁጥሩ እንደዛ ሊሆን ይችላል፡፡ መልሰህ ግን ይህን የኤጀንሲውን መረጃ ስትመረምረው የተሰረዙ ጭምር ተካተው ታገኛለህ፡፡ አዋጁ ከወጣ በኋላ ከ1,000 በላይ ሲቪል ማኅበራት ተዘግተዋል፡፡ ስለዚህ አሁን ያለው ቁጥር ከ2,000 አይበልጥም፤›› ብለዋል፡፡   

ከሦስት ዓመት በፊት በአውሮፓ ኅብረት በተደረገና አቶ ደበበ በተካፈሉበት ሲቪል ማኅበራትን የተመለከተ ጥናትም በሥራ ላይ ያሉ ሲቪል ማኅበራት ቁጥር በኤጀንሲው ከሚገለጸው ያነሰ እንደሆነ ተመልክቷል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2014 በሥራ ላይ የነበሩና ለአንድ ዓመትና ከዚያ በላይ ጊዜ የሚቆይ ፕሮጀክት ኖሯቸው የሚንቀሳቀሱ ሲቪል ማኅበራት ቁጥር ከ500 እንደማይበልጥ ጥናቱ ደምድሟል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 300 የሚሆኑት የውጭ ናቸው፡፡ 

መንግሥት ምን ሊያሻሽል ይችላል?

የፖለቲካ ተንታኙ ሲቪል ማኅበራት የመንግሥት የፖለቲካ መዋቅር መሪና አዝማች መሆናቸው ማቆም እንዳለበት ያሳስባሉ፡፡ ሲቪል ማኅበራት በተፈጥሯቸው በአባላት በጎ ፈቃድ የሚመሠረቱ ቢሆንም፣ ለገዥው ፓርቲ ተቀጥላ የሆኑ አንዳንድ ሲቪል ማኅበራት ግን የተመሠረቱት በራሱ በኢሕአዴግ ነው በማለት ይተቻሉ፡፡ እነዚህ ማኅበራት የፖለቲካ አጀንዳ አላቸው ከሚል ትችት በዘለለ ከአመሠራረታቸው፣ ከገቢ ምንጫቸው፣ ከአመራራቸውና ከእንቅስቃሴ ነፃነታቸው አንፃር በእርግጥም ሲቪል ማኅበራት ናቸው ወይ የሚል ጥያቄ እንደሚቀርብባቸው የፖለቲካ ተንታኙ ያስገነዝባሉ፡፡ ማኅበራቱ በአገሪቱ የፖለቲካ ሕይወት ውስጥ የተሻለ ሚና እንዲኖራቸው ከተፈለገ፣ በውስጥ ጉዳያቸው ከመግባት መቆጠብ ብቻ ሳይሆን ሌላ ማንኛውም ኃይል እንዳይነካቸው የሕግ ጥበቃ ሊያደርግ እንደሚገባም ያክላሉ፡፡

ከምርጫ 2007 በኃላ ኢሕአዴግና መንግሥት የተለያዩ የብዝኃነት መገለጫዎችን በተሻለ መንገድ ለማስተናገድ ተነሳሽነት እንዳላቸው ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡ ለቃላቸው ታማኝ ሆነው ሚናቸውን ለማስፋት ከተፈለገ በነፃነት እንዲደራጁ፣ እንዲናገሩና እንዲቃወሙ መፍቀድ እንደሚገባ ብዙዎች ያሳስባሉ፡፡

ይህን ለማድረግም ሕጉ ያስቀመጠው የቁጥጥር ሥርዓት ሊላላ እንደሚገባ፣ የሲቪል ማኅበራት ጥፋተኛ ናቸው በሚል እምነት የተቀረፀው የሕግ ማዕቀፍም መሠረታዊ ክለሳ ሊደረግበት እንደሚገባም ያስገነዝባሉ፡፡ ለአብነትም 70/30 የሚተረጎምበት መንገድ ሰፋ ማለት እንዳለበት ይመክራሉ፡፡ የፖለቲካ ተንታኙ፣ ‹‹ለሲቪል ማኅበራት ድጋፍ ስትሰጥ ከግብርና ከታክስ ግዴታህ ላይ ተቀናሽ እንዲሆንልህ ማድረግ ይቻላል፤›› ብለዋል፡፡   

Standard (Image)

የአፍሪካ ኅብረት 29ኛው የመሪዎች ጉባዔና የምሥራቅ አፍሪካን በሁለት ጎራ የመሠለፍ ቀውስ የመፍታት ፈተና

$
0
0

29ኛው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ ከሰኔ 20 እስከ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ይካሄዳል፡፡ ስብሰባው ማክሰኞ ሰኔ 20 ቀን 2009 ዓ.ም. የየአገሮቹ ቋሚ መልዕክተኞች ስብሰባ በማካሄድ ተጀምሯል፡፡ የዘንድሮው 29ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ ‹‹Harnessing the Demographic Divided through Investment in Youth›› በሚል መሪ ቃል እንደሚካሄድ፣ የአፍሪካ ኅብረት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ የኅብረቱ ዋና መቀመጫ በሆነችው አዲስ አበባ ጉባዔውን ማካሄድ የጀመረው የአፍሪካ ኅብረት፣ በዋናነት በየአገሮቹ ያሉ ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ አዳዲስ አሠራሮችንና ፖሊሲዎችን እንደሚቀርፅ ይጠበቃል፡፡

በተፈጥሮ ሀብቷ ባለፀጋ መሆኗ የሚነገርላት አፍሪካ በቂ የሠለጠነ የሰው ኃይል የሌላት በመሆኑ፣ የተፈጥሮ ሀብቷን በአግባቡ በመጠቀም በአኅጉሩ ያሉ ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ሥራ እየተከናወነ እንዳልሆነና ለዚህም ዜጎች ለስደት ሰለባ እንደሚሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

አፍሪካ ካለባት የተማረ የሰው ኃይል እጥረትና ድህነት ባሻገር የአሸባሪዎች መናኸሪያ እየሆነች ነው፡፡ መቀመጫውን ሶማሊያ አድርጎ ሽብር በማድረስ ከሚታወቀው አልሻባብ እስከ ናይጄሪያው ቦኮ ሐራም፣ በሊቢያ ከሚንቀሳቀሰው አይኤስ እስከ ሌሎች አሸባሪ ቡድኖች መናኸሪያቸውን አፍሪካ አድርገዋል፡፡  

29ኛ የአፍሪካ የመሪዎች ጉባዔ ልዩ ትኩረት የሚሰጠው ሌላው ጉዳይ በአፍሪካ እየተስፋፋ ስለመጣው ስለዚሁ ሽብርና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ እንደሚሆን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በተለይም ሶማሊያ ከአልሻባብ ጥቃት ነፃ ስለምትወጣበት ጉዳይ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚንቀሳቀስ፣ ከአፍሪካ ኅብረት የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

በአፍሪካ እየተስፋፋ የመጣው የሽብር ጥቃት በአኅጉሪቱ ከፍተኛ ኪሳራ እያደረሰ እንደሆነ የኬንያ ‹‹ዴይሊ ኔሽን›› ባለፈው ሳምንት ዘግቧል፡፡ በዚህ የሽብር ጥቃት በቅርብ ጊዜያት ሶማሊያ፣ ደቡብ ሱዳንና ኬንያ ሰለባዎች እንደነበሩ ይታወሳል፡፡

አፍሪካ ከተጋረጡባት የሽብር ጥቃቶች ባሻገር ሰሞኑን የዓረብ ባህረ ሰላጤ አገሮች ከኳታር ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ማቋረጥ ሌላው ሥጋት እየሆነባት መምጣቱን፣ የተለያዩ የመረጃ አውታሮች ሲገልጹ ሰንብተዋል፡፡

ሳዑዲ ዓረቢያ የባህረ ሰላጤው አገሮች ኳታርን ከአባልነቷ እንድትወጣና ሌሎች አገሮችም ከእሷ ጋር ያላቸውን ግንኙነትና እንቅስቃሴ እንዲያቆሙ ስታግባባ ሰንብታለች፡፡ የሳዑዲ ዓረቢያ ምኞት  ዕውን ሆኖ ዛሬ ታላላቅ አቅም አላቸው ተብለው የሚጠቀሱት የዓረብ ባህረ ሰላጤ አገሮች ግብፅን ጨምሮ፣ ከኳታር ጋር ያላቸውን ግንኙነት አቋርጠዋል፡፡

የባህረ ሰላጤው አገሮች ከኳታር ጋር ያላቸውን ግንኙነት ማቋረጥ፣ በአፍሪካ በተለይም በቀይ ባህር ቀጣና ውስጥ ባሉ አገሮች ቀጥተኛ ተፅዕኖ እየፈጠረ እንደሆነ ሪፖርቶች ያመለክታሉ፡፡

የኳታር ከቀጣናው መውጣት ለአፍሪካ አገሮች መከፋፈል ምክንያት ሊሆን እንደሚችል እየወጡ ያሉ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ሳዑዲ ዓረቢያ መራሹ የባህረ ሰላጤው አገሮች ስብስብ በአፍሪካ ብሎም በዓለም  አገሮች ዘንድ ልዩነት እየፈጠረ መሆኑን፣ የቱርክ ‹‹አናዶሉ›› የመረጃ መረብ ገልጿል፡፡ ሳዑዲ ዓረቢያ ሰሞኑን እያወጣችው ያለው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ የዓለም አገሮች በተለይም የአፍሪካ አገሮች ከኳታር ጋር ያላቸውን ግንኙነት በግልጽ እንዲያቆሙ አሳስባለች፡፡ ይህ የሳዑዲ ዓረቢያ የማስጠንቀቂያ ደወል አፍሪካን የሚያሳስብ ጉዳይ እንደሆነ እየተገለጸ ሲሆን፣ የአፍሪካ ኅብረት ችግሩ በውይይት እንዲፈታ ከዚህ በፊት የአቋም መግለጫ ማውጣቱ ይታወቃል፡፡

የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሞሃማት ሙሳ ፋቂ የዓረብ ባህረ ሰላጤ አገሮች  በኳታር ላይ የወሰዱት የማግለል ዕርምጃ በአገሮች መካከል መከፋፈል የሚፈጥር ከመሆኑ ባሻገር፣ በአፍሪካ አገሮች ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ሊያስከትል እንደሚችል ገልጸው ነበር፡፡

እ.ኤ.አ. ሰኔ 15 ቀን 2017 የገልፍ አገሮች ማለትም ሳዑዲ ዓረቢያ፣ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ፣ ባህሬንና ግብፅ ከኳታር ጋር ያላቸውን ግንኙነት በይፋ አቋርጠዋል፡፡ የእነዚህ አገሮች ከኳታር ጋር ያላቸውን ግንኙነት ማቋረጥ በአፍሪካ በተለይም በኤርትራና በጂቡቲ ላይ ቀጥተኛ ተፅዕኖ ማምጣቱም አልቀረም፡፡

 29ኛው የአፍሪካ የመሪዎች ጉባዔ በዚህ ጉዳይ ላይ ተወያይቶ የመፍትሔ አቅጣጫ የሚያስቀምጥ መሆኑ እየተነገረ ቢሆንም፣ ጉዳዩ ቀላል እንደማይሆን ባለሙያዎች ሲናገሩ ተደምጧል፡፡ የኳታር ከቀጣናው መገለል አሜሪካና ቱርክን ጨምሮ አገሮች የተለያየ አቋም እንዲይዙ እያደረገ ነው፡፡

የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ጉብኝት ያደረጉት በሳዑዲ ዓረቢያ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚህም ተነሳ አሜሪካና ሌሎች አጋር አገሮች ከሳዑዲ ዓረቢያ ጎን መቆማቸው እየተነገረ ነው፡፡ ትራምፕ ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ የተወሰኑ የሙስሊም አገሮች ዜጎች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ የሚከለክል ሕግ አውጥተዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ይህንን ሕግ ለማውጣት ያስገደዳቸው አንዱ ምክንያት የተወሰኑ የሙስሊም አገሮች አሸባሪ ቡድኖችን እንደሚረዱና በአገራቸው ላይም የሽብር ጥቃት እንዳይከሰት በመፍራት እንደሆነ በተደጋጋሚ ጊዜ ሲናገሩ ተደምጧል፡፡

ሳዑዲ ዓረቢያና አጋሮቿ ኳታር ‹‹ሐማስ›› እየተባለ የሚጠራውን ቡድን እንደምትረዳ በመፈረጅ ከቀጣናው እንድትወጣ አድርገዋል፡፡ ሳዑዲ ዓረቢያ መራሹ የባህረ ሰላጤው አገሮች ስብስብ ሰሞኑን በኳታር ላይ ይህን ዓይነት ዕርምጃ መውሰዱ ደግሞ አሜሪካን ጨምሮ የተወሰኑ የአውሮፓ አገሮችን ጮቤ እያስረገጠ መሆኑም ተነግሯል፡፡ በዚህም የተነሳ የተወሰኑ የሙስሊም አገሮች ዜጎች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ጥላው የነበረውን ዕገዳ ልታነሳ እንደምትችል ሰሞኑን ‹‹ሲኤንኤን›› ዘግቧል፡፡

የቱርክ ፕሬዚዳንት ሬሲብ ጣይብ ኤርዶሃን በበኩላቸው ከኳታር ጎን እንደሚቆሙ ገልጸዋል፡፡ የዓረብ ባህረ ሰላጤው አገሮች በኳታር ላይ 13 ቅድመ ሁኔታዎችን ማስቀመጣቸው የአገሪቱን ሉዓላዊነት የሚነካ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

የግብፅና የኳታር ግንኙነት በቀጣናው ለረጅም ጊዜ የዘለቀ ቢሆንም፣ አሁን ግን ጉዳዩ ውኃ የገባው ጨው እንደሆነ ባለሙያዎች ሲናገሩ እየተደመጠ ነው፡፡ ግብፅ በቀይ ባህር በኩል ያለውን ቀጣና በአራት ዓይኗ እየተከታተለች እንደሆነ እየተነገረ ሲሆን፣ የኳታር ጦር ከዱሜራ ግዛት መውጣት ደግሞ ለግብፅ የብሥራት ዜና እንደሆነ ተሰምቷል፡፡

 በቀይ ባህር አካባቢ በተለይም በጂቡቲ ላይ የዓለም አገሮች ትኩረትና ፍላጎት ከፍተኛ እንደሆነ ሪፖርቶች ይጠቁማሉ፡፡ ፈረንሣይ፣ ሳዑዲ ዓረቢያ፣ ቻይና፣ አሜሪካና ሌሎች አገሮችን ጨምሮ ይህን ቀጣና በዕይታቸው ሥር ለማድረግ ደፋ ቀና ሲሉ ቆይተዋል፡፡

አፍሪካ ራሷን በራሷ እንድታስተዳድርና እንድትመራ ብሎም ሀብቷን  እንድትቆጣጠር የተለያዩ ምክረ ሐሳቦች ከተለያዩ አቅጣጫዎች ቢሰሙም፣ በዚህ ቀጣና ያለውን ጂኦ ፖለቲካዊ አንድምታ ከግብፅና ኢትዮጵያ በስተቀር ትኩረት የሚሰጠው እንደሌለ ባለፈው ዓመት በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ማዕከል የቀረበ ጥናት ጠቁሟል፡፡ ግብፅ በቀይ ባህር በኩል የሚያልፍንና ማንኛውንም ጉዳይ በተለየ ዕይታና አመለካከት የምታይ አገር እንደሆነች ይሰማል፡፡ በኤርትራና በጂቡቲ ድንበር አካባቢ ለሰባት ዓመታት ያህል ሰፍሮ የነበረውን የኳታር ጦር መውጣት ተከትሎ የተወሰኑ አገሮች ጮቤ እየረገጡ እንደሆነ እየተነገረ ነው፡፡

የአሰብን ወደብ ለረጅም ዓመት እንደተከራየችው የሚነገርላት ሳዑዲ ዓረቢያ በቀጣናው ያላትን ኃይል ማጠናከር እንደምትፈልግ ሲነገር ይሰማል፡፡ በቀይ ባህር በኩል ደግሞ ግብፅ ከኤርትራ ጋር የጋራ ግብረ ኃይል እንዳቋቋመችም እየተገወራ ነው፡፡ ኤርትራ ከሳዑዲ ዓረቢያና ከግብፅ በዓመት ዳጎስ ያለ ገንዘብ እንደምታገኝ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ አገሮች ወደዚህ ቀጣና መጥተው የራሳቸው ቦታ ለማግኘት የሚያደርጉት ጥረት ከፍተኛ እንደሆነ፣ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ መምህሩ አቶ አበበ ዓለሙ ይናገራሉ፡፡

በዚህ ቀጣና ያለው አሠላለፍ ከባድና ውስብስብ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ለመፍታት አዳጋች እንደሚሆን አቶ አበበ ይስማማሉ፡፡ የአፍሪካ ኅብረት በ29ኛው የመሪዎች ጉባዔ ላይ ይህንን ጉዳይ አንስቶ የሚመክርበት እንደሆነ ቢጠቆምም፣ ዘላቂ መፍትሔ ከማምጣት አንፃር አስቸጋሪ እንደሚሆን ያስረዳሉ፡፡ ይሁንና የአፍሪካ ኅብረት በኤርትራና በጂቡቲ መካከል የተፈጠረውን የግዛት ይገባኛል ጥያቄ ለመፍታት አጣሪ ኮሚቴ አቋቁሞ ወደ ሥፍራው እንደሚልክ የኅብረቱ ኮሚሽነር ቢገልጹም፣ ጉዳዩ ቀላል እንደማይሆን እየተነገረ ነው፡፡ ኤርትራ በተደጋጋሚ ጊዜ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የማዕቀብ ሰለባ መሆኗ ደግሞ ጉዳዩን የከፋ ሊያደርገው እንደሚችል ተሰግቷል፡፡

የሳዑዲ ዓረቢያ አገሮች አሠላለፋቸውን እንዲያሳምሩ ማሳሰቢያ መናገር፣ የግብፅ ወደ ዱሜራ ግዛት ለመሄድ ፍላጎት ማሳየትና የኢትዮጵያ አካባቢውን በንቃት መከታተል ጉዳዩን የከፋ ሊያርገው እንደሚችል እየተነገረ ነው፡፡ ሳዑዲ ዓረቢያ ከእኔ ጋር ወይም ከኳታር ጋር አሠላለፋችሁን ለዩ ማለቷ ስህተት እንደሆነ የሚናገሩት አቶ አበበ፣ የኢትዮጵያ አሠላለፍ የኋላ ኋላ ወደ ጂቡቲ ሊሆን እንደሚችል አስረድተዋል፡፡

የኢትዮጵያ በጂቡቲ ወደብ መጠቀምና የግብፅ ከኤርትራ ጋር የጋራ የጦር ቀጣና መመሥረት ጉዳዩን ትኩረት እንዲሰጠው እንደሚያደርግ፣ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ አንድ የውጭ ፖሊሲ ተንታኝ ተናግረዋል፡፡

ለዘመናት ኢትዮጵያንና ግብፅን ሲያወዛግብ የነበረው የዓባይ ወንዝ አገሮች አሠላለፍ እንዲይዙ ምክንያት እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡ ሰሞኑን ስለናይል በኡጋንዳ የመከረው የአባል አገሮች የመሪዎች ስብሰባ፣ ኢትዮጵያና ግብፅን በመጠኑም ቢሆን እንዳወዛገበ እየተነገረ ሲሆን ባለሙያው ይህ ጉዳይ ከሁለቱ አገሮች አልፎ ወደ ኤርትራና ጂቡቲ ሊሸጋገር የሚችልበት ዕድል ሰፊ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ በፊት በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል ተፈጥሮ የነበረውን ጦርነት ማስቆም ያልቻለው የአፍሪካ ኅብረት፣ አሁንም በኤርትራና በጂቡቲ እንዲሁም ከእነሱ ጎን በተሠለፉ አገሮች ላይ ያለውን ፖለቲካዊ አንድምታ ለመፍታት እንደሚቸገር ባለሙያው አስረድተዋል፡፡

ሰሞኑን ናይልን በተመለከተ በተካሄደው የአባል አገሮች ስብሰባ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ከግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ጋር ተገኝተው ነበር፡፡ የሁለቱ አገር መሪዎች ቁርጥ ያለ ስምምነት ላይ መድረስ እንዳልቻሉ የግብፅ ‹‹ኢንዲፔንደንት›› ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ የዓባይ ወንዝ ቀይ መስመር የተሰመረበት ጉዳይ ነው ብሏል፡፡ ይህ ወንዝ ሁለቱን አገሮች ለዘመናት ሲያጨቃጭቅ መቆየቱ ይታወቃል፡፡ ግብፅ ታሪካዊ መብት እያለች የምትጠራውን እ.ኤ.አ. የ1959 ስምምነት ውድቅ በማድረግ፣ ከዛሬ ስድስት ዓመት በፊት ታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ እየተገነባ ነው፡፡ ግብፅ ግድቡን በአንክሮ እየተከታተለችው እንደሆነም ይታወቃል፡፡

ሰሞኑን እየወጡ ያሉ መረጃዎች እንደሚጠቀሙት የቀድሞው የግብፅ ፕሬዚዳንት የነበሩት ሆስኒ ሙባረክ እስከ ዛሬ ድረስ በሥልጣን ላይ ቢቆዩ ኖሮ፣ ኢትዮጵያ የዓባይን ወንዝ ልትገድብ እንደማትችል መናገራቸውን የተለያዩ ሚዲያዎች ሲዘግቡት ሰንብተዋል፡፡

በዱሜራ ግዛት የተነሳ ወደ ጦርነት ሊገቡ እንደሚችሉ የሚነገርላቸው ኤርትራና ጂቡቲ፣ ከኋላቸው ደግሞ ኢትዮጵያና ግብፅ ጉዳዩን በተለየ ትኩረት እየተከታተሉት እንደሆነ እየተነገረ ነው፡፡

ምንም እንኳ የኢትዮጵያ መንግሥት ሁለቱ አገሮች ጉዳዩን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ መፍታት እንዳለባቸው እየገለጸ ቢሆንም፣ ግብፅ ደግሞ ሠራዊቴን በአካባቢው አሰማርቼ ለሁለቱ አገሮች ሰላም ላስፍን እንዳለች ቢነገርም፣ ጨዋታው ያለው ከበስተጀርባ እንደሆነ  አቶ አበበ ያስረዳሉ፡፡

‹‹ከ1990 ዓ.ም. ወዲህ ከኢትዮጵያ ጋር ዓይንና ናጫ ሆና ለሁለት አሥርት ዓመታት ያህል የዘለቀችው ኤርትራ፣ ከሳዑዲ ዓረቢያና ከግብፅ ጎን የመቆም ምክንያቷ የዓባይ ወንዝ ከኢትዮጵያና ከግብፅ ጋር ያለውን ትስስር በማጥናት ነው፤›› የሚሉት የውጭ ፖሊሲ ተንታኙ፣ ጉዳዩ ከዚህም አለፍ ያለ እንደሆነ ያብራራሉ፡፡ እስከ የሚቀጥለው ሳምንት ሰኞና ማክሰኞ እንደሚቆይ የተነገረው የአፍሪካ የመሪዎች ጉባዔ ጉዳዩን በልዩ ትኩረት ዓይቶ የመፍትሔ አቅጣጫ እንደሚያስቀምጥ ቢነገርም፣ ሁሉም የአፍሪካ አገሮች የራሳቸው አሠላለፍ ስላላቸው አፋጣኝ መፍትሔ ከማምጣት አንፃር ፈተና ሊሆንበት እንደሚችል አቶ አበበ ጠቁመዋል፡፡

በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል ባድመና ሽራሮ፣ በኢትዮጵያና በግብፅ መካከል ዓባይ ወንዝ፣ በኤርትራና ጂቡቲ መካከል ደግሞ የዱሜራ ግዛት ውዝግቦች መኖር ቀጣናው ከባድ እንደሆነና በአንድ ወይም በሁለት ቀናት የአፍሪካ መሪዎች ጉባዔ ሊፈታ እንደማይችል ባለሙያው አስረድተዋል፡፡

‹‹የኳታርና የቱርክ ወዳጆች በአንድ ጎራ፣ የሳዑዲ ዓረቢያና የአሜሪካ፣ እንዲሁም የግብፅ ወዳጆች በሌላ ጎራ የመሠለፍ አዝማሚያ እየታየ በመሆኑ ጉዳዩ የከረረ ነው፤›› ሲሉ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ተንታኙ ያስረዳሉ፡፡

የቱርኩ ፕሬዚዳንት ኤርዶሃን ሳዑዲ ዓረቢያ መራሹ የባህረ ሰላጤው አገሮች ስብስብ በኳታር ላይ ዕርምጃ መውሰድ ዓለም አቀፍ ሕግን የሚጥስ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ይህ ዓለም አቀፍ ሕግን የሚጥስ የባህረ ሰላጤው አገሮች በኳታር ላይ ዕርምጃ መውሰድ መፍትሔ ለማምጣት በሚኬድበት መንገድ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳለው አቶ አበበ ይናገራሉ፡፡ የአፍሪካ ኅብረት ይህንን ጉዳይ በዋናነት ይዞ ሲንቀሳቀስ በመጀመሪያ ሕግ በጣሱ አፍሪካ ውስጥ ባሉ አገሮች ግብፅን ጨምሮ ዕርምጃ በመውሰድ ሊሆን እንደሚገባ ባለሙያዎች እየተናገሩ ነው፡፡ አንድን አገር 13 ያህል መሥፈርቶች ደርድሮ ይህን ግዳጅ ካልተወጣሽ ማለት አሁንም በቀጣናው ሰላም ለማስፈን በሚደረገው እንቅስቃሴ ላይ እንቅፋት ሊሆን እንደሚችል እየተነገረ ነው፡፡

ኤርትራ በመሪ ደረጃ በጉባዔው ላይ አለመሳተፏ ደግሞ ሌላው ችግር ሊሆን እንደሚችል እየተነገረ ነው፡፡ በቀጣናው በተለይም በሰሜን ምሥራቅ ያለውን የአፍሪካ ቀጣና የማተራመስ ዕቅድ እንዳለው የሚነገረው የኤርትራ መንግሥት፣ አሁንም የአፍሪካ ኅብረት የሚወስነውን ውሳኔ ለመቀበል ዝግጁ ሊሆን እንደማይችል መላምቶች አሉ፡፡ ከዚህ በፊት በዱሜራ ግዛት በኤርትራና በጂቡቲ መካከል በነበረው እሰጥ አገባና ጦርነት ምክንያት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የወሰነውን ውሳኔ ኤርትራ አልቀበልም ማለቷ ይታወሳል፡፡ ከዓረብ አገሮች በስተቀር ራሱን እንዳገለለ የሚነገርላት የኤርትራ መንግሥት በምሥራቅ አፍሪካ ለሚከሰቱ ሽብሮችና ግጭቶች ዋነኛውን ሚና እንደሚጫወት፣ በጥር ወር 2009 ዓ.ም. የታተመውና ‹‹ዲስኮርስ›› የተሰኘው መጽሔት ገልጿል፡፡

በምሥራቅ አፍሪካ የተጋረጠውን ፈተና ከመፍታት አኳያ የአፍሪካ ኅብረት ብዙ ሥራዎችን መሥራት እንዳለበት ባለሙያዎች ሲናገሩ ተደምጧል፡፡ በተለይም የ29ኛው የአፍሪካ የመሪዎች ጉባዔ ላይ በዚህ ቀጣና ያለው አሠላለፍ መስመር ማስያዝ እንዳለበት ተጠቁሟል፡፡

በአሁኑ ወቅት ለሁለት እየተከፈለ የመጣውን የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች አሠላለፍ ኢትጵያ ገለልተኛ ሆና እየተከታተለችው እንደሆነ በተደጋጋሚ ጊዜ ስትናገር ተደምጧል፡፡ ኳታርና ኢትዮጵያም ከብዙ ዓመታት በኋላ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን በቅርቡ አድሰዋል፡፡ ከሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት ጋር ያለው ግንኙነትም ጥሩ የሚባል እንደሆነ የኢትዮጵያ መንግሥት በተደጋጋሚ ጊዜ ገልጿል፡፡ በዚህ በሁለት በተከፈለው የኳታርና የሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥታት ጎራ የኢትዮጵያ አሠላለፍ ወዴት መሆን እንደለበት የኋላ ኋላ  እንደሚወሰን የሚታወቅ ቢሆንም፣ አቶ አበበ ግን ከሳዑዲ ጎን ልትሆን እንደማትችል ተናግረዋል፡፡ ‹‹የሳዑዲ ዓረቢያ፣ የግብፅና የኤርትራ በአንድ ወገን መሠለፍ ኢትዮጵያ በግድ ወደ ኳታርና ጂቡቲ እንድትሄድ ያስገድዳታል፤›› ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ሁለቱ ቡድኖች ችግራቸውን በመቀራረብና በመወያየት መፍታት እንዳለባቸው አሳስቧል፡፡ በዚህም የተነሳ ኢትዮጵያ ወደ አንዱ ጎን ልትሄድ እንደማትችልና የማደራደር ተግባሯን እንደምትቀጥል ገልጿል፡፡

ኢትዮጵያ በአፍሪካ ያላትን ተሰሚነትና ኃያልነት ተጠቅማ በቀጣናው እያንዣበበ ያለውን የፖለቲካ መንፈስ ማረጋጋት እንዳለበት እየተነገረ ነው፡፡ የአፍሪካ ኅብረት በ29ኛው የመሪዎች ጉባዔ ላይ ከዚህ በፊቱ የተሻለ አሠራርና የክትትል ሥርዓት በመዘርጋት የቀጣናውን ሰላም ማስከበር እንዳለበት ተነግሯል፡፡

የአፍሪካ አገሮች በዓረብ ባህረ ሰላጤ አገሮች መካከል የተፈጠረውን መከፋፈል መሠረት አድርገው ወደ አንዱ ወገን ሳያዳሉ፣ ሚዛናዊ በሆነና በሰከነ መንገድ ጉዳዩን ማጤንና መከታተል እንዳለባቸው ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡

በቀይ ባህር ያለውን ጂኦ ፖለቲካዊ አንድምታ ኢትዮጵያንና ግብፅን በመያዝና ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ የግጭት ቀጣና እንዳይሆን መሥራት ተገቢ መሆኑን ብዙዎችን ያስማማል፡፡  

Standard (Image)

ልብ አንጠልጣዩ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታና የገጠመው የፋይናንስ ድርቅ

$
0
0

 

የቀድሞ የሥራና ከተማ ልማት ሚኒስትር አቶ መኩሪያ ኃይሌ በ2005 ዓ.ም. ክረምት መንግሥት አራት ዓይነት የመኖሪያ ቤቶች ፕሮግራም እንደሚጀመር ይፋ ሲያደርጉ፣ በመኖሪያ ቤት ዕጦት ሲሰቃይ ለቆየው የአዲስ አበባ ከተማ ሕዝብ ታላቅ የምሥራች ነበር፡፡

አንድ ሚሊዮን የሚጠጉ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች እንደ አቅማቸው በመቆጠብ በ10/90፣ በ20/80፣ በ40/60 እና በመኖሪያ ቤት ኅብረት ሥራ ማኅበራት ጭምር ምዝገባ አካሂደዋል፡፡ ቤቶቹን ለማግኘት የግድ ቁጠባ ብቻ ሳይሆን ሙሉ ክፍያ የፈጸመ ቅድሚያ ያገኛል በመባሉ ጭምር፣ በርካታ ነዋሪዎች ጥሪታቸውን ለማፍሰስ ወደ ኋላ አላሉም፡፡

በ40/60 ፕሮግራም ከተመዘገቡ 164,779 ነዋሪዎች ውስጥ አንዱ አቶ ነገደ ወልደ ሰማያት ናቸው፡፡ አቶ ነገደ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ለዓመታት በኪራይ ቤት ውስጥ የሚኖሩ ሲሆን፣ መንግሥት ከጀመራቸው የመኖሪያ ቤቶች በተለይ በ40/60 ፕሮግራም ተጠቃሚ ለመሆን በመመዝገብ የቀደማቸው ብዙ ነዋሪ አይደለም ይላሉ፡፡

አቶ ነገደ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት የቤት ፕሮግራሞቹን ባስተዋወቁበት ወቅት ቅድሚያ የከፈለ ቅድሚያ የሚያገኝበት አሠራር መኖሩን በመግለጻቸው፣ እሳቸው ካለባቸው የመኖሪያ ቤት ችግርና ለረዥም ዓመታት በማያቋርጥ የኪራይ ዋጋ ጭማሪ ሲሰቃዩ የቆዩ በመሆናቸው ምዝገባ በተጀመረ በመጀመርያው ቀን ጣጣቸውን መጨረሳቸውን ይናገራሉ፡፡

‹‹የ40/60 ቤቶች ፕሮግራም በተጀመረበት ነሐሴ 6 ቀን 2005 ዓ.ም. ረፋድ ላይ ለባለ ሁለት መኝታ ሙሉ ክፍያ የሚጠየቀውን 250 ሺሕ ብር ከፍያለሁ፤›› በማለት አቶ ነገደ ገልጸው፣ ‹‹ነገር ግን የመኖሪያ ቤቶቹ ግንባታ በ18 ወራት ይጠናቀቃል ቢባልም አራት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በቀላል ሒሳብ እኔ ከዚያ ወዲህ ለመኖሪያ ቤት ኪራይ ከ114 ሺሕ ብር በላይ አውጥቻለሁ፤›› በማለት የችግራቸውን ጥልቀት አብራርተዋል፡፡

‹‹ምን ዓይነት አሠራር ነው?›› ሲሉ አቶ ነገደ የ40/60 ቤቶች ፕሮግራም የመዘግየቱን ሚስጥር ይጠይቃሉ፡፡

አቶ ነገደን ጨምሮ በተለይ በ20/80 እና በ40/60 ቤቶች ፕሮግራም ተመዝግበው እየተጠባበቁ የሚገኙ ነዋሪዎችን ያስደነገጠው የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስትሩ  አምባቸው መኮንን (ዶ/ር)፣ የ2009 በጀት ዓመት የአሥር ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡበት ወቅት ያካተቱት ሐሳብ ነው፡፡

‹‹በቤት ልማት ፕሮግራም በሁለተኛው ዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ 750 ሺሕ መኖሪያ ቤቶችን ለመገንባት የታቀደ ቢሆንም፣ በበጀት ያልተደገፈ በመሆኑ ዕቅዱን ለማስፈጸም ትልቅ ችግር ሆኖ ሳይፈታ ቀጥሏል፡፡ በ2009 በጀት ዓመት ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተፈቀደው የቤት ልማት ፋይናንስ ዘግይቶ በመለቀቁ የሥራ ተቋራጮችና የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ሥራ በማቆም ተበትነው የነበረ ሲሆን፣ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በብድር ፋይናንስ ድጋፍ እንዲሰባሰብ በማድረግ ግንባታውን ለማስቀጠል ተችሏል፤›› በማለት ሚኒስትሩ ሪፖርታቸውን አቅርበዋል፡፡

ሚኒስቴሩ በ2009 በጀት ዓመት የስድስት ወራት ሪፖርት ላይ እንደገለጸው፣ ‹‹ለሚገነቡ ቤቶች የግንባታ ግብዓቶች መግዣ የሚውል የቦንድ ብድርና የውጭ ምንዛሪ ፍላጎት ከግንባታ ፕሮጀክቶቹ መረጃ በመሰብሰብ የፍላጎት ሰነድ የተዘጋጀ ሲሆን፣ በዚህ መሠረት 31.03 ቢሊዮን ብር የአገር ውስጥ ገንዘብ ፍላጎት ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ቀርቦ 15 ቢሊዮን ብር የቦንድ ብድር ተፈቅዷል፡፡ ከዚህ ውስጥ 8.5 ቢሊዮን ብር ለአዲስ አበባ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት (20/80)፣ 6.5 ቢሊዮን ብር ለአዲስ አበባ ቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ (40/60) ተደልድሏል፡፡ በዚህም ሥራውን ማስቀጠል ተችሏል፤›› በማለት የሚገልጸው የሚኒስቴሩ ሪፖርት፣ ‹‹ነገር ግን ሀብትን በተገቢው መንገድ ሥራ ላይ ማዋል በሚለው መርህ መሠረት፣ ክፍያዎች በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የቅርብ ክትትል ቁጥጥር ተግባራዊ እንዲደረጉ መወሰኑን ተከትሎ የክፍያ አፈጻጸሙ የተጠበቀውን ያህል ቀልጣፋ ሊሆን ባመቻሉ፣ በስድስት ወራት ውስጥ ያለው የቦንድ ብድር አጠቃቀም በአጠቃላይ 2.45 ቢሊዮን ብር በላይ ከፍ ሊል አልቻለም፡፡ ይኼውም ለ40/60 ቤቶች 1.05 ቢሊዮን ብር፣ ለ20/80 ደግሞ 1.4 ቢሊዮን ብር ብቻ ጥቅም ላይ ውሏል፤›› ሲል ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

ይህ አፈጻጸም ለ40/60ም ሆነ ለ20/80 ተመዝጋቢዎች መልካም ዜና አይደለም፡፡ አቶ ነገደ እንደሚሉት በተለይ የ40/60 ቤቶች ከ2008 ዓ.ም. ጀምሮ በቅርቡ ይተላለፋሉ እየተባለ እስካሁን ቆይተው በድጋሚ የፋይናንስ ጫና አለ በሚል ምክንያት ወደ ሌላ አማራጮች ለመሄድ ማሰቡ አሳሳቢ ነው፡፡

‹‹ሁኔታው ሕዝብ በመንግሥት ላይ ያለውን አመኔታ እንዲያጣ ያደርጋል፤›› ሲሉ አቶ ነገደ ያብራራሉ፡፡ ሚኒስትሩ መንግሥት በቤቶች ልማት ላይ ያለውን ጫና ለመቀነስ አማራጭ አድርገው ካቀረቧቸው መካከል የመኖሪያ ቤት ኅብረት ሥራ ማኅበርን ጠቅሰዋል፡፡ ሚኒስትሩ ሰኔ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዳብራሩት በመንግሥት አስተባባሪነት በአዲስ አበባ የሚገነቡ ቤቶች ቀደም ሲል በርካታ ቤቶች በመጀመራቸው ሥራው ግዙፍ በመሆኑ ለቤቶቹ ልማት የሚያስፈልገውን ፋይናንስ ማግኘት አዳጋች ነው፡፡  

‹‹በከተሞች የሚስተዋለውን የመኖሪያ ቤቶች እጥረት ለመቅረፍ የኅብረት ሥራ ማኅበራት ቤት ግንባታ አማራጭን በሰፊው ለማስቀጠል በልዩ ትኩረት እንዲፈጸም እናደርጋለን፤›› ሲሉ አዲሱን አካሄድ አብራርተዋል፡፡

መንግሥት በ2005 ዓ.ም. ክረምት ይፋ ካደረጋቸው ፕሮግራሞች መካከል አንዱ የመኖሪያ ቤት ኅብረት ሥራ ማኅበር ነው፡፡ በዚህ ፕሮግራም 101 ማኅበራት የተቋቋሙ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ሁሉም ማኅበሮች በየካ ክፍለ ከተማ መሪ ሎቄ አካባቢ ቦታ ተሰጥቷቸው ግንባታ ጀምረዋል፡፡ ነገር ግን ይህ ፕሮግራም ብዙ ቢባልበትም፣ ማኅበራቱ አሁን ያሉበት ደረጃ ለመድረስ ብዙ ውጣ ውረዶችን አልፈዋል፡፡

አቶ ስንታየሁ ምትኩ የአንድ መኖሪያ ቤት ኅብረት ሥራ ማኅበር አባል ናቸው፡፡ አቶ ስንታየሁ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ መጀመርያ የነበረው አሠራር በመቀያየሩ ብዙ ችግሮች አጋጥመው ነበር፡፡  

‹‹መጀመርያ በተዋወቀው ፕሮግራም አፓርትመንቶችና በመሀል ከተማ የሚገኙ ቪላ ቤቶች ነበር እንዲገነቡ የታሰበው፡፡ በኋላ ማሻሻያ ተደርጎ ሁሉም ግንባታዎች አፓርታማ እንዲሆኑ ተደርገዋል፤›› ሲሉ አቶ ስንታየሁ ገልጸው፣ ‹‹ማኅበራት 50 በመቶ የሚሆነውን የግንባታ ወጪ በባንክ ካስገቡ በኋላ በሁለት ወር ውስጥ መሬት እንደሚቀርብ የተገለጸ ቢሆንም፣ ገንዘቡ በዝግ ሒሳብ ተቀምጦ ሁለት ዓመታት ተቆጥረዋል፤›› ሲሉም ፕሮግራሙ ብዙ ውጣ ውረዶች እንደነበሩበት ገልጸዋል፡፡

አቶ ስንታየሁ እንደሚሉት፣ ይህንን አማራጭ መንግሥት ይዞ መቅረቡና ከዚህ በኋላም በሰፊው ይዞ መቀጠል ማሰቡ መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ባንኮች ፋይናንስ ካላደረጉት ፍጥነቱና ተፈጻሚነቱ ጥያቄ ውስጥ እንደሚገባ አቶ ስንታየሁ ተናግረዋል፡፡ ባንኮች በመኖሪያ ቤት ኅብረት ሥራ ማኅበራት ለተደራጁ ሠራተኞቻቸው የፋይናንስ ድጋፍ ያቀረቡ በመሆናቸው፣ የማኅበራቱ የግንባታ አፈጻጸም የተሻለ መሆኑን አቶ ስንታየሁ ጠቁመው፣ ፋይናንስ ማግኘት ያልቻሉ ማኅበራት ግን አሁንም በችግር ውስጥ እንደሚገኙ አክለዋል፡፡

አሁን ለብዙዎች ጥያቄ የሆነባቸው ጉዳይ ባንኮች ለማኅበራት ፋይናንስ ማቅረብ አለማቅረባቸው ብቻ ሳይሆን፣ በተለይ በ20/80 እና በ40/60 ቤቶች ፕሮግራም የተመዘገቡ ነዋሪዎች ገንዘብ እየቆጠቡ የሚገኙ ቢሆንም ለግንባታው የሚሆን ፋይናንስ ግን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሚገባው መጠን እያቀረበ አለመሆኑ ነው፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ 17 ሺሕ የሚጠጉ የ40/60 ተመዝጋቢዎች ሙሉ ክፍያ ፈጽመዋል፡፡ በየዓመቱም ከስድስት ቢሊዮን ብር ያላነሰ ገንዘብ እየተሰበሰበ ነው፡፡

በሚኒስቴሩ የስድስት ወራት ሪፖርት እንደተቀመጠው 31.01 ቢሊዮን ብር የቦንድ ብድር እንዲለቀቅ ቢጠየቅም፣ የተፈቀደው ግማሽ ያህሉ ማለትም 15 ቢሊዮን ብር ብቻ ነው፡፡ ይህ ገንዘብም ቢሆን ፍሰቱን ጠብቆ እየተለቀቀ ባለመሆኑ ኮንትራክተሮች፣ አማካሪዎችና ጥቃቅንና አነስተኛ ድርጅቶች ከግንባታ ሳይቶች እየተበተኑ ነው፡፡ ተቋማቱን በድጋሚ ለማሰባሰብም ትልቅ ችግር እየሆነ ይገኛል፡፡

መንግሥት ከ2008 እስከ 2012 ዓ.ም. ተግባራዊ በሚሆነው ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን 750 ሺሕ ቤቶች እንደሚገነባ ዕቅድ አውጥቷል፡፡ በዕቅዱ መሠረት በየዓመቱ 150 ሺሕ ቤቶችን መገንባት ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን የትራንስፎርሜሸን ዕቅዱ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ ሁለት ዓመታት ቢቆጠሩም ግንባታው በዕቅዱ መሠረት አልሄደም፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት አንድ መኖሪያ ቤት ለመገንባት 200 ሺሕ ብር ያስፈልጋል ቢባል፣ በአጠቃላይ 150 ሺሕ ቤቶች ለመገንባት 30 ቢሊዮን ብር ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን ይህ ገንዘብ እየቀረበ ባለመሆኑ የቤቶች ግንባታ አፈጻጸም ጥያቄ ውስጥ ገብቷል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ አባተ ስጦታው በየካቲት 2009 ዓ.ም. በታተመው ‹ቁጠባ› መጽሔት ባስተላለፉት መልዕክት ላይ እንደገለጹት፣ ባለፉት 12 ዓመታት ከ311 ሺሕ በላይ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ተገንብተዋል፡፡ ከዚህ ቁጥር ውስጥ 175 ሺሕ ቤቶች ለተጠቃሚዎች ተላልፈዋል፡፡ በ20/80 እና በ40/60 ቤቶች ፕሮግራም 136 ሺሕ ቤቶች በግንባታ ላይ ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን ባለፉት 12 ዓመታት የተገነቡትና እየተገነቡ ያሉት የጋራ መኖሪያ ቤቶች 311 ሺሕ ብቻ ቢሆኑም ሁለት ዓመታት በተቀነሱለት የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ላይ 750 ሺሕ ቤቶችን ለመገንባት መታቀዱ፣ የዕቅዱን መነሻ ሐሳብ ጥያቄ ውስጥ ከቶታል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ መኖሪያ ቤት ለማግኘት የተመዘገቡ ነዋሪዎች አንድ ሚሊዮን ይጠጋሉ፡፡ ምዝገባው ከተጠናቀቀ በመጪው ነሐሴ ወር አራተኛ ዓመት የሚያስቆጥር በመሆኑ፣ በየዓመቱ ቤት የሚፈልጉ ዜጎች እየጨመረ በመሄድ ላይ እንደሚገኝ እየታየ ነው፡፡ ተመዝጋቢዎች ቤታቸውን የሚያገኙበት ወቅትና አዳዲስ ቤት ፈላጊዎችም መስተናገድ የሚጀምሩበት ጊዜ አጓጊ ሆኗል፡፡

መንግሥት ለቤት ልማት የሚያስፈልገው ወጪና ግንባታውን የሚያካሂዱ ተቋማት ከአገር ውስጥ ብቻ እንዲሆን አድርጓል፡፡ ነገር ግን ከሁለት ዓመት በፊት የመኖሪያ ቤት ጉዳይ የተቀናጀ መልክ እንዲኖረው የተደረገ ቢሆንም፣ እጥረቱ ግን ማኅበራዊ ቀውስ እየፈጠረ በመሆኑ በፍጥነት ግንባታው እንዲጠናቀቅ ለማድረግ የውጭ ኩባንያዎች ተሳታፊ እንዲሆኑ ተወስኖ ነበር፡፡

ይህንን ዕቅድ ለማሳካት የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ፕሮጀክት ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት ባወጣው ዓለም አቀፍ ጨረታ 28 የሚጠጉ የውጭና የአገር ውስጥ ደረጃ አንድ ኮንትራክተሮች ተወዳድረው ነበር፡፡ ነገር ግን ምክንያቱ ባልተገለጸ ምክንያት ዕቅዱ ተፈጻሚ መሆን ሳይችል ቀርቷል፡፡

በመኖሪያ ቤቶች ግንባታ ዘርፍ የውጭ ኮንትራክተሮች ለማስገንባት የተለያዩ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አቶ መኩሪያና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ በይፋ መግለጫ ሰጥተው እንደነበር ይታወሳል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ1996 ዓ.ም. ባካሄደው የጂአይኤስ ዳሰሳ በከተማው 387 ሺሕ ቤቶች እንዳሉ አመልክቷል፡፡ ከእነዚህ ቤቶች መካከል 269,814 የሚሆኑት የውኃ መስመርና በቂ የመኖሪያ ስፋት የሌላቸው፣ ነዋሪዎች የቤት ባለቤት ያልሆኑባቸው፣ ያረጁና የተጎሳቆሉ ሠፈሮች ውስጥ የሚገኙ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 25 በመቶ የሚሆኑት በግልም ሆነ በጋራ መጠቀም የሚያስችል መፀዳጃ ቤት የሌላቸው ናቸው፡፡

ከ1995 እስከ 1998 ዓ.ም. ድረስ የአዲስ አበባ ከተማ ጊዜያዊ አስተዳደር ከንቲባ የነበሩት  አርከበ ዕቁባይ (ዶ/ር) ይህንን ገጽታ ለመቀየር በርካታ ዕርምጃዎች ወስደው ነበር፡፡ እነዚህ ጎስቋላ መንደሮች በሚገኙባቸው መሀል ከተማ በዚያን ጊዜ በየዓመቱ በ1.5 ቢሊዮን ብር 50 ሺሕ ቤቶች ለመገንባት ታቅዶ ነበር፡፡

በዚህ ዕቅድ ተጠቃሚ ለመሆን ከ400 ሺሕ በላይ የአዲስ አበባ ቤት ፈላጊዎች ተመዝግበው ነበር፡፡ በዶ/ር አርከበ የሚመራው የከተማው ካቢኔ ይህንን ዕቅድ ተግባራዊ ለማድረግ በርካታ መንገዶችን የተጓዘ ቢሆንም፣ በ1997 ዓ.ም. በተካሄደው ምርጫ ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (ቅንጅት) አሸንፎ በተለያዩ ፖለቲካዊ ምክንያቶች ከተማውን መረከብ ባለመቻሉ፣ የዶ/ር አርከበ ካቢኔ በባለአደራ አስተዳደር ተተክቷል፡፡

ከዚያን ጊዜ በኋላ የኮንዶሚኒየም ቤቶች ግንባታ እንደ እንዳጀማመሩ መቀጠል ያልቻለ ሲሆን፣ ከሞላ ጎደል በስኬት መጠናቀቅ የቻለው የ10/90 ፕሮግራም ብቻ ነው፡፡

እስካሁን አንድም ቤት ሊተላለፍለት ያልቻው የ40/60 ቤቶች ፕሮግራም ነው፡፡ በ2005 ዓ.ም. በተካሄደው የቤት ፈላጊዎች ምዝገባ ለባለአንድ መኝታ 16,547፣ ለባሁለት መኝታ 75,547 እና ለባለሦስት መኝታ 72,439 ነዋሪዎች፣ በድምሩ 164,775 ሰዎች ተመዝግበዋል፡፡

የአዲስ አበባ ቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ የኮሙዩኒኬሸን የሥራ ሒደት መሪ አቶ ዮሐንስ ዓባይነህ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የ40/60 ፕሮግራም በሦስት ምዕራፎች ተከፍሎ እየተካሄደ ነው፡፡

በመጀመርያው ምዕራፍ 1,292፣ በሁለተኛው ምዕራፍ 20,932 እና በሦስተኛው ምዕራፍ 17,005 ቤቶች እየተገነቡ ነው፡፡

በድምሩ 39,229 ቤቶች እየተገነቡ ሲሆን፣ በመጀመርያው ምዕራፍ የተጀመሩት 1,292 ግንባታቸው ተጠናቆ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ርክክብ መካሄዱ ተሰምቷል፡፡ ‹‹በ13 ሳይቶች እየተነቡ ካሉት መካከል በሠንጋ ተራና በክራውን ሳይቶች ከተገነቡ 19 ሕንፃዎች ውስጥ 17 ሕንፃዎች (876 ቤቶች) ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አስረክበናል፤›› ሲሉ አቶ ዮሐንስ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

‹‹በሁለተኛው ምዕራፍ እየተገነቡ ያሉት 20,932 ቤቶች የግንባታ አፈጻጸማቸው 65.2 በመቶ፣ በሦስተኛው ምዕራፍ እየተገነቡ የሚገኙት 17,005 ቤቶች 36 በመቶ ደርሰዋል፤›› በማለት አቶ ዮሐንስ አክለዋል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በጀት ዓመት ለ40/60 ቤቶች 6.5 ቢሊዮን ብር በጀት ተመድቦ እየተገነባ ሲሆን፣ የማጠናቀቂያ ዕቃዎች የግዥ ሒደት አስቸጋሪ ነበር፡፡ አሁን ግን ኮንትራክተሮቹ ራሳቸው እየገዙ እንዲያከናውኑ በመደረጉ ችግሩ ተቃሏል ይላሉ አቶ ዮሐንስ፡፡

በ20/80 ቤቶች በኩል በ2006 ዓ.ም. የተጀመሩና በሁለት ፓኬጆች የተከፋፈሉ 52,651 ቤቶች አሉ፡፡ በመጀመርያው ፓኬጅ 26,480 ቤቶች ሲሆኑ፣ አፈጻጸማቸው 65.52 በመቶ ደርሷል፡፡ በሁለተኛው ፓኬጅ የተካተቱት 26,171 ቤቶች አፈጻጸማቸው 48.3 በመቶ መድረስ ተመልክቷል፡፡ ለእነዚህ ግንባታዎች በበጀት ዓመቱ 8.5 ቢሊዮን ብር በጀት ተይዟል፡፡

በአጠቃላይ የ40/60ም ሆነ የ20/80 ቤቶች ግንባታ ዝቅተኛ አፈጻጸም ላይ መሆኑ፣ አቶ ነገደን ጨምሮ ቤት ተመዝግበው ለሚጣበቁ ነዋሪዎች መልካም ዜና አይደለም፡፡

በሁለተኛው ምዕራፍ በግንባታ ላይ ያሉ የ40/60 ቤቶች

ተ.ቁ

የሳይቱ ስም

ብሎክ ብዛት

የቤቶች ብዛት

አሁን ያለበት ደረጃ (%)

1

አስኮ

13

1,836

64.86

2

እህል ንግድ

6

792

90.37

3

ሕንፃ አቅራቢ

8

1,136

81.77

4

መሪ ሎቄ

17

1,988

64.82

5

ቦሌ ቡልቡላ አንድ

28

3,108

86.39

6

ቦሌ አያት ሎት አንድ፣ ሁለትና ሦስት

93

5,691

64.71

7

ቦሌ አያት አንድ ሎት አራት

40

4,038

56.08

8

ቱሪስት

11

2,343

64.82

              68.20 በመቶ

 

 

በሦስተኛው ምዕራፍ በግንባታ ላይ ያሉ የ40/60 ቤቶች

ተ.ቁ

የሳይቱ ስም

ብሎክ ብዛት

የቤቶች ብዛት

አሁን ያለበት ደረጃ (%)

1

ቦሌ በሻሌ

58

5,596

29.16

2

ሰሚት

10

400

46.38

3

ቦሌ አያት ሁለት

48

7,101

38.59

4

ቦሌ ቡልቡላ ሁለት

24

2,908

49.08

                አማካይ 36.91 በመቶ

 

ምንጭ፡- የአዲስ አበባ ቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ

 

 

Standard (Image)

‹‹አዋጁ የኦሮሚያን ክልል ከሌሎች ክልሎች በተለየ ሁኔታ ሌላ ፕላኔት ውስጥ እንዳለች ያደርጋታል ብሎ ማሰብ ስህተት ነው››

$
0
0

ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር)፣ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር

ባለፉት ሃያ ስድስት ዓመታት በኢትዮጵያ ውስጥ ከተከሰቱ አገራዊ ቀውሶች መካከል፣ በ1997 ዓ.ም. በተካሄደው አገር አቀፍ ምርጫና ከዚህ ጋር በተያያዘ የተቀሰቀሰው ግጭት አንዱ ነው፡፡

በ2008 ዓ.ም. በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች የተቀሰቀሰው ሕዝባዊ ተቃውሞና ነውጥ ደግሞ ሌላው ሲሆን፣ በዚህ ችግር የተነሳ ከስድስት መቶ በላይ የሰው ሕይወትና በሚሊዮን የሚቆጠር የአገር ሀብት መውደሙ ይታወሳል፡፡

በ2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ለተቀሰቀሰው ግጭትና ሁከት ዋነኛ ምክንያት እንደሆኑ ከሚጠቀሱት ጉዳዮች መካከል አንደኛው ከኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞችና ከአዲስ አበባ የጋራ ማስተር ፕላን ጋር የተያያዘው ነው፡፡ በሕዝቡ ዘንድ ተፈጥሮ በነበረ ቅሬታና ከዚህ ጋር በተያያዙ ሌሎች ጉዳዮች ከፍተኛ ችግር ተፈጥሮ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

የአዲስ አበባን ከተማ ወደ ጎን ለማስፋት በተደረገው እንቅስቃሴ ከኦሮሚያ ክልል ሕዝብ ከፍተኛ ተቃውሞ የገጠመው ሲሆን፣ ማስተር ፕላኑ ብዙ ጥያቄዎችን አስነስቶ አልፏል፡፡ በኦሮሚያ ክልል ነዋሪዎች ዘንድ በተደጋጋሚ ጊዜ ሲነሳ የነበረው ዋነኛው ጉዳይ ደግሞ ኦሮሚያ ክልል ከአዲስ አበባ ከተማ ልታገኝ ስለሚገባት ልዩ ጥቅም እንደሆነ ይታወቃል፡፡

የዛሬዋ አዲስ አበባ ከዛሬ አንድ መቶ ዓመት በፊት የኦሮሚያ አርሶ አደሮች ይኖሩባትና  ፊንፊኔ እያሉ ይጠሯት እንደነበር ይነገራል፡፡ እ.ኤ.አ. ከ1886 ወደ 1887 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ ላይ የንጉሠ ነገሥቱ መቀመጫ እጅግ ቀዝቃዛና አየሩ ተስማሚ ካልሆነው የእንጦጦ ከፍታ ትንሽ ኪሎ ሜትር ወረድ ብሎ፣ ከባህር ጠለል በላይ 2,500 ሜትር ከፍታ ወዳለው ረባዳ ሥፍራ እንደተዛወረም ይነገራል፡፡ ዋና ከተማውን ወደዚህ ሥፍራ ለማዞር ሐሳብ ያመነጩትና ስሙንም አዲስ አበባ ብለው የሰየሙት የዳግማዊ ምኒልክ ባለቤት እቴጌ ጣይቱ እንደነበሩ ታሪክ ያስረዳል፡፡

ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አዲስ አበባ ተብላ መጠራት እንደጀመረች የሚነገርላት የዛሬዋ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ በአሁኑ ወቅት የአፍሪካ ኅብረት፣ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማትና ሌሎች ድርጅቶች መቀመጫ ሆና በማገልገል ላይ ትገኛለች፡፡

ከዳግማዊ ምኒልክ እስከ አፄ ኃይለ ሥላሴ፣ ከደርግ ዘመነ መንግሥት እስከ ኢሕአዴግ ድረስ በአጠቃላይ ለ130 ዓመታት ያህል የኢትዮጵያ ዋና መዲና ሆና እያገለገለች የምትገኘው አዲስ አበባ፣ ከጥቅም ጋር በተያያዘ ብዙ ጥያቄዎች ሲነሱባት ቆይቷል፡፡ የደርግ መንግሥትን ገርስሶ ወደ ሥልጣን የመጣው የኢሕአዴግ መንግሥት ወደ ሥልጣን ከመጣ አራት ዓመት በኋላ በፀደቀው ሕገ መንግሥት፣ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ከተማ ልዩ ጥቅም ልታገኝ እንደሚገባት ደንግጓል፡፡

በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 49 ንዑስ አንቀጽ 5 ላይ በግልጽ እንደሰፈረው አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል መሀል የምትገኝ በመሆኗ፣ ከአዲስ አበባ ልዩ ጥቅም ማግኘት ይገባታል፡፡ ከዛሬ 22 ዓመታት በፊት የፀደቀው ሕገ መንግሥት ዝርዝሩ በሕግ እንደሚወሰንም አስታውቋል፡፡ በዚህም መሠረት ባለፈው ሳምንት በሚኒስትሮች ምክር ቤት የፀደቀ ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ ቀርቧል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ያሉ የኦሮሚያ ተወላጆች ከከተማዋ የሚገባንን ጥቅም አላገኘንም የሚል ጥያቄ በተደጋጋሚ ጊዜ ሲያነሱ ተደምጧል፡፡ ከዛሬ 22 ዓመታት በፊት በተግባር ላይ የዋለው ሕገ መንግሥት ይኼንን ጥያቄ በሚመልስ ደረጃ የወጣ ቢሆንም፣ ምላሽ ሳይጠሰው ቆይቷል በማለት ምሬት ሲሰማ ነበር፡፡ በዚህና ከዚህ ጋር በተያያዘ ሌሎች ጥያቄዎች አማካይነት በክልሉ ውስጥ ከዓመት በፊት በተቀሰቀሰው የሕዝብ ጥያቄ በርካታ ዜጎች ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ንብረት ወድሟል፡፡

የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሰኔ 20 ቀን 2009 ዓ.ም. ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ልታገኝ ስለሚገባት ልዩ ጥቅም አዲስ ረቂቅ አዋጅ አፅድቋል፡፡ ረቂቅ አዋጁ ይፋ ከሆነ ወዲህ በአገሪቱ ውስጥ ዋነኛ መነጋገሪያ ጉዳይ ቢሆንም፣ ጉዳዩ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ ውይይት ከተደረገበት በኋላ ወደፊት በየደረጃው የሕዝብ ውይይት ይደረግበታል ተብሏል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ቅዳሜ ሰኔ 24 ቀን 2009 ዓ.ም. የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) ጋዜጣዊ መግለጫ በጽሕፈት ቤታቸው ሰጥተዋል፡፡ ዶ/ር ነገሪ ለአንድ ሰዓት ያህል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ከሃምሳ ደቂቃ በላይ ሰሞኑን የኦሮሚያ ክልል ከአዲስ አበባ ልታገኝ ስለሚገባት ልዩ ጥቅም በተመለከተ ስለተደነገገው አዲስ ረቂቅ አዋጅ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ሚኒስትሩ በመግለጫቸው ላይ፣ ‹‹ሕገ መንግሥታችን የህልውናችን መሠረትና በሰላምና በአንድነት ለመኖር ትልቁ እሴታችን ነው፤›› በማለት ንግግራቸውን የጀመሩ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ተፈቃቅደው በተወካዮቻቸው ወይም በቀጥታ በውይይት በመሳተፍ የደነገጉት ሕገ መንግሥት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ስለዚህ በዚህ ገዥ በሆነው ሕገ መንግሥታችን ውስጥ የኦሮሚያን ክልል በተመለከተ የተደነገገ አንቀጽ አለ፡፡ ይኼ ደግሞ ልዩ ጥቅም በማለት የተቀመጠ ጉዳይ ነው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹የኦሮሚያ ክልል ገዢ ፓርቲ ኦሕዴድና በክልሉ መንግሥት ቀደም ሲል ውይይት ተደርጎበት፣ ከዚያ ቀጥሎ ደግሞ የኢሕአዴግ ምክር ቤትና የፌዴራል ተቋማት ኃላፊዎች፣ የሕግ ባለሙያዎችና ሌሎች አካላት ከተወያዩበት በኋላ ወደ ሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቦ ነው ወደ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲሄድ የተደረገው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ደግሞ ይኼንን ጉዳይ በመመርመር ወደሚመለከተው ቋሚ ኮሚቴ እንደመራው አስረድተዋል፡፡

ይኼ ጉዳይ ሕዝቡ ገና በተለያዩ ደረጃዎች የሚወያይበት እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ ‹‹እውነታው ይኼ ሆኖ ሳለ ጉዳዮን በአግባቡ መረዳት የማይችሉ አካላት እንዳሉ እንረዳለን፤›› ሲሉ ከሕዝቡ ጋር ውይይት ሳይደረግ ተግባራዊ ሊሆን እንደማይችል አስረድተዋል፡፡

ዶ/ር ነገሪ የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ላይ ስላለው ልዩ ጥቅም ከመነሳቱ በፊት ለዚህ መሠረት የሆነው ጉዳይ ምን እንደሆነ ማብራርያ ሰጥተዋል፡፡ የዛሬዋ አዲስ አበባ ከዛሬ መቶ ዓመት በፊት የኦሮሚያ አርሶ አደሮች የሚኖሩባት እንደነበረች ጠቅሰዋል፡፡ ከመቶ ዓመት በፊት የኦሮሞ አርሶ አደር ከቀዬውና ከመሬቱ የተፈናቀለበት ጊዜም እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ ሥርዓቱ የዜጎችንና የብሔር ብሔረሰቦችን እኩልነት የሚያስጠብቅ ስላልነበረ፣ በኦሮሚያ አርሶ አደር ላይ ብዙ ችግሮች ደርሰው እንደነበር ገልጸዋል፡፡ በሕዝቦች መፈቃቀድ ላይ የተመሠረተ ባይሆንም ከተማዋ እንደ ተመሠረተች፣ ከዛሬ ሃያ ስድስት ዓመት በፊት የነበሩት ሥርዓቶች ሕዝባዊ ስላልነበሩ በዚህ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ የኦሮሞ ተወላጆችና አርሶ አደሮች ግፍ ሲደርስባቸው እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

በፊትም ቢሆን ሥርዓቱ እንጂ በብሔር ብሔረሰቦች መካከል ችግር እንዳልነበረ የጠቆሙት ዶ/ር ነገሪ፣ አንዱ ብሔረሰብ ሌላውን የመጉዳት ዓላማ እንዳልነበረውም አክለው አስረድተዋል፡፡ ሁሉም ብሔር ብሔረሰቦች በራሳቸው ፈቃድ ተግባብተው የሚኖሩና አብረው የሚሠሩ፣ አገራቸውንም በጋራ ከውጭ ወራሪ ኃይል የጠበቁ፣ በርካታ የጋራ እሴቶች የነበሯቸውና አሁንም ያላቸው መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

አሁን ደግሞ ያ መጥፎ ሥርዓት መቀረፉንና የአሁኑ ሥርዓት ሕዝባዊ መሆኑን ተናግረው፣ የአሁኑ መንግሥት ለፍትሐዊነትና ለሕዝብ አንድነት የቆመ እንደሆነ አስገንዝበዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች እንደተሳተፉበት የገለጹት ሕገ መንግሥት፣ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ልዩ ጥቅም በማግኘት መስተካከል እንዳለበት በሚገልጽ ሁኔታ መደንገጉን አስረድተዋል፡፡

የኦሮሞ ሕዝብ በተለይም ደግሞ በዚህ በአዲስ አበባ ይኖር የነበረው ለአዲስ አበባ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ከዚያም አልፎ ለአፍሪካና ለዓለም ሕዝብ የሰጠው ልዩ ስጦታ እንዳለ ያስታወሱት ዶ/ር ነገሪ፣ ‹‹ልዩ ስጦታ ስንል የበፊቱ ሥርዓት ያደረገው ግፍ እንዳለ ሆኖ አዲሲቷን ኢትዮጵያ ለመገንባት የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች አንድ ላይ በመሆን ሕገ መንግሥት በሚያፀድቁበት ጊዜ፣ የኦሮሞ ሕዝብም በተወካዮቹ በኩል ድምፅ ሰጥቷል፤›› ብለው፣ ‹‹ከዚያን ጊዜ በፊት እንደነበረው በግፍ የፈለገውን ማድረግ ሳይሆን፣ በፈቃደኝነት የሰጠው ስጦታ እንዳለ ማስታወስም ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ከዚያን በኋላ የኦሮሞ አርሶ አደሮች ብዙ ዋጋ ከፍለዋል፡፡ ስለዚህ ልዩ ስጦታውን ማስታወስ ይገባል፤›› በማለት አክለዋል፡፡

ልዩ ስጦታ በልዩ ጥቅም ምላሽ ያገኛል ማለት ሳይሆን፣ አሁን እንደ ልዩ ጥቅም የቀረበው ጉዳይ የተዛባውን ታሪክ ለማስተካከልና ለወደፊት የምትገነባውን አገር የተሻለች ለማድረግ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ እርካታው የኢኮኖሚ እርካታ ወይም ደግሞ የታክስ መሰብሰብ እርካታ ሳይሆን፣ የህሊናና የሞራል እርካታ ነው ብለዋል፡፡

የኦሮሚያ ክልል በሚነሳበት ጊዜ በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ቢሮዎች ውስጥ የሚሠሩት ሁሉ የኦሮሞ ተወላጆች ብቻ ናቸው ብሎ ማሰብ የተሳሳተ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠሩ  የሌላ ብሔር ተወላጆች በኦሮሚያ ውስጥ እንዳሉ ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚመጣ ጥቅም ካለ የእነዚህ ዜጎችም ጥቅም እንደሆነ መገንዘብ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡

‹‹አዲስ አበባ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት መቀመጫ ብቻም ሳትሆን፣ የሁላችንም የጋራ መገለጫችን የሆነች በመሆኗ አዲስ አበባ የሁላችንም የፖለቲካ ማዕከልም ናት፤›› ብለዋል፡፡

ከዚህም ባለፈ የአፍሪካ የፖለቲካና የዲፕሎማሲ ማዕከል፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የኢኮኖሚክ ኮሚሽን መቀመጫና ሌሎች ዓለም አቀፍ ተቋማት ያሉባት ከተማ መሆኗን አብራርተዋል፡፡

‹‹ይኼንን እንደ ልዩ ስጦታ ከተረዳን በኋላ ልዩ ጥቅም የሚባለውን ደግሞ መገንዘብ እንደምንችል ግልጽ ነው፤›› ብለው፣ ‹‹አዋጁ የኦሮሚያን ክልል ከሌሎች ክልሎች በተለየ ሁኔታ ሌላ ፕላኔት ውስጥ እንዳለች ያደርጋታል ብሎ መገንዘብ ስህተት ነው፡፡ ምክንያቱም ኦሮሚያ ከፊንፊኔ በምታገኘው ጥቅም አይደለም የምታድገው፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡ እንደየትኛውም ክልል በሕዝቦች ጥረት እንደምትለማ አክለዋል፡፡

‹‹ኢሕአዴግ ከአራቱ ክልሎች ውጪ ያሉትን ታዳጊ ክልሎች በማለት ልዩ ድጋፍ ያደርግላቸዋል፤›› ካሉ በኋላ፣ ይኼ ደግሞ አንድ ጠንካራ የጋራ ኢኮኖሚና ፖለቲካዊ ማኅበረሰብ ለመፍጠር እንደሚረዳ፣ ስለዚህ ልዩ ጥቅም ሲነሳ አላስፈላጊ ትርጉም የሚሰጡ አካላት ስላሉ መታረም አለባቸው ብለዋል፡፡

ኦሮሚያን የተለየ ፕላኔት ለማድረግ ሳይሆን በታሪክ የተዛባውንና የሚገባውን ልዩ ጥቅም ለማስጠበቅ መሆኑን መገንዘብ እንደሚያስፈልግ ዶ/ር ነገሪ ግልጽ መሆን አለበት በማለት አፅንኦት ሰጥተዋል፡፡ ይኼ ልዩ ጥቅም ሁሉንም ያረካል ወይም ደግሞ ለኦሮሚያ ሕዝብ ካሳ ይከፍላል ተብሎ እንደማይታሰብም አብራርተዋል፡፡ ጥቅሙ የሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ አንድን ብሔር ከሌላ ብሔር ልዩ ለማድረግ እንዳልሆነ ጠቁመዋል፡፡ የተገለጹት ጥቅሞች ግለሰባዊ ሳይሆኑ ተቋማዊ እንደሆኑም ጠቅሰዋል፡፡ ለምሳሌ አንድ የኦሮሚያ ተወላጅ ኦሮሚያ ስለሆነ ብቻ አዲስ አበባ ውስጥ የተለየ ጥቅም ያገኛል ማለት አይደለም ብለዋል፡፡ ስለዚህ ይኼንን ልዩ ጥቅም በተዛባ መንገድ በመረዳትና ክፍተት በመፈለግ፣ በሕዝቦች መካከል መቃቃር እንዲፈጠርና የአብሮነት እሴታቸው እንዲሸረሸር ማድረግ ስህተት ነው ሲሉ ዶ/ር ነገሪ ጠቁመዋል፡፡

ይኼ አዋጅ ምንም እንኳ ከሃያ ሁለት ዓመታት በኋላ የመጣ ቢሆንም ትልቅ ትርጉም የሚሰጠው እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ መንግሥት ለሕዝቡ ትልቅ ክብር እንዳለውና ሕዝባዊ እንደሆነ ያሳየበት መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ‹‹ዜጎቹን በእኩል ዓይን የሚያይና የሚያስተናግድ መንግሥት እንደሆነ ማሳያ ነው፤›› በማለት የመንግሥትን ሕዝባዊነትና ሁሉንም በእኩል ዓይን የሚያይ መሆን በመጥቀስ መንግሥትን አሞካሽተዋል፡፡

‹‹ይኼ አዋጅ አሁን ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ወደሚመለከተው አካል ሄዷል፡፡ ከዚያ በኋላ ደግሞ በየደረጃው ሕዝብ ይወያይበታል፤›› ብለዋል፡፡

ዶ/ር ነገሪ በመግለጫቸው ካነሷቸው ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል ዋነኛው ጉዳይ ይኼ ሲሆን፣ የመነሻ ሐሳባቸውን ካጠቃለሉ በኋላ ጋዜጠኞች በዚህና በሌሎች ተያያዥ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ጥያቄ እንዲያነሱ ዕድል ሰጥተዋል፡፡ የአብዛኛዎቹ ጋዜጠኞች ጥያቄም የነበረው ከዚህ አዋጅ ጋር የተያያዘ ነበር፡፡

ዶ/ር ነገሪ መጀመርያ ከተነሱላቸው ጥያቄዎች አዋጁ ሕዝብ ሳይወያይበት ለምን ወደ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀረበ? ከዚህ በፊት ማስተር ፕላኑን በተመለከተ ሕዝቡ ሳይወያይበት ብዙ ኪሳራ በአገሪቱ አስከትሏልና አሁንም ያንን ዓይነት ቀውስ እንዳያስከትል ምን ተሠርቷል? የሚሉ ናቸው፡፡ ዶ/ር ነገሪ በምላሻቸው፣ ‹‹ሕዝብ ሳይወያይበት ወደ ምክር ቤት ሄዷል ለተባለው የዚህ አዋጅ መጨረሻው አይደለም፡፡ በየደረጃው ያሉ የኅብረተሰብ ክፍሎች ከተወያዩበት በኋላ ነው የሚፀድቀው፡፡ ነገር ግን ይኼ ጉዳይ በመጀመርያ ደረጃ ሕዝብ ውክልና በሰጣቸው፣ በተለይም በክልሉ መሪ ፓርቲና በአዲስ አበባ አስተዳደር አመራሮች ውይይት ተደርጎበታል፡፡ በየደረጃው ሌሎች የመንግሥት አካላትም ተወያይተውበታል፡፡ ሕዝብን በዜሮ ላይ ማወያየት አይቻልም፤›› ብለዋል፡፡

ሌላው የተነሳላቸው ጥያቄ ከአዋጁ ይዘቱ ጋር የተያያዘ ሲሆን፣ አዋጁ የአዲስ አበባን ወሰን አላስቀመጠም፡፡ አሁንም ለአዲስ አበባ ወደ ኦሮሚያ ክልል የመስፋፋት ዕድል የሚፈቅድ እንደሆነ ከብዙ አካላት ሲነሳ እንደሚሰማና በዚህ ላይ ምን የሚሉት ነገር እንዳለ የተጠየቁ ሲሆን፣ ‹‹የአዋጁ ይዘት የአዲስ አበባን ወሰን አይመለከትም፡፡ የወሰን ጉዳይ ራሱን የቻለ ነው፡፡ ከዚህ ከአዋጅ በተለየ በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥትና በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ይኼንን ችግር ለመፍታት እየተሠራ ነው፡፡ ወሰኑን በተለመከተ ከሁለቱ ክልሎች የአመራር አካላት መረጃ ማግኘት ትችላላችሁ፡፡ ይኼንን ለመፍታት የጋራ ምክር ቤት ይቋቋማል፡፡ አሁን የወሰን ማካለሉ ሥራ እየተከናወነ ነው፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

 ‹‹አዲስ አበባ ወደ ኦሮሚያ እንድትስፋፋ ዕድል ይሰጣል ለተባለው ትክክለኛ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ግልጽ ነው፡፡ ሁሉም የምንሠራቸው ሥራዎች ከሕዝብ ሊደበቁ አይችሉም፡፡ ምክንያቱም የሥልጣን ባለቤቱ ሕዝብ ነው፡፡ መንግሥት ራሱን በሌላ ደሴት አድርጎ ከሕዝብ ተለይቶ የሚሠራቸው የሉም፡፡ ዘላቂ ስለማይሆኑ፡፡ ስለዚህ ምንም ሚስጥር የለም፡፡ በተደጋጋሚ እንደተባለው ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር ተያያዞ ብዙ ክርክሮችና ውይይቶች ነበሩ፡፡ የችግሩ መንስዔ ስለነበር አዲስ አበባ አሁን በያዘችው ማደግ ትችላለች፡፡ የምታድገው ደግሞ ወደ ኦሮሚያ በመስፋፋት ሳይሆን ወደ ላይ ነው፡፡ ይኼ ነው የተያዘው አቋም፡፡ ነገር ግን በየትኛውም ዓለም እንደሚደረገው ከባለመብቶች ጋር በመስማማት የሚደረግ ይኖራል፡፡ ምክያቱም ኢትዮጵያን የሚመራ መንግሥት ከኦሮሚያ የተለየ አይደለም፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡

ዶ/ር ነገሪ ሌላ የተነሳላቸው ጥያቄ ከማኅበራዊ ጠቀሜታዎች ጋር የተያያዘ ነው፡፡ በአዋጁ ላይ ልዩ ጥቅም ተብለው የተደነገጉት ጤናና ትምህርት በመሆናቸው የሕዝቡን ተጠቃሚነትን የሚያሳዩ አይደሉም፡፡ ከዚያ ይልቅ ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ያላት ኢኮኖሚያዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች በግልጽ የተቀመጡ ባለመሆናቸው አዋጁ ከይስሙላ ያለፈ ብዙም ምላሽ የሚሰጥ አይደለም የሚል ነገር ይነሳልና በዚህ ዙሪያ የሚሉት ነገር አለ የሚል ነው፡፡ ዶ/ር ነጋሪ በምላሻቸው፣ ‹‹ከዚህ ጋር በተያያዘ ይኼንን ጉዳይ የምናይበት አመለካከት መቃኘት አለበት፤›› ብለዋል፡፡ ከአንዳንድ ወገኖች የሚነሳው ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ግብር ለመሰብሰብ ነው የሚባለው ጉዳይ ለሞራልም ጥሩ እንዳልሆነ ገልጸዋል፡፡ “የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄም አይመስለኝም፤” ብለዋል፡፡ ሌሎች አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ከኢኮኖሚው ተለይተው እንደማይታዩና ገንዘብ ሳይወጣበት የሚገነባ ምንም ነገር የለም ብለዋል፡፡ ስለዚህ አዲስ አበባ ከምታገኘው ገቢ ለኦሮሚያ ልዩ ጥቅም ለተባለው የምታወጣው ወጪ እንደሚኖርና በሕግ በተቀመጠው መሠረት የክልሉን ማንነት የሚያንፀባርቁ ነገሮች እንደሚገነቡ ጠቁመዋል፡፡

ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ከተማ ልዩ ጥቅም ማግኘት እንደሚገባት በሕገ መንግሥቱ ላይ ሰፍሯል፡፡ ይኼ ሕገ መንግሥት ሥራ ላይ ከዋለ ደግሞ ከሃያ ዓመት በላይ አስቆጥሯል፡፡ ለምንድነው በሕጉ ላይ የሠፈረው ጉዳይ እስከዛሬ ተግባራዊ ሊሆን ያልቻለው? ለብዙ የኦሮሞ ወጣቶች ሞት ምክንያት እስከሚሆንስ መጠበቁ ለምን አስፈለገ? አሁን አዋጁን ማውጣት ያስፈለገበት ምክንያትስ ምንድነው? አስገዳጅ ሁኔታዎችስ ምንድናቸው? ተብለው የቀረቡ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ ዶ/ር ነገሪ፣ “ለምን ዘገየ ለተባለው ምናልባት ጥናት ተደርጎበት ምክንያቱን በሳይንሳዊ መንገድ መመለስ የሚሻል ይመስለኛል፤” በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ አሁን ግን የራሱ የሆኑ አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ ምክንያቶች ሊኖሩት እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡ ትርጉም ያለው ጉዳይ ግን ከሕዝቡ ውይይት ጋር ተያያዥ እንደሚሆን አስረድተዋል፡፡   

ሕዝቡ ውይይት በሚያደርግበት ጊዜ ስምምነት ላይ ባይደርስ ረቂቅ አዋጁ የሚሻርበት ዕድልስ አለው? ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ፣ “ሕዝቡ ተስማማበትም አልተስማማበትም እንዴት ነው የሚደረገው ለሚለው ጥያቂ ይኼንን መተንበይ አስፈላጊ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም ተጨባጭ በሆኑ ነገሮች ላይ ብንነጋገር የተሻለ ይመስለኛል፤” በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ‹‹ሕዝቡ በሚወያይበት ጊዜ አቋሙ እንደሚከበርና የሕዝቡ ፍላጐት መሠረታዊ እንደሆነ ግን ሁላችንም መረዳት አለብን፤” ብለዋል፡፡

“አሁን አዋጁ እንዲወጣ ወቅታዊ ምክንያት አለ ወይ ለሚባለው የተለየ ወቅታዊ ጉዳይ ስላለ አይደለም፤” ብለዋል፡፡ “መንግሥት በተለያዩ ምክንያቶች ቅድሚያ ሰጥቷቸው የሚሠራቸው ሥራዎች እንዳሉ እናውቃለን፡፡ ባለፈው ዓመት ከነበረው አለመረጋጋት ጋር የሚያያዝ ነው ብለው የሚገምቱ አካላት ቢኖሩም፣ መንግሥት ግን በሕገ መንግሥቱ ውስጥ የተቀመጠውን መተግበር ግዴታው እንደሆነ ያውቃል፤” በማለት አዋጁን ለማውጣት ወቅታዊ አስገዳጅ ሁኔታ ሳይሆን የመንግሥት የአሠራር ሥርዓት መሆኑን በማስረዳት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ሕዝቡ አስገድዶት ለሕዝብ ጥያቄ ምላሽ መስጠትም ትልቅ ነገር ነው ብለዋል፡፡

የኦሮሚያ ክልል ከአዲስ አበባ ማግኘት ስለሚገባት ልዩ ጥቅም ሰሞኑን ከወጣው ረቂቅ አዋጅ ጋር በተያያዘ የቀረበላቸው ሌላው ጥያቄ፣ አገር የጋራ ነው፡፡ ለአንዱ ልዩ ስጦታ የሚሆንበትና ለሌላው ደግሞ የማይሆንበት መንገድ ምንድነው? ከዛሬ መቶ ዓመት በፊት የነበረውን ነገር ካነሳን በሌላውም አካባቢ ተመሳሳይ ጉዳይ ሊኖር ይችላልና ይኼንን እንደ ልዩ ስጦታ መቁጠሩ ግልጽ ቢደረግ” የሚል ነው፡፡ ዶ/ር ነገሪ በምላሻቸው እንዳስረዱት፣ ልዩ ጥቅምን በሚመለከት ሌላ አካባቢ ጥያቄ ካለ መግለጽ እንደሚቻልና እስካሁን ባለው ሁኔታ ግን እንደሌለ ገልጸዋል፡፡

ዶ/ር ነገሪ ከዚህ ጋር በተያያዘ ከጋዜጠኞች ብዙ ጥያቄዎች ቢቀርቡላቸውም፣ መጨረሻ አካባቢ የተነሳውና የብዙዎችም ጥያቄ የነበረው፣ አሁን ባለንበት ዘመን ክፍለ አኅጉራዊ ውህደት እየተፈጠረ ባለበት ወቅት፣ ለአንዱ ብሔር የተለየ ጥቅም መስጠቱ በአንድ አገር ላይ ኢትዮጵያዊነትን የበለጠ የሚያዳክምና የሚከፋፍል ነገር አይፈጥርም ወይ? ሌላ ጥርጣሬና መፈራራትንስ የሚፈጥር ጉዳይ አይሆንም ወይ? የሚል ጥያቄ ነው፡፡ ‹‹ይኼ አዋጅ ግለሰቦችን መሠረት ያደረገ አይደለም፡፡ ምናልባት የምናይበት መነፅር ችግር ከሌለበት በስተቀር፡፡ ይኼ ሁሉንም በጋራ ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

ዶ/ር ነገሪ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ሰነድ አልባ ኢትዮጵያውያንን ከሳዑዲ ዓረቢያ ለማስወጣት በሚደረገው ጥረት የሳዑዲ ዓረቢያን መንግሥት የአንድ ወር ተጨማሪ የምሕረት ጊዜ መጨመር በተመለከተ መግለጫ የሰጡ ሲሆን፣ የዚህ ቀነ ገደብ መራዘም ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲው ዘርፍ እየተጫወተችው ያለው ሚና አንዱ ማሳያ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅትም ከ111 ሺሕ በላይ ዜጎች የጉዞ ሰነድ ወስደው ለመውጣት እየተጠባበቁ መሆናቸውን፣ የሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት የምሕረት ጊዜውን ማራዘሙን ተከትሎ ብዙ ኢትዮጵያዊያን የመዘናጋት ሁኔታ እየታየባቸው እንደሆነ አብራርተዋል፡፡ ከሳምንት በፊት በሳዑዲ ዓረቢያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ በተመላሾች ሲጨናነቅ የሰነበተ ቢሆንም፣ የጊዜውን መራዘም ምክንያት በማድረግ ብዙ ኢትዮጵያዊያን መዘናጋት እየታየባቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡

በሦስት ወራት ውስጥ ከ45 ሺሕ በላይ ብቻ ማመላለስ የቻለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሃያ ቀናት ውስጥ 111 ሺሕ ሰነድ አልባ ኢትዮጵያዊንን እንዴት ወደ አገራቸው መመለስ ይችላል ተብለው የተጠየቁት ዶ/ር ነገሪ፣ በአሁኑ ወቅት መንግሥት ከአውሮፕላን በተጨማሪ ሌሎች የትራንስፖርት አማራጮችን ለመጠቀም በዝግጅት ላይ ነው ብለዋል፡፡    

 

 

Standard (Image)

የ29ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ ውሳኔዎች ፋይዳ

$
0
0

ሃምሳ አምስት አገሮችን በውስጧ የያዘችው አፍሪካ በድህነትና በኋላቀርነት ከሚታወቁት መካከል አንዷ ነች፡፡ ለዘመናት በአውሮፓውያኖች እጅ የቆየችው አፍሪካ የተፈጥሮ ሀብቷን በእነዚህ ቅኝ ገዥዎች እንደተዘረፈች ብዙ ተብሎበታል፡፡ አብዛኛው ሕዝብ በእርሻ ሥራ እንደሚተዳደሩ መረጃዎች ቢጠቁሙም፣ በኋላቀር አስተራረስ ሳቢያ የአኅጉሪቱን ዓመታዊ ዕድገት ከ3.4 በመቶ ከፍ ማድረግ አልተቻለም፡፡

አፍሪካ በቅኝ ገዥዎች ቀንበር ሥር ውላ በነበረበት ዘመን የአኅጉሪቷ ሕዝብ ጉልበት ከመበዝበዙ ባሻገር፣ የተፈጥሮ ሀብቷ ተዘርፏል፡፡ አፍሪካውያንም  በኢትዮጵያ አነሳሽነትና መሥራችነት በአኅጉሪቷ ውስጥ ያሉ አገሮች አንድ ድምፅ እንዲኖራቸውና ተሰሚነታቸው ከፍ እንዲል፣ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን (አአድ) አቋቁመዋል፡፡ ‹‹አፍሪካ ስትበታተን ለባሰ ችግር ይዳርጋታል፣ አንድ ስንሆን ግን ድምፃችን ይሰማል፤›› ብለው ንግግር አድርገው የነበሩት የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት ለአሁኑ የአፍሪካ ኅብረት መመሥረት ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ድምፅ አንድ እንዲሆንና ተሰሚነት እንዲኖረው የተጫወተችው ሚናም ከፍተኛ ነው፡፡

አፍሪካ በኢትዮጵያ ዋነኛ አንቀሳቃሽነትና በጥቂት የአፍሪካ መሪዎች ደጋፊነት ድምጿን ለማሰማት የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን እ.ኤ.አ. በ1963 መሥርታለች፡፡ በወቅቱ የድርጅቱ መመሥረት ዋነኛ ዓላማ የነበረው የአፍሪካ አገሮች ዳግመኛ በቅኝ ገዥዎች እጅ እንዳይወድቁና አንድ የጋራ ድምፅ በመፍጠር ተሰሚነታቸውን ከፍ ለማድረግ ያለመ ቢሆንም፣ ከዚያን ጊዜ ወዲህ አኅጉሪቱ በማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ትስስር በመፍጠር አንድ የጋራ አኅጉራዊ ማኅበረሰብ ለመፍጠር እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

አገሮችን በጋራ በማስተሳሰር ችግሮችን ለመፍታት አሁንም ደፋ ቀና እያለ እንደሆነ የሚናገረው የአፍሪካ ኅብረት፣ በአኅጉሪቱ ውስጥ ለሚከሰቱ ችግሮች ዘላቂ መፍትሔ በማምጣቱ በኩል ውስንነቶች እንዳሉበት የዘርፉ ባለሙያዎች ሲናገሩ ይደመጣል፡፡ ለዚህ ችግር ዋነኛ መንስዔ ደግሞ የአፍሪካ መሪዎች የሥልጣን ጥም መሆኑን እንደ አንድ ምክንያት ያስቀምጣሉ፡፡ አኅጉሪቱን እንደ አውሮፓና ሌሎች አኅጉሮች በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊና በፖለቲካዊ ጉዳዮች ማፈርጠም ያልተቻለው፣ በውስን አምባገነን መሪዎች ሳቢያ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡

‹‹ለአንድ አገር ዕድገት ዋነኛ መሠረት የሆነው ዴሞክራሲ በአፍሪካ አይከበርም፤›› ሲሉ ናይጄሪያዊው ምሁር አካችኖ አካቾ እ.ኤ.አ. በ2004 ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፍ ገልጸዋል፡፡ ‹‹አፍሪካ በተፈጥሮ ሀብት የታደለች ብትሆንም ወደ ሥልጣን የሚመጡ መሪዎቿ የሥልጣን ጥም ያለባቸው በመሆኑ ብቻ የዴሞክራሲን ፋይዳ ያቀጭጩታል፡፡ የዴሞክራሲ ፋይዳ ሲቀጭጭ ደግሞ ዕድገት ማስመዝገብ አይቻልም፡፡ ከአርባ ዓመት በላይ በሥልጣን ላይ መቆየት አንድ አገር የተለየ አስተሳሰብና አሠራር እንዳትከተል በሩን ይዘጋባታል፡፡ አፍሪካ ውስጥ የተለመደው ይህ ነው፤›› ሲሉ የአፍሪካ መሪዎች ለሥልጣን ያላቸውን ጥም ኮንነዋል፡፡

አፍሪካ ከጊዜ ወደ ጊዜ ችግሮቿ እየቀለሉና እየተቀረፉ እየሄዱ እንደሆነ እየተገለጸ ቢሆንም፣ በዚህ ግሎባላይዜሽን ዘመን አሁንም ማከናወን የሚገባት በርካታ የቤት ሥራዎች እንዳሉ ይነገራል፡፡ በደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ ዩኒቨርሲቲ የሚያስተምሩት ፕሮፌሰር ኒኮላስ ባቫኞ፣ ‹‹አፍሪካ ከውድድሩ ጋር አብራ መሮጥ ካልቻለች ዕጣ ፈንታዋ በእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ መውደቅ ነው፤›› ይላሉ፡፡

የአፍሪካን ድምፅ በአንድ አድርጎ በኃያላኑ ዘንድ የበለጠ ተሰሚነትን ለመፍጠር የተቋቋመው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ከዓመታት ወዲህ የአፍሪካ ኅብረት እየተባለ የሚጠራ ሲሆን፣ የአፍሪካን ችግር ለመፍታት የተቋቋመው ይህ ኅብረት ዋና መቀመጫው ኢትዮጵያ ነች፡፡ በአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት ሆና የምትቆጠረው ኢትዮጵያ የሃምሳ አምስት አገሮች ድምፅ ማረፊያና ዋነኛ መቀመጫ ነች፡፡

የአፍሪካ ኅብረት በመሪዎች ደረጃ በዓመት ሁለት ጊዜ ጉባዔ የሚያካሂድ ሲሆን፣ በጥር ወር የሚካሄደውን የኅብረቱ ጉባዔ ዘወትር ኢትዮጵያ ነው የምትስተናገደው፡፡ በሐምሌ ወር ላይ የሚካሄደውን ደግሞ መሪዎች በጥር ወር በሚያደርጉት ስብሰባ ላይ የሚወስኑት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በሐምሌ ወር የሚካሄውን የዘንድሮውን ጉባዔ ታንዛኒያ እንደምታስተናግደው በጥር ወር አዲስ አበባ ላይ በተካሄደው ጉባዔ ላይ የተወሰነ ቢሆንም፣ ዝርዝር ጉዳይ ግልጽ ባይሆንም ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ ተደርጓል፡፡

29ኛው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ ለዘጠኝ ቀናት የዘለቀ ቢሆንም፣ በመሪዎች ደረጃ የተካሄደው ጉባዔ ግን ለሁለት ቀናት የቆየ ነበር፡፡ ከሰኞ ሰኔ 26 እስከ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. በመሪዎች ደረጃ የተካሄደው 29ኛው የኅብረቱ ጉባዔ አዲስ አበባ በሚገኘው የኅብረቱ አዳራሽ ነው የተካሄደው፡፡ ከሃምሳ አምስት አባል አገሮች ሃያ አራት ፕሬዚዳንቶችን ብቻ ያሳተፈው የዘንድሮው ጉባዔ በተሳትፎ ደረጃ ዝቅ ብሎ መታየቱን በሥፍራው የነበሩ ባለሙያዎች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ ከታንዛኒያ የመጣው ጋዜጠኛ ኢማኑኤል ፓማርኖ በ29ኛው የኅብረቱ የመሪዎች ጉባዔ ላይ አብዛኛዎቹ የአፍሪካ መሪዎች ባለመገኘታቸው ይኼኛው ክብደት ሊሰጠው እንደማይችል ተናግሯል፡፡

ከኬንያ እንደመጣች የምትናገረዋ ጋዜጠኛ   ቼቪሪቾ ኮኮቪያ ደግሞ፣ ‹‹የግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ የት አሉ?›› በማለት አስተያየቷን በጥያቄ ጀምራለች፡፡ የራሷን አገር ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታን ጨምሮ፣ የደቡብ አፍሪካ፣ የናይጄሪያና ሌሎች ተሰሚነት ያላቸው የአፍሪካ አገር መሪዎች ባለመገኘታቸው የአሁኑን ጉባዔ በተለየ መንገድ እንደምታየው ሐሳቧን ለሪፖርተር አጋርታለች፡፡

29ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ ላይ በአፍሪካ ትልቅ አቅም አላቸው የሚባሉ አገሮችን ፕሬዚዳንቶች አላሳተፈም፡፡ በአካባቢው ተሰሚነት አላቸው ከሚባሉት አገሮች መካከል አንዷ ግብፅ ስትሆን፣ የፕሬዚዳንቱ በጉባዔው ላይ አለመሳተፍ በምሥራቅ አፍሪካ ያለውን ቀውስ ለመፍታት በሚደረገው ጥረት ላይ የራሱ አሉታዊ ተፅዕኖ ሊኖረው እንደሚችል ተነግሯል፡፡ የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ አለመገኘትም ጥያቄ አጭሯል፡፡ ሳዑዲ ዓረቢያ ኳታርን ከዓረብ ባህረ ሰላጤ አገሮች ስብስብ ማስወጣት ተከትሎ የሥጋት ምንጭ እየሆነ የመጣው የኤርትራና የጂቡቲ ጉዳይ ላይ እልባት ይሰጣሉ ተብለው ከሚጠበቁ አገሮች መካከል ኬንያ፣ ግብፅና ኢትዮጵያ ይገኙበታል፡፡ የኬንያና የግብፅ ፕሬዚዳንቶች በዚህ ጉባዔ ላይ አለመሳተፍ ኅብረቱ ይህንን ችግር ለመፍታት በሚንቀሳቀስበት ጊዜ እክሎች ሊገጥሙት እንደሚችሉ ግምቶች ተሰንዝረዋል፡፡

ባለፋ ሳምንት ሰኞ ዕለት ጉባዔው በተጀመረበት ወቅት የሃያ አራት የአፍሪካ አገሮች ፕሬዚዳንቶች፣ የፍልስጤሙን ራስ ገዝ አስተዳደር መሐሙድ አባስንና የሳዑዲ ዓረቢያን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጨምሮ የተለያዩ ክፍላተ አኅጉር ዲፕሎማቶች፣ ተወካዮችና ጋዜጠኞች ተገኝተዋል፡፡ 29ኛው የኅብረቱ ጉባዔ ‹‹ሀርነሲንግ ዘ ዲሞግራፊክ ዲቫይድድ ስሩው ኢንቨስትመንትስ ኢን ዘ ዩዝ›› በሚል መሪ ቃል ተካሂዷል፡፡

በመክፈቻው ዕለት የየአገሮች ፕሬዚዳንቶችና ተወካዮች ፕሮግራሙ ከመጀመሩ በፊት ዝግ ስብሰባ አድርገዋል፡፡ በወጣው ፕሮግራም መሠረት በአምስት ሰዓት መሪዎች ዝግ ስብሰባቸውን ጨርሰው በዋናው አዳራሽ በመገኘት 29ኛው የኅብረቱ የመሪዎች ጉባዔ በንግግር እንደሚከፈት ቢገለጽም፣ የመሪዎች ዝግ ስብሰባ የተጠናቀቀው ስድስት ሰዓት ተኩል ላይ ስለነበር በተጋባዥ እንግዶችና ጋዜጠኞች ዘንድ ከፍተኛ መዳከምና መሰላቸት ታይቶ ነበር፡፡

መሪዎች በወጣው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ዝግ ስብሰባቸውን መጨረስ ያልቻሉት፣ ኅብረቱ ያለበትን የገንዘብ እጥረት ለመቅረፍ በሩዋንዳ ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ ሰብሳቢነት ተቋቁሞ የነበረው ቡድን ሪፖርት በሚቀርብበት ጊዜ በመሪዎች መካከል ስምምነት ላይ መድረስ አለመቻሉ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሪፖርቱን ያቀረቡት የሩዋንዳ ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ ሲሆኑ፣ የአፍሪካን ኅብረት የፋይናንስ ችግር ለመቅረፍና የኅብረቱን የአሠራር ሥርዓት ለማሻሻል በቀረበው ሪፖርት ላይ  ውይይቶችና ክርክሮች መካሄዳቸውን ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡ በጣም ዘግይቶም ቢሆን የመሪዎች ዝግ ስብሰባ ተጠናቆ በ6፡45 ሰዓት ላይ የአገሮቹ ፕሬዚዳንቶችና ተወካዮቻቸው ወደ አዳራሹ መጥተዋል፡፡

በመክፈቻው ላይ ንግግር ያደረጉት የኅብረቱ ኮሚሽነር ሙሳ ፋቂ መሃማት፣ ‹‹አፍሪካን ካለባት ችግር እንታደግ እያልን ዘወትር እንናገራለን፡፡ እስከ ዛሬ ግን ተጨባጭ ለውጥ አላስመዘገብንም፡፡ ስለሆነም በዚህ ጉባዔና ወደፊት በምናደርጋቸው ውይይቶችና ስብሰባዎች የሚወሰኑ ውሳኔዎችን ቁርጠኛ ሆነን ልንተገብር ይገባል፤›› በማለት መሪዎች ከወሬ ያለፈ ተጨባጭ ለውጥ ሊያመጣ በሚችል ደረጃ መሥራት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2020 የጥይት ድምፅና ኮሽታ የማይሰማባትን አኅጉር ለመፍጠር የተሻለ ሥራ ማከናወን፣ በአጀንዳ 2063 ወጣቶችን ተጠቃሚ ለማድረግ የተቀረፁ ፕሮግራሞችና የዘላቂ ልማት ግቦች ዕውን እንዲሆኑ መሥራት እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡ በአፍሪካ ዘላቂ የሆነ የሰላምና መረጋጋት እንዲኖር መሥራት ተገቢ እንደሆነ አክለዋል፡፡ ኮሚሽነሩ ከኳታር ቀውስ ጋር ተያይዞ በኤርትራና በጂቡቲ መካከል የተፈጠረው ውጥረትና የደቡብ ሱዳን ወቅታዊ ሁኔታ ኅብረቱን እንደሚያሳስበው ተናግረዋል፡፡

የጊኒ ፕሬዚዳንትና የአፍሪካ ኅብረት የወቅቱ ሊቀመንበር አልፋ ኮንዴ በበኩላቸው፣ በአፍሪካ ዋነኛ ችግር የሆነውን የወጣቶችን የሥራ ዕድል ፈጠራ አገሮች ትኩረት ሰጥተው መሥራት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡ ‹‹አፍሪካውያን በአንድነት ከቆምን ሁሉን ማድረግ እንችላለን፡፡ ከአፍሪካችን የወጡት ኢትዮጵያዊው ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ደግሞ ለዚህ ምሳሌ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ምክትል ዋና ጸሐፊ አሚና መሐመድ በበኩላቸው፣ ‹‹ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች አገሮች ለስደተኞች በሮቻቸውን ክፍት በማድረግ ላከናወኑት ተግባር ምሥጋና ይገባቸዋል፤›› በማለት ኢትዮጵያ ስደተኞችን በማስጠለል እያደረገች ያለችውን ተግባር አሞካሽተዋል፡፡ ሌሎች የአፍሪካ አገሮችም የእሷን ተሞክሮ በመውሰድ በሰብዓዊነት ሥራቸውን እንዲያከናውኑ አሳስበዋል፡፡

በጉባዔው ላይ የፍልስጤም ራስ ገዝ አስተዳደር ሙሐመድ አባስ ባደረጉት ንግግር፣ አፍሪካ ከእስራኤል ጋር ያላትን ግንኙነት ከፍልስጤም ጋርም እንዲኖራት ተማፅነዋል፡፡ ፍልስጤምና እስራኤል ለበርካታ ዓመታት ቀውስ ውስጥ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ የፍልስጤም ፕሬዚዳንት በኅብረቱ ጉባዔ ላይ እንደናገሩት፣ ከእስራኤል ጋር ያለውን ግጭት አፍሪካ እንድታሸማግልና ገለልተኛ ሆና ችግሩ እንዲፈታ ከፍተኛ ሚና መጫወት እንዳለባት ጠይቀዋል፡፡

29ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ በአዲስ አበባ ሲካሄድ ብዙ አንድምታዎች እንዳሉት የፖለቲካ ተንታኞች ይናገራሉ፡፡ ኢትዮጵያ ከአንድ ዓመት በላይ ከቆየችበት ሁከት ተረጋግታ ረብሻ ነፃ ሆና ይህንን አኅጉር አቀፍ ጉባዔ ማካሄዷ ትልቅ እመርታ እንደሆነ የተናገሩ ነበሩ፡፡ በተለይ በአስቸኳይ አዋጅ ሥር ሆና ይህንን ጉባዔ መወጣቷ አሁን በትክክለኛ መንገድ ላይ የምትገኝ መሆኗ ማሳያ እንደሆነ፣ አንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለሙያ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ ‹‹ከዚህ ቀደም በነበረብን ቀውስ የእኛ ጠላት የነበሩ አገሮች በደስታ ተውጠው ኢትዮጵያ ትፈርሳለች ይሉ ነበር፡፡ እኛ ግን ሁሌም ባለን የጠራ ፖሊሲ ወደፊት እንጂ ወደኋላ የማንሄድ አገር ሆነናል፤›› ብለዋል፡፡

ለዘጠኝ ቀናት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የነበረው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ ማክሰኞ ሰኔ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ ሲጠናቀቅ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የኅብረቱ ኮሚሽነር ሙሳ ፋኪ መሃማት፣ የአሁኑ የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ በሦስት ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ያተኮረ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ የመጀመሪያው አጀንዳ ኅብረቱን እንደገና ማደራጀት የተመለከተ ሲሆን፣ ይህንን ጉዳይ ተፈጻሚ ለማድረግ በዋና ሰብሳቢነት ተሰይመው የነበሩት የሩዋንዳ ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ በኅብረቱ የመሪዎች ጉባዔ ላይ ፕሮግራሙ በይፋ ከመጀመሩ በፊት የየአገሮች ፕሬዚዳንቶች ባካሄዱት ዝግ ስብሰባ ላይ ሪፖርታቸውን አቅርበዋል፡፡ ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ በሪፖርታቸው ካቀረቡት የማሻሻያ ፕሮግራም አንዱ፣ ኅብረቱ ዓመታዊ በጀቱን አባል አገሮች በሚያዋጡት ገንዘብ እንዲሸፈን የሚል ውሳኔ እንደሆነ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡  የአፍሪካ ኅብረት በበጀት ራሱን አለመቻሉና የሌሎች ጥገኛ መሆኑ፣ የአባል አገሮች መዋጮ አለመክፈልና ዳተኝነት ለህልውናው አሥጊ እንደሆነ በተደጋጋሚ ተነግሯል፡፡

በዚህ ርዕስ ውስጥ ትኩረት ተሰጥቶት የነበረው ሌላው ጉዳይ በአኅጉሪቱ ውስጥ ነፃ የንግድ ቀጣና እንዲኖር የሚፈቅድ ሪፖርት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ግን ሳትቀበለው ቀርታለች፡፡ የነፃ ንግድ ቀጣናውን የሚመሩት የኒጀር ፕሬዚዳንት ማሃማዱ ኢሱፍ በሰጡት መግለጫ፣ ድርድሩ በአባል አገሮች የንግድ ሚኒስትሮችና በመሪዎች ደረጃ ሲካሄድ መቆየቱን አስታውሰዋል፡፡ ድርድሩ አገሮች እስከ 90 በመቶ የሚደርሱ የሌሎች አገሮችን ምርቶች ከቀረጥ ነፃ ወደ አገራቸው እንዲያስገቡ ለማስቻል የሚደረግ መሆኑንም አውስተዋል፡፡ የአገሮችን ምርቶች ወደ አባል አገሮች ያለቀረጥ እንዲገባ የሚያደርገው የኅብረቱ ዕቅድ ግን፣ ሳይቀረጥ በነፃ ይገባል በተባለው የምርት መጠን ላይ ከተለያዩ አገሮች ተቃውሞ እንደገጠመው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ተቃውሞ ካነሱ አገሮች መካከል አንዷ ኢትዮጵያ እንደሆነችም ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ማክሰኞ ሰኔ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ከጉባዔው መጠናቀቅ በኋላ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል፡፡ ኢትዮጵያ፣ ሱዳን፣ ጂቡቲና ሌሎች ሰባት አገሮችን ጨምሮ ይህንን ውሳኔ እንደተቃወሙት ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአገሮች መካከል ተመጣጣኝ ኢኮኖሚ አለመኖርና የተሻለ ኢኮኖሚ ያላቸው አገሮች የሚጭኑትን ሸክም ለመሸከም የሚከብድ በመሆኑ፣ ላለመስማማታቸው እንደ ምክያት ሆኖ መቅረቡን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ሁለተኛው አጀንዳ የአፍሪካ ወጣቶች ከስደት ይልቅ በአገራቸው ውስጥ ሠርተው የሚያድጉበትን ሁኔታ ለማመቻቸት የቀረበ የውሳኔ ሐሳብ ነው፡፡ ይህንን የውሳኔ ሐሳብ ሁሉም ተሳታፊ አገሮች በሙሉ ድምፅ እንዳፀደቁት ታውቋል፡፡ አፍሪካ በተፈጥሮ ሀብቷ የታደለች ብትሆንም፣ የተፈጥሮ ሀብቷን በአግባቡ በመጠቀም ወጣቶችን ተጠቃሚ በማድረግ በኩል ክፍተቶች እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡ አፍሪካ የወጣቱን ዕውቀትና ኃይል በመጠቀምና ተገቢ የሆነ አመራር በመስጠት፣ የወጣቶችን ችግር መፍታት እንደሚገባት ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡

ሦስተኛው አጀንዳ ደግሞ በአፍሪካ የሚስተዋለውን የፀጥታ ችግር መፍታትን የተመለከተ ነው፡፡ እ.ኤ.አ. በ2020 አፍሪካ ምንም ዓይነት የተኩስ ድምፅ የማይሰማባት አኅጉር ለማድረግ ስምምነት ላይ መደረሱ ታውቋል፡፡ የኅብረቱ ኮሚሽነር በመክፈቻ ንግግራቸው ላይ ትኩረት ሰጥተው የተናገሩት አፍሪካን ከሽብርተኞችና ከእርስ በርስ ጦርነት፣ እንዲሁም ከጎረቤት አገሮች ጋር የሚፈጠር ግጭት የአኅጉሪቱ ዋነኛ መገለጫ መሆኑን ነው፡፡ የኅብረቱ አባል አገሮች ትኩረት ሰጥተውት መፍታት እንደለበትም አሳስበዋል፡፡ ኮሚሽነር ሙሳ ፋኪ እንደገለጹት፣ ኅብረቱ በመጨረሻ በአኅጉሪቱ ያለውን ግጭት ለመከላከል የሚያስችል አዲስ አሠራር መዘርጋቱን ገልጸዋል፡፡

በተደጋጋሚ የአፍሪካ ፈተና እንደሆነ የሚገለጸው የደቡብ ሱዳን፣ የሶማሊያ፣ በአሁኑ ወቅት ደግሞ የኤርትራና ጂቡቲ ጉዳይ ኅብረቱ ትኩረት ሰጥቶ የሚሠራባቸው እንደሆኑ ተገልጿል፡፡ በእነዚህ አገሮች የሚታየውን ግጭት ለመፍታት ግብረ ኃይል መቋቋሙንም አስታውቀዋል፡፡

የዓረብ ባህረ ሰላጤ አገሮች በኳታር ላይ በጣሉት ዕግድ የተነሳ ኳታር በኤርትራና በጂቡቲ መካከል አሰማርታው የነበረውን ጦር አስወጥታለች፡፡ የኳታር ጦር ሁለቱ አገሮች ይወዛገቡበት ከነበረው አካባቢ መውጣት ደግሞ ኤርትራንና ጂቡቲን አፋጥጧል፡፡ በአፍሪካ ኅብረት ሥር ሆኖ ይህንን ችግር ለመፍታት ተሰይሞ የነበረው የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) እውነታ አፈላላጊ ቡድን ወደ ሥፍራው አቅንቶ ሁኔታውን ለማጣራት ቢሞክርም፣ ኤርትራ እሺ አለማለቷን የኢጋድ የወቅቱ ሊቀመንበር የሆነችውን ኢትዮጵያ በመወከል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡ የኢጋድ አባል አገሮች ውሳኔ ወደ አፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ ሄዶ በአፍሪካ ደረጃ መፈታት እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

በኅብረቱ የመሪዎች ጉባዔ ላይ የተገኘችው ጂቡቲ አፍሪካ በሁለቱ አገሮች መካከል ባለው ድንበር ተጠባባቂ ኃይል እንዲያሰማራ ጠይቃለች፡፡ የአፍሪካ ኅብረት የሰላምና ደኅንነት ኮሚሽነሩ ኢስማኤል ቼሪጉዊ በሁለቱ አገሮች መካከል ያገረሸውን ቀውስ ለመፍታት፣ የሁለቱን አገሮች ፕሬዚዳንቶች በተናጠል ለማነጋገር መወሰናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሁለቱ አገሮች መካከል ያለው ውዝግብ ሥር የሰደደና ከአፍሪካ ውጪ ካሉ አገሮች ጋር የሚያያዝ በመሆኑ፣ በቀላሉ መፍትሔ ለማበጀት እንደሚከብድ የፖለቲካ ተንታኞች ይናገራሉ፡፡

በኅብረቱ 29ኛው የመሪዎች ጉባዔ ላይ የተገኙት የሳዑዲ ዓረቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አደል ቢን አህመድ አል ጁቤር የአፍሪካ አገሮች ከአገራቸው ጎን እንዲቆሙ ቅስቀሳ ሲያደርጉ መሰንበታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ሳዑዲ ዓረቢያ የአፍሪካ አገሮች ከኳታር ጋር ያላቸውን ግንኙነት በይፋ እንዲያቋርጡ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሲያግባቡ መሰንበታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ጋር እንደመከሩና ኢትዮጵያ ከኳታር ጋር ያላትን ግንኙነት እንድታቋርጥ በይፋ መጠየቃቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከዚህ በፊት ከኳታር ተመሳሳይ ጥያቄ ቀርቦላት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ዳሳለኝ ኢትዮጵያ ሁለቱ ወገኖች በውይይት የተፈጠረውን ችግር እንዲፈቱ ማሳሰባቸው ይታወሳል፡፡ የኢትዮጵያ አቋም ከውጭ ግንኙነት ፖሊሲዋ እንደሚመነጭ መናገራቸው አይዘነጋም፡፡

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርም በጉባዔው ላይ ተገኝተው ሃማስን እየረዳች ነው ያሏትን ኳታርን ለማግለል የአፍሪካ አገሮችን ሲያግባቡ መሰንበታቸውን ምንጮች ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ በኩል፣ ኢትዮጵያ ሁሌም በውጭ ግንኙነት ፖሊሲ ላይ ተመሥርታ ከሌሎች አገሮች ጋር የሁለትዮሽ ግንኙነት እንደምትፈጥር የተገለጸ ሲሆን፣ ከኳታር ጋር ያለውን ግንኙነት ከማቋረጥ ይልቅ ኢትዮጵያ ሁለቱን ወገኖች ለማግባባት እንደምትንቀሳቀስ መገለጹ ተጠቁሟል፡፡

በቀይ ባህር በኩል ባለው ውዝግብ በአሁኑ ወቅት በቀጣናው የተለየ አሠላለፍ እየተፈጠረ መምጣቱ እየተገለጸ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ አጣብቂኝ ውስጥ መሆኗም ይሰማል፡፡ ኢትዮጵያና ኳታር ግንኙነታቸውን ካደሱ አጭር ጊዜ ቢሆንም፣ የሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት ግን በተደጋጋሚ ለኢትዮጵያ ጥያቄ ማቅረቡን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ ገለልተኛነትን መምረጧ ነው የሚነገረው፡፡

29ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ ይህንን ሁሉ ችግር የመፍታት ኃላፊነት የተጣለባት ቢሆንም፣ የአሁኑ ጉባዔ በብዙ ነገሮች ለየት ያለ እንደነበር ሪፖርተር በቦታው ተገኝቶ ለማረጋገጥ ችሏል፡፡ የኅብረቱ ኮሚሽነር፣ ‹‹ጊዜው ከአሁን በኋላ የምናወራበት ሳይሆን የምንሠራበትና ተጨባጭ ለውጥ የምናመጣበት መሆን አለበት፤›› በማለት የኅብረቱን የዘንድሮ ጉባዔ ፋይዳ ገልጸዋል፡፡ ‹‹በአኅጉራችን ያለውን የሰላምና የፀጥታ ችግር ዛሬ መፍታት ካልቻልን ስማችንን ማደስ አንችልም፤›› በማለት፣ በአኅጉሪቱ የተጋረጡ ችግሮችን ጊዜ ሳይሰጥ መፈታት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡

በበዚህ ጉባዔ ላይ ኢትዮጵያ ከተለያዩ የአፍሪካ አገሮች ጋር ከኅብረቱ ስብሰባ ጎን ለጎን የሁለትዮሽ ግንኙነት ያደረገች ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ከፍልስጤም ራስ ገዝ አስተዳደር ፕሬዚዳንት መሐሙድ አባስ ጋር ያደረጉት ውይይት የብዙዎችን ቀልብ ስቦ ነበር፡፡ በዝግ የተካሄደውን የሁለቱ አገር መሪዎች ስብሰባ ሪፖርተር የተከታተለ ሲሆን፣ የፍልስጤም ፕሬዚዳንት ኢትዮጵያ ከእስራኤል ጋር ባላት ግንኙነት ብዙም ደስተኛ እንዳልሆነች ለመገንዘብ ተችሏል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም፣ ‹‹እኛ ከአገሮች ጋር ግንኙነት የምንፈጥረው በውጭ ግንኙነት ፖሊሲያችን መሠረት ነው፡፡ የውጭ ፖሊሲያችን ደግሞ ከአንዱ ጋር ወዳጅ ስንሆን ከሌላው ጋር ጠላት እንድንሆን አያዝም፡፡ ይህ ችግር በእናንተ መካከል እንጂ የእኔ አገርና ሕዝብ ከእስራኤልም ሆነ ከእናንተ ጋር ያለንን ግንኙነት አያሻክርም፡፡ ይህን ላረጋግጥልዎት እወዳለሁ፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋቸዋል፡፡

በዚህ ጉባዔ ላይ እንደ አዲስ ሆኖ በማጠቃለያ ላይ የተበሰረው ለቀድሞዎቹ የኢትዮጵያ መሪዎች ለቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና ለቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ፣ በአፍሪካ ኅብረት ቅጥር ግቢ ውስጥ የመታሰቢያ ሐውልት ለማቆም ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ ይህንንም ሐሳብ ያቀረበችው ጋና ናት፡፡

29ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ በአኅጉሪቱ በተለይም በምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና ያለውን ችግር ለመፍታት ቃል የተገባበት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ የአፍሪካን ችግሮች ጊዜ ሳይሰጡ በመፍታት አኅጉሪቱን እ.ኤ.አ. በ2063 ያቀደችውን ዕቅድ ግብ ለመምታት ቁርጠኛ አቋም መያዟ ተጠቁሟል፡፡

የኅብረቱ ከፍተኛ አመራሮች ይህን ይበሉ እንጂ የአፍሪካ መሪዎች በሰላማዊ መንገድ ከሥልጣን እየወረዱና ለወጣቱ አርዓያ እየሆኑ ካልመጡ፣ አሁንም ውኃ ቅዳ ውኃ መልስ ነው የሚሆነው እያሉ የሚሞግቱ አሉ፡፡ አፍሪካውያን ለአፍሪካውያን በመቆም በመካከላቸው ያለውን እሴት በመጨመርና ለችግሮች በጋራ በመቆም ወደፊት መራመድ እንደሚቻል ግን ከመግለጽ አልተቆጠቡም፡፡

በአፍሪካ ኅብረት አዳራሽ የተገኙ ዲፕሎማቶች፣ ጋዜጠኞች፣ የፖለቲካ ተንታኞችና ሌሎች በአብዛኛው ሲናገሩ የተደመጡት አፍሪካ ከመቼውም ጊዜ በላይ ትልቅ ነገር እንደሚያስፈልጋት ነው፡፡ በአኅሪቱ ውስጥ የሚታየው ድህነት፣ ግጭት፣ ሽብርተኝነትና የመሳሰሉት አሁንም ጥያቄ እያስነሱ ነው፡፡ አፍሪካ ወደፊት ተስፋ ያላት አኅጉር እንድትሆን ከተፈለገ የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት ጉዳይም ትልቅ ትኩረት እንደሚሻ ተደምጧል፡፡ ከዚህ አንፃር የመሪዎች ጉባዔ ምን ያህል ተሳክቶለታል መባል እንዳለበትም ተወስቷል፡፡ አፍሪካዊያን ለዘመናት ከቆዩበት ድህነትና ኃላቀርነት ለማላቀቅ፣ አኅጉሪቱን ደግሞ የወደፊቷ ተደማጭ ኃይል ለማድረግና በኢኮኖሚ ለማበልፀግ ጠንካራና ትክክለኛ ዕርምጃዎች መውሰድ እንዳለባቸው የብዙዎች ሐሳብ ነው፡፡   

Standard (Image)

የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ሒደትና ማብቂያው

$
0
0

ለአንድ አገር ዕድገት ቁልፍ ተደርገው  ከሚወሰዱት ጉዳዮች መካከል አንዱ የዴሞክራሲ ሥርዓት መጎልበት ነው፡፡ በአንድ አገር የዴሞክራሲ ደረጃው ከፍ ባለ ቁጥር በመንግሥትና በሕዝብ መካከል ከፍተኛ የሆነ ቅርርብና ቁርኝት በመፍጠር፣ የአገርን ሁለንተናዊ ዕድገት ማምጣት ይቻላል፡፡ መንግሥት ጠንካራ የሆነ የዴሞክራሲ ሥርዓት ሲገነባ በሕዝቦች መካከል ብሔራዊ አንድነት ከመፍጠር ባሻገር፣ አገሪቱን ከሌሎች አገሮች የተሻለችና ከፍ ያለች በማድረግ በኩል የሚኖረው ሚና ጉልህ ነው፡፡

የዴሞክራሲ ሥርዓት በጎለበተበት አገር ዕድገቱም አብሮ እየጎለበተ እንደሚሄድ የአውሮፓና የአሜሪካ ማሳያዎች ናቸው፡፡ ሰዎች መሠረታዊ መብቶቻቸው ሲከበሩላቸው ሙሉ በሙሉ ጊዜያቸውንና አዕምሮአቸውን በሥራ የሚያሳልፉ ይሆናሉ፡፡ ይህ ሲሆን ደግሞ ራስን በኢኮኖሚ የተሻለ በማድረግ አገርንም የሚያለማ ዜጋ መፍጠር እንደሚቻል ብዙዎችን ያስማማል፡፡

በአፍሪካ አገሮች ውስጥ መሪዎች ከተወሰኑት በስተቀር የሰው ልጆችን መሠረታዊ መብቶች ባለማክበራቸው የተነሳ ዜጎች መብቶቻቸውን ለማስከበር ደፋ ቀና ሲሉ ይታያሉ፡፡ መብቶቻቸው የተከበሩላቸው ባለመሆናቸውም ጊዜያቸውን በሥራ ከማሳለፍ ይልቅ መሠረታዊ መብቶቻቸውን ለማስከበር ከላይ ታች ሲሉ ይታያሉ፡፡ ገፋ ሲል በሰላማዊ ሠልፍና በተለያዩ መንገዶች ጥያቄዎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡ ሳይሆን ሲቀር ደግሞ ስደትን መዳረሻቸው ያደርጋሉ፡፡ የዴሞክራሲ ሥርዓት ባልሰፈነባቸው የአፍሪካ አገሮች እየሆነ ያለውም ይህ ነው፡፡

መንግሥታት ለይስሙላ በሕገ መንግሥት ላይ ዴሞክራሲ እንዲጎለብትና የሰው ልጅ መሠረታዊ መብቶች እንዲከበሩ ሕግ ቢያወጡም፣ ተግባራዊ ስለማያደርጉት ከሕዝብ ጋር ሆድና ጀርባ ሲሆኑ ይታያል፡፡ በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር ኢማኑኤል ሲግማ (ፕሮፌሰር) ‹‹መንግሥት ዴሞክራሲን በአገሩ ካልገነባ ሕዝቡ ጀርባውን ይሰጠዋል፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ የመንግሥቱም ጊዜ ያጥራል፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚም ይመነምናል፤›› በማለት ለአንድ አገር ዕድገት የዴሞክራሲ መጎልበት ያለውን ፋይዳ ያስረዳሉ፡፡

ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ዋነኛ ተዋናይ እንደሆኑ ከሚጠቁሰት መካከል አስፈጻሚው አካል፣ ሚዲያ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችና የሲቪል ማኅበራት ሚና ትልቁን ድርሻ ይይዛል፡፡ በአንድ አገር ውስጥ ካሉት ሦስቱ የመንግሥት አካላት ማለትም ሕግ አውጭ፣ ሕግ አስፈጻሚና ሕግ ተርጓሚው መካከል ሕግ አስፈጻሚው አካል ከፍተኛ የሆነ የቁጥጥር ሥርዓት በመዘርጋት፣ በአገሪቱ ውስጥ የሚከናወኑ ሥራዎችን በትክክል ከተቆጣጠረና ሕግና ሕገ መንግሥቱን ብቻ መሠረት አድርጎ ሕዝብን ካገለገለ፣ አገር በሁለንተናዊ ዕድገቷ ከአንድ ምዕራፍ ወደ ሌላ የዕድገት ምዕራፍ መሸጋገሯ የማይቀር ይሆናል፡፡

የዴሞክራሲ ሥርዓት ከተዘረጋ ሚዲያው ኅብረተሰቡን መሠረት ያደረገ ሥራ በማከናወን በአገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ ለውጥ ማምጣት እንደሚችል ይታመናል፡፡ በበለፀጉ አገሮች ሚዲያ እንደ አራተኛ መንግሥት የሚቆጠረው ለዴሞከራሲ ሥርዓት ያለው አቅም ከፍተኛ በመሆኑ ነው፡፡ የሚዲያ ሚና እጅግ ከፍተኛ ቢሆንም፣ እንደ አፍሪካ ባሉ አገሮች በመንግሥት ቁጥጥር ሥር ሆኖ የሕዝቡን ፍላጎት ሳይሆን የገዥውን ፓርቲ ራዕይና ዓላማ የሚያራምድ በመሆኑ፣ ብዙ እንደማይራመድ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይህ በሚሆንበት ጊዜ ደግሞ ሕዝብና መንግሥት በሐሳብ ሳይገናኙ ይቀራሉ፡፡

ለዴሞክራሲ ግንባታ ሌላው ማራመጃ መሣሪያ ተደርገው ከሚቆጠሩ ባለድርሻ አካላት መካከል ሲቪል ማኅበራት ይካተታሉ፡፡ ሲቪል ማኅበራት ዜጎች በመደራጀት ዴሞከራሲያዊ መብቶቻቸውን እንዲያከብሩና እንዲያስከብሩ የሚያስችሉ መሣሪያዎች እንደሆኑ ይነገራል፡፡

ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ቁልፍ ሚና አላቸው ተብለው የሚጠሩት እነዚህ አካላት ተግባራቸውን በትክክል ሲወጡ ብቻ ውጤታማ ሥራ ሊከናወን እንደሚችል ምሁራን ይናገራሉ፡፡ በዚህ መሠረት ሰኔ 23 ቀን 2009 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) ‹‹የኛ ጉዳይ›› በሚል ርዕስ ለሚተላለፈው የቴሌቪዥን ፕሮግራም፣ በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል የውይይት መድረክ አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በውይይቱ ላይ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሲቪል ማኅበራት፣ የአስፈጻሚ አካላትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተወካዮች ተገኝተው ነበር፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመጡ መምህራን ለውይይቱ መነሻ የሚሆን ጽሑፍ አቅርበዋል፡፡

የመነሻ ጽሑፍ ካቀረቡት መካከል አንዱ ደመቀ አቺሳ (ዶ/ር) ሲሆኑ፣ ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ የአስፈጻሚው አካልና የፖለቲካ  ፓርቲዎች ሚና ምንድነው? ለዴሞክራሲ ሥርዓት እሴቶች ምንድናቸው? በዴሞክራሲ ግንባታ ሒደት ላይ የነዚህ ባለድርሻ አካላት ተግዳሮቶች ምንድናቸው? ወዘተ. የሚሉትን አብራርተዋል፡፡ ደመቀ (ዶ/ር) እነዚህ ባለድርሻ አካላት ለዴሞክራሲ ግንባታ ያላቸውን አስተዋጽኦ ሲያብራሩ፣ ተሳታፊዎች በጥሞና ያዳመጡ ቢሆንም፣ ወደ ጥያቄና መልስ በተሄደበት ወቅት ግን ከታዳሚው በጣም ብዙ ቅሬታዎችና አስተያየቶች ይሰሙ ነበር፡፡

‹‹ከኃይለ ሥላሴ ጀምሮ ሕግ አስፈጻሚዎች ለብዙ ዘመናት ከሕገ መንግሥቱ ውጪ የሆነ ሥልጣን ነበራቸው፡፡ ንጉሡ ተጠያቂነት አልነበራቸውም፡፡ በደርግ ዘመነ መንግሥትም ሕገ መንግሥት ለይስሙላ ቢኖርም አስፈጻሚው አካል ተጠያቂ አልነበረም፤›› በማለት የኢሕአዴግን መንግሥት የአስፈጻሚ አካላት ተጠያቂነት ከድሮው ሥርዓት ጋር እያነፃፀሩ አቅርበዋል፡፡ ጥናት አቅራቢው ይህንን ቢሉም፣ ቅንጅትን የወከሉ አንድ ተሳታፊ፣ ‹‹እኔ ራሴን አሁን ካለው የኬንያና የአሜሪካ ዜጋ ጋር ነው የማወዳደረው እንጂ፣ በደርግ ዘመን ወይም ከዚያ በፊት ከነበረው ሥርዓት ጋር አላወዳድርም፤›› በማለት ኢሕአዴግ ራሱን ካለፉት ሥርዓቶች ጋር እያወዳደረና ራሱን እያሞካሸ በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት ከሚያጣ፣ ችግሩን በተለይም በአስፈጻሚው አካል ዘንድ እየታየ የመጣውን ሥር የሰደደ ችግር መፍታት እንደሚገባው ጠቁመዋል፡፡

ቪኮድ ሲቪል ማኅበርን የወከሉት አቶ ታደለ ደርሰህ በበኩላቸው፣ የዴሞክራሲ ውበቱ ልዩነትን ማስተናገድ ቢሆንም ኢሕአዴግ ወደ ሥልጣን ከመጣ ወዲህ 26 ዓመታት ሙሉ አንድ ወጣት ከዩኒቨርሲቲ ዲግሪ ይዞ የሚወጣበት በመሆኑ፣ ኢሕአዴግ በደርግና በኃይለ ሥላሴ መፅናናት እንደሌለበት ገልጸዋል፡፡ የፌዴራልና የአርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስትር አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን በበኩላቸው፣ በአገሪቱ ታሪክ ውስጥ መንግሥታት የሚወቀሱት ከወደቁ በኋላ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

ጥናት አቅራቢው በመነሻ ጽሑፋቸው ላይ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ቁጥር መብዛትና ግልጽ ዓላማ ያላቸው ባለመሆኑ፣ በአገሪቱ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ እንዳይፈጠር እንቅፋት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ እሳቸው ይህን ይበሉ እንጂ የሰማያዊ ፓርቲ የወቅቱ ፕሬዚዳንት አቶ የሸዋስ አሰፋ በጽሑፍ አቅራቢው ላይ ከፍተኛ የሆነ የተቃውሞ አስተያየት ሰንዝረዋል፡፡ አቶ የሺዋስ፣ ‹‹ያለንን ዓላማ የምናስተላልፍለት ሚዲያ እስካላገኘን ድረስ ዓላማችንን በምን እናሳውቅ?››  የሚል ጥያቄ አዘል አስተያየት አቅርበዋል፡፡ ኢቢሲን ጨምሮ ሁሉም ሚዲያዎች የአንድ ፓርቲ ሐሳብ ብቻ መፍሰሻዎች እንደሆኑ በቅሬታ አቅርበዋል፡፡ የራዕይ ፓርቲ ፕሬዚዳንት አቶ ተሻለ ሰብሮ በበኩላቸው፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ቁጥር ለምን ጨመረ ለሚለው አስተያየት፣ ‹‹ይሂዱና ሕገ መንግሥቱን ይጠይቁት፤›› በማለት የተቃዋሚ ፓርቲዎች ቁጥር መጨመር ሕጉ የሚፈቅደውና ቁጥራቸው የበዛ ቢሆንም፣ ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡

ደመቀ (ዶ/ር) በመነሻ ጽሑፋቸው ላይ ኢሕአዴግ ብቻ ግልጽ ፖሊሲ እንዳለው አብራርተዋል፡፡ አቶ የሺዋስ፣ ‹‹ኢሕአዴግ ብቻ ነው ግልጽ ፖሊሲ ያለው ብለው ባቀረቡት ሐሳብ በጣም ነው የተገረምኩት፡፡  ምክንያቱም መደገፍ ይቻላል፡፡ አባል ከሆኑ ሊገባዎት ይችላል፡፡ ነገር ግን የሰማያዊን ፓርቲ ሳያነቡ የለም ብለው ደምድመው መናገርዎ ስህተት ነው፤›› በማለት ተቃውመዋል፡፡

አቶ ታደለ በበኩላቸው፣ ‹‹በአሁኑ ወቅት ወደ 17 የፖለቲካ ፓርቲዎች አሉ ተብሏል፡፡ በየትኛው ሰዓትና ሚዲያ ነው አጀንዳቸውን አቅርበው ሕዝብ እንዲመርጣቸውና ግልጽ ፖሊሲያቸውን እንዲያሳውቁ የሚያደርጉት?›› በማለት የጥናት አቅራቢውን ሐሳብ ተቃውመዋል፡፡ አቶ ተሻለ በበኩላቸው፣ ‹‹ይቅርታ ይደረግልኝና ምነው አንድ ቀን እኛ ወንበር ላይ ተቀምጠው ቢያዩት? ወይም በአንድ ምርጫ ገብተው እንቅስቃሴውን ቢያዩ? እንደ ኢትዮጵያዊ ይህንን ስናገር ልቤ ይቆስላል፡፡ ይሰማኛል፡፡ ምክንያቱም ከአንድ ኢትዮጵያዊ ያውም ከአንጋፋው ዩኒቨርሲቲ የወጣ ምሁር እንደ ውጭ ዜጋ ይህን መሰል አስተያየት በተቃዋሚዎች ላይ መስጠት ተገቢ አይመስለኝም፤›› ብለዋል፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ፣ ኢሕአዴግ ይዞት ከተነሳው ራዕይ አንፃር በአሁኑ ወቅት ግልጽ የሆነ ፖሊሲ እንዳለው አስረድተው፣ በአሁኑ ወቅት እየተፈጠረ ባለው የአውራ ፓርቲ ሥርዓት ተቃዋሚዎች ተጎጂ እንዳይሆኑ ፖሊሲያቸውን የሚያስተዋውቁበት መድረክ ሊዘጋጅ እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡

የቅንጅት ተወካይ ደግሞ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እጅና እግር ታስሮ ባለበትና በነፃነት የጻፈና የተናገረ እስር ቤት በሚገባበት ወቅት፣ በምን ሁኔታ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ፖሊሲያቸውን ማስተዋወቅ እንዳለባቸው ጥያቄ አዘል አስተያየታቸውን ተናግረዋል፡፡

በመድረኩ ላይ የአውራ ፓርቲ ሥርዓት እየመጣ መሆኑ ተገልጿል፡፡ አቶ የሺዋስ የአውራ ፓርቲ ሥርዓት እየመጣ መሆኑን ጠቅሰው፣ እያንዳንዱ ፓርቲ ደንብና ሥርዓት ቢኖረውም ጽሑፍ አቅራቢው ጠቅልለው መናገራቸውን ኮንነዋል፡፡ በዚህም የወገንተኝነት ነገር እንደሚታይባቸው ተናግረዋል፡፡

በውይይቱ ላይ የተነሱ አስተያየቶችና ጥያቄዎች በአብዛኛው ትኩረት ያደረጉት በተያዘው አጀንዳ ላይ ሳይሆን፣ በአገሪቱ ላይ በሚታዩ ሌሎች ተያያዥ ወቅታዊ ጉዳዮች ነበር፡፡

ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ የባለድርሻ አካላት ሚና ምንድነው የሚለው የመወያያ ርዕስ ሆኖ ቢቀርብም፣ ብዙ ሐሳቦች ከዚህ አጀንዳ ውስጥ ሲንሸራሸሩ ነበር፡፡ የቅንጅት ተወካይ፣ ‹‹አሁን የዴሞክራሲ ሥርዓት ለመገንባት ምን ያህል ዓመታት ያስፈልገናል?  ዛሬ ላይ ብንጀምር ምን ያህል ዓመት ይፈጅብናል?  ምክንያቱም ኢሕአዴግ 26 ዓመት ሙሉ ዴሞክራሲ ሒደት ነው እያለን ነው፡፡ ስለዚህ ሒደት ሆኖ የሚኖረው እስከ መቼ ነው?›› የሚል ጠንከር ያለ ጥያቄያቸውን በወቅቱ ለነበሩ የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች አቅርበዋል፡፡ ‹‹በአሁኑ ጊዜ የመጻፍ ነፃነት ተከብሯል ይባላል፡፡ ስለጻፉ አይደለም እንዴ ጋዜጠኞች እስር ቤት የሚገቡት? በአሁኑ ጊዜስ የሕዝቡን ብሶት የሚናገሩ ምን ያህል ሚዲያዎች አሉ? ባለሥልጣናት በምን ሁኔታ እዚህ ቦታ ላይ እንደወጡ ብናውቅም ባናውቅም በማስፈጸም ቦታ ላይ ያሉ ሰዎች ይጠየቃሉ ወይ?›› የሚል ጥያቄ ሰንዝረዋል፡፡

አቶ አባዱላ በበኩላቸው፣ የዴሞክራሲ ግንባታ በ24 ሰዓት ሊፈጸም እንደማይችል ግልጽ አድርገዋል፡፡ ‹‹ይህ ቢሆን ኖሮ ከ1984 ዓ.ም. ማግሥት ጀምሮ ተግባራዊ ባደረግነው ነበር፤›› ብለዋል፡፡ በመሠረታዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት ያልተፈጠረባቸው ጉዳዮች ቢኖሩም፣ በማማረር የተለወጠ አገር እንደሌለ አስረድተዋል፡፡

መድረኩን ይመራ የነበረው ጋዜጠኛ የሚሰጡ አስተያየቶችና ጥያቄዎች ከአጀንዳው እንዳይወጡ በተደጋጋሚ ጊዜ አስተያየት ቢናገርም፣ ተሳታፊዎች ግን ከመናገር አልተቆጠቡም ነበር፡፡ የቅንጅት ተወካይ ይህን አስተያየት ከሰጡ በኋላ አንጋፋው ፖለቲከኛ አቶ ዓባይ ስብሃት አካሄዱ መስተካከል እንዳለበት ጣልቃ በመግባት አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ ‹‹አጀንዳው ለዴሞክራሲ ግንባታ የባለድርሻ አካላት ሚና ምን መሆን አለበት የሚል እንጂ ስለኢሕአደግ፣ ቅንጅትና ሰማያዊ ፓርቲ ምን አገባን? በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ደግሞ ፕሮግራም ያዙልንና በሌላ ቀን እንወያያለን፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ከመሠረቱ ወደ ጭቃ እየገባን ነው፤›› በማለት አካሄዱ እንዲስተካከል ጠይቀዋል፡፡

በዚህ የውይይት መድረክ ብዙ ተሳታፊዎች አስተያየት ለመስጠት ዕድል እንዲሰጣቸው በተደጋጋሚ ቢጠይቁም ባለማግኘታቸው፣ መድረኩን ጥለው ሲወጡ ተስተውሏል፡፡

በዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ የሚዲያውና የሲቪል ማኅበራት ሚና ምን መሆን አለበት የሚለውን የመነሻ ጽሑፍ ያቀረቡት ደግሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር መሰለ መንግሥተአብ (ዶ/ር) ሲሆኑ፣ ሚዲያ አገር መገንባትና ዴሞክራሲን የማስፈን አቅም ቢኖረውም የማፍረስ አቅም እንዳለውም አብራርተዋል፡፡ በብዙዎች ዘንድ አራተኛ መንግሥት እየተባለ እንደሚጠራም አስረድተዋል፡፡ ሚዲያ ሁሉንም ዓይነት መስተጋብሮች የሚያራምድ ከመሆኑ አንፃር ፋይዳው የጎላ እንደሆነ በመግቢያ ጽሑፋቸው ላይ አብራርተዋል፡፡

ሚዲያ ያለው ፋይዳ ጉልህ እንደሆነና ከዚህ እስከዚህ ተብሎ ሊለካ እንደማይችል የተናገሩት አንድ ስማቸውን ያልጠቀሱ አስተያየት ሰጪ፣ ሚዲያው በገዥው ፓርቲ ሥር ተጠርንፎ የተያዘ በመሆኑ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ሆኑ ሌሎች ማኅበራት ለሕዝቡ የሚጠቅሙ የዴሞክራሲ እሴቶችንና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን ማስተላለፍ እንደማይቻል ገልጸዋል፡፡

ጥናት አቅራቢው ሲቪል ማኅበራት ለዴሞክራሲ ግንባታ የራሳቸው ዋጋ ቢኖራቸውም፣ ባልተገባ መንገድ ሲተገበሩ እንደሚታዩም ጠቅሰዋል፡፡

በኢትዮጵያ በተለይም ባለፉት ሁለት ዓመታት በርካታ ችግሮች ተከስተዋል፡፡ እነዚህ ችግሮች አስፈጻሚው አካል በተገቢው መንገድ ለሕዝብ አገልጋይ ካለመሆኑ የመነጩ እንደሆኑ በተደጋጋሚ ጊዜ ሲነገር ቆይቷል፡፡ ኢሕአዴግም በአሠራሬ ላይ ክፍተት ስላለ ቆም ብዬ በመፈተሽ ችግሬን ለማስተካከል እየሞከርኩ ነው ሲል የተደመጠ ሲሆን፣ በጥልቅ ተሃድሶ ውስጥ እያለፈ መሆኑንም ይናገራል፡፡ ይህ እንዳለ ቢሆንም አቶ ተሻለ ከረቂቅ እስከ ደቂቅ፣ ከመሬት እስከ ጠፈር ያሉት ጉዳዮች በሙሉ በኢሕአዴግ ቁጥጥር ሥር እንደሆኑ ያብራራሉ፡፡ ‹‹ሁሉም ነገር እኔም ጭምር በእነሱ ቁጥጥር ሥር ነኝ፤›› በማለት የኢሕአዴግን የበላይነትና ሁሉንም የእኔ ባይነት አባዜ ተቃውመዋል፡፡ ዓላማው በሥልጣን መቆየት እንጂ ይህንን ሥልጣን ሕዝባዊ አድርጌ ከወገኖቼ ጋር በዴሞከራሲ መንገድ እንዴት ልቀጥል? የሚል እንዳልሆነ አስረድተዋል፡፡ አቶ ካሳ በበኩላቸው፣ ችግሮችን ወደ ውጭ ከመግፋት ይልቅ ወደ ውስጥ በማየት እያንዳንዱ ሰው አስተዋጽኦውን ማበርከት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ ሁሉንም ነገር እኔ ብቻ ልቆጣጠር የሚል ቅዠት የለበትም፤›› በማለት ሚኒስትሩ ገልጸው፣ አሁን ባለው ሁኔታ እንከን የሌለበት አስፈጻሚ አካል በአገሪቱ ተገንብቷል ማለት እንደማይቻል ተናግረዋል፡፡

አቶ ካሳ በአሁኑ ወቅት ኢሕአዴግም እየሠራ ያለው አንድ ጊዜ ከወደቀ በኋላ ሌላ ኃይል መጥቶ ትክክል አይደለም ብሎ እንዲተቸው ሳይሆን፣ ያልሠራኋቸው ሥራዎች አሉ እያለ እየተመለከተ የሚሠራ መንግሥት እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

በመድረኩ ላይ መንግሥት ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ድጋፍ እንደሚያደርግ የተገለጸ ሲሆን፣ አቶ ታደለ አጥር በማጠር በአገሪቱ ላይ ለውጥ ሊመጣ እንደማይችል በመግለጽ፣ ለተቃዋሚ ፓርቲዎች የተወሰነ ኪሎ ሜትር ተሂዶ የአበባ እቅፍ ሊሰጣቸው እንደሚገባ መንግሥትን አሳስበዋል፡፡

በውይይት መድረኩ ላይ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎችና አመራሮች የተገኙ ሲሆን፣ ከነዚህ መካከል ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ አባዱላ ገመዳና ምክትላቸው ወ/ሮ ሽታየ ምናለ፣ የፌዴራልና አርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስትር አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን፣ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዩች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ዛዲግ አብርሃና ሌሎችም ተገኝተዋል፡፡

ደመቀ (ዶ/ር) ባቀረቡት የመነሻ ጽሑፍ ብዙ የተቃውሞ አስተያየቶችና ጥያቄዎች የተነሱ ሲሆን፣ በማጠቃለያ ንግግራቸው፣ ‹‹እኔ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ብሆን ኖሮ እንደዚህ ዓይነት አስተያየት የሰጡትን ግለሰቦች ወደ እስር ቤት እወረውራቸው ነበር፤›› በማለታቸው፣ ብዙዎች በመደናገጥ ከአንድ አንጋፋ ዩኒቨርሲቲ ከሚያስተምር ምሁር የማይጠበቅ እንደሆነ ሲናገሩ ተደምጧል፡፡

በመድረኩ ላይ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ሊረጋገጥ የሚችለው በሒደት እንደሆነ ቢገለጽም ሒደት ነው፣ ሒደት ነው እየተባለ 26 ዓመታት ሙሉ ለውጥ የታየ ባለመሆኑ መንግሥት እንዲያስብበት አስተያየቶች ቀርበዋል፡፡ ለሕዝብ የዴሞክራሲ ሥርዓት በመገንባት ላይ ነን እየተባለ ሁሌ የማታለያ ቃላትና የመደለያ ጥቅማ ጥቅም ከመስጠት ይልቅ፣ ቁርጠኛ ሆኖ ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ዛሬ ነገ ሳይባል መግባት ተገቢ እንደሆነ ተብራርቷል፡፡ የመንግሥት አስፈጻሚ አካላት ራሳቸውን ፈትሸውና የሕዝብ አገልጋይነት ስሜት ተላብሰው ዕርዳታ እየለመኑ ሕዝቡን ከማስተዳደር አባዜ ወጥተው፣ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት መሥራት እንዳለባቸው በርካቶች አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ነፃ መድረክ በማዘጋጀትና የፖለቲካ ምኅዳሩን በማስፋት ያላቸውን ፖሊሲና ስትራቴጂ ለሕዝቡ ማሳወቅ እንዳለባቸው፣ እነሱም ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ የሚል አስተያየትም ተሰንዝሯል፡፡

በአገሪቱ ያሉ ሚዲያዎች በተለይም የመንግሥት ሚዲያዎች ባለቤትነት በመንግሥት ቢሆኑም ነፃ፣ ግልጽና ሕዝብን መሠረት አድርገው እንዲሠሩም ጥያቄ ቀርቧል፡፡ ሲቪል ማኅበራትም እንዲደራጁና ለዴሞክራሲ ግንባታ የራሳቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ መንግሥት ድጋፍ ሊያደርግላቸው እንደሚገባ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል፡፡  

Standard (Image)

የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና የሥራ ቀጣሪዎች ትስስር ገፊዎች

$
0
0

 

በአዲስ አበባ ከተማ ሁሌም በሰዎች ከሚጨናነቁ ቦታዎች መካከል አራት ኪሎ ጆሊ ባር አጠገብ የሥራ ማስታወቂያ የሚለጠፍባቸው ሰሌዳዎች የሚገኙበት ቦታ ተጠቃሽ ነው፡፡ በዚህ ሥፍራ በአብዛኛው አዳዲስ የዩኒቨርሲቲ ተመራቂዎች የሚታዩ ቢሆንም፣ እንደ ቅዱስ ሥፍራ ለዓመታት የተመላለሱበትን ወጣቶች ማግኘት ብርቅ አይደለም፡፡ ለእነዚህ ወጣቶች ከዚህ ስፍራ በቅርብ ርቀት የሚገኙት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ትምህርት ሚኒስቴርና ፓርላማው በቂ ምላሽ የሰጧቸው አይመስልም፡፡

ከእነዚህ ተመራቂዎች መካከል ‘ዕድለኛ የሆኑት’ ጥቂቶች ቶሎ ሥራ ያገኛሉ፡፡ ‘ዕድለኛ ያልሆኑት’ ብዙኃኑ ደግሞ ለዓመታት በሥራ ፍለጋ ይንከራተታሉ፡፡ የአገሪቱ ገበያ ቁጥራቸው በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ለመጣው ተመራቂዎች ሥራ ለማቅረብ አቅም እንደሌለው ለዓመታት ሲገለጽ ቆይቷል፡፡ ይሁንና ችግሩ ከመሠረቱ ስለመፈታቱ አሁንም ማሳያ ማቅረብ አይቻልም፡፡

በየዓመቱ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚመረቁ ተማሪዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ የሚሰጡትን መፍትሔዎች እንዳይታዩ ያደረጋቸው ይመስላል፡፡ ዘንድሮም ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ በ2009 ዓ.ም. በአገሪቱ ከሚገኙ የመንግሥት ትምህርት ተቋማት ብቻ 126 ሺሕ ተመራቂዎች በተለያዩ የትምህርት መስኮችና ደረጃዎች ትምህርታቸውን እንዳጠናቀቁ የትምህርት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል፡፡ ከዚሁ ውስጥ 109 ሺሕ ተመራቂዎች በመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርታቸውን የተከታተሉ ናቸው፡፡

በ1983 ዓ.ም. ኢሕአዴግ ወደ ሥልጣን ሲመጣ በአገሪቱ የነበሩ ዩኒቨርሲቲዎች ሁለት ብቻ ነበሩ:: በወቅቱ በመላው አገሪቱ የነበሩት 16 ኮሌጆችም የቅበላና የማስመረቅ አቅማቸው ደካማ የሚባል ነበር:: በ1993 ዓ.ም. መንግሥት ሰባት ተጨማሪ ዩኒቨርሲቲዎችን ሲከፍት በተለያዩ የፌዴራል መንግሥት ተቋማት የሚተዳደሩ ሦስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት (የመከላከያ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ፣ የቴሌኮሙዩኒኬሽንና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኮሌጅና ሲቪል ሰርቪስ ኮሌጅ) ሥራ ጀምረው ነበር:: በክልል መንግሥታት የሚተዳደሩ ስምንት የመምህራን ማሠልጠኛ ኮሌጆችም የማይናቅ ሚና መጫወት ጀምረው ነበር:: በ1996 ዓ.ም. ግንባታቸው የተጀመረው አሥራ ሦስት ዩኒቨርሲቲዎችም በ1999 ዓ.ም. ሥራ ጀምረዋል:: በሦስተኛው ዙር ማስፋፊያ አሥር ተጨማሪ ዩኒቨርሲቲዎች በ2003 ዓ.ም. ሥራ የጀመሩ በመሆኑ፣ በጠቅላላው አሁን በአገሪቱ ያሉት ዩኒቨርሲቲዎች ቁጥር 33 ደርሷል:: ከዚህ በተጨማሪም መንግሥት የብቃት ማረጋገጫ የተሰጣቸው ከስልሳ በላይ የግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት አሉ:: የክልል መምህራን ማሠልጠኛ ኮሌጆች ቁጥርም ከ30 በላይ ደርሷል:: በቅርቡ ደግሞ 11 አዳዲስ ዩኒቨርሲቲዎችን ለመገንባት መንግሥት ዕቅድ ይዟል፡፡

የእነዚህ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መብዛት የቅበላ አቅምንና የተመራቂ ተማሪዎችን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሮታል:: የቁጥሩ ጭማሪ እንደ ትልቅ ዕርምጃ የሚታይ ቢሆንም፣ የትምህርት ጥራትና የምሩቃን ሥራ አጥነት ጥያቄ ሆኖ መነሳቱ ግን አልቀረም::

                   

በ1987 ዓ.ም. ወደ ዩኒቨርሲቲዎች የገቡ ተማሪዎች ቁጥር 35,000 ብቻ ሲሆን፣ በ2005 ዓ.ም. የዩኒቨርሲቲዎች የቅበላ አቅም ወደ 99,973 አድጎ ነበር:: 2005 ዓ.ም. ብቻ 67,595 አዲስ ምሩቃን ሥራ ፈላጊ ሆነው ገበያውን ተቀላቅለዋል::

በሌላ በኩል ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርሲቲ መግባታቸውና ተመርቀው መውጣታቸው ያለ በቂ ዝግጅት የተደረገ ለውጥ እንደሆነ በመጠቆም፣ ጥራት ለመጓደሉና ለሥራ ዓለም ብቁና ዝግጁ ያልሆኑ ተመራቂዎች ለመውጣታቸው ቁጥሩ ምክንያት መሆኑን የሚሞግቱም አሉ::

የአገሪቱ ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያም ማክሰኞ ሐምሌ 4 ቀን 2009 ዓ.ም. ካስተላለፋቸው ዜናዎች መካከል በአንዱ፣ የተመራቂዎች ቁጥርና የአገሪቱ የሰው ኃይል የመቅጠር አቅም ያልተመጣጠነ ስለመሆኑ ገልጿል፡፡ የትምህርት ሚኒስትሩ ሽፈራው ተክለ ማርያም (ዶ/ር) ይህን ክፍተት ለመሙላት መንግሥት እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ አመልክተዋል፡፡

መንግሥት ለወጣቶች በቂ የሥራ ዕድል መፍጠር አለመቻሉ ከኢኮኖሚ ችግርነት በመዝለል የፖለቲካ ችግር እየሆነ መምጣቱን ያምናል፡፡ በተለይ በቅርቡ አገሪቱ በተቃውሞና አመፅ ወደ አለመረጋጋት በገባች ወቅት፣ የወጣቶች ሥራ አጥነትን በዋና መነሻ ምክንያትነት የለየው መንግሥት ይህንን ክፍተት ለመሙላት እንደሚሠራ ቃል መግባቱም ይታወሳል፡፡

መንግሥት አሥር ቢሊዮን ብር የሥራ ፈጠራ ፈንድ በመመደብ ይህንኑ ቃሉን ለማክበር መንገድ መጀመሩንም መግለጹ አይዘነጋም፡፡ ወጣቶች አምስትና ከዚያ በላይ ሆነው በመደራጀት የቢዝነስ ዕቅድ አቅርበው አዋጭነቱ ተቀባይነት ካገኘ ብድር እንዲያገኙ ፈንዱ ያስችላል፡፡ አዳዲስ የዩኒቨርሲቲ ምሩቃንም የዚህ ዕድል ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ይጠበቃል፡፡

ሪፖርተር ያነጋገራቸውና ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አመራርና አስተዳደር ላይ ትኩረት አድርገው የሚመራመሩ የትምህርት ኤክስፐርት፣ ለሥራ ፈጠራ ገንዘብ ሲመደብ ሥራ እንዴት ነው የሚፈጠረው በሚለው ጥያቄ ላይ በቅድሚያ መግባባት እንደሚያፈልግ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ሥራ በሁለት ዓይነት መንገድ ነው ሊፈጠር የሚችለው፡፡ አንደኛው ኢንቨስትመንትን በመሳብ ሰፋ ያሉ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ ተቋማት በአገሪቱ እንዲንቀሳቀሱ ማመቻቸት ነው፡፡ ሁለተኛው ራሳቸው ተመራቂዎቹ ሥራ እንዲፈጥሩ ማድረግ ነው፡፡ ይኼ በዋነኛነት አነስተኛና ጥቃቅን ድርጅቶችን ነው በመሣሪያነት የሚጠቀመው፡፡ ስለዚህ ይኼ የተመደበ ገንዘብ በምን ዓይነት መንገድ ነው ሥራ ላይ የሚውለው ወይም እንዴት ሆኖ ነው ሥራ የሚፈጥረው የሚለውን በተመለከተ፣ እስካሁን ምንም ያየሁት ወይም የሰማሁት ነገር የለም፡፡ የተመደበው ገንዘብ በጣም ትልቅ ነው፡፡ ነገር ግን በምን መንገድ እንደሚጠቀመው ይፋዊ የሆነ የመንግሥት ስትራቴጂ ወይም የፖሊሲ ለውጥ አላየሁም፤›› ብለዋል፡፡

ይኼ ገንዘብ ራሱ የተመደበው ከፖለቲካ ቀውሱ በኋላ መንግሥት አጣብቂኝ ውስጥ ሲገባ መሆኑ ሌላው የችግሩ ምንጭ እንደሆነም ኤክስፐርቱ አመልክተዋል፡፡ ቀድሞ ተገቢ የሆነ ስትራቴጂ ተዘጋጅቶለት የመጣ ቢሆን ኖሮ የግልጽነት ጥያቄ ሊነሳበት እንደማይችልም ተከራክረዋል፡፡ ‹‹እንደ ፖለቲካዊ ምላሽ እንጂ እንደ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ ለመውሰድ ይከብደኛል፤›› ብለዋል፡፡

 

ኤክስፐርቱ አገሪቱ ለአዳዲስ ተመራቂዎች ተጨማሪ ሥራዎችን ለማቅረብ ተስፋ ያደረገችው የኢኮኖሚ ዕድገቷን፣ በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ መስፋፋትንና የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መስህብን እንደሆነ አስታውሰዋል፡፡ ነገር ግን በሁለቱም ዘርፎች የሚጠበቀው ዕድገት እንዳልታየ ራሱ መንግሥት እንደሚገልጽም አመልክተዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአገሪቱ በተቀሰቀሰው አለመረጋጋት የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት እየተሸማቀቀ መምጣቱ አዲስ ሥጋት መሆኑንም አክለዋል፡፡

የ27 ዓመቱ ደረጀ ለሚ ከሁለት ዓመት በፊት ከወሎ ዩኒቨርሲቲ በቴክስታይል ኢንጂነሪንግ የተመረቀ ነው፡፡ ደረጀ በዩኒቨርሲቲ ቆይታው በኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ፋብሪካዎች ተግባራዊ ሥልጠና የወሰደ ቢሆንም፣ በአብዛኛው በንድፈ ሐሳብ ላይ ያተኮረ ሥልጠና መሆኑን ለሪፖርተር ገልጿል፡፡ ይሁንና እሱና ጓደኞቹ ወደ ቻይና አቅንተው በጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ አሠራር ላይ ለስድስት ወራት ተግባራዊ ሥልጠና መውሰዳቸው ትልቅ ዕድል እንደሆነ ይገልጻል፡፡

ደረጀ አሁን በሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ ከሚገኙት ፋብሪካዎች ውስጥ በአንዱ በቻይናው ጀይፒ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ እየሠራ ይገኛል፡፡ ይህን የሥራ ዕድል ከማግኘቱ በፊት ተጨማሪ ሥልጠና መውሰዱንም ይናገራል፡፡ ጀይፒ ጨርቃ ጨርቅን የሚቆጣጠረው የውክሲ ጅንማኦ ኃላፊነቱ የተወሰነ ፋብሪካ የቦርድ ሊቀመንበር ሚስተር ያንግ ናን፣ አንድ ኢትዮጵያዊ ተመራቂ አንድ ቻይናዊ የጨርቃ ጨርቅ ሠራተኛ 40 በመቶ ብቃት ላይ ለመድረስ የስድስት ወራት ሥልጠና፣ 80 በመቶ ብቃት ላይ ለመድረስ ደግሞ የሁለት ዓመታት የሥራ ላይ ሥልጠና እንደሚያስፈልገው ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ደረጀ በኢትዮጵያዊ ሠራተኞችና በቻይናዊ ኤክስፐርቶች መካከል ድልድይ ሆኖ ያገለግላል፡፡ አብዛኛዎቹ ምሩቃን ዘርፉ የሚጠብቀው ክህሎት እንደሌላቸውም አመልክቷል፡፡

በርካታ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎችን እየሳበ የሚገኘው የሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ለ60,000 ኢትዮጵያዊያን የሥራ ዕድሎችን እንደሚፈጥር ታሳቢ ተደርጓል፡፡ ባለፈው ሳምንትም የመቐለነ የኮምቦልቻ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ተመርቀዋል፡፡ በቀጣዮቹ ዓመታትም 13 የኢንዱስትሪ ፓርኮችን የመገንባት ዕቅድ ተይዟል፡፡

በእነዚህ ኢንዱስትሪ ፓርኮች የተቀጠሩትን ጨምሮ ተጨማሪ ሥራ መፍጠሩን መንግሥት በየዓመቱ ሪፖርት ያደርጋል፡፡ አንዳንዶች የመንግሥት ቁጥሮችን እንዳለ መውሰድ ቢቻል እንኳን የተወሰኑ ሥራዎችን ዓይነትና የዜጎችን ሕይወት ምን ያህል ይቀይራሉ የሚለው ግምት ውስጥ እንዲገባ ይጠይቃሉ፡፡ ኤክስፐርቱ፣ ‹‹በመንግሥት ሪፖርት ውስጥ ኮብልስቶንና አነስተኛና ጥቃቅን ይካተታሉ፤›› ብለዋል፡፡

ተማሪዎቹ በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው የሚወስዱት ሥልጠና ከዚያ ወጥተው ሥራ ላይ የሚፈለገውን አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል ክህሎት እንዲኖራቸው የሚያደርግ እንዳልሆነም ኤክስፐርቱ ሞግተዋል፡፡ ‹‹ሥልጠናው አሁንም ድረስ ንድፈ ሐሳብ ላይ ያተኮረ ነው፡፡ የሥልጠናው ደረጃ ራሱ ደግሞ በጣም ዝቅ ያለ ነው፡፡ ወደ ዩኒቨርሲቲ ከሚገቡ ተማሪዎች አብዛኛዎቹ ከዝቅተኛው መሥፈርት ውስጥ ከ50 በመቶ በታች ያመጡ እንደሆኑ የመንግሥት ሰነድ ያሳያል፡፡ የዩኒቨርሲቲ መምህራንና ኃላፊዎችም የሚመጡትን ተማሪዎች ምንም ልናደርጋቸው የማንችላቸው ዓይነት ናቸው በማለት ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡ ቀጣሪዎች ደግሞ ተመራቂዎች የሚፈልጉትን ክህሎት ወይም አመለካከት ያላቸው አይደሉም ሲሉ ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡ ለእኔ መሠረታዊ ችግር የሚመስለኝ የሥልጠናው ተፈጥሮ ነው፡፡ ጥራቱን የጠበቀ ግብዓትና ሒደት ስለሌለው ጥራቱን የጠበቀ ውጤት ሊያመጣ አልቻለም፤›› ብለዋል፡፡

መንግሥት የአዳዲስ ተመራቂዎች ሥራ አጥነት ጉዳይ ሲነሳበት፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መንግሥት ሥራ እንዲሰጣቸው ከመጠበቅ ተላቀው ራሳቸው ሥራ ፈጣሪ እንዲሆኑ ሲመክር ይስተዋላል፡፡ ከላይ የተገለጸው የብሔራዊ ቴሌቪዥን ዜና በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሰጠው የሥራ ፈጠራ ትምህርት በሚፈለገው ልክ ለውጥ አለማምጣቱን ለዘርፉ ቅርብ የሆኑ ባለሙያዎች ስለመግለጻቸው ያትታል፡፡ ባለሙያዎቹ የተመራቂዎች ቁጥርና የአገሪቱ የሰው ኃይል የመቅጠር አቅም ያልተመጣጠነ በመሆኑ፣ ተመራቂዎች ሥራ ፈጠራ ላይ እንዲያተኩሩ መክረዋል፡፡

ኤክስፐርቱ፣ ‹‹ዝም ብለህ ተመራቂዎችን ሥራ ፍጠሩ ስላልካቸው ሥራ አይፈጥሩም፡፡ በሥራ መፍጠር ሒዶት ላይ ያሉ እንቅፋቶች ካልተነሱ፣ በደንብ የተሳለጠ ተቋማዊ አሠራር እንዲቋቋም ካልተደረገ ሥራ ፈጠራ ዝም ብሎ በራሱ የሚመጣ ነገር አይደለም፤›› ብለዋል፡፡  

የትምህርት ሚኒስትሩ ሽፈራው ተክለ ማርያም (ዶ/ር) በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሰጠው ትምህርት የሥራ ፈጠራ ክህሎትን በማዳበር ላይ መሠረት አድርጎ ለውጥ እንዲያመጣ እየተቃኘ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ በሙያና ቴክኒክ ማሠልጠኛ ኮሌጆች የተግባር ትምህርት ድርሻ 70 በመቶ፣ ቀሪው 30 በመቶ ደግሞ የንድፈ ሐሳብ እንዲሆን መደረጉ ተመራቂዎችን ሥራ ፈጣሪ ለማድረግ የታለመ ነው ብለዋል፡፡ በዩኒቨርሲቲዎች ደረጃ ጅምሮች ቢኖሩም ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት፣ ለሚቀጥሉት 15 ዓመታት የሚያገለግል የሥርዓተ ትምህርቱን ክፍተቶች የሚለይና የሚሞላ ፍኖተ ካርታ መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡

የትምህርት ተቋማት ከኢንዱስትሪዎች ጋር ተሳስረው እንዲሠሩ ማድረግና ሌሎች ጅምሮችም የሥራ ፈጠራ ክህሎት ያለው የሰው ኃይል ለማፍራት ዓይነተኛ ሚና እንደሚጫወትም ሚኒስትሩ አክለዋል፡፡ 

መንግሥት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የጥራት ችግር መኖሩን ባይክድም፣ የትምህርት ተደራሽነት ከትምህርት ጥራት ያልተናነሰ ትኩረት የሚያሻው ችግር እንደሆነ ያስገነዝባል:: በዚህም ምክንያት የትምህርት ፖሊሲው የትምህርት ዕድልን ማስፋትንና የትምህርት ጥራት የማረጋገጥን ጉዳይ ጎን ለጎን እንዲካሄዱ የሚያደርግ መሆኑን ያመለክታል:: ሥራ አጥ ተመራቂ ተማሪዎችን በተመለከተም እንደ ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ያሉ የሥራ ዕድል የሚያስፋፉ ስትራቴጂዎችን ከመንደፍ ጎን ለጎን፣ ሥራ ፈጣሪ ምሩቃንን ለማፍራት አመቺ ሁኔታዎች መፍጠሩንም ይገልጻል::

የሥራ አጥ ምሩቃን መበራከትና በመንግሥት የተፈጠሩት የሥራ ዕድሎች ከሠለጠኑበት የትምህርት መስክና ከወሰደው ጊዜ ጋር የማይጣጣሙ እንደሆኑ በመግለጽ የሚተቹ አካላት፣ የመንግሥት 70/30 ፖሊሲ ምሩቃኑን የመቅጠር አቅም ያለው የማኑፋክቸሪንግ ሴክተር መፈጠርን ታሳቢ ያደረገ ቢሆንም ዘርፉ በሚጠበቀው ደረጃ አለማደጉን ይጠቁማሉ፡፡ በዩኒቨርሲቲዎች ሥልጠናና በገበያው መካከል የላላ ግንኙነት መፈጠሩ የሥራ አጥ ምሩቃንን ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ እንዲመጣ ማድረጉንም ያስረዳሉ::

መንግሥት ለትምህርት ዘርፍ በአጠቃላይ የሰጠው የተለየ ትኩረት ዘርፈ ብዙ ጥቅሞችን ማምጣት መጀመሩን ይገልጻል:: የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሰፊ የትምህርትና የሥልጠና ሥርዓት ከአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ ልማት ጋር የተቀናጀና የሕዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጠ ማኅበራዊ ልማት እያመጣ እንደሆነም ይከራከራል:: ዩኒቨርሲቲዎቹ ምሩቃኑን የቀለም ትምህርትና ዕውቀት ብቻ ሳይሆን በሙያዊ ክህሎት የተካኑ፣ ሥራ ፈጣሪና አምራች ጭምር እንዲያደርጉ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ እያፈሰሰ እንደሚገኝም ይገልጻል:: ለ2010 ዓ.ም. ለመንግሥት ከተፈቀደው በጀት ውስጥ ለትምህርት ዘርፍ የሚውለው 43 ቢሊዮን ብር መሆኑ ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት አመላካች እንደሆነም መንግሥት ይሞግታል:: በእርግጥም መንግሥት ለትምህርት ዘርፍ የሚመድበው በጀት እየጨመረ መሄዱን የተለያዩ ጥናቶች ይጠቁማሉ::

የትምህርት ዘርፍ ተመራማሪዎች የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚከፍቷቸው የጥናት ዘርፎች በገበያው የሚፈለጉ ስለመሆናቸው የተጠና እንደማይመስላቸውም ያመለክታሉ:: በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ተመሳሳይ የትምህርት ክፍሎች መኖርንም ለዚህ እንደ ዋቢነት ይጠቅሳሉ:: ነገር ግን የመንግሥት ፖሊሲ ሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ተመሳሳይ የትምህርት ክፍሎች እንዲከፍቱ አያስገድድም:: በ70/30 ፖሊሲም ቢሆን ከአጠቃላይ የትምህርት ዘርፎች ውስጥ ምን ያህል በመቶው ሳይንስ፣ ቢዝነስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ማኅበራዊ ሳይንስ መሆን እንዳለበት ብቻ ነው የሚያስቀምጠው::

የትምህርት ሚኒስቴር የትምህርት ዘርፍን ለመከታተልና ለመምራት የተቋቋመ የፌዴራል ተቋም ሲሆን፣ የግልም ሆነ የመንግሥት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጥራትና ተፈላጊነት ያላቸውና ደረጃቸውን የጠበቁ ስለመሆናቸው ያረጋግጣል:: ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ናቸው፡፡ ይህን ሹመት ከማግኘታቸው በፊት በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ጉዳዮች ክፍል ዳይሬክተር ነበሩ:: በወቅቱ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ተማሪዎቹ በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው የሚያገኙት ትምህርት ለገበያው ዝግጁ እንዲያደርጋቸው ሲባል የሚማሩት ትምህርት ካሪኩለም ሲዘጋጅ ጀምሮ የገበያው አስፈላጊ ባለድርሻ አካላት ፍላጎት እንዲያካትት ተደርጎ ነው የተቀረፀው:: ተማሪዎቹ አስፈላጊው ዕውቀት፣ ክህሎትና አመለካከት እንዲኖራቸው ማድረግ አስፈላጊ ጉዳይ እንደሆነም አመልክተዋል::

ዶ/ር ሳሙኤል መንግሥት ለምሩቃኑ ሁሉ ሥራ ባለማዘጋጀቱ እንደሚተች ግንዛቤው እንዳላቸው ገልጸው፣ የአገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ለዚህ ክፍተት በአጭር ጊዜ ምላሽ እንደሚሰጥ ተስፋቸው እንደሆነ ገልጸዋል:: ‹‹የትም አገር የሚመረቀውን ተማሪ ሁሉ የሚቀጥር ገበያ የለውም:: ስለዚህ የሥራ ፈጠራ ክህሎት አንዱ የሚማሩት መሠረታዊ ነገር ነው:: መንግሥት በአነስተኛና ጥቃቅን ኢንተርፕራይዞች አማካይነት የሥራ ፈጠራ ክህሎታቸውን ሥራ ላይ እንዲያውሉ እያደረገ ነው:: ሥራ ፈጠራው ሀብት መፍጠር ብቻ ሳይሆን፣ ለሀብት ክፍፍልም መሣሪያ በመሆኑ የራሱ የሆነ ፖለቲካዊ አንድምታም አለው:: እነዚህ ኢንተርፕራይዞች ለትላልቅ ኢንዱስትሪዎችም ድጋፍ ናቸው፤›› በማለት ዶ/ር ሳሙኤል አብራርተዋል::

የተመራቂ ተማሪዎች ቁጥር በምንም መመዘኛ ትልቅ እንዳልሆነ ያስታወሱት ዶ/ር ሳሙኤል፣ ለትምህርት ዕድሜአቸው ብቁ ከሆኑት ውስጥ ዘጠኝ በመቶ የሚሆኑትን በዚህ ወቅት ለማስመረቅ ዕቅድ ቢያዝም የተሳካው ከስድስት በመቶ ያነሰ እንደሆነም ጠቁመዋል:: መንግሥት የትምህርት ጥራትና ኢኮኖሚያዊ ሽግግሩን ጎን ለጎን እያካሄደ መሆኑንም በማውሳት፣ የምሩቃኑ ቁጥር ትርፍ ቢመስልም ይኼ የአጭር ጊዜ ነፀብራቅ እንደሆነና በአገሪቱ የረዥም ጊዜ ራዕይ ኢኮኖሚው እየተስፋፋ የመጣውን የተማረ የሰው ኃይል ለማስተናገድ የሚችል አቅም እየተፈጠረ ለመሆኑ በርካታ ማሳያዎች እንዳሉ ገልጸዋል::

የትምህርት ጥራት በዋነኛነት ለተመራቂዎች ሥራ ማጣት እንደ ምክንያትነት የሚጠቅሱ አስተያየት ሰጪዎች ግን፣ መንግሥት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ማስፋፋት ላይ ዓይኑን አዙሮ ወደ ትምህርት ጥራትና የሥራ ዕድል ማስፋፋት ላይ የማተኮሪያ ጊዜው አሁን ነው ሲሉ ይመክራሉ::

በትምህርት ዘርፍ ውስጥ የተለያዩ ሥራዎችን ያበረከቱት የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፣ መንግሥት ዩኒቨርሲቲዎችን በብዛት መክፈት ላይ ትኩረት ያደረገው በፖለቲካ ስሌት ተነሳስቶ እንደሆነ እንደሚያምኑ ገልጸው፣ ‹‹የትምህርት ተደራሽነት ግን በጣም አስፈላጊ ነው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹ነገር ግን የትምህርት ጥራትና ፍልስፍናው ራሱ ችግር አለበት፡፡ ዩኒቨርሲቲዎቻችን እየተመሩ ያሉት በካድሬዎች ነው፡፡ ለትምህርት ተቋማቱ አንፃራዊ ነጻነት መሰጠት አለበት፤›› ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፣ በተለይ መንግሥት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱን ዋነኛ አጀንዳዬ የሚለው የልማት መሣሪያዎች አድርጎ መውሰዱ መሠረታዊ ችግር እየፈጠረ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ ቁሳዊ ዕድገት ላይ ከመጠን ያለፈ ትኩረት በመሰጠቱ በሌሎች ዘርፎች ለዩኒቨርሲቲዎች የተሰጠው ኃላፊነት እንደተዘነጋ ጠቁመዋል፡፡

የትምህርት ሥርዓቱ በአጠቃላይ ከፍተኛ የጥራት ችግር ስላለበት በቂ ጊዜ ወስደው የማይማሩ ተማሪዎች ሲመረቁ በቂ ዕውቀትና የራስ መተማመን እንደማይኖራቸው ገልጸዋል፡፡ ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርሲቲ ሲገቡ መሠረታዊ ችግር እንዳለባቸው የማይክዱት ዶ/ር ዳኛቸው፣ የዩኒቨርሲቲዎቹ አደረጃጀትና አሠራር ግን ተማሪዎቹ ይዘውት የገቡትን ችግር ለመቅረፍ የሚያስችል እንዳልሆነ አመልክተዋል፡፡

ተማሪዎች የራሳቸው ሥራ ፈጣሪ እንዲሆኑ ቅድመ ዝግጅት እስከተደረገ ድረስ፣ ለሌሎች የመፍትሔ ሐሳቦች አጋዥና አንድ አማራጭ መንገድ ሆኖ መዝለቁ  አይቀርም፡፡ ይሁንና ተመራቂዎች ሥራ እንዲፈጥሩ እየተጠየቁ ያሉት መሠረታዊ ጥያቄዎች ቀድመው ሳይመለሱ መሆኑን በመጥቀስ መንግሥትን የሚተቹ አሉ፡፡

ከዚሁ ጉዳይ ጋር የሚያያዘው አንድ ነጥብ የአገሪቱ ዩንቨርሲቲዎች የፖለቲካው ምኅዳር ከፍተኛ ተፅዕኖ እያሳረፈባቸው መገኘቱ ነው፡፡ ተማሪዎች ከካምፓስ ከመውጣታቸው በፊት በአንድም ይሁን በሌላ በጎሳ ፀብ ይካፈላሉ፣ አልያም ሌሎች ሲካፈሉ ያያሉ፡፡ የአገሪቱ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ከትምህርታቸው ባልተናነሰ በገዥው ፓርቲ ፖለቲካ ሲጠመዱም ይስተዋላሉ፡፡ ኢሕአዴግ በሐሳብ ያልተስማሙትን የዩንቨርሲቲ መምህራን ከማባረር ጀምሮ የተለያዩ ተፅዕኖዎች እንደሚያደርግባቸውም የተለያዩ ሪፖርቶች ይጠቁማሉ፡፡ በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ከትምህርትና ከዕውቀት አዘል ጉባዔዎች ወይም ውይይቶች ይልቅ፣ የፖለቲካና የኢንዶክትሪኔሽን ዓላማ ያላቸው ስብሰባዎች ይበልጥ ይስተዋላሉ፡፡ ገዥው ፓርቲ በመላ አገሪቱ ውስጥ በሚገኙ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ አባላት እንዳሉትና በእያንዳንዱ የትምህርት ክፍሎች ውስጥ ህዋስ እንደዘረጋ ይነገራል፡፡ በዚህም አብዛኞቹ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የሥርዓቱ አካልና አስፈጻሚ መሆናቸውን የተለያዩ ሪፖርቶች ይጠቁማሉ፡፡

እነዚህ ሁሉ ችግሮች ተደማምረው የሥራ አጥነት ችግሩን እንዳባባሱት መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ በተመሳሳይ የዓለም ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ከ15 ቀናት በፊት ያፀደቀው የባንኩና የኢትዮጵያ የቀጣይ አምስት ዓመታት የግንኙነት ማዕቀፍም፣ በአገሪቱ ሥራ ፈጠራ እያደገ የመጣ ተግዳሮት መሆኑን ይገልጻል፡፡ የአገሪቱ ሕዝብ የዕድሜ ስብጥር ላይ እየታየ ያለው ፈጣን ለውጥ ጉዳዩን ይበልጥ አሳሳቢ እንደሚያደርገውም ሪፖርቱ ይጠቁማል፡፡ እ.ኤ.አ. ከ1985 እስከ 2010 ድረስ ከአጠቃላይ ሕዝቡ መካከል ግማሽ ያህሉ ለሥራ ዝግጁ የሆኑ አምራች ኃይሎች መሆናቸውን የሚጠቁመው ሪፖርት፣ ይኼ ቁጥር እ.ኤ.አ. በ2055 ወደ 67.5 በመቶ እንደሚያሻቅብ እንደተተነበየም አመልክቷል፡፡ ይህ ፈጣን ሽግግር ፈጣን ዕድገት ለማምጣት ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው ቢሆንም፣ ለአዳዲስ ሥራ ፈላጊዎች ግን ሥራ ማግኘት ከፍተኛ ተግዳሮት እንደሆነባቸው አስገንዝቧል፡፡ በተጨማሪም በመጪዎቹ አሥር ዓመታት በአገሪቱ ለሥራ ዝግጁ የሆኑ አምራች ኃይሎች ቁጥር በየዓመቱ በሁለት ሚሊዮን እንደሚጨምርና እ.ኤ.አ. በ2025 ዕድሜያቸው ከ15 እስከ 29 ያሉ ወጣቶች ቁጥርም በተመሳሳይ በ8.5 ሚሊዮን እንደሚጨምር ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ በገጠሪቱ የአገሪቱ ክፍል የሚኖሩ ወጣቶች ባላቸው ዝቅተኛ የትምህርት ደረጃ፣ የፆታ እኩልነት ባለመረጋገጡና እየጨመረ በመጣው የመሬት እጥረት የተነሳ በአብዛኛው ክህሎት ለሌለው ወጣቱ የኅብረተሰብ ክፍል የሥራ ዕድል መፍጠርን አዳጋች እንዳደረገውም አክሏል፡፡

የዓለም ባንክ ሪፖርት የግሉ ዘርፍ የተለያዩ ማነቆዎች ስላለበት ሥራ በመፍጠር ረገድ የሚጠበቅበትን ያህል እያገዘ እንደማይገኝ አመልክቷል፡፡ ዘርፉ ከብድር አቅርቦት ውስንነት፣ ከንግድና ሎጂስቲክስ ውጤታማነት፣ ከአቅርቦት ተደራሽነት፣ ከታክስና ግብር አስተዳደር፣ ከሕግ ማዕቀፎች ተገማችነት፣ ጥራትና ጫና፣ ከውጭ ምንዛሪ፣ ከመሬትና ጫና ከሚያሳርፉ የመግቢያ መሥፈርቶች ምክንያት ማነቆዎች እንዳሉበትም ጠቅሷል፡፡

በኢትዮጵያ ለወጣቶች ሥራ ማግኘት አዳጋች መሆኑን ያብራራው ይኼው የዓለም ባንክ ሪፖርት፣ መንግሥት 100 ሺሕ ለሚሆኑ በኢትዮጵያ ለተጠለሉ ስደተኞች በአገር ውስጥ በሚገነቡ የኢንዱስትሪ ፓርኮች የሥራ ዕድል ለመስጠት ማቀዱንም ይጠቅሳል፡፡

በኢትዮጵያ 800 ሺሕ የሚሆኑ የጎረቤት አገሮች ስደተኞች በተለያዩ የአገሪቱ የድንበር አካባቢዎች በተከለሉ ካምፖች ውስጥ ተጠልለው እንደሚገኙ፣ በሰነዱ ያካተተው ሪፖርት ያመለክታል፡፡ እነዚህ ስደተኞች የተወሰነ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን እንዲያገኙ የኢትዮጵያ መንግሥት ቀድሞውንም ቢሆን የፈቀደ እንደነበር በማስታወስ፣ በቀጣይ ግን እነዚህ ስደተኞች ከአካባቢው ማኅበረሰብ ጋር ተዋህደው እንዲኖሩና ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን ለማግኘት እንዲችሉ ዕቅድ መነደፉን ይገልጻል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ዘጠኝ ነጥቦችን የያዘ ዕቅዳቸውን እንዳቀረቡ የዓለም ባንክ ሰነድ የገለጸ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል አሥር በመቶ የሚሆኑት ስደተኞች ቀስ በቀስ ከካምፕ ወጥተው እንዲኖሩ ማድረግ፣ እስከ 100 ሺሕ ስደተኞችን በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በሚገነቡ የኢንዱስትሪ ፓርኮች እንዲቀጠሩ ማድረግ ዋነኞቹ ናቸው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም አሥር ሺሕ ሔክታር የእርሻ መሬት በማቅረብ በእርሻ እንዲተዳደሩ ማድረግ፣ እስከ 213 ሺሕ ለሚደርሱ ስደተኛ ተማሪዎች የትምህርት ዕድል መስጠት፣ ሕጋዊ የሥራ ፈቃድ እንዲያገኙ ማድረግ፣ ከ20 ዓመታት በላይ የኖሩ ሕጋዊ የኢኮኖሚና ማኅበራዊ መስተጋብር እንዲፈጥሩ ማድረግ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ መንግሥትን ዕቅድ ያደነቀ ሲሆን፣ የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግም ዝግጁ መሆኑን ጠቁሟል፡፡

ይሁን እንጂ ሊፈጠሩ ይችላሉ ያላቸውን ሥጋቶቹንም አልሸሸገም፡፡ ከእነዚህም መካከል በአገር ውስጥ ሊኖረው የሚችለው ፖለቲካዊ ተቀባይነት አንዱ ነው፡፡ ሌላው ሥጋት የክልል አስተዳደሮች ምን ያህል ዕቅዱን ተቀብለው ተግባራዊ ያደርጉታል የሚለው ይገኝበታል፡፡

በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ወጣቶቿን በተለይ በከተሞች አካባቢ ሥራ ማስያዝ እንዳልቻለች በአደባባይ የምትናገር አገር፣ ለ100 ሺሕ ስደተኞች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ማቀዷ ለብዙዎች እንቆቅልሽ መሆኑ አልቀረም፡፡ 

Standard (Image)

የአማራ ክልል ወቅታዊ ችግሮችን ለመፍታት የተጋረጡ መሰናክሎች

$
0
0

የአማራ ክልል በፌዴራል ሥርዓቱ ከተዋቀሩ ዘጠኝ ክልሎች መካከል አንዱ ነው፡፡ በውስጡ የጣና ሐይቅን፣ የስሜን ተራራ ብሔራዊ ፓርኮችን፣ የፋሲል ግንብን፣ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትንና ሌሎች ታላላቅ የቱሪስት መስህቦችን አቅፎ የያዘ ነው፡፡ የመልከዓ ምድር አቀማመጡ ሜዳማ እየተባለ የሚጠራ ሲሆን ለእርሻና ሌሎች የልማት ሥራዎች ምቹ እንደሆነ ይነገራል፡፡ በኢትዮጵያ ትልቁ የራስ ዳሽን ተራራ የሚገኝበት ይህ ክልል፣ በምዕራብና በሰሜን ምዕራብ ከሱዳን፣ በሰሜን ከትግራይ፣ በምሥራቅ ከአፋር፣ በምዕራብና ደቡብ ምዕራብ ከቤንሻንጉል ጉሙዝና በደቡብ አቅጣጫ በኩል ደግሞ ከኦሮሚያ ክልሎች ጋር ይዋሰናል፡፡

ይህ አካባቢ በንጉሠ ነገሥቱና በደርግ ዘመናት በተለያዩ አውራጃዎችና ግዛቶች ተከፍሎ የቆየ ሲሆን፣ በአሁኑ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዴሪ) መንግሥት የክልሎች አወቃቀር መሠረት በ11 ዞኖች የተከፋፈለ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ማዕከላዊ ስታትስቲክስ ባለሥልጣን የዛሬ አሥር ዓመት ባወጠው መረጃ መሠረት የክልሉ ሕዝብ ከ17 ሚሊዮን የማይበልጥ የነበረ ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት ከ25 ሚሊዮን በላይ እንደ ደረሰ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ አብዛኛው የክልሉ ሕዝብ የሚኖረው በገጠር ሆኖ ዋነኛ የኢኮኖሚ ምንጩ እርሻ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በከተማ የሚኖረው የክልሉ ሕዝብ ቁጥር 20 ከመቶ በላይ እንዳልዘለለ በቅርብ የወጡ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡

በገጠር የሚኖረው የኅብረተሰብ ክፍል በእርሻ ሥራ የሚተዳደር በመሆኑ መሠረታዊ የሆኑ የንፁህ መጠጥ ውኃ፣ የኃይል፣ የጤናና የትምህርት አቅርቦት ችግሮች በስፋት እንዳሉበት ይነገራል፡፡ ይህን ሥር የሰደደ ችግር ለመፍታት የክልሉ መንግሥት የሚጀማምራቸው ሥራዎች ቢኖሩም፣ ከዳር ደርሰው የሕዝብን ተጨባጭ ችግሮች ከመፍታት አኳያ ብዙ ውስንነቶች እንዳሉ ይገለጻል፡፡

በከተማ የሚኖረው የኅብረተሰብ ክፍል በቁጥር አነሰተኛ እንደሆነ ቢገለጽም፣ እነዚህን መሠረታዊ የሆኑ ፍላጎቶች ከማሟላት አኳያ አሁንም ሰፊ ክፍተቶች እንዳሉ ነዋሪዎች ሲናገሩ ይሰማል፡፡ በክልሉ የተንሰራፉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችና የመሠረተ ልማቶች በበቂ ደረጃ አለመሟላት በክልሉ የሚኖሩ ዜጎችን ለከፍተኛ ጉዳትና እንግልት እየዳረገ እንደሆነ ነዋሪዎች ሲናገሩ ይደመጣል፡፡

በ2008 ዓ.ም. ተቀስቀሶ የነበረው ሁከትና ተቃውሞ በአገር አቀፍ ደረጃ ያደረሰው ጉዳትና ኪሳራ እጅግ ከፍተኛ ቢሆንም፣ በአማራ ክልል በተለይም ከቱሪዝም ዘርፉ ይገኝ የነበረው የገቢ መጠን በእጅጉ ቀንሷል፡፡ ሰሞኑን የክልሉ ምክር ቤት ጉባዔውን በባህር ዳር ሲያካሂድ በጉባዔው ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው እንደተናገሩት፣ ባለፈው ዓመት ተቀስቀሶ በነበረው ሕዝባዊ ተቃውሞ በክልሉ ከነበረው የቱሪዝም ፍሰት ከዚህ በፊት ይገኝ የነበረው ገቢ 53 በመቶ ቀንሷል፡፡

የክልሉ ምክር ቤት አምስተኛ ዙር ሁለተኛ ዓመት የሥራ ዘመን ሰባተኛ መደበኛ ጉባዔውን ሰሞኑን ሲያካሂድ፣ የ11 ወራት የበጀት ሪፖርት ቀርቦ ተገምግሟል፡፡ ጉባዔው በዋናነት በአሁኑ ወቅት ክልሉን በከፍተኛ ደረጃ ሥጋት ላይ በጣሉ ጉዳዮች ላይ የተለየ ትኩረት ሰጥቶ ተወያይቷል፡፡ እነዚህ ጉዳዮችም በክልሉ ተካሂዶ በነበረው የቀን ገቢ ግምት ጥናት፣ እንቦጭ ዓረም በጣና ሐይቅ ላይ እያደረሰ ስላለው ጉዳት፣ አደገኛና ሁሉን አውዳሚ ስለሆነው ተምችና በክልሉ ስላለው የኃይል አቅርቦት ችግሮች ውይይት ተደርጓል፡፡

የክልሉ ምክር ቤት አባላት በክልሉ ውስጥ ስለሚከናወኑ ሥራዎች ሁሉን አቀፍ የሆነ ጥያቄና አስተያየት ሲያቀርቡ ነበር፡፡ ብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) ብቻ በተቆጣጠረው በዚህ ምክር ቤት እጅግ የመንግሥትን ኋላ ቀር የአሠራር ሥርዓት የሚተቹ የምክር ቤት አባላት እንደነበሩ መታዘብ ተችሏል፡፡ የክልሉን መንግሥት የሚተቹ፣ የሚሞግቱ፣ የሚቃወሙና የሚደግፉ አስተያቶችና ጥያቄዎች ሲሰነዘሩ ነበር፡፡

በክልሉ ለረጅም ዓመታት ሲንከባለል የመጣና አሁንም ድረስ ሊፈታ ያልቻለው አንዱ የኃይል አቅርቦት ሲሆን፣ በክልሉ ያለው የኃይል አቅርቦት እጅግ ከማነሱ የተነሳ መለስተኛ ፋብሪካዎች እንኳ ሥራቸውን በማቆም ላይ እንደሆኑ እየተነገረ ነው፡፡ በዚህ ችግር የተነሳ በርካታ የክልሉ ነዋሪዎች በልተው ማደር እንኳ እንዳልቻሉ ተገልጿል፡፡

በፍኖተ ሰላም ከተማ ነዋሪ የሆኑት አቶ ቢያድግልኝ ጫኔ (የአባታቸው ስም ተቀይሯል) የእህል ወፍጮ ያላቸው ሲሆን ከአምስት ዓመት በላይ ኃይል የሚለቀቅላቸው በፈረቃ እንደሆነ ለሪፖርተር በስልክ ተናግረዋል፡፡ ከሳምንት ሁለት ቀናት ብቻ ኃይል እንደሚመጣላቸውና በእነዚህ ቀናት ብቻ እንደሚፈጩ ገልጸዋል፡፡ ‹‹በእነዚህ ቀናት ብቻ እየሠራን እንዴት ነው መኖር የምንችለው? እንዴትስ ነው መንግሥት በአሁኑ ጊዜ አደግንና ተለውጠን የሚለው? በምንስ ሁኔታ ነው ለክልላችን ብሎም ለአገራችን አስተዋጽኦ የምናደርገው?›› በማለት አስተያየታቸውን በቅሬታ አቅርበዋል፡፡

በክልሉ ያለው የኃይል አቅርቦት ባለመፈታቱ ምክንያት የተለያዩ ኢንቨስተሮችና ባለሀብቶች ወደ ክልሉ ገብተው ኢንቨስት ለማድረግ እንዳልቻሉ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ በ2009 ዓ.ም. ብቻ ከ1,700 በላይ ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ቢወስዱም፣ በኃይል አቅርቦት ችግር የተነሳ አብዛኛዎቹ ወደ ሥራ መግባት እንዳልቻሉ የክልሉ የኢንቨስትመንት ኮሚሽን ባለሙያዎች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በክልሉ ከ20 የማይበልጡ ማከፋፈያዎች እንዳሉ የሚታወቅ ሲሆን፣ እነዚህ ማከፋፈያዎች የተገነቡት ከዛሬ ዘጠኝና አሥር ዓመት በፊት እንደሆነ ሲነገር ተደምጧል፡፡ እነዚህ ማከፋፈያዎች በአሁኑ ጊዜ ሌላ ኃይል መሸከም ስለማይችሉ በክልሉ የኢንዱስትሪዎችንና የፋብሪካዎችን መስፋፋት የገታ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

አገሪቱ የኤሌክትሪክ ኃይል ለጎረቤት አገሮች በመሸጥ ላይ ብትሆንም፣ በአገር ውስጥ ያሉ ክልሎች በዚህ ችግር ከፍተኛ እየተመቱና ለማደግ በሚያደርጉት ጥረት እንቅፋት እየሆነባቸው መምጣቱን ባለሙያዎች እየተናገሩ ነው፡፡ በክልሉ ከመቶ የማይበልጡ ከአነስተኛ እስከ ከፍተኛ የሚደርሱ ፋብሪካዎች እንዲገነቡ ታቅዶ ባለሀብቶችም ፍላጎት እንዳላቸው ያሳዩ ቢሆንም፣ ወደ ተግባር ለመግባት እንቅስቃሴ እንዳልተጀመረ እየተነገረ ነው፡፡ አሁን ያለው የኃይል አቅርቦት ከሕዝቡ ፍላጎት ጋር እጅግ የማይጠጣም መሆኑ ተገልጿል፡፡

በዚህም የተነሳ ከዚህ በፊት መለስተኛ ፋብሪካ ከፍተው ሥራ የጀመሩ መለስተኛ ባለሀብቶች ከፍተኛ የሆነ ኪሳራ እየደረሰባቸው መሆኑን፣ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የክልሉ ነዋሪዎች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ከክልሉ ምክር ቤት መደበኛ ጉባዔ ለመረዳት እንደተቻለው፣ በክልሉ ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎች የክልሉን ሕዝብ በመለወጥ በኩል ያላቸው ሚና እስካሁን ዝቅተኛ ነው፡፡ ምንም እንኳ የክልሉ ምክር ቤት ሙሉ በሙሉ በብአዴን የተያዘ ቢሆንም፣ የተለያዩ ሐሳቦች ሲንሸራሸሩ ከወሬ ያለፈ ተጨባጭ ሥራ በማከናወን በክልሉ ውስጥ የተጋረጠውን ችግር በቁርጠኝነት መፍታት ተገቢ እንደሆነ ከርር ያሉ አስተያቶች ተደምጠዋል፡፡

በክልሉ አሳሳቢ የሆነውን የኤለክትሪክ ችግር ለመፍታት ሰሞኑን የኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አዜብ አስናቀን (ኢንጅነር) ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ ኃላፊዎች በተገኙበት ከአማራ ክልል ከተውጣጡ ባለሀብቶች፣ ከሥራ ኃላፊዎችና ከዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች ጋር የውይይት መድረክ ተዘጋጅቶ እንደነበር የሪፖርተር ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ምንጮች እንደገለጹት፣ በአገር አቀፍ ደረጃ የኤሌክትሪክ አቅምን ለማሳደግ በርካታ ውጤታማ ሥራዎች እየተከናወኑ ቢሆንም፣ ለጎረቤት አገሮች ጭምር በመሸጥ የውጭ ምንዛሪ ማግኘት ቢጀመርም፣ ከዚህ ዘርፍ ክልሉ ተጠቃሚ እንዳልሆነ በመድረኩ ተገልጿል፡፡

ባለፉት አሥር ዓመታት አንድም የኃይል ማከፋፈያ በክልሉ ባለመሠራቱና ከዚህ ቀደም የነበሩት የኃይል ማከፋፈያዎች ኃይል የመሸከም አቅማቸው ዝቅተኛ ስለሀሆነ ችግር እየተፈጠረ መሆኑን የክልሉ ምክር ቤት ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ለጣና በለስ ኃይል ማመንጫ ማሳቸውን የሰጡ የኅብረተሰብ ክፍሎች ሻይ አፍልተው መጠጣት እንኴ እንዳልቻሉ ለኃላፊዎች አስረድተዋል፡፡ በክልሉ ውስጥ ስኬታማ የኢንዱስትሪ ልማት የማይታይበትም አንዱ ምክንያት ይህ እንደሆነ  ተገልጿል፡፡

በክልሉ ያለው የኃይል አቅርቦት ችግር ከክልሉ አቅም በላይ እንደሆነና መሠረተ ልማቶችን ለማከናወን እንቅፋት መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ ይህንን ችግር ለመፍታት የፌዴራሉ መንግሥት መጠየቁንና መቼ ምላሽ እንደሚሰጥ ግን አይታወቅም ተብሏል፡፡

በዘንድሮው ጉባዔ ትኩረት ከተሰጣው ጉዳዮች መካከል በክልሉ ተካሂዶ የነበረው የቀን ገቢ ግምት ጥናትና ከዚህ ጋር ተያይዞ የመጣውን የሕዝብ ቅሬታ የተመለከተ ነው፡፡

ዘንድሮ በአገሪቱ በተካሄደው የቀን ገቢ ግምት ጥናት መሠረት ከ100 ሺሕ የሚበልጡ ነጋዴዎችን ወደ ታክስ ሥርዓቱ ማስገባት እንደተቻለ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በአማራ ክልልም በተካሄደው የቀን ገቢ ግምት ጥናት በዚህ ዓመት ከ30 ሺሕ በላይ ነጋዴዎች ወደ ታክስ ሥርዓቱ እንዲገቡ መደረጉን ምንጮች ቢጠቀሙም፣ ግመታው የተጋነነና የነጋዴዎችን የዕለት ገቢ በትክክል መሠረት ያደረገ አይደለም ተብሎ የተለያዩ ቅሬታዎች እየተደመጡ ነው፡፡

 ለአብነት ያህል ዘንድሮ በኦሮሚያ ክልል ከ46 ሺሕ በላይ ነጋዴዎች ወደ ታክስ ሥርዓቱ እንዲገቡ የተደረገ ሲሆን፣ ባለፈው ሐሙስ ሐምሌ 6 ቀን 2009 ዓ.ም. በተነሳው የሕዝብ ቅሬታና ተቃውሞ በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱ ይታወሳል፡፡

በአማራ ክልልም እነዚህ ዓይነት ጥያቄዎች ከየአቅጣጫው እየተነሱ ሲሆን፣ የክልሉ መንግሥት ይህንን ችግር ለመፍታት ከላይ ታች ሲል ተስተውሏል፡፡ ጉዳዩ ወቅታዊና አንገብጋቢ ከመሆኑ አንፃር የክልሉ ምክር ቤትም በስፋት ተወያያቶበታል፡፡ የክልሉ ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መሐመድ አብዱ፣ ‹‹በክልሉ ያሉ መሠረት ልማቶችን ከግብ ለማድረስ ገቢ መሰብሰብ ግድ ይላል፡፡ በዚህም በክልሉ የቀን ገቢ ግምት ጥናት ተግባራዊ ሆኗል፡፡ ይሁን እንጂ አንዳንድ ነጋዴዎች ግብር በዛብን እያሉ ጥያቄ ሲያነሱ፣ ይኼንን አጋጣሚ ተጠቅመው የሚያጯጩሁ ኃይሎች አሉ፤›› ብለዋል፡፡

የክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ ይርሳው ታምሬ ለሪፖርተር በስልክ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ በአሁኑ ወቅት በነጋዴዎች ላይ ያላግባብ ተጣለ የተባለውን ግብር የክልሉ መንግሥት በጥንቃቄ መፍታት እንዳለበት በጉባዔው መወሰኑን ገልጸዋል፡፡ ቅሬታ ካለ ቅሬታውን በመስማትና ችግሮችን በመፍታት ነጋዴዎች ተገቢውን ግብር ብቻ መክፈል እንዳለባቸው በምክር ቤቱ መወሰኑን፣ ለዚህም የክልሉ መንግሥት የተለየ ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንዳለበት ስምምነት ላይ መደረሱን አቶ ይርሳው አስረድተዋል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ የክልሉ ምክር ቤት ትኩረት ሰጥቶ ከተወያየባቸው መካከል ሌላው ጉዳይ ደግሞ፣ መጤ የሆነው የእንቦጭ ዓረም በጣና ሐይቅ ላይ እያደረሰ ስላለው ጉዳት ነው፡፡ የእንቦጭ አረም በአሁኑ ወቅት ከ50 ሺሕ ሔክታር በላይ ስፋት ያለውን የጣና ሐይቅ እንደሸፈነና የውኃውን መጠን እንደቀነሰ ይነገራል፡፡ የእንቦጭ አረም በባህሪው የውኃ ትነትን በእጥፍ የሚጨምርና ውኃን በቶሎ የሚያደርቅ እንደሆነ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡

በአሁኑ ወቅት ችግሩን ለመከላከል በባህር ዳርና በጎንደር ዩኒቨርሲቲዎች የተለያዩ ሙከራዎችና ጥረቶች እየተደረጉ ቢሆንም፣ ከጊዜ ወደ ጣናን የታደገው አካል እንደሌለ እየተገለጸ ነው፡፡ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ችግሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ እጅግ አሳሳቢ በሆነ ሁኔታ እየጨመረና እየተስፋፋ ነው፡፡ የምሁራኑ አስተያየትና በአካባቢው ያለው ተጨባጭ ሁኔታ ይኼ ቢሆንም የክልሉ የአካባቢ ጥበቃ፣ ደንና የዱር እንስሳት ቢሮ ኃላፊ በላይነህ አየለ (ዶ/ር) ለክልሉ ምክር ቤት ባቀረቡት ሪፖርት፣ ጣና ሐይቅ በእንቦጭ አረም የተወረረበት መጠኑ ካለፈው ዓመት የበለጠ አየደለም ብለዋል፡፡ እንደ ዶ/ር በላይነህ ገለጻ፣ ጣና ሐይቅ ሀብትነቱ የአማራ ክልል ብቻ ሳይሆን የምሥራቅ አፍሪካ እንደሆነና ሐይቁን ከሚፈታተኑ ለመጠበቅ ችላ እንደማይባል አስረድተዋል፡፡ ይሁን እንጂ ልዩ አጀንዳ ያላቸው ወገኖች መነጋገሪያ እያደረጉት ነው ብለዋል፡፡

የክልሉ መንግሥት በጣና ሐይቅ ዙሪያ የሚገኙ አምስት ወረዳዎችን በማነቃነቅ በእንቦጭ አረም የተወረረውን 21 ሺሕ ሔክታር ስፋት ካለው የሐይቁ አካል በሕዝብ ንቅናቄ ለማስወገድ እንደተቻለ ተናግረዋል፡፡

 የክልሉ አፈ ጉባዔ አቶ ይርሳው ይኼ ችግር ከተከሰተ ዕለት ጀምሮ የክልሉ መንግሥት እየጣረ መሆኑን ለሪፖርተር ገልጸው፣ በአሁኑ ጊዜ የተለያዩ ኮሚቴዎች ተቋቁመው ችግሩን ለመከላከል እየተሠራ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ መንግሥት ችግሩ ከተከሰተ ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ ትኩረት ሰጥቶ ከሠራ የመስፋፋት ዕድል እንዴት አገኘ? የሚል ጥያቄ ከሪፖርተር ቀርቦላቸው በሰጡት ምላሽ፣ የክልሉ ምክር ቤት በዚህ ላይ እንዳልተወያየ ለዚህ ምክንያቱ ምን እንደሆነ ግልጽ የሆነ መረጃ የለኝም ብለዋል፡፡

የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በዚግ ጉዳይ ላይ ለምክር ቤቱ አባላት በሰጡት ምላሽ፣ ጣና ሐይቅ የክልሉን ቅርስ አቅፎ የያዘና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው የጎላ ነው ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ አረም ሐይቁ ክፉኛ እየተጎዳ መሆኑን አስረድተው፣ አረሙን ሙሉ በመሉ በክልሉ አቅም ማስወገድ አለመቻሉን ተናግረዋል፡፡

የጣና ሐይቅ መጤ በሆነው የእንቦጭ አረም ክፉኛ እየተጎዳና አፋጣኝ መፍትሔ እየተሰጠው እንዳልሆነ በተለያዩ የመረጃ ምንጮች ቢገለጽም፣ እስካሁን ድረስ የፌዴራሉ መንግሥትና የክልሉ መንግሥት በቅንጅት ሆነው በመሥራት ረገድ የቁርጠኝነት ማነስ እንደሚታይባቸው እየተገለጸ ነው፡፡ ይኼ አረም በተፈጥሮው እጅግ ከባድና በቀላሉ ሊወገድ የሚችል ባለመሆኑ ዛሬ ነገ ሳይባል የመፍትሔ ዕርምጃ እንዲወሰድ እየተጎተጎተ ነው፡፡

ምክር ቤቱ በአራተኛ ደረጃ ትኩረት ከሰጣቸው ጉዳዮች ሌላው ሁሉን አውዳሚ ሰለሆነው ተምች ነው፡፡ ባለፉት ሁለትና ሦስት ወራት በክልሉ በተለይም በምዕራብ አካባቢ ያደረሰው ጉዳት እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ በጉባዔው ተጠቅሷል፡፡ የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ አይተነው እንዳሻው ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ማብራሪያ፣ ‹‹ሁሉን አውዳሚ የሆነው ተምች በክልሉ በ57 ወረዳዎችና በ715 ቀበሌዎች የተከሰተ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት በቁጥጥር ሥር ውሏል፤›› ብለዋል፡፡ አቶ አይተነው ይኼን ይበሉ እንጂ፣ በምዕራብ ጎጃም በተወሰኑ አካባቢዎች አሁንም ድረስ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ነዋሪዎች እየተናገሩ ነው፡፡

 አቶ ይርሳው በበኩላቸው ጉባዔው ይኼንን ጉዳይ ትኩረት ሰጥቶ መነጋገሩን  ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅት በተወሰኑ የመንግሥት አመራሮችና ባለሙያዎች ዘንድ መዘናጋት እየተፈጠረ መሆኑን ምክር ቤቱ እንደገመገመ አስረድተዋል፡፡

‹‹ክረምቱ በመግባቱ ዝናብ እየዘነበ ቢሆንም፣ ተምቹ ሙሉ በሙሉ እስኪጠፋና በክልሉ ባለሙያዎች እስኪረጋገጠ ድረስ ባለመዘናጋት መሥራት እንደሚገባ ምክር ቤቱ ስምምነት ላይ ደርሷል፤›› ብለዋል፡፡ አቶ ገዱ በበኩላቸው፣ ‹‹ይኼ ሁሉን አውዳሚ መጤ ተምች በቀን ከ200 እስከ 250 ኪሎ ሜትሮች የሚጓዝ ፈጣን ፀረ ሰብል ተባይ በመሆኑ በትኩረት ሊሠራ ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

በአማራ ክልል ውስጥ የኅብረተሰብ በርካታ ፍላጎቶች ሲኖሩ፣ እነዚህን ፍላጎቶች መሠረት አድርጎ መፍትሔ ከመስጠት አኳያ ውስንነቶች እንዳሉ እየተገለጸ ነው፡፡ ከወጣቶች ሥራ አጥነትና ሌሎች ጉዳዮች ጋር ተያይዞ በክልሉ ከፍተኛ የሆነ ውድመት ተከስቶ እንደነበር ይታወሳል፡፡

ከዚህ አገር አቀፍ ረብሻና ሁከት በኋላ የፌዴራሉ መንግሥት የክልል መንግሥታትን ጨምሮ በጥልቅ ውስጥ ተሃድሶ በማለፍ የሕዝብን ጥያቄ መመለስ ተገቢ እንደሆነ አቅጣጫ ያቀመጡ ቢሆንም፣ በክልሉ ያሉ መሠረታዊ ችግሮችን በአፋጣኝና በተቀላጠፈ ሁኔታ መፍታት እንዳልተቻለ የክልሉ ነዋሪዎች እየገለጹ ነው፡፡ በክልሉ ለተንሰራፋው ሁለንተናዊ ችግር በይዋል ይደር ምክንያት ሕዝቡ ከፍተኛ የሆነ ቅሬታ ሲያሰማ ተደምጧል፡፡

 

Standard (Image)

ተቃውሞ የቀሰቀሰው የቁርጥ ግብር ከፋዮች አቤቱታ

$
0
0

 

የፌዴራል መንግሥት የአገሪቱ ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ በይበልጥ ለመሰብሰብ ባለፈው ዓመት አዋጅ ቁጥር 929/2008 አውጥቷል፡፡ ዘጠኙ ክልሎችና ሁለቱ የከተማ አስተዳደሮችም ከራሳቸው ነባራዊ ሁኔታ በመነሳት፣ ይህ አዋጅ በሚፈቅደው መሠረት ገቢያቸውን ለመሰብሰብ ካለፈው ወር ጀምሮ በሰፊው መንቀሳቀስ ጀምረዋል፡፡

አዋጅ ቁጥር 929/2008 ቀደም ሲል ሲሠራበት የቆየውን የግብር ከፋዮች ደረጃ ቀይሮታል፡፡ ቀደም ሲል ደረጃ ‹‹ሀ›› ግብር ከፍዮች ከ500 ሺሕ ብር በላይ፣ አሁን በተቀየረው አሠራር ደግሞ ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ሆኖ ተመድቧል፡፡ ቀደም ሲል ደረጃ ‹‹ለ›› ከ100 ሺሕ እስከ 500 ሺሕ ብር በላይ ነበር፡፡ አሁን ባለው አሠራር ከ500 ሺሕ እስከ አንድ ሚሊዮን ብር ድረስ ሆኖ ተመድቧል፡፡ አወዛጋቢው ደረጃ ‹‹ሐ›› ቀደም ሲል እስከ አንድ መቶ ሺሕ ብር ድረስ ሽያጭ ያላቸው የሚመደቡበት ነበር፡፡ አሁን ባለው አሠራር የደረጃ ‹‹ሐ›› ቁርጥ ግብር ከፋዮች እስከ 500 ሺሕ ብር ድረስ ሽያጭ ያከናውናሉ ተብሏል፡፡

ይህ አዋጅ መነሻ ተደርጎ ከሚያዝያ እስከ ግንቦት ወር 2009 ዓ.ም. ድረስ በደረጃ ‹‹ሐ›› ግብር ከፋዮች የዕለት ገቢ ቅኝት ሲካሄድ ቆይቶ፣ ሰሞኑን ውጤቱ ለእያንዳንዱ ነጋዴ ተገልጿል፡፡

በዚህ ወቅት በአገሪቱ የሚገኙ አብዛኞቹ ነጋዴዎች ቅሬታ በማሰማት ላይ ናቸው፡፡ ይህ ቅሬታ በኦሮሚያ ክልል በአምቦ፣ በወሊሶ፣ በጊንጪና በሌሎች ከተሞች ግጭት እስከ መቀስቀስ ድረስ ዘልቋል፡፡

የአነስተኛ ነጋዴዎችን ቅሬታ በተገቢው ለመግለጽ ያህል በአዲስ አበባ ጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ የቁርጥ ግብር ምጣኔ ከተገለጸላቸው 927 አነስተኛ ነጋዴዎች መካከል፣ ከ700 በላይ የሚሆኑት ቅሬታ ማቅረባቸውን የወረዳው ገቢዎች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ከበደ ጫኔ ከሪፖርተር ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፣ በአዲስ አበባ ጥናት የተካሄደባቸው 148 ሺሕ አነስተኛ ነጋዴዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 47 ሺሕ የሚሆኑት ቅሬታ አቅርበዋል፡፡ ከመቶ ሺሕ በላይ የሚሆኑት የሚያቀርቡት ቅሬታ ቢኖራቸውም፣ ግምቱ ተቀራራቢ መሆኑን በመረዳት ግምቱን መቀበላቸው ተገልጿል፡፡

በደረጃ ‹‹ሐ›› ሥር የተደለደሉ ቁርጥ ግብር ከፋዮች የግብር አተማመን ሒደቱ በትክክለኛ መረጃ ላይ ያልተመሠረተ መሆኑን እየገለጹ ይገኛሉ፡፡

ከእነዚህ ውስጥ በአዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ የሚገኙት አቶ አሰፋ መኮንን፣ በኦሮሚያ ክልል አምቦ ከተማ የሚገኙት ወ/ሮ ጌጤ ፈይሳና በአማራ ክልል ምዕራብ ጎጃም ዞን የሚገኙት አቶ ፈቃዱ ዘገዬ ይገኙበታል፡፡

የወ/ሮ ጌጤና የአቶ ፈቃዱ ስም ለደኅንነታቸው ሲባል የተየቀረ ነው፡፡ አቶ አሰፋ መኮንን ለረዥም ዓመታት በውጭ አገር ሲኖሩ ቆይተው ወደ አገራቸው የተመለሱ ናቸው፡፡ እኚህ ግለሰብ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 ሃና ማርያም አካባቢ ‹‹ሕገወጥ›› የተባሉ ቤቶች ሲፈርሱ የእሳቸውም አብሮ ፈርሷል፡፡

በዚህ ምክንያት ለችግር የተዳረጉት አቶ አሰፋ፣ ከዘመድ በመጠጋት ቦሌ ቡልቡላ አካባቢ አነስተኛ የመጠጥ ግሮሰሪ ከፍተው በመሥራት ላይ እንደነበሩ ይናገራሉ፡፡ አቶ መኮንን ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የቀን ገቢየቸው እስከ 240 ብር ድረስ እንደሆነ አሳውቀው ነበር፡፡ ነገር ግን የክፍለ ከተማው ገቢዎች ጽሕፈት ቤት ያሳወቃቸው የቀን ገቢ ግምት 2,000 ብር እንደሆነ ነው፡፡

ይህን ያህል ገቢ በፍፁም ሊያገኙ እንደማይችሉና ተመኑ በዚህ ከፀና ሕይወታቸው የተመሰቃቀለ እንደሚሆን አቶ አሰፋ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በቁርጥ ግብር ምክንያት ግጭት በነበረበት አምቦ ከተማ ውስጥ በአነስተኛ ንግድ የሚተዳደሩት ወ/ሮ ጌጤም መረር ያለ ቅሬታ አላቸው፡፡

ወ/ሮ ጌጤ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የተሰማሩበት የንግድ ሥራ በለስላሳ መጠጦችና በቡና ችርቻሮ ነው፡፡ በዚህ ንግድ ሥራ በቀን ከ250 ብር እስከ 300 ብር ድረስ እንደሚያገኙ የተናገሩት ወ/ሮ ጌጤ፣ ነገር ግን የገቢዎች ጽሕፈት ቤት በቀን 4,500 ብር ሽያጭ እንደሚያከናውኑ አድርጎ አሳውቋቸዋል፡፡

‹‹እኔ በቀን ይህን ያህል ገንዘብ ሠርቼ አላውቅም፤›› በማለት ግምቱ ጭራሽ ለእውነታ ቅርብ እንዳልሆነ አብራርተዋል፡፡ አቶ ፈቃዱም ተመሳሳይ ሐሳብ አላቸው፡፡ አቶ ፈቃዱ በሚኖሩበት ቡሬ ከተማ በሸቀጣ ሸቀጥ መደብር ይተዳደራሉ፡፡ አቶ ፈቃዱ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በቀን ቢበዛ እስከ 800 ብር ድረስ ይሠራሉ፡፡ ይህንንም ለመንግሥት አሳውቀዋል፡፡ ነገር ግን የቡሬ ከተማ ገቢዎች ጽሕፈት ቤት 1,600 ብር በቀን እንደሚሠሩ አድርጎ ግምት ጥሎባቸዋል፡፡

‹‹ይህን ያህል ገንዘብ በቀን መሥራት የሚያስችል መደብር የለኝም፤›› ሲሉ አቶ ፈቃዱ ይናገራሉ፡፡ አዲሱ ግምት በተጨባጭ ሁኔታ ላይ ያልተመሠረተ፣ ከደረጃ ‹‹ሐ›› ወደ ደረጃ ‹‹ለ›› የሚያሸጋግራቸው በመሆኑ በኋላ ምን ሊመጣ እንደሚችል መገመት እንዳልቻሉ እነዚህ አነስተኛ ነጋዴዎች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ መንግሥት የአገሪቱ ኢኮኖሚ ከራስ አቅም በሚሰበሰብ ገቢ ላይ እንዲመሠረት ይፈልጋል፡፡ ለቀጣዩ 2010 ዓ.ም. ከተያዘው 320.8 ቢሊዮን ብር በጀት ውስጥ 190 ቢሊዮን የሚሆነው ከአገር ውስጥ ምንጮች እንዲሰበሰብ ታሳቢ ተደርጓል፡፡ ክልሎችም በአብዛኛው የሚይዙት በጀት ከራስ ገቢ ሳይሆን በፌዴራል መንግሥት ድጎማ ላይ የተንጠለጠለ በመሆኑ፣ ከዚህ በኋላ ባሉት ዓመታት የራሳቸውን ገቢ እስከ መጨረሻው ጥግ መሰብሰብ እንዳለባቸው ከየምክር ቤታቸው ጋር መተማመን ላይ ደርሰዋል፡፡  

የፌዴራል መንግሥት ለበጀት ዓመቱ ከያዘው በጀት ውስጥ የአንበሳውን ድርሻ የሚይዘው የክልሎች ድጎማ ነው፡፡ ክልሎች 117 ቢሊዮን ብር በድጎማ፣ ሰባት ቢሊዮን ብር ደግሞ ለድህነት ቅነሳ ፕሮግራሞች ተመድቦላቸዋል (የ2010 ዓ.ም. ድጎማ አዲስ አበባ ከተማንም ይጨምራል)፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በዓመት 40 ቢሊዮን ብር የማመንጨት አቅም ላይ መድረሱን ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ ነገር ግን በ2008 ዓ.ም. የተሰበሰበው 22.1 ቢሊዮን ብር ብቻ ሲሆን፣ በ2009 ዓ.ም. 11 ወራት ውስጥ 31.5 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ፣ የተሰበሰበው ግን 26.5 ቢሊዮን ብር ብቻ ነው፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከተማው የሚፈልገውን አገልግሎት በይበልጥ ለማሳካት የከተማው ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን በሙሉ የመሰብሰብ ፍላጎት አለው፡፡ ይህንንም ለማሳካት በቀድሞው ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ ጊዜ የከተማው ገቢዎች ባለሥልጣን፣ በፌዴራል ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሥር እንዲታቀፍ ተደርጓል፡፡

በእርግጥ ከዚህ ወቅት ጀምሮ የከተማው ገቢ የመሰብሰብ አቅም ያደገ ቢሆንም፣ የአሁኑ ከንቲባ ድሪባ ኩማ ከዚህም በላይ እንዲያድግ ይፈልጋሉ፡፡ እንደ ሌሎቹ ሁሉ በአዲስ አበባ ከተማም ለሚካሄደው ልማት የፋይናንስ መሠረት ከግብር የሚሰበሰበው ገቢ ነው፡፡ በዚህ መሠረትም በ2003 ዓ.ም. ላይ የቆመውን የቀን ገቢ ግምት፣ እንደ አዲስ ከስድስት ዓመት በኋላ ለማንቀሳቀስ ተሞክሯል፡፡

በአማራ ክልልም በተመሳሳይ የክልሉን ገቢ በይበልጥ ለመሰብሰብ ታቅዷል፡፡ የክልሉ ምክር ቤት ባለፈው ሳምንት ባካሄደው ስብሰባ ክልሉ ለ2009 ዓ.ም. ከያዘው 32 ቢሊዮን ብር ውስጥ ከራስ ምንጮች መሰብሰብ የቻለው 8.5 ቢሊዮን ብቻ ነው፡፡ የክልሉ ፋይናንስና ኢኮኖሚ ቢሮ ኃላፊ ለምክር ቤት አባላት እንዳብራሩት፣ መሰብሰብ የተቻለው የበጀቱን 20 በመቶ ያህል ብቻ ነው፡፡ ይህንን ማሳደግ እንደሚያስፈልግ አበክረው ተናግረዋል፡፡

የአማራ ክልል ምክር ቤት ለቀጣዩ 2010 በጀት ዓመት 37.6 ቢሊዮን ብር በጀት አፅድቋል፡፡ የኦሮሚያ ክልልም እንዲሁ የክልሉ የወጪ ፍላጎት 56 ቢሊዮን ብር ቢሆንም፣ ከግብር የሚገኘው ግን ከአሥር ቢሊዮን ብር እንደማይበልጥ የኦሮሚያ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ አዲሱ አረጋ ለጋዜጠኞች ገልጸዋል፡፡ ይህንንም ለማሻሻል የተጀመረው የገቢ ግብር ግምት ግጭት የተስተናገደበት ሲሆን፣ አቶ አዲሱ በዕለት ገቢ ግምት ላይ የሚቀርቡ ቅሬታዎች በሰላማዊ መንገድ እንዲቀርቡ ማሳሰቢያ ሰጥተዋል፡፡

‹‹ከገቢ ግምት ጋር ተያይዞ የተነሳውን ቅሬታ ምክንያት በማድረግ፣ ሌላ ዓላማ ይዞ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት መሞከር ፍፁም ተቀባይነት የለውም፤›› ያሉት አቶ አዲሱ፣ ክልሉ ይህንን እንደማይታገስ አጥብቀው አስታውቀዋል፡፡ የቁርጥ ግብር ተመን ይፋ ከተደረገ በኋላ በኦሮሚያ ክልል አምቦ፣ ወሊሶና ጊንጪ ከተሞች አመፅ የተቀሰቀሰ ሲሆን፣ በእነዚህ ከተሞች የተወሰኑ ተሽከርካሪዎች መሰባበራቸውና መቃጠላቸው ተገልጿል፡፡ ሱቆችም እንዲሁ ተዘግተው የዋሉባቸው ጊዜያት መኖራቸው፣ እንዲሁም በቡሌ ሆራ (ሀገረ ማርያም) አመፅ ቀስቃሽ ጽሑፎች እየተበተኑ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳ ዓርብ ሐምሌ 14 ቀን 2004 ዓ.ም. ከወሊሶና ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር ውይይት አድርገው ነበር፡፡ የክልሉ መንግሥት የተጣለበትን ኃላፊነት በመወጣት የሕዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ያለዕረፍት እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በውይይቱ ላይ የተገኙት ነዋሪዎች መንግሥት ግብር መሰብሰብ እንዳለበት፣ ነገር ግን የቀን ገቢ ግምቱ ፍትሐዊነት የጎደለው እንደሆነ ነግረዋቸዋል፡፡ አቶ ለማ በሰጡት ምላሽ ተጋነነ የተባለው የዕለት ገቢ ግምት በመተማመን እንደሚፈታ፣ የሚቀርቡ ቅሬታዎችም እንደሚጣሩ ገልጸዋል፡፡ ነጋዴዎችም በአቅማቸው መጠን ለመንግሥት ግብር መክፈል እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡ እስከ ሰኔ 30 ቀን የነበረው ክፍያም እስከ ሐምሌ 15 ቀን ያለቅጣት መደረጉንና ነጋዴዎችም በጊዜው ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

የደቡብ ክልልም በቀጣዩ በጀት 10.23 ቢሊዮን ብር ከራሱ ምንጮች ለመሰብሰብ ማቀዱም ባለፈው ሳምንት መጨረሻ በተካሄደው የምክር ቤት ስብሰባ ላይ ተገልጿል፡፡ ይህም ተግባራዊ የሚሆነው በሦስቱም ደረጃዎች ከሚገኙ 183,136 ግብር ከፋዮች መሆኑን የክልሉ ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሤ አስረስ በስብሰባው ላይ ተናግረዋል፡፡ በአጠቃላይ ክልሎች የወጪ ፍላጎታቸው እስከ 60 ቢሊዮን ብር የሚደርስ ቢሆንም፣ በአብዛኛው የበጀታቸው ምንጭ የፌዴራል መንግሥት ድጎማ ነው፡፡ ከራሳቸው የገቢ ምንጭ የሚያሰባስቡት ከ20 በመቶ እንደማይበልጥ በተደጋጋሚ እየገለጹ ይገኛሉ፡፡

ማክሰኞ ሐምሌ 11 ቀን 2009 ዓ.ም. ለጋዜጠኞች መግለጫ የሰጡት የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትሩ አብርሃም ተከስተ (ዶ/ር) ለሪፖርተር ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ ክልሎች በድጎማ ብቻ ልማታቸውን ማካሄድ አይችሉም፡፡ የራሳቸውን ገቢም አሟጠው መሰብሰብ አለባቸው፡፡ ሚኒስቴሩም ድጋፍ ያደርግላቸዋል ብለዋል፡፡ ‹‹ክልሎች ገቢያቸውን አሟጠው ለመሰብሰብ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ጥሩ ምልክት እያሳየ ነው፡፡ ክልሎች ወጪያቸው በጣም እየጨመረ ነው፡፡ የፌዴራል መንግሥት ድጎማ የወጪ ፍላጎታቸውን ማርካታ እንደማይቻል ተገንዝበዋል፤›› ሲሉ ዶ/ር አብርሃ ክልሎች ገቢያቸውን በቁርጠኝነት ለመሰብሰብ መነሳታቸውን ገልጸዋል፡፡

ግብር የመክፈል ግዴታ እንዳለባቸው አብዛኞቹ አነስተኛ ነጋዴዎች የሚያምኑ ቢሆንም፣ የገቢ መሥሪያ ቤቶች ግምት በሚያካሂዱበት ወቅት የመደብሮችን መረጃ አጣርቶ አለመለየት፣ ተመሳሳይ ለሆኑ መደብሮች የተለያየ ግመታ ማካሄድ፣ አጋኖና አሳንሶ መገመት ዋነኞቹ ችግሮች መሆናቸውን ነጋዴዎቹ እየተናገሩ ነው፡፡

የቅሬታ ሰንሰለቱ ረዥምና ቅሬታ ተሰማ ከተባለም ከእውነታው ጋር ያልተቀራረበ ማስተካከያ ማድረግ ተጠቃሾች ችግሮች ሆነው ቀርበዋል፡፡ የገቢ መሥሪያ ቤት የሥራ ኃላፊዎች ቅሬታ እየቀረበ ባለበት ወቅት ጉዳዩን ለማስረዳት ታች ላይ እያሉ ይገኛሉ፡፡ ግብር ከፋዩ ኅብረተሰብ አካባቢም ችግር እንዳለ መንግሥት እየገለጸ ነው፡፡ ከችግሮቹ መካከልም ግምት በሚከናወንበት ወቅት ዕቃ ማሸሽ፣ መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆን፣ መረጃ አሳንሶ መስጠት፣ ውክልና የሌለው ሰው በመደብር ውስጥ ማስቀመጥና ዘግቶ መጥፋት ተጠቃሽ ሆነው ቀርበዋል፡፡ በቀን ገቢ ግምት ሒደት ወቅትም የሚከፍሉትን ሳያውቁ ቅሬታ ማቅረብ፣ ውጤቱን ለመውሰድ ፈቃደኛ አለመሆን፣ የታክስ ኦፊሰሮችን ማስፈራራትና የደረጃ ለውጥ ሊደረግብን አይገባም የሚሉ ጭምር እንዳሉ ተጠቅሷል፡፡

የተፈጠረውን ችግር ለማርገብ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን በቀን ገቢ ግምቱ ላይ ከንግድና ዘርፍ ማኅበራት አመራሮች ጋር ውይይት አካሂዷል፡፡ የቀን ገቢ ግምት ተካሂዶ ውጤቱ የተለገጸበትንና ቅሬታ የማስተናገድ ሒደት ላይ ያለውን ጉዳይ አስመልክቶ፣ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የዳይሬክተሮች ቦርድ አመራሮች ጋር ውይይት ባካሄዱበት ወቅት የተለያዩ ጥያቄዎች ተነስተዋል፡፡ አማካይ የቀን ገቢ ግምት መሠረትና ፍትሐዊነት ላይ የንግዱ ማኅበረሰብ አባላት ጥያቄዎች አቅርበዋል፡፡ የባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ የአዲስ አበባ ታክስ ፕሮግራም ልማት ሥራዎች ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ነፃነት አበራ ለጥያቄዎቹ በሰጡት ምላሽ፣ በየጊዜው እያደገ ያለ ኢኮኖሚና የንግድ እንቅስቃሴ ዕድገት ታሳቢ ባደረገ መንገድ የገቢ ግብርና የታክስ አስተዳደር አዋጆች ላይ ማሻሻያ በመደረጉ የግብር ማስከፈያ ማዕቀፎች መለወጣቸውን አስታውሰዋል፡፡

ባለሥልጣኑ የቀን ገቢ ግምት ያካሄደበት ምክንያት፣ በከተማ ደረጃ የቀን ገቢ ግምት ከተገመተ ከ2003 ዓ.ም. በኋላ ወደ ንግድ ሥርዓቱ የገቡና ግምት ያልተካሄደባቸው አዳዲስ ግብር ከፋዮች ቁጥር በርካታ መሆኑን አመልክተዋል፡፡ እንዲሁም በ2003 ዓ.ም. የቀን ገቢ ግምት የቀረበባቸው፣ ነገር ግን ዘርፍ የለወጡ፣ የጨመሩና የቀነሱ ግብር ከፋዮች ቢኖሩም በዚሁ መሠረት ማስተካከያ ሳይደረግ በመዘግየቱ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ ግምቱ በተካሄደበት ወቅት በአንዳንድ ግብር ከፋዮች ዕቃ ማሸሽ፣ የንግድ ቦታ መዝጋት፣ መረጃ አሳንሶ መስጠትና የመሳሰሉ ችግሮች ግምቱ ሙሉ በሙሉ ፍትሐዊ እንዳይሆን ቢያደርገውም፣ እነዚህን ሰዎች የኢንስፔክሽን ኮሚቴ ተከታትሎ እርማት እንደሚሰጥ አስታውቀዋል፡፡

የአዲስ አበባ ደንበኞች አገልግሎትና ትምህርት ዳይሬክተር አቶ ቱሉ ፊጤ፣ በግምት ሥራው ላይ ለምሳሌ በርበሬና ቅማመ ቅመም ንግድ ሥራ ላይ የተሰማራ ነጋዴ የቀን ገቢው 1,500 ብር ከሆነ በዓመቱ ቀናት ተባዝቶ ግብር የሚከፈልበት አሥር በመቶው ብቻ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ ይኼም ተከፋይ ዓመታዊ ግብር 5,370 ብር ይሆናለ፡፡ በቀን ገቢ ግምት የሽያጭ መጠኑን በማየት ብቻ ያንን ያህል ግብር ክፈሉ እንደተባሉ ቆጥረው፣ የመደናገጥና የማማረር ሁኔታዎች መስተዋላቸውን አብራርተዋል፡፡ የግብር ከፋዮች ዓመታዊ የቀን ገቢ ግምቱንና ዓመታዊ ሽያጩን መሠረት አድርጎ ገቢ ግብር እንዴት እንደሚሠላ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የሚከተለውን ቀመር አቅርቧል፡፡

ምሳሌ 1፡- በርበሬ ቅመማ ቅመም ንግድ ዘርፍ

የቀን ገቢ ግምት መጠን 1,500 ብር

ብር 1,500 x በ365 ቀናት = 547,500 ብር (ዓመታዊ ጠቅላላ የሽያጭ ገቢ)

የዘርፉ ትርፍ መተመኛ 10%=547,500 ብር

ግብር የሚከፈልበት ገቢ = 54,750 ብር

ግብር ምጣኔ 20% = 10,950 ብር

ተቀናሽ 3,630 ብር

ተከፋይ ግብር = 7,320 ብር

ምሳሌ 2፡- የባህል ዕቃዎች ንግድ ዘርፍ

የቀን ገቢ ግምት መጠን፡- 2,000 ብር

ብር 2000 x በ300 ቀናት = ብር 600,000 (ዓመታዊ ጠቅላላ የሽያጭ ገቢ)

የዘርፉ ትርፍ መተመኛ 14% = 600,000 x 14% = 84,000 ብር

ግብር የሚከፈልበት ገቢ = 84,000 ብር

ግብር ምጣኔ 25% = 84,000 x 25% = 21,000 ብር

ተቀናሽ = 6,780 ብር

ተከፋይ ግብር = 14,220 ብር

ምሳሌ 3፡- የፀጉር ቤት የሥራ ዘርፍ

የቀን ገቢ ግምት መጠን = 2,800 ብር

2,800 ብር x በ365 ቀናት = 1,022,000 ብር (ዓመታዊ ጠቅላላ የሽያጭ ገቢ)

ዓመታዊ ጠቅላላ የሽያጭ ገቢ = 1,022000 ብር

የዘርፉ ትርፍ መተመኛ 10% = 102,200 ብር

ጠቅላላ ወጪ = 919,800 ብር

ጠቅላላ ግብር የሚከፈልበት ገቢ = 102,200 ብር

ግብር ምጣኔ 30% = 30,660 ብር

ተቀናሽ 11,460 ብር

ተከፋይ ግብር = 19,200 ብር

የቀን ገቢ ግምቱ ይፋ ከተደረገ በኋላ የተነሳውን ቅሬታ የሚመለከታቸው የመንግሥት ባለሥልጣናት እንደመረምሩት ምንጮች ገልጸዋል፡፡ የመጀመርያው ጉዳይ ለንግዱ ኅብረተሰብ መረጃው ሲቀርብ የቀን ሽያጭ ግምቱ ብቻውን መቅረብ እንዳልነበረበት፣ ይልቁንም ታክስ የሚከፈልበትና ፍሬ ግብሩ ተያይዞ ሊቀርብ ይገባው እንደነበር መግባባት ላይ ተደርሶበታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የገቢ መሥሪያ ቤት ባለሙያዎች ግመታ ሲያካሂዱ በቂ መረጃ ያላገኙበትን መደብር ከጎረቤት መደብሮች በመነሳት መገመታቸው ተደርሶበታል፡፡

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ከበደ ጫኔ በርካታ ቅሬታዎች እየቀረቡ መሆኑን አምነው፣ መፍትሔም እየተሰጠ ነው፡፡ አቶ ከበደ እንዳሉት በብዛት ቅሬታ እያቀረቡ የሚገኙት፣ በዝቅተኛና በአነስተኛ የንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ናቸው፡፡

‹‹በእነዚህ ላይ የተወሰደው ግምት ከፍተኛ ጫጫታ አስነስቷል፤›› ያሉት አቶ ከበደ፣ ‹‹እነሱ ራሳቸው በልተው ካደሩ በቂ አይሆንም ወይ? ለምንድነው እነሱ ላይ ይህንን ያህል ግምት የሚጫነው? የሚል ተደጋጋሚ ስሞታ ቀርቧል፤›› በማለት የቅሬታውን ስፋት አስረድተዋል፡፡

አቶ ከበደ ከዚህ አንፃር መንግሥት የደረሰበትን ውሳኔ ሲያስረዱም፣ በዝቅተኛ ንግድ ላይ የተሰማሩ ተለይተው በተለይ የጀበና ሥራ፣ ልብስ ስፌት፣ ፑል ቤትና በመሳሰሉት ንግድ ሥራዎች ላይ የተሰማሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ያመኑበትን እንዲከፍሉ ተወስኗል፡፡

‹‹ያላግባብ የተጫነባቸው ካሉ እንዲነሳላቸው አቅጣጫ አስቀምጠናል፡፡ እነዚህ የኅብረተሰብ ክፍሎች ራሳቸውን ችለው በልተው ካደሩ የመንግሥትን ሸከም ማቃለል በመሆኑ፣ ነገር ግን ትንሽም ቢሆን ከሚያገኙት ገቢ በራሳቸው እምነት በመክፈል ወደ ታክስ ሥርዓቱ መግባት አለባቸው፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም የደረጃ ለውጭ ያደርጉ ነጋዴዎችም ከ ‹‹ሐ›› ወደ ‹‹ለ› እና ከ‹‹ለ›› ወደ ‹‹ሀ›› የተሸጋገሩ አሉ፡፡ በተለይ ደረሰኝ የማይገኝላቸው የንግድ መስኮች ላይ አስቸጋሪ የሆኑ፣ ሲገመትላቸው ባልተሟላ ማስረጃ የተጋነነ ግምት እንደተጣለባቸው የሚናገሩ አሉ፡፡

አቶ ከበደ እንደገለጹት፣ ቅሬታ አቅራቢዎች የደረጃ ‹‹ሐ›› የመጨረሻ ጣሪያ ላይ ሆነው የሚታዩበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡ ለምሳሌ የደረጃ ‹‹ለ›› ሆኖ 600 ሺሕ ብር የነበረ ከሆነና የተጋነነ ከሆነ ወይም ባልተሟላ ደረጃ የተገመተ ከሆነ በደረጃ ‹‹ሐ›› የመጨረሻ ጣሪያ ከ400 ሺሕ ብር እስከ 500 ሺሕ ብር ባለው ውስጥ እንዲስተናገዱ ተወስኗል፡፡

ከንቲባ ድሪባም ይህንኑ ሐሳብ ከአቶ ከበደ ጋር ይጋራሉ፡፡ ከንቲባው እንዳሉት መንግሥት ዝቅተኛ ንግድ ውስጥ ያሉ የኅብረተሰብ ክፍሎች በልተው እንዲያድሩ ነው የሚፈልገው፡፡ ነገር ግን ወደ ታክስ ሥርዓቱ መግባታቸው ለእነሱም ቢሆን ጠቃሚ ነው በማለት ሁኔታውን ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የንግዱ ኅብረተሰብ ከፍተኛ ቅሬታ እያቀረበ ነው፡፡ ለሚቀርቡ ቅሬታዎችም ተገቢው ምላሽ በወቅቱ እየቀረበ አይደለም፡፡ መንግሥት ለንግዱ ማኅበረሰብም ቁርጥ ግብርን የሚመለከት የተሟላ መረጃ እየቀረበ እንዳልሆነ ገልጿል፡፡ እነዚህ ችግሮች ተፈተው ወደ ትክክለኛው የንግድ ሥራ ለመግባት አቶ መኮንን፣ ወ/ሮ ጌጤና አቶ ፈቃዶን ጨምሮ በአገሪቱ የሚገኙ አነስተኛ ነጋዴዎች እየጠየቁ ናቸው፡፡ (ለዚህ ዘገባ ዘመኑ ተናኘ፣ ዳዊት ቶሎሳና ዳዊት እንደሻው አስተዋጽኦ አድርገዋል)

 

 

Standard (Image)

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ውስጥ ተጀምሮ የተጠናቀቀው የአምስተኛው ፓርላማ ሁለተኛ ዓመት የሥራ ዘመን

$
0
0

የሰኔ ወር ከመገባደዱ ከቀናት በፊት የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ኃላፊዎች፣ ወደ 80 ሺሕ ብር የሚገመት የሕዝብ ገንዘብ በማባከንና ባልተገባ መንገድ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል በመባል ተከሰው ክስ ለሕግ መቅረባቸው ይታወሳል፡፡ ይህ ዓይነቱ ክስ በመንግሥት ተቋማት ውስጥ የሕዝብን ተጠያቂነት ለማረጋገጥ የሚወሰድ ዕርምጃ እንደሆነ ይታሰባል፡፡ ዕርምጃው ደግሞ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአምስተኛው የፓርላማ የሁለተኛ ዓመት የሥራ ዘመን ሊዘጋ ቀናት ሲቀሩት የተወሰደ ነበር፡፡

ክሱ የተመሠረተው በፌዴራል ዋና ኦዲተር ሪፖርት መሠረት በተገኘ ማስረጃ ነው፡፡ ለሕግ አውጭው በሚቀርብለት ሪፖርት መሠረት ሊጠየቁ በሚገባቸው አካላት ላይ ምክር ቤቱ በሚያደርገው ግፊት ወይም ማሳሰቢያ መሠረት ክሱ መቅረቡ ይታመናል፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ምክር ቤቱ በየዓመቱ ተመሳሳይ የኦዲት ሪፖርቶች መሠረት በአስፈጻሚ አካላት የሚቀርቡ ግድፈቶችን፣ ደካማ አሠራሮችን፣ ከሙስና ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ጥፋቶችን በተመለከተ ሊጠየቁ የሚገባቸው ተቋማትና አመራሮች ላይ ጥብቅ ዕርምጃ እንዲወሰድ የሚሉ ማሳሰቢያዎች ሲያስተላልፍ ጎልቶ ይሰማል፡፡

እንዲህ ዓይነት የቁጥጥርና የክትትል ሥራዎችን (Check and Balance) አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተስፋ ተደርጎበት ነበር ከቀናት በፊት የምክር ቤቱ ቆይታ የተጠናቀቀው፡፡ የምክር ቤቱ የሥራ ዘመን መስከረም 30 ቀን 2009 ዓ.ም. መጀመሩ ይታወሳል፡፡

‹መስከረም ሲጠባ ጥቁሩ አደይ ሲፈነዳ›

አገሪቱ በምትመራበት የሕጎች ሁሉ የበላይ የሆነው ሕገ መንግሥት ምክር ቤቱ ስለሚሰበሰብበትና የአገልግሎት ዘመኑን በሚደነግገው አንቀጽ 58፣ በመስከረም ወር የመጨረሻው ሰኞ ዕለት ይከፈታል፡፡ እንዲሁም የርዕሰ ብሔሩን ሥልጣንና ተግባር በሚወሰነው አንቀጽ 71 ለፕሬዚዳንቱ ከተዘረዘሩት ተግባራት የመጀመርያው፣ የሁለቱ ምክር ቤቶች (የሕሥብ ተወካዮችና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች) አካላት ከ2/3ኛው በላይ ሲገኙ የዓመቱን የሥራ ዘመን ይከፍታሉ፡፡ በዚሁ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓትና በምክር ቤቶቹ የአባላት አሠራርና ሥነ ምግባር ደንብ፣ ርዕሰ ብሔሩ በሁለቱ ምክር ቤቶች አፈ ጉባዔዎች መካከል ተሰይመው የመክፈቻ ንግግር በማቅረብ የአዲሱን የፓርላማ የሥራ ዘመን በይፋ ያበሥራሉ፡፡

በዚህ ዕለት የመክፈቻው ሥነ ሥርዓት በአብዛኛው ከሚከናውነት መደበኛ ስብሰባዎች በተለየ ደማቅ ድባብና በዓላዊ ስሜት አለው፡፡ ያለፈው ዓመት የሥራ ዘመን ከመጠናቀቁ ጋር ተያይዞ የምክር ቤቱ አባላት ወደ ተመረጡበት አካባቢ በመሄድ፣ ወይም በሌላ ተልዕኮዎች ለሦስት ወራት ተለያይተው የሚገናኙበት ወቅት በመሆኑ አንዱ ድምቀት ነው፡፡ እንዲሁም አባላቱ ከወትሮዎቹ የመደበኛ ስብሰባዎች በተለየ የሚወክሏቸውን ብሔር ብሔረሰቦች የሚወክሉ ባህላዊ ልብሶች ተላብሰው የምክር ቤቱን የመክፈቻ ስብሰባ ያደምቁታል፡፡ የጽሕፈት ቤቱ ሠራተኞች ለአባላቱ የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል ያደርጉላቸዋል፡፡ የአበባ ዘንጎችንና አዲስ ዘመን የሚያመላክት የአደይ አበባ ምሥል የታተመበት ፖስት ካርድ በመስጠት፣ የመልካም ምኞት መልዕክቶችን ያስተላልፉላቸዋል፡፡ ይኼ ዓይነቱ ሥርዓት ባለፉት ሁለት አሥርት የተለመደ ነው፡፡ ነገር ግን መስከረም 30 ቀን የተጀመረው የ2009 ዓ.ም. የሥራ ዘመን መክፈቻ ይኼንን ዓይነት የተለመደ ድባብ አልነበረውም፡፡ ምንም እንኳ አባላት የብሔረሰቦቻቸውን መገለጫ የሆኑ አልባሳትን ለብሰው ቢመጡም፣ እንዲሁም የመነፋፈቅ ስሜታቸው ቢስተዋልም በወቅቱ በአገሪቱ ውስጥ ተከስተው በነበሩ ሁከቶች ስሜታቸው ቀዝቅዞ ነበር የተስተዋለው፡፡

ወርኃ መስከረም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚታወቅበት ልዩ ባህሪው የክረምት ጭጋግ ወደ ብርሃን ወቅት መሸጋገሪያ፣ ልምላሜና በአደይ አበባ ያሸበረቀ ብርሃን የሚፈነጥቅበት መሆኑ በተለይ ስሜት ይታያል፡፡ ነገር ግን ቀደም ብሎ በ2008 ዓ.ም. የመጨረሻ ወራት ተቀስቅሶ እስከ መስከረም 2009 ዓ.ም. የዘለቀው ሁከትና ከፀጥታ ኃላፊዎች ጋር በተደረገ የግጭት ወቅት ነበር የምክር ቤቱ ሥራ የተጀመረው፡፡ በኋላም በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ሪፖርት እንደተገለጸው፣ በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች 669 ዜጎች የተገደሉበት፣ ከ1,200 በላይ የቆሰሉበት፣ እንዲሁም በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ የታሰሩበት ጊዜ ነበር፡፡ በተለይም በአሳዛኙ የኢሬቻ የበርካቶች ሞት፣ በዚህም ሳቢያ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለስድስት ወራት ባወጀበት ማግሥት ነበር የፓርላማው መክፈቻ ቀን የነበረው፡፡

በ2009 ዓ.ም. ምክር ቤቱ ካከናወናቸው ተግባራት ውስጥ አስቸኳይ አዋጁን ከርዕሰ ብሔሩ የመክፈቻ ንግግር ተከትሎ ማፅደቁ ነበር፡፡ በበርካቶች ዘንድ ‹‹ጥቁር መስከረም›› በተባለው ወቅት የፀደቀው አስቸኳይ አዋጅ የመጀመርያው የስድስት ወራት ከተጠናቀቀ በኋላ፣ በድጋሚ ለአራት ወራት የተራዘመውም በዚሁ የምክር  ቤቱ የሥራ ዘመን ነው፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በኢሕአዴግ የአስተዳደር ዘመን ለመጀመርያ ጊዜ የታወጀ ነው፡፡ በቅርቡ ለተጠናቀቀው ለአምስተኛው ፓርላማ ሁለተኛው የሥራ ዘመንም ታሪካዊ ውሳኔ ያስተላለፈበት ሆኖ አልፏል፡፡ ፓርላማውም የተዘጋው ይኼው አዋጅ ለሁለተኛ ጊዜ የተራዘመበት ቀነ ገደብ ለመጠናቀቅ 43 ቀናት ሲቀሩት ነው፡፡

ከ2008 እስከ 2009 ዓ.ም. ተከስቶ ከነበረው ተቃውሞና ግጭት ጋር በኋላ፣ መንግሥት መልካም አስተዳደርን ለማስፈንና ‹‹የሕዝብን ጥያቄ›› በአግባቡ ለመመለስ በማለት ጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲሱን የመንግሥታቸውን ካቢኔ እንደገና እንዳዋቀሩ ይታወሳል፡፡ የአዲሱንም የካቢኔ አባላት ሹመት ማፅደቅን ምክር ቤቱ በቀዳሚነት ተግባራዊ ካደረጋቸው ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡

በምክር ቤቱ የአሥር ወራት የሥራ ጊዜ ውስጥ በጉልህ ሊጠቀሱ ከሚችሉ ሌሎች ተግባራት ውስጥ፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አፈጻጸም መርማሪ ቦርድ መቋቋም አንዱ ነው፡፡ ሰባት አባላት ያሉት ቦርድ በምክር ቤቱ አባል አቶ ታደሰ ሆርዶፋ ሰብሳቢነት የተሰየመ ነበር፡፡ ሥራውን በጥቅምት ወር መጨረሻ በይፋ የጀመረው መርማሪ ቦርድ፣ አንድ ጊዜ ለምክር ቤቱ ሪፖርት ማቅረቡ ይታወሳል፡፡

በተመሳሳይ ለአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መታወጁ ምክንያት የሆነው ተቃውሞና የፀጥታ ኃይል የወሰዱትን ዕርምጃ ተመጣጣኝነት በተመለከተ፣ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እንዲያጣራ የታዘዘበት ጊዜ ነበር፡፡ የኮሚሽኑ የማጣራት ሥራም በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች ከተከሰተው ሁከት በተጨማሪ፣ በተመሳሳይ ወቅት በደቡብ ክልል ጌዴኦ ዞን በዲላና በአጎራባች ወረዳዎች ተከስቶ የነበረውን ግጭት አብሮ እንዲያጣራም ነበር ውሳኔ የተላለፈው፡፡ ኮሚሽኑም በሚያዝያ ወር 2009 ዓ.ም. የምርመራ ውጤቱን ግኝቶች በተጠናቀቀው የፓርላማው የሥራ ዘመን ነበር ያቀረበው፡፡ ከሰብዓዊ መብት አያያዝ ጋር በተያያዘ ኮሚሽኑ በተመሳሳይ ምክር ቤቱ ከመከፈቱ አንድ ወር ቀደም ብሎ፣ በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ተቀስቅሶ በነበረውና 23 ታራሚዎች የሞቱበትን ክስተት እንዲያጣራ በታዘዘው መሠረት፣ የምርመራ ግኝቱን ሪፖርት ያቀረበበት ጊዜ ነበር፡፡

ዓመቱ ከፖለቲካውና ከአስተዳደራዊ ግጭቶች በተጨማሪ የተለያዩ አሳዛኝ ክስተቶች የታዩበት እንደነበር ይታወሳል፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች ምክር ቤቱ ብዙም ያልተለመዱ ውሳኔዎችን እንዲያሳልፍ ለመደረጉ የተለያዩ ጉዳዮችን ማንሳት ይቻላል፡፡ ለአብነት በዓመቱ ሁለት ብሔራዊ የሐዘን ቀናትን ማወጁ ይታወሳል፡፡ የመጀመርያው የምክር ቤቱ የሥራ ዘመን ከመከፈቱ አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ በተከሰተው የኢሬቻ በዓል አደጋ 55 ሰዎች ሲሞቱ፣ ከ100 በላይ በመቁሰላቸው ሳቢያ ነው፡፡ ሁለተኛው አዲስ አበባ ውስጥ በተለምዶ ቆሼ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ 130 ሰዎች የቆሻሻ ክምር ተንዶ በመሞታቸው ነበር፡፡

በእርግጥ የዓመቱ ሁለት ብሔራዊ ሐዘኖች ለአምስተኛው የፓርላማ ዘመን የመጀመርያ አይደሉም፡፡ ከዚያ በፊት ተመሳሳይ የሐዘን ቀናት በጋምቤላ ክልል በደቡብ ሱዳናውያን ለተገደሉ ዜጎችና በ2007 ዓ.ም. በሊቢያ አይሲኤስ በተባለው ሽብርተኛ ቡድን ግድያ ለተፈጸመባቸው ዜጎች መታወጃቸውም ይታወሳል፡፡

ፓርላማው በመደበኛ ሥራው በአሥር ወራት ካከናወናቸው ውስጥ ከቀረቡለት ረቂቅ ሕጎች 68 ያህሉን ያፀደቀው ይገኝበታል፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎንም የተለያዩ መሥሪያ ቤቶችን ሪፖርቶች በማዳመጥ፣ የተቋማት ኃላፊዎች ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡ ጥያቄዎች የሰጡዋቸውን ምላሾች ሲያደምጥም ከርሟል፡፡

ከተቋማት ሪፖርቶች ውስጥ በዋነኛነት የዋና የኦዲተር መሥሪያ ቤት ሪፖርት በቀዳሚነት ይጠቀሳል፡፡ ምንም እንኳ የዋና ኦዲተር ሪፖርት በአብዛኛው የፓላማ አባላትን ቀልብ እንደሚይዝ ቢታወቅም፣ በዘንድሮው ሪፖርት የምክር ቤት አባላት በተለየ ሁኔታ ምላሻቸው ተሰምቷል፡፡

‹‹አሁንስ የኦዲት ሪፖርትን ባየሁ ቁጥር ተመሳሳይ ጥፋቶችን፣ ተመሳሳይ ጉድለቶችንና ችግሮችን መስማት እያመመኝ ነው፤›› ሲሉ ነበር በግንቦት ወር ወ/ሮ ሙሉ ገብረ እግዚአብሔር የተባሉ የምክር ቤት አባል የገለጹት፡፡

‹‹የማይጠየቁ›› ተጠያቂዎች

በዋና ኦዲተሩ የሚቀርቡ ጉድለቶችም ሆኑ ሌሎች ተቋማት የሚነሱ ሊያስጠይቁ የሚችሉ ጉዳዮች በሕዝብም ቢሆን በቀዳሚነት የሚነሱ ናቸው፡፡ ከምክር ቤት የሚመጡ ማሳሰቢያዎችን ተመርኩዘው ሊጠየቁ ሲገባቸው ሳይጠየቁ መቅረታቸው፣ ምክር ቤቱን ጉልበት አልባ አድርጎታል የሚሉ ትችቶች በስፋት የሚነሱት ከዚህ ጋር በተገናኝ ነው፡፡

አፈ ጉባዔው በአንፃሩ ምክር ቤቱ በሥራ አስፈጻሚው ተፅዕኖ ሥር አለመሆኑን በተደጋጋሚ አስረድተዋል፡፡ እንዲሁም ባለፉት ጥቂት ዓመታት ብቻ ተጠያቂነት ለማስፈን ማንኛውንም ተቋም ሆነ አመራሮችን ከዚህ በኋላ እንደማይታገሱ፣ ምክር ቤቱ ግፊት እንደሚያደርግ በተደጋጋሚ ሲገልጹም ነበር፡፡

በዚህም የተነሳ ይመስላል በዘንድሮው የዋና ኦዲተር ሪፖርት አባላቱ ምሬት በተሞላበት ስሜት ትችታቸውን የሰነዘሩት፡፡

‹‹በየዓመቱ ተመሳሳይ ነገር እየደገምን መሄድ የለብንም፣ ዕርምጃ መውሰድ መጀመር አለብን፤›› ሲሉም ወ/ሮ ሙሉ ገልጸዋል፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በበጀት ዓመቱ ያከናወናቸው ተግባራት በሁሉም ዘርፎች የተሻለና ውጤታማ እንደነበር አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ መግለጻቸው ይታወሳል።

የምክር ቤቱን የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ያቀረቡት አፈ ጉባኤ አቶ አባዱላ ገመዳ፣ በበጀት ዓመቱ ምክር ቤቱ ያከናወናቸው ተግባራት በሁሉም ዘርፎች የተሻሉና ውጤታማ ነበር፤"ብለዋል። ቅድሚያ ተሰጥቷቸው ከተከናወኑ ተግባራት መካከል የአቅም ግንባታ ዋነኛው መሆኑን ጠቁመው በዚህም የዕውቀት፣ የክህሎትና የአመለካክት አቅምን ወደ ላቀ ደረጃ በማድረስ አባላትን ወቅቱ ለሚጠይቀው ተልዕኮ ማብቃት መቻሉን ተናግረዋል።

እንዲሁም የሕዝብን ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት በተሻለ ደረጃ ያረጋገጡ ጥራት ያላቸው ሕጎች መውጣታቸው ተመልክቷል።

የ2010 ዓ.ም. የፌዴራል መንግሥትን የበጀት አዋጅን ጨምሮ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የተረቀቁ 68 ልዩ ልዩ፣ የብድርና ዓለም አቀፍ ስምምነቶችና የማሻሻያ ረቂቅ አዋጆች ውይይት ተደረጎባቸው ፀድቀዋል።

በዓመቱ 46 ያህል ወሳኝ ሕጎች ላይ ውይይት መደረጉን ከምክር ቤቱ መዘጋት በኋላ ተገልጿል፡፡ ኃላፊዎች ይኼንን ይበሉ እንጂ ከኦዲትና ከተለያዩ የመልካም አስተዳደር ችግሮች አኳያ የሚነሱ ጥያቄዎች በምክር ቤቱ አሠራር ላይ ጥያቄ ያስነሳሉ፡፡

 የፌዴራል ዋና ኦዲተር በየዓመቱ የሚያወጣው የተጠቃለለ የኦዲት ሪፖርት ላይ የሚስተዋሉት የኦዲት ችግሮች እየተባባሱ እንጂ እየተቃለሉ አልሄዱም መባላቸው ተጠቃሽ ነው፡፡

ለዚህ ደግሞ ዋነኛ ምክንያት ባለበጀት መሥሪያ ቤቶቹ በተለያዩ ነጥቦች ላይ በተሰጣቸው የኦዲት ሪፖርት መሠረት ማስተካከያ አለማድረጋቸው መሆኑን፣ የፌዴራል ዋና ኦዲተር አቶ ገመቹ ዱቢሶ አስገንዝበዋል።

በኦዲት ግኝቶች ላይ ዕርምጃ መውሰድ የማይፈልጉ መሥሪያ ቤቶችና ኃላፊዎች ምክር ቤት ቀርበው እንኳን የዋና ኦዲተሩን አስተያየት የማይቀበሉ መሆኑን ነው የተናገሩት።

እነዚህ መሥሪያ ቤቶችና የሥራ ኃላፊዎች ያለበቂ ምክንያት በፌዴራል ዋና ኦዲተሩ በቀረቡ የኦዲት ሪፖርቶች በተሰጡ የማሻሻያ አስተያየቶች ላይ በወቅቱ ዕርምጃ ባለመውሰዳቸው፣ የሕግ ተጠያቂነትን የሚያስከትልባቸው መሆኑን በአግባቡ ሊገነዘቡት እንደሚገባም ነው ያሳሰቡት።

ዋና ኦዲተሩ ይኼን ይበሉ እንጂ በየዓመቱ ተደጋጋሚ የኦዲት ችግር የሚጋጥማቸው ተቋማትም ሆኑ የሥራ ኃላፊዎች በሕግ ተጠያቂ ሲሆኑ አይታይም። ተደጋጋሚ የኦዲት ግኝት ችግር ካለባቸው ተቋማት ውስጥ ደግሞ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአንበሳውን ድርሻ ይይዛሉ።

የፌዴራሉ ዋና ኢዲተር መሥሪያ ቤት የተቋማትን የኦዲት ግኝት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከማሳወቅ ባለፈ በራሱ የሚወስደው ዕርምጃ አለመኖሩ ይታወቃል።  የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትም ሪፖርቱን ከማዳመጥ ያለፈ ሚና እንዳልነበራቸውም ነው የሚገለጸው።

ከነዚህ ጋር በተያያዘ በቅርቡ በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ላይ የተወሰደው ዕርምጃ ምናልባትም የፓርላማው ግፊት ለውጥ ማሳየት መጀመሩን ሊያሳይ ይችላል፡፡ ነገር ግን በተለይ በዋና አባካኝ በሆኑ ትልልቅ ተቋማት ላይ ተመሳሳይ ዕርምጃ ስለመወሰዱ አሁንም ጥያቄ ይነሳል፡፡ እንዲሁም መጠየቅ ሲገባቸው ሊጠየቁ ስላልቻሉ ተቋማትና ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጥያቄዎች መነሳታቸው አልቀረም፡፡ ጥያቄዎቹ ደግሞ በምክር ቤቱም ቀደም ብለው ሲነሱ የነበሩ፣ ወደፊትም ሊቀጥሉ የሚችሉ ናቸው፡፡

ዘመነ ታብሌት

በሌላ በኩል ምክር ቤቱ ከሚታወቅባቸው ልማዳዊ አሠራሮች ሁለት አዳዲስ ለውጦችም የተስዋሉበት ነበር፡፡ አንደኛው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለመጀመርያ ጊዜ በአዳራሹ የመጀመርያ ረድፍ ይቀመጡበት ከነበረው ወንበር በመነሳት ወደ ዋናው መድረክ ከአፈ ጉባዔው ጎን በመቀመጥ ንግግር ማድረጋቸው ነው፡፡  

የወረቀት ሰነዶች ሥርጭትና የኅትመት ወጪን በመቀነስ ዘመናዊ አሠራርን ተግባራዊ ለማድረግ ፕሮግራም የቀረፀው የሕዝብ ወካዮች ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት፣ ለምክር ቤቱ አባላት በሙሉ ታብሌት ኮምፒዩተሮችን ገዝቶ የተከፋፈለው በዚሁ ዓመት ነበር፡፡

‹‹የምክር ቤቱን አሠራር ወደ ወረቀት አልባ እንቀይረው በማለት ነው የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፕሮጀክት የቀረፅነው፤›› ሲሉ የምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ከረዩ ባናታ በወቅቱ ለሪፖርተር ገልጸው ነበር፡፡

በምክር ቤቱ ሰፊ የሆነ የወረቀት ሥራ የሚከናወን መሆኑንና ትልቅ ማተሚያ ቤትም እንደሚገኝ የገለጹት አቶ ከረዩ፣ በተለይ ረቂቅ የበጀት ሰነድ በሚቀርብበት ወቅት ለአንድ የምክር ቤት ተመራጭ ሁለት እሽግ ወረቀት እንደማይበቃ ጠቁመዋል፡፡

ስለዚህም ምክር ቤቱ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሥርዓት በመዘርጋት አሠራሮቹን ወደ ዲጂታል እንዲቀይር አስፈላጊ እንዳደረገው አስረድተዋል፡፡

ነገር ግን የታብሌት አገልግሎቱ ከመጋቢት ወር ቢጀምርም ፓርላማው እስከተዘጋበት ሰኔ መጨረሻ ድረስ አንዳንድ አባላት ስለአጠቃቀሙ ግራ ሲጋቡና እርስ በርስ ሲረዳዱም ማየት ተችሏል፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ሪፖርት በሚቀርብበትና በረቂቅ አዋጁ ውይይት ወቅት የግል ጉዳያቸውን በተሰጣቸው ታብሌት ሲመለከቱና አጠገባቸው ለተቀመጡ የምክር ቤት አባላት ሲያጋሩም ማስተዋል ተችሏል፡፡

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ድንጋጌ ሥራውን የጀመረው ፓርላማ፣ ለመጪው ዓመት 320.8 ቢሊዮን ብር በጀት በማፅደቅ ተጠናቋል፡፡

Standard (Image)

የፖለቲካ ሹማምንት ዲፕሎማትነት መበራከትና አንድምታው

$
0
0

 

ከቀናት በፊት የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) ኢትዮጵያን በውጭ አገር ለሚወክሉ አምባሳደሮች ሹመት ሰጥተዋል። በዚህም መሠረት በባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደርነት የተሾሙት አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን፣ ወ/ሮ አስቴር ማሞ፣ ዶ/ር ሽፈራው ተክለ ማርያም፣ አምባሳደር ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ፣ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና፣ አቶ ዓሊ ሱሌይማን፣ ፕሮፌሰር አድማሱ ፀጋዬ፣ አምባሳደር ተበጀ በርሄ፣ አቶ መታሰቢያ ታደሰ፣ አቶ ሙሉጌታ ዘውዴና ወ/ሮ ሉሊት ዘውዴ ናቸው፡፡ አቶ እውነቱ ብላታ ደግሞ በአምባሳደርነት ተሹመዋል፡፡

ከእነዚህም መካከል ከሹመታቸው በፊት አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን የፌዴራልና አርብቶ አደር ጉዳዮች ሚኒስትርና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቦርድ ሰብሳቢ፣ ዶ/ር ሽፈራው ተክለ ማርያም የትምህርት ሚኒስትር፣ አቶ ዓሊ ሱሌይማን የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር፣ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ፣ አቶ እውነቱ ብላታ የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ፣ እንዲሁም ፕሮፌሰር አድማሱ ፀጋዬ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ነበሩ፡፡ ወ/ሮ አስቴር ማሞ ደግሞ ፌዴራል መንግሥቱን፣ ኦሮሚያ ክልልንና ኦሕዴድን በተለያዩ ኃላፊነቶች ያገለገሉ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትርና የመልካም አስተዳደር ክላስተር አስተባባሪ ተጠቃሽ ናቸው።

ለገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ በሚኒስትር ደረጃ ያሉትን ጨምሮ ከፍተኛ ባለሥልጣናቱን ከኃላፊነታቸው በማንሳት በአምባሳደርነት መሾም አዲስ ነገር አይደለም። ለአብነት ያህል ከዚያ ቀደም የቀድሞ የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ አያሌው ጐበዜ፣ የማዕድን ሚኒስትሯ ወ/ሮ ስንቅነሽ እጅጉ በኢሕዴድ መሥራችነትና ታጋይነት የአዲስ አበባ ከንቲባነትን ጨምሮ በተለያዩ የመንግሥት ተቋማትና የክልል ፕሬዚዳንትነት ያገለገሉት አቶ ኩማ ደመቅሳ፣ እንዲሁም ለ15 ዓመታት ገደማ የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር የነበሩት ወ/ሮ ሳሚያ ዘካሪያ በአምባሳደርነት ተሹመዋል::  

ይህ ዓይነት አሠራር አሁን በሥራ ላይ በሚገኘው ‹‹የውጭ ግንኙነት አገልግሎት አዋጅ ቁጥር 790/2005›› ሕጋዊ መሠረት ያለው ነው፡፡ አዋጁ በአንቀጽ ስምንት የዲፕሎማቲክ አገልግሎት ዘርፎችን ከፍተኛ፣ መካከለኛ፣ መጀመሪያ ደረጃና የቆንስላ አገልግሎት ምድብ በማለት በአራት ደረጃ ይከፍላቸዋል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የዲፕሎማቲክ አገልግሎት ምድብ ሁለተኛና ሦስተኛ ጸሐፊዎችና አታሼዎች የሚገኙበት ነው፡፡ በከፍተኛው ደረጃ ላይ ደግሞ አምባሳደሮች፣ ልዩ መልዕክተኞችና ሁለገብ አምባሳደሮች የሚመደቡበት ነው፡፡

የውጭ ግንኙነት አገልግሎት የፖለቲካ ሹመቶች ልዩ መልዕክተኞችንና ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደሮችን፣ አምባሳደሮችንና ሁለገብ አምባሳደሮች ያካታል፡፡ ልዩ መልዕክተኞችና ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደሮችና አምባሳደሮች በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 71(3) መሠረት በጠቅላይ ሚኒስትሩ አቅራቢነት በፕሬዚዳንቱ ይሾማሉ፡፡

ይሁንና የፖለቲካ ሹመት አምባሳደሮችን ለመሾም ዋነኛ መንገድ እንዳልሆነ ከአዋጁ አጠቃላይ መንፈስ መረዳት ይቻላል፡፡ በአዋጁ መግቢያ እንደተገለጸው ይህ ሕግ የወጣው የውጭ ግንኙነት አገልግሎቱን ወጥነት ባለውና በተቀናጀ ተቋማዊ የአሠራር ሥርዓት ለማስተዳደር የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍ መዘርጋት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፣ የተለያዩ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የሚያከናውኗቸውን ከውጭ ግንኙነት አገልግሎት ጋር የተያያዙ ተግባራትን በተቀናጀ መንገድ ለማከናወን የሚያስችል ሥርዓት መዘርጋት ጠቃሚ መሆኑ ስለታመነበትና ሙያዊ አቅሙ፣ ብቃቱና ክህሎቱ የዳበረና የተጣለበትን አገራዊ ተልዕኮ በታማኝነትና በቁርጠኝነት የሚወጣ ጠንካራ የሰው ኃይል ለማፍራት የሚያስችል፣ የሥራ ተነሳሽነትን የሚፈጥር፣ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት ሙያዊ የውጭ ግንኙነት አገልግሎትን ዕውን ለማድረግ የሚያስችል ቀልጣፋና ውጤታማ የአደረጃጀት፣ የአሠራርና የአስተዳደር ሥርዓት መዘርጋት በማስፈለጉ ነው፡፡

በአንቀጽ ሦስት ላይ ከተዘረዘሩት የውጭ ግንኙነት አገልግሎት ሥልጣንና ተግባራት መካከል በሁለትዮሽና በባለብዙ ወገን ግንኙነቶች አማካይነት የፖለቲካ፣ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ትብብሮችን መፍጠርና ማጠናከር፤ በተለይም ቴክኖሎጂን በማሸጋገር፣ ንግድና ኢንቨስትመንትን በማስተዋወቅ፣ የባህል ግንኙነትና የቱሪዝም አድማስን በማስፋፋትና በማጠናከር የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅሞች ማረጋገጥና ማስከበር፣ ከልማት አጋሮች የሚገኙ አዳዲስ የፋይናንስ፣ የቴክኒክና የአቅም ግንባታ ድጋፎችን ማፈላለግ፣ በውጭ አገር የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንን መብቶችና ጥቅሞች ማስጠበቅ፣ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮዽያዊያንና የውጭ ዜግነት የያዙ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸውን ትስስር እንዲያጠናክሩና በኢትዮጵያ የልማትና የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ሒደት በንቃት ተሳትፈው ራሳቸውንና አገራቸውን እንዲጠቅሙ ማስቻል፣ የአገሪቱን መልካም ገጽታ በቀጣይነት ለመገንባትና ለልማት የተመቻቸ ሁኔታን ለመፍጠር በውጭ አገር የፐብሊክ ዲፕሎማሲና የሕዝብ ግንኙነት ሥራዎችን ማስተባበርና ማካሄድ ተጠቃሽ ናቸው፡፡

እነዚህን የውጭ ግንኙነት አገልግሎት ሥልጣንና ተግባራት በብቃት ለመወጣት በአብዛኛው ባለሙያ ዲፕሎማቶችን መጠቀም እንደሚመረጥ የፖለቲካ አዋቂዎች ይመክራሉ፡፡ አዋጁ ራሱ የዲፕሎማቲክ አገልግሎት ሠራተኞች ምልመላ ዕውቀትና ችሎታን መሠረት ባደረገ ግልጽ ውድድር መሠረት እንደሚፈጸም ይደነግጋል፡፡

ከዚህ አንፃር የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተለይም በአፈጻጸማቸው ጥያቄ የሚቀርብባቸው በአምባሳደርነት መሾም መቀጠላቸውን ብዙዎች እየተቹት ይገኛሉ፡፡ እርግጥ መንግሥት ይህን ዕርምጃ አሁን ለመውሰድ ምን አነሳሳው? ወይም አስገደደው? ለሚለው እስካሁን በይፋ የተሰጠ መግለጫ የለም። ነገር ግን ኢሕአዴግ በአንድ ሚኒስቴር የአቅም ችግር የተስተዋለበት ሰው በሌላ ቦታ ስኬታማ ሥራ ማከናወን አይችልም ማለት አይደለም ሲል መከራከሪያ ያቀርባል።

በፖለቲካ ሹመት አማካይነት ዲፕሎማቶችን መመደብ በኢትዮጵያ ለበርካታ ዓመታት ይከናወን የነበረ ቢሆንም፣ ይህ ተግባር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተስፋፋ መምጣቱን የፖለቲካ ተንታኞች ይናገራሉ::

በአፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በዕውቀታቸውና በችሎታቸው የላቁ ባለሙያዎች እየተመለመሉ በዲፕሎማትነት እንዲሠሩ የማድረጉ ዕርምጃ ተጠናክሮ፣ የአገሪቱን ገጽታ ለመቀየር ቁልፍ ሚና መጫወቱን የታሪክ ሰነዶች ያትታሉ፡፡ በንጉሡ ዘመን የውጭ ግንኙነት ትምህርትን በተለያዩ የውጭ አገሮች እንዲቀስሙ ተልከው የተመለሱ ኢትዮጵያውያን የተደራጀ የዲፕሎማሲ ሥራ ይከውኑ እንደነበር፣ በአሁኑ ወቅት በጡረታ ላይ የሚገኙ አምባሳደሮች ይናገራሉ::

የዲፕሎማሲ ሥራ በዕውቀትና በልምድ የተጠናከረ በመሆኑም በወታደራዊው ሥርዓት ወቅት ምንም እንኳን የርዕዮተ ዓለም መሠረታዊ ለውጥ ቢኖርም፣ አብዛኛዎቹ አምባሳደሮች በአገልግሎታቸው ቀጥለዋል፡፡ የእነዚህ አንጋፋ ዲፕሎማቶች አገልግሎት የኢሕአዴግ መንግሥት ወደ ሥልጣን ከመጣ በኋላ ግን ሙሉ በሙሉ መቀጠል አልቻለም፡፡ በምትኩ በደርግ አገዛዝ ተገፍተው በውጭ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያንና በኢሕአዴግ ትግል ውስጥ የተሳተፉ በአብዛኛው መመደባቸውን አንዳንድ ጽሑፎች ያስገነዝባሉ፡፡ በተለይ ከ1997 ዓ.ም. በኋላ በዲፕሎማሲ ሥራ ውስጥ የፖለቲካ ተሿሚዎች እየተበራከቱ መምጣታቸውንም ያሳያሉ፡፡ በዚህም ኢሕአዴግ በፓርቲ ሥራ ላይ እንዲሁም በመንግሥት ሥራ አስፈጻሚነት ለረዥም ጊዜ ያገለገሉ ግለሰቦች በዲፕሎማሲ ሥራው ላይ መመደብ ቀጥሏል::

ተንታኞች በአብዛኛው የዲፕሎማቶች አመዳደብ በዕውቀት፣ በችሎታና በውድድር ላይ የተመሠረተ እንዲሆን ያሳስባሉ፡፡ ኢትዮጵያ የፖለቲካ ሹመትንም በዲፕሎማሲ ሙያ ላይ የቆዩትንም በውጭ አገልግሎት ላይ ትመደባለች፡፡ ይሁንና በከፍተኛ የመንግሥት ሥልጣን ላይ የነበሩ ተሿሚዎች ከ‹‹ኬርየር ዲፕሎማት›› (የረዥም ጊዜ የዲፕሎማሲ አገልግሎት፣ ልምድና ዕውቀት ያላቸው) በተቃራኒ የአጭር ጊዜ ሥልጠናዎችን አግኝተው ወደ ሥራ ይገባሉ፡፡

የቀድሞው የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጌታቸው ረዳ በአንድ ወቅት፣ ‹‹በፖለቲካ የሚመደቡ አምባሳደሮች ለረዥም ጊዜ የመንግሥትን ፖሊሲ ሲያስፈጽሙ የቆዩ በመሆናቸው የአጭር ጊዜ የዲፕሎማሲ ሥልጠና ወስደው እንዲመደቡ ይደረጋል፡፡ ምክንያቱም የፖሊሲ ሥልጠና በአጭር ጊዜ ሰጥቶ አምባሳደር ማድረግ ስለማይቻል፤›› በማለት ለሪፖርተር ተናግረው ነበር፡፡

ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባልደረባ፣ ‹‹ኬርየር ዲፕሎማቶች በተለይ ጥልቅ የሆነ የዲፕሎማሲ ሥራ የሚጠየቅባቸው እንደ ተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በሚገኙባቸው አገሮች ይሾማሉ:: የመንግሥት ፍላጐት ለምሳሌ ዳያስፖራውን ማንቀሳቀስ ከሆነ በፖለቲካ ሹመት የሚመደብ አምባሳደር ይኖራል፤›› በማለት ያስረዳሉ::

ነገር ግን የፖለቲካ ተሿሚዎች ጥራትና ብዛት ላይ በርካታ ቅሬታዎች ይሰማሉ፡፡ ለአንዳንዶች አምባሳደርነት የተከበረ ሙያ ቢሆንም ከንጉሡ ዘመን ጀምሮ ቦታው ሰዎችን ገለል ማድረጊያ፣ የደከመን፣ ያኮረፈን ማባበያና ጡረታ ማውጫ ሆኖ ማገልገሉ አሳዛኝ እንደሆነ የሚናገሩ አሉ፡፡

የመድረክ የወቅቱ የውጭ ግንኙነት ኃላፊ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፣ ‹‹በሌሎች አገሮች የአምባሳደሮች ሹመት አገር የሚወክሉ ከፍ ያለ ብቃት ያላቸው ሰዎች የሚመለመሉበት ነው፡፡ በእኛ አገር ግን የፓርላማን እንኳን ይሁንታ የማያገኝ ነው፡፡ ሥልጣን ላይ ያለው ጠቅላይ ሚኒስትር ሰዎችን እንደፈለገ ወዲያ ወዲህ የሚያደርግበት ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ የአምባሳደርነት ሹመት መጦሪያና የውለታ መክፈያ ሆኗል፡፡  ከሥልጣን ማዕከል ገለል ማድረጊያ መሣሪያም ነው፤›› በማለት ለሪፖርተር  ተናግረዋል፡፡

የኢዴፓ መሥራችና የቀድሞ ሊቀመንበር አቶ ልደቱ አያሌውም የአምባሳደርነት ሹመት በአግባቡ ሥራ ላይ እየዋለ እንደማይገኝ ያምናሉ፡፡ ‹‹ብዙ ጊዜ በዲፕሎማት ደረጃ የሚሾሙ ሰዎች ጥሩ የሥራ ብቃት የሌላቸው፣ በጤናና በሌሎች ምክንያቶች ገለል እንዲሉ የሚፈለጉና ለሰጡት አገልግሎት እንደ ውለታ መክፈያ የሚቆጠሩላቸው ናቸው፡፡ ይኼ የሚያሳዝንና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየባሰበት የመጣ ችግር ነው፡፡ በዲፕሎማትነት የሚመደቡ ሰዎች በሙያው ብቃት ያላቸው መሆን አለባቸው፤›› ሲሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

አቶ ልደቱ ኢሕአዴግ ሁሌም ችግር በመጣ ቁጥር ባለሥልጣናቱን ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ማዛወሩ መፍትሔ አድርጎ ማየቱን በመተው ዘላቂ መፍትሔ እንዲሻ መክረዋል፡፡ ‹‹የፖለቲካ ሹመት አስፈላጊ እንደሆነ እገነዘባለሁ፡፡ ነገር ግን የፖለቲካ ታማኝነትና ወገንተኝነት ለሁሉም ነገር መሥፈርት መሆን የለበትም፡፡ ኃላፊነት በዕውቀትና በሥነ ምግባር መመዘን አለበት፡፡ ግለሰቦችን መቀያየር መፍትሔ  አይሆንም፡፡ አጠቃላይ ሥርዓቱ መዋቅራዊና የአስተሳሰብ ችግር ነው ያለበት፤››  ብለዋል፡፡

ለሌሎች አስተያየት ሰጪዎች ደግሞ የአምባሳደሮቹ ሹመት ከጥቂት ወራት በፊት የነበረውን ሹምሽር ያልተጠና ያስመሰለ ነው፡፡ ፕሮፌሰር በየነም በተመሳሳይ ዕርምጃው የተረጋጋ መንግሥት አለመኖሩን የሚያሳይ ነው ነው ሲሉ ተከራክረዋል፡፡ ‹‹የካቢኔ ሚኒስትሮቹ በቅርቡ የተሾሙ ናቸው፡፡ በወራት ውስጥ ሌላ ብወዛ መደረጉ በአገሪቱ የተረጋጋ መንግሥት እንደሌለ ማረጋገጫ ነው፤›› ብለዋል፡፡

የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና በአምባሳደርነት መሾማቸው በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ላይ ለሚነሳው የገለልተኝነት ጥያቄ ማረጋገጫ አድርገው ያዩትም አሉ፡፡ ፕሮፌሰር በየነ፣ ‹‹ፕሮፌሰር መርጋ ገለልተኛ እንዳልነበሩ በጉልህ ይታይ ነበር፡፡ ፍርደ ገምድል ውሳኔ ሲያሳልፉና በደንታ ቢስነት ብዙ ጥፋት ሲያጠፉ የነበሩ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡

አቶ ልደቱ ግን የምርጫ ቦርድ ችግር ከአንድ ግለሰብ ጉዳይ የዘለለ እንደሆነ በማስታወስ፣ የፕሮፌሰር መርጋ ሹመትን የገለልተኝነት መለኪያ ማድረግ ስህተት ነው ሲሉ ሞግተዋል፡፡ ‹‹በእኔ አመለካከት የምርጫ ቦርድ ጉዳይ የአንድ ግለሰብ ጉዳይ አይደለም፡፡ እንዲያውም የምርጫ ቦርድ ዋና ኃላፊ አጠቃላይ ምርጫውን በማስፈጸም ረገድ ያላቸው ሚና ያን ያህል አይደለም፡፡ የምርጫ ቦርድ የገለልተኝነት ጉዳይ ከላይ እስከ ታች ያለ ነው፡፡ ችግሩ ተቋማዊ ነው፤›› ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡

አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች የትምህርት ሚኒስትሩ፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንትና የቦርድ ሰብሳቢው አንድ ላይ መነሳት የትምህርት ዘርፉ በአጠቃላይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ በተለይ ችግር እንዳለባቸው ማሳያ እንደሆነ ይጠቅሳሉ። ፕሮፌሰር በየነ፣ ‹‹አንጋፋው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሒሳቡን ባለማወራረዱ በከፍተኛ ሁኔታ ተጠያቂነት ያልሰፈነበትና በዚህ ረገድ ብቃት ያጣ ነበር፡፡ የቦርዱ ሰብሳቢ፣ፕሬዚዳንቱና ሚኒስትሩ መነሳታቸው ከዚህ ጋር የተያያዘ ይመስለኛል፡፡ ለዚህም የተሰጣቸውን አዲሱን ኃላፊነት ሹመት አድርጌ አልቆጥረውም፡፡ ችግሩ ግን በሌሎች ዩኒቨርሲቲዎችም የሚስተዋል ነው፤›› ሲሉ ከዚሁ ግምገማ ጋር እንደሚስማሙ አመልክተዋል፡፡

አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ግን አገሪቱ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአስተዳደር ረገድ ከገጠማት ዘርፈ ብዙ ችግሮች አኳያ ማን ተነሳ ሳይሆን ማን ነው የሚተካው የሚለው ይበልጥ አሳሳቢ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ 

Standard (Image)

የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታና ተሸላሚዎቹ

$
0
0

ኢትዮጵያ ከአፍሪካ በግዙፍነት ታላቅ የሆነውን የታላቁ ህዳሴ ግድብ ለመገደብ የመሠረት ድንጋይ ከጣለች ስድስት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ኢትዮጵያውያንም የግድቡን መጠናቀቅ በጉጉት በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ፡፡ በግድቡ መጠናቀቅ ብዙ ነገሮች እንደሚቀየሩም ተስፋ አድርገዋል፡፡

ምቹ የሆነ የአየር ንብረት፣ ለማዕድንና ለተለያዩ መሠረተ ልማቶች የሚውል መሬት፣ ለኤሌትሪክ ኃይል ማመንጫ የሚውሉ ወንዞችና ተፋሰሶች ያሏት አገር እስከ ዛሬ ድረስ ከድህነት መውጣት አለመቻሏ የብዙዎች ቁጭት ነበር፡፡ ይህ ግድብ እስከ 6,000 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል እንደሚያመነጭ ይጠበቃል፡፡ ግድቡ በአሁኑ ወቅት ከግማሽ በላይ ሥራው ተጠናቋል፡፡ የኢትዮጵያን የኤሌክትሪክ ኃይል ችግር ከመፍታቱ ባሻገር፣ አገሪቱ ለማደግ በምታደርገው ሁለንታዊ እንቅስቃሴ የጀርባ አጥንት ሆኖ እደሚያገለግልም ይጠበቃል፡፡ አገሪቱ ከፍተኛ የሆነ ኃይል የማመንጨት ዕምቅ አቅም ቢኖራትም ሳትጠቀምበት ቆይታለች፡፡

ሚያዚያ 24 ቀን 2003 ዓ.ም. የግድቡ የመሠረት ድንጋይ ሲቀመጥ የቀድሞው  ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ‹‹የግድቡ መሐንዲሶች እኛ፣ የገንዘብ ምንጮቹ እኛው . . . ነን፤›› በማለት ንግግር  ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡ በወቅቱ ይህን የተናገሩት ኢትዮጵያ የዓባይን ወንዝ ገድባ የኤሌክትሪክ ኃይል ለማመንጨት መንቀሳቀስ ስትጀምር የግብፅ መንግሥት ዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት ለኢትዮጵያ ምንም ዓይነት የገንዘብ ድጋፍ እንዳያደርጉ ያደርግ በነበረው ውትወታና ጥያቄ መሠረት፣ አበረታች ምልክት ባለመስጠታቸው የተነሳ እንደሆነ ይነገራል፡፡ የህዳሴ ግድብ የመሠረት ድንጋይ መጣሉን የተረዳው የአገሬው ሕዝብም ከጫፍ እስከ ጫፍ ደስታውን የገለጸበት ወቅት እንደነበር ይታወሳል፡፡

የግብፅ የዓባይን ወንዝ ለብቻዬ ልጠቀም አባዜ ተሽሮ ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ኢትዮጵያ ተጠቅማ ሌሎች የተፋሰሱ አገሮች እንዲጠቀሙ እየተሄደበት ያለው መንገድም በብዙዎች ዘንድ ደስታ የፈጠረ ነበር፡፡

የግድቡ የመሠረት ድንጋይ ከተጣለ ወዲህ የኅብረተሰቡ ተሳትፎ እንደቀጠለ መሆኑም እየተገለጸ ነው፡፡ የህዳሴ ግድቡ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ኃይሉ አብርሃም ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በአሁኑ ወቅት የግድቡ የግንባታ ሒደት 58.4 በመቶ ላይ ይገኛል፡፡ ፕሮጀክቱ ይፈጃል ተብሎ የተገመተው ገንዘብ 80 ቢሊዮን ብር ነው፡፡ እስካሁን ድረስ ከኅብረተሰቡ አሥር ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡

የሕዝቡ ተሳትፎ በገንዘብ ሲተመን ከ10 እስከ 15 በመቶ ይጠበቅ እንደነበር የገለጹት አቶ ኃይሉ፣ በአሁኑ ወቅት ስምንት በመቶ መድረሱንና ይህም ተሳትፎ በጥሩ ሁኔታ እየቀጠለ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ይህን የኅብረተሰብ ተሳትፎ ቀጣይነት ለማረገገጥ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪ ብሔራዊ ምክር ቤት ጽሐፈት ቤት በ2008 እና በ2009 ዓ.ም.  ባዘጋጃቸው ሁነቶችና ፕሮጀክቶች ላይ ሁለንተናዊ ድጋፍ ላደረጉ ተቋማትና ግለሰቦች ሰኞ ሐምሌ 24 ቀን 2009 ዓ.ም. የምሥጋና ፕሮግራም አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በሒልተን ሆቴል በተዘጋጀው በዚህ የምሥጋና ፕሮግራም ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የህዳሴ ግድቡ ሕዝባዊ ተሳትፎ ብሔራዊ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ደመቀ መኮንን፣ የመገናኛና ቴክኖሎጂ ሚኒስትርና የምክር ቤቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ደብረ ፅዮን ገብረ ሚካኤል፣ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሯ ዶ/ር ሒሩት ወልደ ማርያም የምክር ቤቱ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሮማን ገብረ ሥላሴ፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ ባለሀብቶችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተጋብዘው ነበር፡፡

በዕለቱ በተዘጋጀው የሽልማትና የምሥጋና ፕሮግራም ላይም ባለፉት ሁለት ዓመታት ግደቡ ዕውን እንዲሆን የተሻለ አስተዋጽኦ ያደረጉ አካላት ተሸልመዋል፡፡

በዚህ የሽልማት ፕሮግራም ላይ የተመሠገኑት አካላት በተሳትፎአቸው መሠረት አንደኛ ደረጃ የወርቅ ሽልማት፣ ሁለተኛ ደረጃ የክሪስታል ዋንጫ ሽልማት፣ ሦስተኛ ደረጃ የላቀ የምስክር ወረቀትና አራተኛ ደረጃ የምስክር ወረቀት አግኝተዋል፡፡

አንደኛ ደረጃ የወርቅ ሽልማት የሚባለውን የሽልማት ዓይነት ያገኙት ዘጠኙ ክልሎችና ሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች ናቸው፡፡ ሁለተኛ ደግሞ የክሪስታል ዋንጫ ሽልማት የተሰኘውን ሽልማት ያገኙት 46 ተቋማትና ግለሰቦች ናቸው፡፡ አራተኛ ደረጃ የምስክር ወረቀት የተሰኘውን የሽልማት ዓይነት ያገኙ ተቋማት ከ350 በላይ እንደሆኑ የተጠቆመ ሲሆን፣ በአጠቃላይ ለዚህ ሽልማት የበቁ ተቋማትና ግለሰቦች ቁጥር ከ460 በላይ እንደሆነ በዕለቱ ይፋ ሆኗል፡፡

በሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ላይ የመግቢያ ንግግር ያደረጉት ወ/ሮ ሮማን፣ ‹‹የዓባይ ወንዝን ለመገደብ ምንም ዓይነት ልዩነት ሳያግደን በጠንካራ ኅብረ ብሔራዊ ክንዳችን ታላቁ የህዳሴ ግድባችንን ከግማሽ በላይ አድርሰነዋል፤›› ብለዋል፡፡ የህዳሴ ግድቡ ጠቅላላ የሥራ ክንውን 58 በመቶ በላይ እንደደረሰ የተገለጸ ሲሆን፣ ከአሁን በኋላ የሚቀረው ሥራ ቀላል እንደሆነና በአጭር ጊዜ ተጠናቆ ወደ ሥራ እንደሚገባ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ አንድ ከፍተኛ ኃላፊ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድቡን የመሠረት ድንጋይ ከጣለች በኋላ በግብፅ በኩል የተለያየ አቋም ሲያዝ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በቅርቡ የቀድሞው የግብፅ ፕሬዚዳንት የነበሩት ሆስኒ ሙባረክ እስከ ዛሬ ድረስ ሥልጣን ላይ ቢቆዩ ኑሮ ግድቡን ሊያፈርሱት እንደሚችሉ ስለመናገራራው ሪፖርቶች መውጣታቸው አይረሳም፡፡

በተቃራኒው ደግሞ በአሁኑ ወቅት የግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ከተፋሰስ አገሮች ጋር ተቀራርበው  ለመሥራት ዝግጁ መሆናቸው  ይታወቃል፡፡ ምንም እንኳ ግብፅ የዓባይ ወንዝን ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ለመጠቀም የተፋሰስ አገሮች ያረቀቁትን ስምምነት እስከ ዛሬ ድረስ ባትፈርምም፣ ወደ ስምምነት መድረኩ መጥታ መደራደር መጀመሯ ትልቅ እመርታ እንደሆነ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ ግብፅ ቀደም ሲል እ.ኤ.አ. በ1929 በኋላ ደግሞ በ1959 ከሱዳን ጋር በመሆን የዓባይ ወንዝን ለብቻቸው ለመጠቀም ስምምነት መድረሷ ይታወሳል፡፡

በአሁኑ ወቅት የህዳሴ ግድቡ በተፋሰስ አገሮች ላይ ሊያሳድር የሚችለውን ተፅዕኖ ለመረዳት ኢትዮጵያ፣ ሱዳንና ግብፅ ዓለም አቀፍ አጥኝ ቡድኖችን ቀጥረው እያሠሩ መሆኑ ይታወቃል፡፡

ኢትዮጵያ በዚህ ሒደት ውስጥ የገባችው መተማመን ለመፍጠር እንጂ የግንባታው ዕጣ ፈንታ ላይ ውሳኔ ለማሳለፍ እንዳልሆነ ደጋግማ ትገልጻለች፡፡ በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያ ግንባታውን ሌትና ቀን እያከናወነች ነው፡፡ የዚህን ግድብ ግንባታ ጫፍ ለማድረስም ብሔራዊ ምክር ቤቱ የተለያዩ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅቶችን ከማዘጋጀት ባሻገር፣ ዜጎች የማያቋርጥ ሁለንተናዊ ድጋፋቸውን እንዲያደርጉ ጥሪ እያደረገና ለዚህም በጎ ምላሽ እያገኘ መሆኑን አቶ ደመቀ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ታላቁ የህዳሴ ግድብ የአገራችንን ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ይበልጥ እያጎለበተ ከመምጣቱ በላይ፣ ከጎረቤት አገሮች ጋር ያለንን የዲፕሎማሲ ግንኙነት በማዳበር በመተማመንና በመተባበር መኖር እንድንችል የመሠረት ድንጋይ ሆኗል፤›› በማለት ገልጸዋል፡፡

የዚህ ሽልማት መዘጋጀት ዓላማም ቀሪ ሥራውን ዕውን ለማድረግ የሚያስችል ጉልበት ለመፍጠር እንደሆነም አቶ ደመቀ ተናግረዋል፡፡ በዕለቱ አንደኛ ደረጃ የወርቅ ሽልማት የተሰኘውን ሽልማትና ምሥጋና ያገኙት ዘጠኙ ክልሎችና ሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች ናቸው፡፡ ሁለተኛ ደረጃ ክሪስታል ዋንጫ ተሸላሚዎች መካከል ደግሞ ኢትዮ ቴሌኮም፣ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪነግ ኮርፖሬሽን፣ ሞኤንኮ፣ ቢጂአይ ኢትዮጵያ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ የኢትዮጵያ አየር ኃይል፣ ጊፍት ሪል ስቴት፣ አዲስ ፓርክ ዴቨሎፕመንት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ ሸራተን  አዲስ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ አምቼ፣ ሪየስ ኢንጂነሪንግ፣ ኒያላ ሞተርስ ኮርፖሬሽን፣ ሰንሻይን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ ኢኳቶሪያል ቢዝነስ ግሩፕ፣ ማራቶን ሞተርስ፣ በጥረት ኢንተርናሽናል ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ ኢትዮ ኒፖንና ሆራ ትሬዲንግድ ናቸው፡፡ በዚህ ዘርፍ ስፖርታዊ ሒደቱን በመደገፍና በማስተባበር የተሸለሙት ደግሞ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽንና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ናቸው፡፡

በማስታወቂያ ሥራዎች ሁለተኛ ደረጃ የክሪስታል ተሸላሚ ከሆኑ ተቋማትና ግለሰቦች መካከል ደግሞ ሳምሶን አድቨርታዚንግ፣ ደቦል መልቲ ሚድያ ፕሮዳክሽን፣ አንበሳ ማስታወቂያ፣ ሠራዊት መልቲ ሚድያ፣ ሸዋፈራሁ ማስታወቂያ፣ ርሆቦት ፕሮሞሽን ናቸው፡፡ በዚህ ዘርፍ ተሸላሚ ከሆኑት የሚድያ ተቋማት መካከል ደግሞ የኢትዮጵያ ብሮድ ካስቲንግ ኮርፖሬሽን፣ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት፣ አዲስ አበባ መገናኛ ብዙኃን ኤጀንሲና የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ (ኢቢኤስ) ናቸው፡፡

በዚሁ ዘርፍ ሙያዊ ድጋፍ በማድረግ የተሸለሙት ደግሞ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሸንና ብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር ናቸው፡፡ ለተለያዩ ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ የሚሆን ገንዘብ በማዋጣት ድጋፍ አድርገው ከተሸለሙት መካከል ደግሞ ቫርኔሮ ሪል ስቴት፣ ዳሸን ባንክ፣ አቢሲኒያ ባንክ፣ ኦሮሚያ ኢንተርናሽናል ባንክ፣ ዓባይ ባንክ፣ ወጋገን ባንክ፣ አንበሳ ኢንተርናሽናል ባንክ፣ ኦሮሚያ ኅብረት ሥራ ባንክ፣ የብሔራዊ አደጋ ሥራ አመራር ኮሚሽንና በላይነህ ክንዴ አስመጭና ላኪ ይገኙበታል፡፡

በዕለቱ በተዘጋጀው የሽልማት ሥነ ሥርዓት ላይ ሦስተኛ ደረጃ  የላቀ የምስክር ወረቀት ተሸላሚ የሆኑ ግለሰቦችና ተቋማት በአሥር የተለያዩ ዘርፎች ተለይተው ለሽልማት በቅተዋል፡፡ ከእነዚህ ግለሰቦችና ተቋማት መካከል ደግሞ ጥቂቶቹ ሐበሻ ዊክሊ፣ ቦስተን ፓርትነር፣ ዋቢ ሸበሌ ሆቴል፣ የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ሚኒስቴር፣ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት፣ አልታ ኮምፒውተር፣ ስናፕ ኮምፕዩተርና ዮናስ ታደሰ ይገኙበታል፡፡

በዚሁ ዘርፍ ተሸላሚ ከሆኑ የሚዲያ ተቋማት መካከል ጥቂቶቹ ናሁ ቲቪ፣ ጄ ቲቪ፣ ቃና ቲቪ፣ ዛሚ ኤፍኤም፣ ብሥራት ኤፍኤም፣ ሸገር  ኤፍኤም፣ ኦሮሚያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ድርጅት፣ ሪፖርተር ጋዜጣ፣ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት፣ ፕሬስ ድርጅት፣ ሰንደቅ ጋዜጣና የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ይገኙበታል፡፡ በዚሁ የሽልማት ዘርፍ ሌሎች ያልተጠቀሱ ተቋማትና ግለሰቦች ለሽልማት በቅተዋል፡፡   

በአሁኑ ወቅት የህዳሴ ግድቡ 24 ሰዓት የግንባታ ሒደቱ እየተከናወነ ሲሆን፣ የግድቡ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት የሕዝቡ ተሳትፎ እንዳይቆምና ከዚህ በተሻለ ሁኔታ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በማሰብ የምሥጋናና የሽልማት ፕሮግራም ማዘጋጀቱን ገልጿል፡፡ በዚህ ግድብ ሁሉም ኢትዮጵያዊ አሻራውን እንዳስቀመጠ እየተናገረ ሲሆን፣ መንግሥት ደግሞ የተሻለ ተሳትፎ የነበራቸውን ግለሰቦችና ተቋማት በአቋራጭ ሸልሟል፡፡

ፖለቲካዊ አንድምታው ጉልህ የሆነው ይህ ግድብ በአሁኑ ወቅት በሦስቱ አገሮች ማለትም በኢትዮጵያ፣ በግብፅና በሱዳን ስምምነት መሠረት ግድቡ ሊኖረው የሚችለውን ተፅዕኖ ለማስጠናት ዓለም አቀፍ የአጥኝዎች ቡድን ተቋቁሞ አያጠና መሆኑ ይታወቃል፡፡

በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የድንበርና ድንበር ተሻጋሪ ሀብቶች ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር ሸምሰዲን አህመድ ማክሰኞ ሐምሌ 25 ቀን 2009 ዓ.ም. ለሪፖርተር፣ ‹‹ኢትዮጵያ ይህን ግድብ ገንብታ ድህነትን ከመቅረፏ ባሻገር ለታችኞቹ ተፋሰስ አገሮችም ጠቃሚ ነው፡፡ ይሁንና በዚህ ጉዳይ ላይ ጥያቄ የሚያነሳ አካል ካለ  ዓለም አቀፍ ፓናል ኦፍ ኤክስፐርትስ ተቋቁሞ ሊያየው ይችላል ማለት፣ ኢትዮጵያ ይህን ክፍት አድርጋ በአሁኑ ወቅት ዓለም አቀፍ አጥኝዎችን በመሰየምና ከሦስቱ አገሮች ባለሙያዎችን በመመደብ እ.ኤ.አ. ከመስከረም 2014 ጀምሮ ጥናት እየተደረገ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ይህን ጥናት የሚያካሂዱት የፈረንሣይ ኩባንያዎች ሲሆኑ አንደኛና ዋነኛው ኩባንያ ቢአርኤልአይ ሲሆን ሁለተኛው ኩባንያ ደግሞ አርቲሊያ ነው፡፡ እነዚህ ኩባንያዎች ሥራቸውን የሚያከናውኑት ሦስቱ አገሮች ባስቀመጡት መመርያ መሠረት እንደሆነም አምባሳደር ሸምሰዲን ጠቁመዋል፡፡ እስካሁን ድረስ እነዚህ ሦስቱ አገሮች 13 ዙር ውይይቶች እንዳደረጉ አስረድተዋል፡፡

 እነዚህ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች እያደረጉት ያለውን ጥናት በየጊዜው ለአገሮቹ እያቀረቡና እያስገመገሙ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ እስካሁን ድረስ እያቀረቡት ባለው የጥናት ውጤትም በብዙ ጉዳዮች ላይ ስምምነት መድረስ አመቻላቸው እየተገለጸ ሲሆን፣ አምባሳደር ሸምሰዲን ደግሞ፣ ‹‹ካይሮ ላይ ተካሂዶ በነበረው 13ኛው ሰብሰባ ላይ ስምምነት ያልደረስንባቸው ጉዳዮች ነበሩ፡፡ ነገር ግን በግንቦት ወር አዲስ አበባ ባካሄድነው 14ኛው ዙር ስብሰባ ልዩነታችንን በመፍታት አጥኝዎቹ ሥራቸውን እንዲቀጥሉ ተደርጓል፤›› ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት አጥኝ ቡድኑ ሥራን በተገቢው ሁኔታ እያካሄደ መሆኑን ጠቁመው፣ 15ኛው ዙር ስብሰባ በሱዳን ካርቱም እንደሚካሄድ አስታውቀዋል፡፡

ለእነዚህ ዓለም አቀፍ አጥኝ ኩባንያዎች የሚከፈለውን ክፍያ ሦስቱ አገሮች እኩል አዋጥተው እንደሚከፍሉ መስማማታቸው ይታወሳል፡፡

 

  

Standard (Image)

የከፍተኛ አመራሩ ተጠያቂነት የት ድረስ ነው?

$
0
0

 

ዶ/ር ዋባና ኩንደር ይባላሉ፡፡ በጋናውያን ዘንድ ሚኒስትር ዱምሶር (Dumsor) በሚባል ቅፅል ስማቸው ይታወቃሉ፡፡ ዶ/ር ዋባና እ.ኤ.አ. በ2014 የጋና የኤሌክትሪክ ሚኒስትር ሆነው በአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሲሾሙ ትልቅ ኃላፊነት ተጥሎባቸዋል፡፡ ጋናን በወቅቱ ከነበረችበት የኃይል አቅርቦት ችግር ማውጣት ዋና ተልዕኳቸው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ እ.ኤ.አ ከ2012 ወዲህ ተባብሶ የቀጠለው የኃይል አቅርቦት መቆራረጥና ጭለማ፣ የጋናውያን በተለይም የዋና ከተማዋ አክራ ሕይወት ነበር፡፡ ፋብሪካዎች ሠራተኞቻቸውን የመቀነስ ሒደት ውስጥ ገብተው ነበር፡፡ ተስፋ የተጣለባቸው ሚኒስትር ልፋትም ተስፋን መፈንጠቅ አልቻለም፡፡ ይልቁንም ‘ሚኒስትር ዱምሶር’ በሚባል ቅጥያ ስም እንዲጠሩ ምክንያት ሆነባቸው፡፡ ጋናውያን ዱምሶር የሚሉት ሁለት የእንግሊዝኛ ቃላትን ‘Dum’ እና ‘Sor’ ገጣጥመው ነው፡፡ ትርጓሜውም ብልጭ ድርግም እንደ ማለት ነው፡፡

ፋታ የማይሰጥ ችግርን በአጭር ጊዜ እንዲፈቱ ኃላፊነት የተሰጣቸው ሚኒስትሩ ግን፣ በማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ እየሸነገሉ መኖርን አልመረጡም፡፡ አ.ኤ.አ በዲሴምበር 2015 ከተሾሙ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ በገዛ ፈቃዳቸው ሥልጣናቸውን ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርበው ተቀባይነትን አግኝተዋል፡፡

ከላይ የተገለጸው በአፍሪካ ዘመናዊ የዴሞክራሲ ታሪክ ተጠቃሽ ከሆነችው ጋና የተገኘ ነው፡፡ ባለፈው ሰኔ ወር በእንግሊዝ ለንደን ግሪንፌል የመኖርያ አፓርትመንት ላይ በደረሰው ቃጠሎ፣ ከ80 በላይ ሰዎች ተቃጥለው ሕይወታቸው ማለፉ ይታወሳል፡፡

በዚህ አደጋ የተቆጡ እንግሊዛውያንና የአገሪቱ የሚዲያ ተቋማት በፈጠሩት ጫና፣ አደጋው የተከሰተበት የኬንሲንግተንና የቼልሲ ዲስትሪክት ካውንስል መሪ ሚስተር ኒክ ፓጌት ብራውን በፈቃዳቸው ሥልጣናቸውን ለቀዋል፡፡ ‹‹በደረሰው አደጋ ከፊል ኃላፊነት እወስዳለሁ፤›› ሲሉም ተደምጠዋል፡፡

በተለያዩ አገሮች ከፍተኛ ባለሥልጣናት ኃላፊነታቸውን ባለመወጣታቸው፣ እንዲሁም ጥፋት በመፈጸማቸው ራሳቸውን ከኃላፊነት በማንሳት ሞራላዊ ግዴታቸውን ሲወጡ በአገሪቱ የፍትሕ አካላትም በሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ ይደረጋሉ፡፡

በኢትዮጵያ ግን ይህ ሲሆን አይታይም፡፡ በሥራ አፈጻጸሙ የተተቸ አመራር ወደ ሌላ ኃላፊነት ሲዘዋወር ወይም በዲፕሎማሲ የሥራ ዘርፍ በአምባሳደርነት ሲመደብ ማየት የተለመደ እየሆነ መጥቷል፡፡ ሕግን የተላለፉ ከፍተኛ አመራሮችም ፖለቲካዊ ከለላ ሲሰጣቸው እንጂ በሕግ ሲጠየቁ አይታይም፡፡

ባለፉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ የአገሪቱ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ባካሄደው የፀረ ሙስና ዘመቻ 50 የሚሆኑ መካከለኛ አመራሮችንና ባለሀብቶችን በቁጥጥር ሥር አውሏል፡፡ በቁጥጥር ሥር የዋሉት ተጠርጣሪዎች በአገሪቱ ላይ የአራት ቢሊዮን ብር ጉዳት እንዳደረሱ መንግሥት የሰጠው መግለጫ ያመለክታል፡፡

ይህንን ዕርምጃ በርካታ ኢትዮጵያውያን ያደነቁት ቢሆንም፣ ተመሳሳይ መጠን ያላቸው ኢትዮጵያውያን ደግሞ ለሙስና መንሰራፋት በር የከፈቱ ከፍተኛ አመራሮች በሕግ የማይጠየቁበት የፀረ ሙስና ዘመቻ የትም አይደርስም ሲሉ ይተቻሉ፡፡

መንግሥት ስለወሰደው የፀረ ሙስና ዘመቻና በቁጥጥር ሥር ስላዋላቸው አመራሮች፣ ቅዳሜ ሐምሌ 22 ቀን 2009 ዓ.ም. በጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ አቶ ጌታቸው አምባዬ አማካይነት መግለጫ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

በዚህ መግለጫ ላይ ከፍተኛ አመራሩ ለምን በሕግ ተጠያቂ እንደማይሆን ማብራሪያ እንዲሰጡ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ ተጠይቀው ነበር፡፡ በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹የመንግሥት ከፍተኛ ኃላፊዎች ብለን የምናስበው በሚኒስትርና በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ ብቻ ያሉትን ከሆነ ስህተት ይሆናል፡፡ ለእኔ እስከሚገባኝ ድረስ የመንግሥት ኃላፊነት ደረጃ ላይ ከፍተኛ የመወሰን ድርሻ ያለው በዳይሬክተርነት ደረጃ ያለው ኃይል ነው፤›› ብለዋል፡፡

በማከልም፣ ‹‹አንዳንድ ወገኖች መንግሥት ሚኒስትርና ሚኒስትር ዴኤታ ካልተጠየቀ ራሱን አላየም የሚሉት ጉዳይ የዋህነት ነው፡፡ ምክንያቱም የመንግሥት ሀብትና ገንዘብ በስፋት የማንቀሳቀስና የማሰማራት ኃላፊነት የተሰጠው ኃይል በዳይሬክተርነት ደረጃ ያለው ኃይል ነው፡፡ ጉዳዮችን የሚያመቻቸውና የሚፈጽመው ይኼ ኃይል ነው፡፡ ይህ ኃይል በሚያቀርባቸው የውሳኔ ሐሳቦችና ሙያዊ አስተያየቶች ላይ ተመሥርቶ ሚኒስትሩ ወይም ሚኒስትር ዴኤታው ሊወስን ይችላል፡፡ ይህ ማለት ግን ኃላፊነት የለበትም አይደለም፡፡ ኔትወርክ ውስጥ ገብተው ከተገኙ ተጠያቂ ከመሆን አያመልጡም፤›› የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

ከፍተኛ አመራሩ ማነው?

ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ በሰጡት መግለጫ በመንግሥት የኃላፊነት ደረጃ ላይ ከፍተኛ የመወሰን ድርሻ ያለው በዳይሬክተር ደረጃ ያለው መሆኑንና የከፍተኛ አመራሩ ሚና ተቋምን የመምራትና የማንቀሳቀስ ኃላፊነት ነው ቢሉም፣ የአገሪቱ የተለያዩ ሕጎች ግን በተቃራኒው ነው የሚደነግጉት፡፡

ሀብትን ለማሳወቅና ለማስመዝገብ የወጣው አዋጅ 668/2002 የመንግሥትን አሠራር በግልጽነትና በተጠያቂነት መመሥረት አስፈላጊ በመሆኑ፣ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች የግል ጥቅማቸውንና ኃላፊነታቸውን ሳይቀላቅሉ መሥራት እንዲችሉ ሀብትና ንብረታቸውን ማስመዝገብ እንዳለባቸው ይደነግጋል፡፡

በዚህ አዋጅ መሠረት የአገሪቱ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮችን ተሿሚዎች የሚል ስያሜ ይሰጣቸዋል፡፡ በትርጉሙም የአገሪቱ ፕሬዚዳንት፣ ጠቅላይ ማኒስትር፣ ሚኒስትሮች፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ ምክትል ሚኒስትሮች፣ ኮሚሽነሮች፣ ምክትል ኮሚሽነሮች፣ ዋና ዳይሬክተሮችና ምክትሎች መሆናቸውን ያስቀምጣል፡፡

በተመሳሳይ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ ለመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች ወይም የፌዴራል መንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ተመሳሳይ ትርጓሜ ይሰጣል፡፡ የመንግሥት ሠራተኞች በሚለው ትርጓሜ ሥር ደግሞ በተቋማት ውስጥ የሚገኙ ዳይሬክቶሬት ኃላፊዎና ከዚያ በታች ያሉ ሠራተኞች መሆናቸውን ይገልጻል፡፡

በሌላ በኩል ከፍተኛ የልማት ሥራዎችን የሚያንቀሳቅሱ የመንግሥት ልማት ድርጅቶች መሆናቸው ይታወቃል፡፡ የመንግሥት ልማት ድርጅቶች አዋጅ ቁጥር 25/1992 ድንጋጌ መሠረት በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ውስጥ ለሚፈጸሙ ጥፋቶች ሥራ አስፈጻሚዎች ብቻ ሳይሆኑ፣ የቦርድ አመራሮች ጭምር ሕጋዊ ተጠያቂነት እንደሚወድቅባቸው ይደነግጋል፡፡

ከአዋጁ ድንጋጌዎች መካከል የአንድ የልማት ድርጅት ቦርድ የተቋሙን የሥራ አመራር እንደሚሾምና ከሥራ እንደሚያሰናብት ይደነግጋል፡፡ የቦርድ አመራሮች የሥራ ኃላፊነታቸውን በጥንቃቄ እንደሚወጡ፣ ሥራቸውን በአግባቡ ባለመወጣታቸው በተቋሙ ላይ ለደረሰው ጉዳት በቡድንና በተናጠል ተጠያቂ እንደሚሆኑ ይደነግጋል፡፡

የመንግሥት ልማት ድርጅቶች የሥራ አመራሮች (ማኔጀሮች) ተጠሪነት ለቦርድ መሆኑን፣ በቸልተኝነትም ይሁን ሆን ተብሎ ለደረሰ ጉዳት በሕግ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ይደነግጋል፡፡

በመሆኑም ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ የሰጡት አስተያየት ሕጋዊ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ያመለክታል፡፡

ፖለቲካዊ አንድምታ

ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ጌታቸው አምባዬ በሰጡት መግለጫ ከፍተኛ አመራሩን ከተጠያቂነት ያገለለ አስተያየት መስጠታቸው፣ የፖለቲካ ስህተት መሆኑንና ከአገሪቱ ዓቃቤ ሕግ የማይጠበቅ ሲሉ የተለያዩ ባለሙያዎች እየተቹት ይገኛሉ፡፡

አቶ ውብሸት ሙላት የሕግ ባለሙያ ሲሆኑ ለሪፖርተር በሰጡት አስተያየት፣ የሚኒስትሮችና የሚኒስትር ዴኤታዎች ሚና የፖለቲካ አቅጣጫ መስጠት ነው የተባለው አስገራሚ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡

ለአብነት የአገሪቱን የፋይናንስ አስተዳደር ሕግ የሚጠቅሱት አቶ ውብሸት፣ ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ የሆነ ግዥ ያለ ሚኒስትሩ ይሁንታ (ውሳኔ) ሊፈጸም እንደማይችል ያስረዳሉ፡፡

በመንግሥት ተቋማት ከከፍተኛ አመራሩ በታች ያለው የፋይናንስ ክፍል ኃላፊ ከ500 ሺሕ ብር በታች የተመለከቱ ወጪዎች ላይ ብቻ የመወሰን ሥልጣን እንዳለው በሕጉ መደንገጉን ያስረዳሉ፡፡ በመሆኑም አንድ ግለሰብ በሚኒስትርነት ሲሾም ዝም ብሎ ፊርማውን እንዲያስቀምጥ ሳይሆን፣ እያንዳንዱን የተቋሙን እንቅስቃሴዎች ለመከታተል መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌዴራሊዝም ጥናት ማዕከል መምህር የሆኑት አቶ ናሁሰናይ በላይ በበኩላቸው፣ ‹‹ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ ያላገናዘቡት ለሙስና ምቹ የሆነ ሁኔታ የፈጠረው አመራር ተጠያቂ መሆን እንዳለበት ነው፤›› ብለዋል፡፡

ለሙስና ምቹ ሁኔታን የፈጠረ፣ እያየ እንዳላየ የሆነና በሰዓቱ እንዲቀጣ ያላደረገ በሙሉ ተጠያቂነት ሊኖርበት እንደሚገባ ይከራከራሉ፡፡ ‹‹ሙስና ሠረቀ አልሠረቀም ብቻ አይደለም፡፡ በአንድ ጊዜ ውጊያ ወይም እሳት ለማጥፋት በሚደረግ እንቅስቃሴ የማይፈታ  ውስብስብ ተግባር ነው፤›› ብለዋል፡፡

ቀደም ሲል በዓቃቤ ሕግነት ያገለገሉት የሕግ ባለሙያ አቶ ዮሐንስ ወልደ ገብርኤል በበኩላቸው፣ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ በሰጡት መግለጫ ተጠርጥረው የተያዙት አመራሮች ከፍተኛ ባለሥልጣናት መሆናቸውን ለመግለጽ የተጠቀሙበት መንገድ፣ የታሰሩትን ግለሰቦች በፍርድ ቤቶችና በዓቃቢያነ ሕጎች ዘንድ ጥፋተኛ ሆነው እንዲገመቱ ያደርጋል ሲሉ ተችተዋል፡፡

‹‹እንደምናውቀው ዓቃቤ ሕግ ከፖሊስ የተቀበለውን መረጃና ማስረጃ መርምሮ አልጨረሰም፡፡ በመሆኑም ገና ክስ አልተመሠረተም፡፡ ታዲያ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ ዋነኛ ሙሰኞች እነማን እንደሆኑ ቀድመው ተናግረው፣ ዓቃቢያነ ሕጎች እንዴት አድርገው ነው በነፃነት ክስ የሚመሠርቱት?›› ሲሉ ይሞግታሉ፡፡

በዚህ አገር ላለፉት ዓመታት ሙስና በዘመቻና በዙር በተመሳሳይ መንገድ ሲካሄድ እንደቆየና በዚያው መንገድ መቀጠሉን አቶ ዮሐንስ ያምናሉ፡፡ ‹‹ከአቶ ታምራት ላይኔ ጀምሮ ይኼኛው ዘጠነኛ ዙር ዘመቻ ነው፤›› ይላሉ፡፡

በጉዳዩ ላይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ባለሙያዎች በጋራ የሚስማሙት ግን፣ ሙስና በዙር የሚካሄድ ወይም የፖለቲካ ትኩሳት በተነሳ ቁጥር ለማብረድ የሚዘመትበት ሳይሆን፣ ንቁ ሥርዓት መፍጠር የሚጠይቅ የማያቋርጥ ዘመቻን የግድ የሚል መሆኑን ያሳስባሉ፡፡ (ሰለሞን ጎሹ ለዚህ ዘገባ አስተዋጽኦ አድርጓል) 

Standard (Image)

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከስድስት ዓመታት በኋላ

$
0
0

 

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የግንባታ ሒደት በአሁኑ ወቅት 60 በመቶ እንደደረሰ መንግሥት ሰሞኑን ይፋ አድርጓል፡፡ ለስድስት ዓመታት ያህል በግንባታ ላይ ያለው ይህ ግድብ እስከ አሁን ድረስ ከ45 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበት መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ምንም እንኳ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በአምስት ዓመት ውስጥ በከፊልም ቢሆን የግንባታ ሒደቱ ተጠናቆ ኃይል ማመንጨት እንደሚጀምር ይፋ አድርገው የነበረ ቢሆንም፣ እስከ ዛሬ ድረስ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት አልቻለም፡፡ ይሁን እንጂ ግንባታው በአሁኑ ወቅት በጥሩ ሒደት ላይ እንደሚገኝና በቅርቡ ኃይል ማመንጨት እንደሚጀምር የህዳሴ ግድቡ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) ሰሞኑን ለመንግሥት ሚዲያዎች ገልጸዋል፡፡

ባለፈው ሳምንት የህዳሴ ግድቡ ምክር ቤት ዘጠነኛ ጉባዔውን  በካፒታል ሆቴል ባካሄደበት ወቅት የፕሮጀክቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ስመኘው በቀለ (ኢንጂነር) እንደተናገሩት፣ ግድቡ በአሁኑ ወቅት በጥሩ የግንባታ ሒደት ላይ ይገኛል፡፡

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የብሔራዊ ምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት አቶ ደመቀ መኮንን በበኩላቸው፣ እስካሁን ድረስ በግንባታ ሒደቱ የገንዘብ እጥረት እንዳልገጠመ ጠቁመዋል፡፡ ‹‹ምንም ያህል የፖለቲካና የአመለካከት ልዩነቶች ቢኖሩንም ግድባችን  ብሔራዊ መግባባት የፈጠረና ሁሉንም ኢትዮጵያዊ በአንድ መስመርና ዓላማ ያሠለፈ ፕሮጀክት  ነው፤›› ብለዋል፡፡

የህዳሴ ግድቡ የመሠረት ድንጋይ በተጣለ ማግሥት በአገሪቱ በአራቱም አቅጣጫዎች በርካታ የድጋፍ ሠልፎች መካሄዳቸው ይታወሳል፡፡ ባለፉት ስድስት ዓመታት ከልጅ እስከ አዋቂ፣ ከተማሪ እስከ ምሁሩ ድረስ ያለው በጉልበቱ፣ በገንዘቡና በዕውቀቱ ለመርዳት  ቁርጠኝነቱን በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲገልጽ ተስተውሏል፡፡ ይህ ትብብር ግድቡን ከግማሽ በላይ እንዲደርስ ያስቻሉ ድጋፎችን ለማስተባበር ትልቅ ሚና መጫወቱም ይነገራል፡፡

የግብፅ መንግሥትና ፖለቲከኞች የግድቡን መሠረት መጣል ሲኮንኑና ሲቃወሙ መስማት አደስ አገር አልነበረም፡፡ በዚያን ጊዜ ይታተሙ የነበሩ የግብፅ ጋዜጦች ይዘውት ይወጡ የነበረው ርዕስ አንቀጽና የርዕስ አንቀጹን ዋነኛ መልዕከት የያዘው የካርቱን ሥዕል ይህንኑ ያንፀባርቁ ነበር፡፡ ግብፃዊያን የግድቡን ዕውን መሆን እንዲቃወሙ ከመሥራትም አልፎ፣ በጉልበታቸው እንዲያፈርሱ የሚጠይቁ መልዕክቶችን ሳይቀር እነዚህ የሚዲያ ውጤቶች ይዘው ይወጡ ነበር፡፡

አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ከዘመናት ህልምና ቁጭት በኋላ ያገኘው እንደሆነ የሚገለጸው ይኼ ፕሮጀክት ልዩነት ሳይታይ መላ ሕዝቡ በጉልበት፣ በገንዘብና በዕውቀት ከጎኑ ሆኖ እንዲደግፍና እንዲጠብቀው መንግሥት በተደጋጋሚ ጊዜ ሲጠይቅም ተደምጧል፡፡

ግብፅ ከአፍሪካ እስከ እስያ፣ ከእስያ እስከ አውሮፓና አሜሪካ ድረስ እጇን በማስገባት ኢትዮጵያ ለምትገነባው ግድብ ዕርዳታ እንዳታገኝ ማድረጓ በተደጋጋሚ ጊዜ ሲገለጽ ቢሰማም፣ አገሪቱ በራሷ አቅም ከአፍሪካ ግዙፍ የሆነውን ግድብ ለመገንባት ቁርጠኛ መሆኗ በብዙዎች ዘንድ አድናቆት ፈጥሯል፡፡

በተለይ ኢትዮጵያ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የገጠማትን ሕዝባዊ ተቃውሞና ጥያቄ ተቋቁማ የግድቡን ግንባታ ማስቀጠል መቻሏና ከግማሽ በላይ ማድረሷ፣ እንደ ጠንካራ ጎን የሚወሰድ መሆኑን የውጭ ሚዲያዎች ሳይቀሩ ይገልጻሉ፡፡

ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ በአገሪቱ በተከሰተው ተቃውሞ በርካታ የሰው ሕይወት የጠፋ ቢሆንም፣ የግድቡ ግንባታ አንድም ቀን ሳይቋረጥ 24 ሰዓት ሙሉ እየተከናወነ መሆኑን መንግሥት አመልክቷል፡፡

ግድቡ ሲጠናቀቅ እስከ 6,450 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅም ይኖረዋል፡፡ የአገሪቱን የኤሌክትሪክ ችግር እንደሚፈታ በብዙዎች ዘንድ ተስፋ ተጥሎበታል፡፡ ይህ ግድብ ሲጠናቀቅ በአርባ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘዋን ሱዳን ሳይቀር ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ኢንጂነር ስመኘው ተናግረዋል፡፡

በበርካታ ኢትዮጵያዊያን ዘንድ የግንባታ ሒደቱ መጠናቀቅ በጉጉት የሚጠበቀው ይህ ግድብ፣ በአሁኑ ወቅት ወሳኝ ምዕራፍ ላይ እንደደረሰ አቶ ደመቀ ገልጸዋል፡፡ የህዳሴ ግድቡ ማስተባባሪያ ጽሕፈት ቤት የግድቡን የግንባታ ሒደት በተመለከተ በ2009 ዓ.ም. የተካሄደውን አጠቃላይ እንቅስቃሴ ለምክር ቤቱ አባላት ሪፖርት አቅርቧል፡፡ ይህ በ28 ገጽ ተቀንብቦ የቀረበው ሪፖርት በዋናነት ያተኮረው በበጀት ዓመቱ የተሠሩ ዋና ዋና ተግባራት ላይ ነው፡፡ ሪፖርቱ በህዳሴ ግድቡ ግንባታ ዙሪያ የመላውን ኅብረተሰብ ተሳትፎ ለማጎልበት የተሠሩ ሥራዎች፣ የዲያፖራ ተሳትፎን ለማጠናከር የተከናወኑ የፐብሊክ ዲፕሎማሲ ዓለም አቀፍ ድጋፍ ሥራዎች፣ እንዲሁም የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎችን አካቷል፡፡

የታላቁ ህዳሴ ግድብ ሩጫ፣ የቦንድ ሽያጭ ሳምንት፣ የችቦ መቀባበል ሥነ ሥርዓት፣ የዓባይ ቀን የሥነ ጽሑፍ ምሽት፣ የእግር ኳስ ውድድር፣ የዓባይ ቀን የጎዳና ላይ ትርዒት፣ የብስክሌት ውድደር፣ የሕፃናት የሥዕል ውድድር፣ የሥዕልና የፎቶግራፍ ዓውደ ርዕይ፣ ሊቀ ናይል የጥያቄና መልስ ውድድር፣ የስድስተኛ ዓመት አከባበር በበጀት ዓመቱ ትኩረት ተሰጥቶ የተሠራባቸው መሆኑን በሪፖርቱ ላይ ተጠቅሷል፡፡

በ2008 ዓ.ም. ተገኝቶ የነበረው 8.7 ቢሊዮን ብር እንደነበር ሪፖርቱ አስታውሷል፡፡ ነገር ግን በ2009 ዓ.ም. የአገሪቱን የኅብረተሰብ ክፍሎች ማለትም የመንግሥት ሠራተኞች፣ አርሶና አርብቶ አደሮች፣ ባለሀብቶች፣ የከተማ ነዋሪዎች፣ ዳያስፖራው፣ በአጠቃላይ የአገሪቱ ሕዝብ በቦንድ ግዥ፣ በልገሳና በገቢ ማስገኛ ፕሮጀክቶች ላይ ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርጉ በማድረግ 10.5 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ አርሶና አርብቶ አደሮች በ2009 ዓ.ም. ያደረጉት አስተዋፅኦ በጉልበት ሲተመን 23.85 ቢሊዮን ብር የሚገመት ገንዘብ ማበርከት መቻሉም ተጠቅሷል፡፡ ከ19.8 ሚሊዮን በላይ የሰው ኃይል የተሳተፈበት ሥራ መከናወኑም ተብራርቷል፡፡

በዚህ ዓመት የህዳሴ ግድቡን ዕውን ለማድረግ እየተደረገ ባለው እንቅስቃሴ  ክፍተቶችና ችግሮች እንደነበሩም ተጠቁሟል፡፡ በተለይ በየደረጃው ያለው አመራር እንደ ሌሎች ሥራዎች እኩል በመያዝ ማንቀሳቀስ ላይ ውስንነቶች እንደነበሩ ተለይቷል፡፡ የዳያስፖራ ቦንድ መረጃ አያያዝና አመላለስ ላይ እየታዩ ያሉ ችግሮች በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክና በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መሥሪያ ቤት መካከል የቅንጅት ማነስ እንዳለ ተገልጿል፡፡

 በዚህ ሪፖርት የምክር ቤቱ አባላት የተለያዩ ጥያቄዎችን አንስተዋል፡፡ በወቅቱም የህዳሴ ግድቡ ሕዝባዊ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሮማን ገብረ ሥላሴና አቶ ደመቀ መኮንን ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋ ይርዳው (ዶ/ር) የህዳሴ ዋንጫው ከክልል ክልል ብቻ ለምን ይንቀሳቀሳል? ወደ ግል ተቋማትስ ለምን እንዲሄድ አይደረግም? የሚል ጥያቄ ያነሱ ሲሆን፣ ወ/ሮ ሮማን በምላሻቸው፣ ‹‹ይህ ዋንጫ ሐሳቡ ሲጠነሰስ ለኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች የተሰጠ ነው፡፡ ዓድዋ ይፋ ሲሆንም ከህዳሴ ግድቡ ጋር የሚያመሳስለው ነገር ስላለና የአሸናፊነት ምልክት ስለሆነ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ለብሔር ብሔረሰቦች የተሰጠ በመሆኑ ወደ ግል ተቋማት ሊሄድ እንደማይችል አስረድተዋል፡፡ ‹‹ዋንጫው በአንድ ክልል ለአንድ ዓመት ነው የሚቆየው፡፡ ችቦው ግን ለአንድ ወር ብቻ ነው፡፡ ይህንን ችቦ ወደ ተቋም እንዲሄድ ማድረግ ይቻላል፡፡ ዋንጫው ግን የብሔር ብሔረሰቦች ምልክት ነው፤›› ብለዋል፡፡

ዶ/ር አረጋ፣ ‹‹በማዕድን ኢንዱስትሪ መሬት ውስጥ ያለውን ወርቅ መሸጥ ይቻላል፡፡ የህዳሴ ግድቡ ወደ ፊት የሚያመነጨውን ኤሌክትሪክ ኃይል ካሁኑ ለምን መሸጥ አልተቻለም?›› የሚል ጥያቄ ቢያቀርቡም ከመድረኩ ምላሽ ሳይሰጥ ቀርቷል፡፡

የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ አቶ አባተ ስጦታው የባለሀብቱን ተሳትፎ ከማሳደግ አኳያ በተለይ በፌዴራሉና በአዲስ አበባ ከተማ መካከል ተቀናጅቶ ከመሥራት አኳያ ክፍተት እንዳለ ጠቁመዋል፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ ነዋሪውና ዝቅተኛ ባለሀብቱ ብቻ እንደሚሳተፍ ገልጸዋል፡፡ ‹‹ሻል ሻል ያለው ባለሀብት ደግሞ በፌዴራል የመሳተፍ አዝማሚያ ስላለው፣ በጋራ መሥራት ካልተቻለ ክፍተቶችን መፍታት አንችልም፤›› የሚል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ ወ/ሮ ሮማን በምላሻቸው፣ ‹‹ከአዲስ አበባ ጋር ተቀናጅቶ ከመሥራት አኳያ የተነሳው ጥያቄ ትክክል ነው፣ እንቀበላለን፡፡ ወደ ፊትም መስተካከል ያለበት ጉዳይ ነው፡፡ ትክክለኛ አቅጣጫ አስቀምጠን በዚያ መንገድ መሄድ ይኖርብናል፤›› ብለዋል፡፡

ከምክር ቤቱ አባላት የቦንድ ግዥን በተመለከተ የተለያዩ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ተነስተዋል፡፡ አንድ አባል፣ ‹‹የቦንድ ግዥ ገደቡ እስከምን ድረስ ነው?›› በማለት ሲጠይቁ፣ ሌላ አባል ደግሞ፣ ‹‹በቦንድ ግዥ ላይ ሰፊ ልዩነቶች አሉና ይኼንን እንዴት ነው ማጣጣም የሚቻለው?›› የሚል ጥያቄ አንስተዋል፡፡ ወ/ሮ ሮማን መንግሥት አዲስ አቅጣጫ ማስቀመጡን ይፋ አድርገዋል፡፡ ኅብረተሰቡን ከሦስት ጊዜ በላይ እንዲገዛ ማድረግ ሊጎዳው ስለሚችል መንግሥት እንደማይገፋፋ ተናግረዋል፡፡ ይህም ቢሆን ግን ለስድስት ዓመታት ያህል የቦንድ ግዥ ያላቋረጡ ተቋማትና ግለሰቦች እንዳሉ ይፋ አድርገዋል፡፡ ከእነዚህ መካከልም የመከላከያ ሠራዊት፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ)፣ የፌዴራል ፖሊስና በስልጤ ዞን ውስጥ የምትገኘውና የም ተብላ በምትጠራው ወረዳ ውስጥ የሚኖሩ የመንግሥት ሠራተኞችን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡

ከምክር ቤቱ አባላት ከተነሱ ሌሎች ጥያቄዎች መካከል ግድቡ የሚፈጥረውን ሰው ሠራሽ ሐይቅ መጠበቅን በተመለከተ ምን እየታሰበ ነው? የሚል ይገኝበታል፡፡ የግድቡ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ስመኘው የሰው ሠራሽ ሐይቁ የቱሪዝም መዳረሻ እንዲሆን ሰፊ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የዓሳ ዕርባታ፣ የቴክኖሎጂ ፓርኮችና የጥናት ማዕከሎች በሐይቁ ዙሪያ እንደሚኖሩ አስረድተዋል፡፡ ከሐይቁ በሦስት ኪሎ ሜትር ርቀት ሌላ ምንም ዓይነት መሠረተ ልማት እንደማይኖርም አክለዋል፡፡

የህዳሴ ግድቡ ኢኮኖሚያዊ አዋጭነቱ ተረጋግጦ ወደ ግንባታ እንደተገባ አስታውሰው፣ ለኢትዮጵያ ከሚሰጠው ጥቅም ባልተናነሰ ለታችኞቹ ተፋሰስ አገሮች የሚሰጠው ጥቅም እንዳለም ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ደራሲያን ማኅበር ፕሬዚዳንት ሙሴ ያዕቆብ (ዶ/ር) የግድቡን ዋስትና ለማረጋገጥ እየተሠራ ያለው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ አነስተኛ በመሆኑ፣ ብዙ ወንዞችና የተፈጥሮ ሀብቶች አደጋ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ አቶ ደመቀ በበኩላቸው የትኩረት ማነስና የተፋሰስ ልማት ጉዳዮችን አቀናጅቶ ከመምራት አኳያ ክፍተቶች እንዳሉ አውስተዋል፡፡ በዓባይ ተፋሰስ ያሉ 22 ወረዳዎችን እስከ ደቡብና ሰሜን ጎንደር፣ እንዲሁም ከእንጦጦ እስከ ቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ያለውን ተፋሰስ መጠበቅና መንከባከብ እንደሚገባም አስረድተዋል፡፡

ባህር ዳር ያለው የጣና ተፋሰስ ማዕከልም ተፋሰሶችን ከህዳሴ ግድቡ ዘላቂነት ጋር ቃኝቶ ሥራውን የመምራትና ተቋማዊ ተልዕኮውን የመውጣት ግዴታ እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡

ግድቡ እስከ 375 ዓመታት ድረስ ያገለግላል ተብሎ የታቀደ ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት ለአካባቢ ጥበቃ ካለው አናሳ ግንዘቤ የተነሳ ግድቡ የታሰበውን ያህል ጊዜ  ሊያገለግል እንደማይችል የምክር ቤቱ አባላት ሥጋታቸውን ገልጸዋል፡፡ የጣና ሐይቅ በእንቦጭ አረም መወረር፣ የጉናና የጮቄ ተራሮች አደጋ ላይ መውደቅ የግድቡን ህልውና የሚፈታተኑ ችግሮች እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስትሩ ስለሺ በቀለ (ዶ/ር)፣ ‹‹በጣና ዙሪያ ያሉ ተፋሰሶችን መታደግ ግድቡን በዘላቂነት እንድንጠቀምበት ያስቻላል፤›› ብለዋል፡፡

ከህዳሴ ግድቡ ጎን ለጎንም ሌሎች የመንገድ፣ የመልሶ ማቋቋም፣ የግንባታና  የደን ምንጣሮ እየተከናወነ መሆኑን ኢንጂነር ስመኘው ገልጸዋል፡፡

ብሔራዊ ምክር ቤቱ ዘጠነኛ መደበኛ ጉባዔውን በካፒታል ሆቴል ባካሄደበት ወቅት እንደተገለጸው፣ በ2009 ዓ.ም. በፐብሊክ ዲፕሎማሲ የተከናወነው ሥራ አነስተኛ ነው፡፡

አንድ የምክር ቤት አባል፣ ‹‹በራሳችን ውኃ ስንዋረድ ኖረናል፡፡ እኛ ለሌሎች የተፋሰሱ አገሮች ውኃችንን ስንሰጣቸው ብንኖርም እነሱ ግን ዋጋ ሳይሰጡን ኖረዋል፡፡ የተዋረድን ሰዎች ነበርን፡፡ ከአሁን በኋላ ግን ዋጋ እንዳለን እናሳያቸዋለን፤›› በማለት በቁጭት ተናግረዋል፡፡ ‹‹ይሁን እንጂ ቀይ ባህር በጀርባችን እየመጣ ስለሆነ (ሰው ሠራሽ ሐይቁን ሲገልጹ) በዙሪያው ምን የታቀደ ነገር አለ?››  በማለት ጠይቀዋል፡፡

ወደ ፊት የኤሌክትሪክ ኃይል እንደሚጎርፍ ተስፋቸውን የገለጹት ሌላ የምክር ቤት አባል፣ የቻይናዋ ሻንጋይ ከተማ እ.ኤ.አ. በ2020 ከበካይ ጋዝ ነፃ የሆነ ተሽከርካሪዎች ለመጠቀም ማቀዷን ገልጸው ኢትዮጵያ ወደ ፊት በተለይ የቤት መኪና፣ ታክሲና የሕዝብ አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች የውጭ ምንዛሪን በማስቀረት ረገድ ጉልህ ሚና ስለሚኖረው በኤሌክትሪክ ኃይል እንዲነዱ ቢደረግ የተሻለ እንደሆነ ሐሳብ አቅርበዋል፡፡

በህዳሴ ግድቡ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት በ2009 ዓ.ም. የተሠራው ሥራ ምን እንደሚመስል በቀረበው ሪፖርት የምክር ቤቱ አባላት ከተወያየ በኋላ፣ በ2010 ዓ.ም. ዕቅድ ላይ ውይይት አድርገዋል፡፡ በ2009 ዓ.ም. የነበሩ ውስንነቶችን በማረምና የመፍትሔ አቅጣጫ በማስቀመጥ የግድቡን ግንባታ ወደ ተሻለ ደረጃ ከፍ ለማድረግ በምክር ቤቱ አባላት ዘንድ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ በ2009 ዓ.ም. የተገኘውን 10.5 ቢሊዮን ብር ወደ 11.5 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ የተቀመጠውን ዕቅድ ለማሳካት፣ ሁሉም ርብርብ እንዲያደርግ በማሳሰብ ስብሰባው ተጠናቋል፡፡

Standard (Image)

የሕገ መንግሥቱ ቅቡልነትና ተፈጻሚነት አሁንም እያከራከረ ነው

$
0
0

ባለፉት 23 ዓመታት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሚዲያዎች፣ ሲቪል ማኅበራት፣ ሙያ ማኅበራትና ምሁራን በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ላይ ጥያቄዎች ማንሳታቸውና አሉታዊ ትንታኔዎች መስጠታቸው የተለመደ ነበር፡፡

የአንዳንዶች ሕገ መንግሥታዊ ትንታኔ በሕገ መንግሥቱ ተቀባይነት ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡ ሕገ መንግሥቱን ‹‹የኢሕአዴግ ሕገ መንግሥት›› ብለው የሚጠሩት በርካታ አካላት የመኖራቸውን ያህል ጥቂቶች ‹‹የአቶ መለስ ሕገ መንግሥት›› እስከ ማለት ደርሰዋል፡፡ ይህን ጥያቄ ለማንሳትና አቋም ለመያዝ የሚያቀርቧቸው መከራከሪያ ነጥቦች በሕገ መንግሥት ማርቀቅ ሒደት፣ በሕገ መንግሥቱ አፈጻጸምና በሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱ ያለው የለውጥ ዝግጁነት ላይ ይሽከረከራሉ፡፡ በእርግጥም ኢሕአዴግ ሕገ መንግሥቱን በማርቀቅ፣ አፈጻጸሙ ላይ ተፅዕኖ በማሳረፍና የማሻሻያ ሐሳቦችን በመከላከል ጉልህ ሚና ተጫውቷል፡፡

እነዚህ ትችት የሚያቀርቡ አካላት በሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱ ላይ ለውጥ እንዲደረግ ሲጠይቁም ይስተዋላል፡፡ በተጨማሪም በሥርዓቱ ላይ ተፅዕኖ አላቸው ብለው የለዩዋቸው የመንግሥት ፖሊሲዎችም እንዲለወጡ ወይም እንዲከለሱ በተደጋጋሚ ይጠይቃሉ፡፡ የገዥው ፓርቲ የረዥም ጊዜ መሪና ቁልፍ ቀያሽ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከአምስት ዓመታት በፊት በድንገት ሕይወታቸው ሲያልፍና አዲስ አመራር ወደ ሥልጣን ሲመጣ እነዚህ ጥያቄዎች ተጠናክረው ቀርበው ነበር፡፡

በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትርን ‹‹ሌጋሲ ሳይበረዝ ለመቀጠል›› እንደሚሠሩ በመግለጽ ሳይገደቡ፣ ፓርቲው ያለምንም የፖሊሲ ለውጥ ለመቀጠል መወሰኑን አውስተው ነበር፡፡  ይሁንና በመጀመርያው ይፋዊ ንግግራቸው ከምሁራን፣ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ ከጥናትና ምርምር ተቋማት፣ ከሚዲያ ተቋማት፣ ከሙያ ማኅበራት፣ ከሲቪል ማኅበራትና ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ተባብረው ለመሥራት ቃል መግባታቸው ይታወሳል፡፡ በዚህም ሕገ መንግሥቱን ጨምሮ በተለያዩ አንገብጋቢ አገራዊ ጉዳዮች ላይ እነዚህ አካላት ያላቸውን ሐሳብ በነፃነት እንዲሰጡ በማድረግ፣ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱ በተሻለ መልኩ አካታች እንደሚሆን ብዙዎች ጠብቀው ነበር፡፡ በተግባር ግን ድኅረ መለስ አመራሩ እንደ ቀደመው መቀጠል የተሳነው ይመስላል፡፡ በዚህም የሕገ መንግሥት ቅቡልነት ላይ የሚነሱ ጥያቄዎች ይበልጥ እየተጠናከሩ መጥተዋል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ከተነሳው አመፅና ተቃውሞ ጋርም ይኼው ጥያቄ ተጠናክሮ አገርሽቷል፡፡

በርካታ የጥናት ሥራዎች የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ሥልጣን ላይ ያለው የኢሕአዴግ በተለይ ሕወሓት ፕሮግራም ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ ያመለክታሉ:: ይህም በሕገ መንግሥቱ ዋነኛ አንቀጾች ላይ ለምሳሌም የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ሉዓላዊነት ላይ፣ የመገንጠል መብት ላይ፣ የመሬት ባለቤትነት መብት ላይ እንደሚንፀባረቅ ይጠቅሳሉ:: የሕገ መንግሥት ትርጉም ላይ፣ የሕገ መንግሥት ማሻሻያ፣ የዴሞክራሲያዊና የሰብዓዊ መብት ልዩነት ላይ፣ የክልልና የፌዴራል መንግሥቱ የሥልጣን ክፍፍል ላይ ደግሞ ከዲዛይን አንፃር ተጨማሪ ጥያቄዎች ይቀርባሉ፡፡

ኢሕአዴግ ሥልጣን ላይ እስካለ ድረስ ሕገ መንግሥቱ ምንም ዓይነት ለውጥ አያስተናግድም በማለት የሚከራከሩ አካላት፣ ኢሕአዴግ በሰላማዊ የመድበለ ፓርቲ የምርጫ ውድድር ሥልጣን ቢያጣ ሕገ መንግሥቱ የመቀጠል ዕድሉ ምን ያህል ነው? ሲሉም ይጠይቃሉ፡፡ ሕገ መንግሥቱ ላይ ከሚነሳው የተቀባይነት ጥያቄ አንፃር በበላይነት ካረቀቀው ኢሕአዴግ ባሻገር፣ ሁሉም የሚሠራበት ሕገ መንግሥት ለመሆን ሊስተካከሉ የሚገቡ ነጥቦችን ምሁራኑ ያስረዳሉ፡፡

የሕገ መንግሥት ማርቀቅ ሒደቱ እንደ ማንኛውም ሌላ ሕገ መንግሥት ኮሚሽን ተዋቅሮ፣ የሌሎች አገሮች ተሞክሮ ተወስዶ፣ ሕዝብ እንዲወያይበት ተደርጎ፣ ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈውበት በክርክር፣ በውይይት፣ በአስተያየቶች ዳብሮና በአብላጫ ድምፅ መፅደቁን ሁሉም ይጠቅሳሉ፡፡ ይሁንና ከኢሕአዴግ የጎላ ተፅዕኖ ጋር መወዳደር የሚችሉ አማራጭ ሐሳቦች እንዳልነበሩ በተወካዮች ምክር ቤት፣ በሕገ መንግሥቱ አርቃቂ ኮሚሽንና በሕገ መንግሥታዊ ጉባዔው የተሳተፉ አካላት ይገልጻሉ፡፡

በሽግግር መንግሥቱ ቻርተር አማካይነት የሕገ መንግሥት አርቃቂ ኮሚሽኑ በወቅቱ ሕግ አውጪ አካል እንዲዋቀርና ያረቀቀውን ሕገ መንግሥት በተወካዮች ምክር ቤትና በሕዝቡ ውይይት ተደርጎበት፣ አስተያየቶቹ ተካተውበት ለሕገ መንግሥታዊ ጉባዔ በመጨረሻ ቀርቦ እንዲፀድቅ ተደንግጓል፡፡

አንድ ሕገ መንግሥት ተቀባይነቱ የሚለካው በሕጋዊነት፣ በሞራልና በማኅበራዊ መሥፈርት መሆኑን የሕገ መንግሥት ጥናት ምሁራን ይጠቅሳሉ፡፡ ይሁንና ተቀባይነት አንፃራዊ ቃል በመሆኑ አንድ ሕገ መንግሥት ተቀባይነት አለው ወይም የለውም ለማለት አስቸጋሪ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ አንድ ሕገ መንግሥት ከመነሻው ከማርቀቅ ሒደቱ ጋር በተያያዘ የተቀባይነት ጥያቄ የሚነሳበት ቢሆንም፣ በሒደት ቅሬታዎችን አሳታፊ በሆነ ሁኔታ በመቅረፍ ተቀባይነት ሊጎናጸፍ እንደሚችል የሚሞግቱ ምሁራንም አሉ፡፡ ከተቀባይነት በተጨማሪ ሕገ መንግሥታዊነትና አፈጻጸም የተሻለ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት ለመፍጠር አስፈላጊ መሆናቸውንም ይጠቁማሉ፡፡ ሕገ መንግሥቱ የሁሉንም ዜጋ የባለቤትነት ስሜት እንዲያገኝ ከሕገ መንግሥቱ ጋር የሚጋጩ ነገሮችን በማስወገድ ሕገ መንግሥታዊ የበላይነትን ማረጋገጥ፣ በባለሥልጣናትና በዜጎች በእኩል እንዲከበር ማድረግ፣ ሕገ መንግሥታዊ ተቋማት እንዲጠናከሩ፣ ነፃ እንዲሆኑና ራሳቸውን የቻሉ እንዲሆኑ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑንም ይመክራሉ፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሕግ ትምህርት ቤት ነሐሴ 1 እና 2 ቀን 2009 ዓ.ም. ለመጀመርያ ጊዜ ባዘጋጀው ዓመታዊ የጥናት ኮንፈረንስ ይኼው ጉዳይ የመወያያ ርዕስ ሆኖ ነበር፡፡ በተሳታፊዎች ንቁ ተሳትፎ በታጀበው ኮንፈረንስ ሕገ መንግሥት፣ ሰብዓዊ መብት፣ ዓለም አቀፍ ሕግና ቢዝነስ ሕግ የተካተቱ ቢሆንም ርዕሰ ጉዳዩ የተነሳው በመጀመርያው ቀን የሕገ መንግሥቱ ቅቡልነት ላይ ባተኮረው ፕሮግራም ነው፡፡ በጉዳዩ ላይ አራት ጥናታዊ ጽሑፎች የቀረቡ ቢሆንም፣ በርካታ ጥያቄዎችና አስተያየቶችን የሳቡት ግን በዶ/ር አበራ ደገፋና በዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ የቀረቡት ላይ ነው፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አንጋፋ መምህርና የሕገ መንግሥት ጥናት ኤክስፐርቱ ዶ/ር አበራ ደገፋ ‹‹State-building and Issues of Legitimacy in Ethiopia: Chronicling Achievements, Failures and Prospects›› በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጥናት፣ የአገረ መንግሥት ግንባታ ታሪኮች ብዙዎቹ ዘመናዊ አገሮች የተመሠረቱት በኃይል እንደሆነና ወደ ፍላጎትን መሠረት ያደረገ አገዛዝ ለመለወጥ በርካታ ጊዜያት እንደወሰደባቸው አስታውሰዋል፡፡

በኢትዮጵያ ግን አሁንም ፍላጎትን መሠረት ያደረገ አገዛዝ መመሥረት እንዳልተቻለ አመልክተዋል፡፡ ለረዥም ዘመናት በሥልጣን ላይ የቆዩት መንግሥታት ፍላጎትን መሠረት ያደረገ አገዛዝ ባለመተግበራቸው የቅቡልነት ችግር እንደነበረባቸውና አሁንም በሥልጣን ላይ የሚገኘው መንግሥት ይህን እንዳልቀረፈ ዶ/ር አበራ ገልጸዋል፡፡ ‹‹በአጠቃላይ የተረጋጋ የፖለቲካ ሥርዓት፣ ዘላቂ ሰላምና ልማት ከማምጣት አንፃር በጣም ትንሽ መሻሻል ነው የተመዘገበው፤›› ብለዋል፡፡

ዶ/ር አበራ በመንግሥት ቅቡልነትና በአገር መረጋጋት መካከል ጥብቅ ግንኙነት እንዳለ አውስተው፣ የዜጎችን አዎንታ ያላገኘ መንግሥት ተረጋግቶ ለመቀጠል እንደማይችል አመልክተዋል፡፡ በተለይ የፖለቲካ ቀውስ በሚያጋጥምበት ወቅት የመንግሥት ቅቡልነት ይበልጥ አሳሳቢ ጉዳይ እንደሚሆን አስገንዝበዋል፡፡ የፖለቲካ ቀውስ ቅቡልነት የሌላቸው፣ ገና እየመሠረቱ ያሉና እያጠናከሩ ያሉ መንግሥታትን ይበልጥ ፈተና ላይ እንደሚጥል ጠቅሰዋል፡፡

የመንግሥት ቅቡልነት ከሒደት፣ ከአፈጻጸምና ከጋራ እምነት አንፃር እንደሚታይ የጠቆሙት ዶ/ር አበራ፣ ከሒደት አንፃር የመንግሥት ቅቡልነት የሚለካው ዜጎች በተስማሙባቸው ሕጎችና ሥነ ሥርዓቶች መሠረት እየመራ በመሆኑና ባለመሆኑ እንደሆነም አመልክተዋል፡፡ ከአፈጻጸም አንፃር ደግሞ መንግሥት ለሕዝቡ በሚሰጠው አገልግሎት ጥራትና ብዛት እንደሚለካ ጠቅሰዋል፡፡ የጋራ እምነት ደግሞ ሕዝቦች በጋራ መንግሥት ስላለው የመግዛት ሥልጣን በሚሰማቸው ስሜት እንደሚለካ ገልጸዋል፡፡ 

የመንግሥት ቅቡልነት በኃይል ከመምራት ይልቅ በዜጎች ፍላጎትና ይሁንታ ለመምራት እንደሚያገለግል የጠቆሙት ዶ/ር አበራ፣ ይህንንም በጣም ውስን የሆነ ኃይል በመጠቀም ለማሳካት እንደሚያስችል አስገንዝበዋል፡፡ ከዚህ በተቃራኒ የቅቡልነት ችግር ያለበት መንግሥት አገዛዙን በኃይል ለማስቀጠል ሰፊ ሀብት ለመጠቀም እንደሚገደድ አመልክተዋል፡፡ ይህም ድጋፍ ስለሚቀንስ መልሶ በኃይል እንዲወርድ መነሻ እንደሚሆን ጠቁመዋል፡፡

ኢትዮጵያን የመሩና እየመሩ ያሉ ሦስት መንግሥታት በኃይል ወደ ሥልጣን እንደመጡ አስታውሰው፣ ሁለቱ በመጡበት መንገድ በኃይል ከሥልጣናቸው እንደተወገዱም አውስተዋል፡፡ ሦስቱም መንግሥታትና የመሠረቷቸው ተቋማት ከዜጎች ጋር መልካም የሚባል ግንኙነት እንዳልነበረባቸውም ገልጸዋል፡፡ የኃይለ ሥላሴና የደርግ መንግሥታት ፈላጭ ቆራጭ የሆነ የፖለቲካ ባህል በመመሥረታቸው የአገሪቱ የፖለቲካ ልሂቃን አስተሳሰብ በዚሁ እንዲቃኝ ማድረጉንም ተችተዋል፡፡ ‹‹ልሂቃኑ የፖለቲካ ሥልጣንን በብቸኝነት ለመጠቀም በተለይም እንደ መሬት ያለን ሀብትም በተማከለ ሁኔታ ለመጠቀም እንዲያልሙ ያደረጋቸው ይኼ የተወረሰ ባህል ነው፤›› ብለዋል፡፡ በዚህ የተነሳ ያለፉት ሁለት መንግሥታት የቀረጿቸው ሕገ መንግሥታትና ተቋማት ከመንግሥታቱ ጋር አብረው መጥፋታቸውንም አስታውሰዋል፡፡

ዶ/ር አበራ የ1983 ዓ.ም. ሽግግር ኢትዮጵያን በአዲስ መልኩ ፍላጎት ላይ መሠረት ባደረገ አገዛዝ እንደገና ለማዋቀር ዕድል ፈጥሮ የነበረ ቢሆንም ጥቅም ላይ እንዳልዋለ አመልክተዋል፡፡ ‹‹ከአኃዳዊ አገዛዝ ወደ ኅብረ ብሔራዊ ፌዴሬሽን የተደረገው ሽግግር መሠረታዊ ለውጥ አምጥቷል፡፡ ከአፈጻጸምም አኳያ በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት አገልግሎት በመስጠትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን በማረጋገጥ የሚታይ ስኬት አስመዝግቧል፡፡ ነገር ግን ሁሉን አካታች የሆነ የፖለቲካ ማኅበረሰብ በመፍጠር ረገድ አሁንም ክፍተቶች አሉ፤›› ብለዋል፡፡

በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ቅቡልነት ላይ ጥያቄዎች እንደሚነሱ ጊዜ እየጠበቁ የሚነሱት አመጾችና ተቃውሞዎች የማያጠራጥሩ ማሳያ እንደሆኑም አመልክተዋል፡፡ ‹‹የእነዚህ አመጾችና ተቃውሞዎች ሥረ መሠረት በአግባቡ መጠናት አለበት፡፡ ኢትዮጵያ የተመሠረተችው በወረራና በኃይል ቢሆንም ዘላቂ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት ለመገንባት በፈቃድ ላይ የተመሠረተ አገዛዝ ሊመሠረት ይገባል፡፡ ያለፉት ሥርዓቶች መለያ ከሆኑት ልሂቃንን መሠረት ያደረገ አገዛዝና ፈላጭ ቆራጭ ከሆነ የፖለቲካ ባህል ተላቀን፣ ፍትሐዊ የሥልጣንና የሀብት ክፍፍል የሚያደርግ ሥርዓት ለመገንባት መጣር አለብን፤›› ሲሉ ደምድመዋል፡፡

ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ በበኩላቸው ‹‹Constitutionalism without Liberals, Democracy without Democrats: The Ethiopian Case›› በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጥናት፣ የኢትዮዽያ የዴሞክራሲ ባህል ሕገ መንግሥታዊ ዴሞክራሲን ለመገንባት ለሚደረገው ጥረት ትልቅ እንቅፋት እንደሆነ ተከራክረዋል፡፡ ዴሞክራቶችና ሊበራሎች ሳይኖሩ ዴሞክራሲንና ሕገ መንግሥታዊነትን ለማረጋገጥ የተደረገው ሙከራ ትልቅ ውድቀት እንደሆነም አመልክተዋል፡፡

በዴሞክራሲ ላይ የሚመራመሩ እንደ ሳሙኤል ሃንቲንግተን፣ ማርቲን ሊፕሲትና ሮበርት ዳል ያሉ ምሁራን የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ዋነኛ መገለጫ ፍትሐዊ ውድድር የሚደረግበት ሥነ ሥርዓት መሆኑን እንደሚያሰምሩበት ጠቅሰዋል፡፡ ሒደቱ ዕድሜያቸው ለአቅመ አዳምና ሔዋን ለደረሱ ግለሰቦች በተወዳዳሪነት፣ በመራጭነት፣ በተንታኝነት፣ በተችነትና በመሳሰሉ እንቅስቃሴዎች እንዲሳተፉ ምኅዳር እንደሚያመቻችም አስገንዝበዋል፡፡ ይኽም በዋነኝነት የተሻለ ፖሊሲ ያለውንና የፖለቲካ ውሳኔ የሚሰጠውን ኃይል ለትልቁ የፖለቲካ ሥልጣን ዜጎች እንዲያበቁ ዕድል በመስጠት እንደሚገለጽ ገልጸዋል፡፡

በአጠቃላይ በአንድ አገር ዴሞክራሲያዊ አገዛዝ እንዲሰፍን ለማድረግ ከሚያስፈልጉ ተቋማዊ ማስተማመኛዎች መካከል ፖለቲካ ፓርቲዎችንና ሲቪል ማኅበራትን ጨምሮ ማኅበራት የመፍጠር ነፃነት፣ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት፣ የመምረጥና የመመረጥ መብት፣ የፖለቲካ ድጋፍ የማሰባሰብ ነፃነት፣ ነፃና ፍትሐዊ ምርጫ ማድረግና የመንግሥት ፖሊሲዎችን የሚያወጡ ተቋማት ውሳኔዎች በመራጩ ሕዝብ ፍላጎትና ጥቅም እንዲቃኙ ማድረግ ተጠቃሽ እንደሆኑ አስረድተዋል፡፡

ሕገ መንግሥታዊነትም በዋነኛነት የሚገለጸው በመንግሥት ሥልጣን ላይ ሕጋዊ ገደብ በማድረግ እንደሆነም አስታውሰዋል፡፡ ሕገ መንግሥቱም በዋነኛነት የመንግሥት ሥልጣን ላይ ገደብ ለማድረግ የተቀረፀ ከመሆኑ አኳያ፣ ሕገ መንግሥታዊነት ወይም ሕገ መንግሥቱን መሠረት ያደረገ አገዛዝ ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ይህ ገደብ መንግሥት የዜጎችን ሲቪል መብት እንዲያከብር፣ የሥልጣኑ ወሰን እንዲታወቅና ሥልጣኑን እንዴት እንደሚጠቀምበት በመደንገግ እንደሚገለጽም ጠቁመዋል፡፡ እነዚህን ሕገ መንግሥታዊ ገደቦችን ያላከበረ መንግሥት ቅቡልነት ያለውና የመግዛት ሥልጣኑ ሊከበርለት የሚገባ ተደርጎ እንደማይወሰድም አመልክተዋል፡፡

በጽንሰ ሐሳብ ደረጃ ‹ሊበራሊዝም› እና ‹ኮንስቲቲውሽናሊዝም› የማይነጣጠሉ ናቸው፡፡ ሊበራሊዝም ለግለሰቦች ነፃነት ሲባል በመንግሥት ሥልጣን ላይ ገደብ እንዲደረግ ይጠይቃል፡፡ በዚህም ሊበራሊዝም ለኮንስቲቲውሽናሊዝም ርዕዮተ ዓለማዊ መሠረት ይጥላል፡፡ ዴሞክራሲና ‹ኮንስቲቲውሽናሊዝም› ሲቀላቀሉ ደግሞ ሕገ መንግሥታዊ ዴሞክራሲን ይፈጥራሉ፡፡

አንድ ሕገ መንግሥት ለአንድ ማኅበረሰብ የተስማማና ረግቶ የሚቆይ መሆኑን የሚወስነው የፖለቲካ ባህሉ እንደሆነም አመልክተዋል፡፡ የፖለቲካ ባህል በዋነኛነት የሚገለጸው ዜጎች በፖለቲካ ተዋናዮች ላይ ባላቸው የአተያይ አዝማሚያ ስብጥር እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡ በተጨማሪም የፖለቲካ ሥርዓቱ ላይ ተፅዕኖ መፍጠር የሚችሉና በአብዛኛው ማኅበረሰብ ዘንድ የሚንሸራሸሩ እምነቶች፣ እሴቶችና አመለካከቶች የፖለቲካ ባህሉን እንደሚቀርፁ አስገንዝበዋል፡፡ የፖለቲካ ልሂቃኑ የፖለቲካ ባህልን በመቀየር ረገድ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱም አክለዋል፡፡

በ1987 ዓ.ም. ሕገ መንግሥት ላይ የመንግሥት ሥልጣን የተገደበ ቢሆንም፣ በተግባር ግን ይህ እንደማይስተዋል ይልቁንም በየቀኑ እንደሚጣስ ገልጸዋል፡፡ ሥልጣን በዘፈቀደ ጥቅም ላይ እንደሚውልም አመልክተዋል፡፡ አገሪቱ በአንድ ፓርቲ ሥር መሆኗም ይህንን እንዳጠናከረው ገልጸዋል፡፡ ሕገ መንግሥቱ በወረቀት ላይ ቢኖርም በተግባር አለመቀየሩ ‹‹አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም›› የሚለውን አባባል እንደሚያስታውሳቸው አስረድተዋል፡፡

በእውነታውና በዜጎች ፍላጎት መካከል ላለው አለመመጣጠን ዋነኛው ተጠያቂ የአገሪቱ የፖለቲካ ባህል መሆኑን ያመለከቱት ዶ/ር ጌድዮን፣ የ1966 ዓ.ም. አብዮት፣ የ1983 ዓ.ም. ሽግግርና የ1997 ዓ.ም. ምርጫ የኅብረተሰቡን የፖለቲካ ባህልና እምነት በመቅረጽ ጉልህ ሚና መጫወታቸውን አስገንዝበዋል፡፡ በተለይ ከ1966 ዓ.ም. አብዮትና ከ1960ዎቹ የተማሪዎች ንቅናቄ የተወረሰው በማርክሲስትና ሌኒኒስት ርዕዮተ ዓለም የተቃኘው የግራ ፖለቲካ በአገሪቱ የፖለቲካ ባህል ላይ ጠባሳ ትቶ እንዳለፈ ሞግተዋል፡፡

ዶ/ር ጌድዮን ሲደመድሙ፣ ‹‹በአብዛኛው ዴሞክራሲያዊና ሊበራል የሆነ ሕገ መንግሥት ሠርተናል፡፡ አሁን ዴሞክራቶችንና ለሕገ መንግሥት መከበር የሚተጉ ወይም ሊበራሎችን የምንፈጥርበት ጊዜ ነው፤›› ብለዋል፡፡ በሕግና በተቋማት ላይ ከመጠን ያለፈ ትኩረት በማድረግ ለውጥ ሊደረግበት የሚገባው የሕገ መንግሥት ተግባራዊነትና ለሕገ መንግሥታዊነትና ለዴሞክራሲ የሚመች አዲስ የፖለቲካ ባህል ግንባታ በቂ ትኩረት እንዳልተሰጠው በማመልከትም እዚህ ላይ መረባረብ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ሁለቱ ምሁራን ጥናቶቻቸውን ካቀረቡ በኋላ ታዳሚዎች የተለያዩ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ሰንዝረዋል፡፡ የሕግና ፍትሕ ሥርዓት ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ‹‹ቅቡልነት የውይይት ውጤት ነው ወይስ ሁሉን አካታች የሆነ የልሂቃን የድርድር ውጤት ነው?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

አቶ ጌታቸው፣ ‹‹ዶ/ር ጌድዮን ምዕራብ አትላንቲክ ላይ ያመዘኑ ምሁራንን ነው የጠቀሱት፡፡ ከሞላ ጎደል የጠቀሱት የዴሞክራሲ ጽንሰ ሐሳብ ሊበርቶሪያን የሚባለው ነው፡፡ ማርቲን ሊፕሲት፣ ሳሙኤል ሃንቲንግተን፣ ሮበርት ዳል አንዳቸውም ቢያንስ የሰሜን አትላንቲክን አስተሳሰብ የሚወክሉ አይደሉም፡፡ ሁሉንም ወገን የሚወክሉ ምሁራን ሥራዎች ቢጠቀሱ ጥሩ ነው፤›› የሚል አስተያየትም አክለዋል፡፡

‹‹የፖለቲካ ባህል በጣም አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ የሚስትን እኩል መሆን የማይቀበል አባወራና ሚስቱ ጥያቄ ባቀረበች ቁጥር ግልምጫና ዱላ የሚቀናው ሰው ድንገት የሥልጣን ኮሪደር ላይ ራሱን ቢያገኘው፣ ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብ ሊያራምድ አይችልም፡፡ ፓርቲዎቹም እንደዚሁ ናቸው፤›› ሲሉም አቶ ጌታቸው በፖለቲካ ባህል ግንባታ ላይ ከታች  ጀምሮ ሊሠራ እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡

ሌላኛው አንጋፋ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር ዶ/ር መሓሪ ረዳኢ ለዶ/ር አበራ አንድ ወሳኝ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ ‹‹የኢትዮዽያ መንግሥታት የቅቡልነት ዕጦት አለባቸው ብለው ደምድመዋል፡፡ ምናልባት መደምደሚያው ላይ ብዙም ችግር ላይኖር ይችላል፡፡ የእኔ ጥያቄ ድምዳሜው የተደረሰበት መንገድ ላይ ነው፡፡ የኃይለ ሥላሴና የደርግ መንግሥታት አሀዳዊ የመንግሥት መዋቅር ነበራቸው፡፡ አሁን የምንከተለው ደግሞ የፌደራል መዋቅር ነው፡፡ አሀዳዊ የመንግሥት መዋቅር ያለበትን የቅቡልነት ዕጦት ለመመርመር የምንጠቀመው መሣሪያ በተመሳሳይ የፌዴራል መዋቅርን ለመመርመር ጥቅም ላይ መዋል አለበት ወይ? ወይስ ተጨማሪ መሣሪያ ያስፈልጋል? የቅቡልነት ዕጦትስ አለ እያልን ያለነው በፌዴራል ደረጃ ነው ወይስ በክልል ደረጃ?›› ብለዋል፡፡

የቀድሞው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ዶ/ር ጴጥሮስ ኦላንጎ፣ ‹‹የነባሮቹን መንግሥታት ቅቡልነት መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ የአሁኑ መንግሥት ላይ ግን ልዩነት አለኝ፡፡ አመጣጡ በኃይል መሆኑ አንድ ጉዳይ ነው፡፡ ግን የሕዝብ ተሳትፎን ከማረጋገጥ አኳያ፣ በምርጫ አሸንፎ ከመምራቱ አንፃር፣ ሕገ መንግሥቱ ላይም መጀመርያ ሕዝቡ እንዲወያይበት በኋላ ላይ ደግሞ በሕዝብ ተወካዮች እንዲፀዲቅ መደረጉ ከመጀመርያዎቹ አይለየውም ወይ?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ዶ/ር ጴጥሮስ፣ ‹‹የምርጫ 97 ቅድመ ምርጫ ዴሞክራሲያዊ ከሆነ ድኅረ ምርጫው እንዴት ኢዴሞክራሲያዊ ሊሆን ይችላል? የተወሰነ ኃይል የሚፈልገውና ያሸንፋል ተብሎ የተገመተው ክፍል ሲሸነፍ ዴሞክራሲ አይደለም ብሎ እንደ መደምደም አይወሰድም ወይ?›› ሲሉም ሌላ ጥያቄ አክለዋል፡፡ 

ብሎገሩ አቶ በፍቃዱ ኃይሉ በበኩላቸው፣ ‹‹በሥራ ላይ ያለው ሕገ መንግሥት ላይ ተቃውሞ ያላቸው አካላት የመኖራቸውን ያህል ተጠብቆ እንዲቆይ የሚፈልጉም አካላት አሉ፡፡ አሁን ደግሞ እያደጉ የመጡ አመጾች ወይም ተቃውሞዎች አሉ፡፡ ባለፈው አንድ ክፍለ ዘመን ሕገ መንግሥቶችን እያፈረስንና እየገነባን ነው የመጣነው፡፡ አሁን በአገሪቱ ያሉ አመጾች ወይም ንቅናቄዎች አዲስ ሕገ መንግሥት እንዲረቀቅ ነው የሚፈልጉት? ወይስ እንዲጠበቅ ነው እየጠየቁ ያሉት? የትኛው ድምፅ ነው የሚያደላው?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ሌላኛው አንጋፋ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር አቶ ዘካሪያስ ቀንአ፣ ‹‹ሕገ መንግሥትና ሕገ መንግሥታዊነት እንደ ሌላው ሕግ ከሌሎች አገሮች በመቅዳት የምንሞክረው ነው? ኢትዮጵያ ውስጥ ላለፉት 60 ዓመታት የውጭ ሕጎች አልሠሩም፡፡ ከሞላ ጎደል ዘይትና ውኃ ሆነው ነው የቆዩት፡፡ ዛሬም ባህላዊና ልማዳዊ ሕጎች በብዙ መልኩ የበላይነት አላቸው፡፡ ስለዚህ ስለባህል ስናወራ በሕዝቡ ዘንድ ያለውን ባህል ነው? ወይስ ዘመናዊ ሕጎችን በተመለከተ ስላለው ባህል ነው የምናነሳው? ብዙ ነገሮቻችን ዘመናዊ ሕጎቻችንን ጨምሮ ለዕይታና ለማስመሰል ብቻ የሚውሉ ናቸው፡፡ ጥሩ ሕገ መንግሥትና ሕጎች ቢኖሩም አንተገብራቸውም፤›› ሲሉ ጥያቄና አስተያየታቸውን አቅርበዋል፡፡

የሕወሓት መሥራችና አንጋፋው ፖለቲከኛ አቶ ስብሐት ነጋ ደግሞ በአቶ በፍቃዱ ጥያቄ ላይ አስተያየት ሲሰጡ፣ ‹‹አሁን ያለው ተቃውሞ መነሻ በሕገ መንግሥቱ ቃል ገብቶ ያልፈጸማቸውና ያጎደላቸው መሠረታዊ ጉድለቶች አሉ መባሉ ነው እንጂ፣ ሕገ መንግሥቱ ይለወጥ አይደለም፡፡ ይኼ ማለት ሕገ መንግሥቱን የሚቃወም የለም ማለት አይደለም፤›› ብለዋል፡፡

በጥያቄዎቹና በአስተያየቶቹ ላይ ጥናት አቅራቢዎቹ በድጋሚ ሐሳባቸውን አካፍለዋል፡፡ በዚህም ዶ/ር አበራ በአጠቃላይ አሁን በሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት ቅቡልነት አስመልክተው ሲናገሩ፣ ‹‹የአገር ግንባታ በተቋማት ግንባታ መታገዝ አለበት፡፡ ይኼ ዴሞክራሲያዊ ሕገ መንግሥትን ይጨምራል፡፡ ተቋማቱ ሁሉን አካታች መሆን አለባቸው፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥታት ግን አግላይ፣ በዝባዥና ጠቅላይ የሆኑ ተቋማትን ነው ሲፈጥሩ የኖሩት፡፡ የኢኮኖሚውም ሆነ የፖለቲካው ዘርፍ ለልሂቃኑ ብቻ የተመቸና የተማከለ ነው፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ የተከፋፈሉ ማኅበረሰቦች የሚኖሩባቸው አገሮች ተቋማቱ ሁሉን አካታች መሆን አለባቸው፡፡ በተለይ ጠንካራ ቡድኖችን ካገለሉ ቀውስ ውስጥ መግባታቸው አይቀርም፡፡ መንግሥትም ቅቡልነት የሚያገኘው በአግባቡ ከተካተተውና ጥቅሙ ከተከበረለት ቡድን በተለይም ከቡድኑ ልሂቃን ነው፡፡ ሌሎቹ የተገለሉት ቡድኖች ግን ቅቡልነቱን መገዳደራቸው አይቀርም፤›› ብለዋል፡፡

ዶ/ር አበራ፣ ‹‹በሥራ ላይ ያለውን የፌዴራል መዋቅር ቅቡልነት እገዳደራለሁ፡፡ ኃይልን መሠረት ካደረገ አመራር ፈቃድን መሠረት ወዳደረገ አመራር አልመጣንም፡፡ የመንግሥት የመምራት መብት በሕዝቡ ተቃውሞ ጥያቄ ከቀረበበት የቅቡልነት ዕጦት መገለጫ ሊሆን ይችላል፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ በአግባቡ ሕዝቡ የመከረበት ሕገ መንግሥት አፅድቀን አናውቅም፡፡ ባህሉ እስካሁን ድረስ ልሂቃንን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ ሕዝብን መሠረት ያደረገና ከታች ወደ ላይ የሚሄድ አገዛዝም ኖሮ አያውቅም፡፡ ጥሩ ሕገ መንግሥት መያዝና ምርጫ ማካሄድ ቅቡልነት አያስገኝም፡፡ ሕገ መንግሥቱ ተግባር ላይ ካልዋለ በእውነታው ያ አገር ሕገ መንግሥት የለውም ማለት ነው፡፡ በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት የተወሰኑ ስኬቶች አስመዝግቧል፡፡ ከአሀዳዊ የመንግሥት መዋቅር ወደ ፌዴራል መዋቅር መምጣት በኢትዮጵያ ላሉት መሠረታዊ ችግሮች በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ዕውቅና ለመሰጠቱ ማሳያ ነው፡፡ ነገር ግን በትክክል ለመተርጎም ብዙ አልተሄደበትም፡፡ ከዴሞክራሲያዊ አገር የሚጠበቀው ሁሉን አካታችነት በተግባር የለም፡፡ አንድ ፓርቲ ፓርላማው ላይ ፍፁም የበላይ መሆኑ የት እንደምንገኝ ግልጽ ማሳያ ነው፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡

ዶ/ር ጌዲዮን በበኩላቸው፣ ‹‹መንግሥትና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ብቻ የፖለቲካ ባህሉን ሊቀይሩት አይችሉም፡፡ አብዛኛው ሥራ ከመንግሥት ውጪ ባሉ አካላት የሚከናወን ነው፡፡ አመለካከታችንና አስተሳሰባችንን የሚቀርፁ እንደ ቤተሰብ፣ ትምህርት ቤት፣ ሲቪል ማኅበራት፣ የሃይማኖት ተቋማትና የመሳሰሉት አካላት ቁልፍ ሚና አላቸው፡፡ ነገር ግን ለዚያ የሚሆን ምኅዳር መንግሥት መፍጠር አለበት፡፡ የፖለቲካ ባህሉን ከግምት ውስጥ ካስገባን ሕገ መንግሥታዊ ዴሞክራሲን ለመገንባት የምናደርገው ጥረት ከባድ እንደሚሆን ግምት ውስጥ ማስገባት አለብን፡፡ የፖለቲካ ባህላችን ይበልጥ ፈላጭ ቆራጭ በሆነ ቁጥር ጉዞው ይበልጥ ይከብዳል፡፡ የፖለቲካ ባህል ባይኖረንም መፍጠር እንችላለን፡፡ ከራሳችን ልማድና ባህል ጋር የተያያዘ ሕገ መንግሥት ብናፀድቅ በተሻለ ተግባራዊ ልናደርገው እንችላለን የሚል ክርክር ይነሳል፡፡ እኔ በዚህ አልስማማም፡፡ ምክንያቱም በባህላችንና በታሪካችን ያልነበሩ እንደ ፖሊስና እስር ቤት ያሉ አዳዲስ ተቋማትንና የአገዛዝ ሥርዓትን ከውጭ ሕጎች ውስጥ ነው ያገኘናቸው፡፡ የግድ ከውጭ ሕጎች ማምጣት አለብን ብዬ አላምንም፡፡ ነገር ግን የነበረው የሚበቃን አልመሰለኝም፡፡ መጨመርና አዲስ ነገር መፍጠር ይኖርብናል፤›› ብለዋል፡፡ 

‹‹በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 14፣15 እና 17 በሕይወት ስለመኖር፣ ስለአካል ደህንነትና ነፃነት መብት የዛሬ 22 ዓመት ቃል የገባውንና አሁን ያለንበትን ሁኔታ ስናይ፣ ሕገ መንግሥቱ ሕያው ነው ብሎ በሙሉ አፍ ለመናገር የሚያስደፍር አይመስለኝም፤›› ሲሉም ደምድመዋል፡፡   

 

Standard (Image)
Viewing all 475 articles
Browse latest View live