Quantcast
Channel: እኔ የምለዉ
Viewing all 475 articles
Browse latest View live

ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በኋላ

$
0
0

ባለፉት ሁለት ዓመታት በኢትዮጵያ ተከስቶ የነበረው አመፅና ተቋውሞ ከፍተኛ ጉዳት አስከትሎ አልፏል፡፡ የሰው ሕይወት ጠፍቷል፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር ንብረት ወድሟል፡፡ ከጎንደር እስከ ባህር ዳር፣ ከአሞቦ እስከ ወለጋ እንዲሁም ከኮንሶ እስከ ጉጂ ዞን ድረስ የተለያዩ ግጭቶችም ተፈጥረው ነበር፡፡

ኢሕአዴግ ወደ ሥልጣን ከመጣ ወዲህ በእንደዚህ ዓይነት ችግር ሲፈተን ከ1997 ዓ.ም. ምርጫ ወዲህ ይኼ ሁለተኛውና ትልቁ እንደሆነ ተንታኞች ሲናገሩ ተደምጧል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ ወጣቶች ስለቅማንትና ወልቃይት የማንነት ጥያቄ፣ ስለጠገዴና ፀገዴ፣ ኦሮሚያ ክልል ከአዲስ አበባ ልታገኘው ስለሚገባት ጥቅም፣ በአገሪቱ ስለተንሰራፋው ሙስናና ብልሹ አሠራር፣ በዳኝነት ስላለው የፍትሕ መጓደል፣ ስለወጣቱ የሥራ ዕድል ፈጠራና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ ጥያቄና ተቃውሞ ሲያነሱ ነበር፡፡

በእነዚህና ሌሎች ጥያቄዎች የተነሳ ተከስቶ በነበረው ተቃውሞ የበርካታ የሰው ሕይወት ከመጥፋቱ ባሻገር፣ የመሠረተ ልማቶችና የኢንቨስትመንት ተቋማት ወድመዋል፡፡ በርካታ ዜጎችም ለአስከፊ ችግር ተዳርገዋል፣ ከመኖሪያቸው ተፈናቅለዋል፡፡

የመከላከያ ሚኒስትርና ከሳምንት በፊት የፈረሰው ኮማንድ ፖስት ሴክሬታሪያት ኃላፊ የነበሩት አቶ ሲራጅ ፈጌሳ ዓርብ ሐምሌ 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንዲነሳ ባደረጉት ንግግር፣ ‹‹በአገሪቱ ተከስቶ በነበረው ብጥብጥ ዜጎች በሰላም ወጥተው መግባትና መደበኛ ሥራቸውን ማከናወን የማይችሉበት ሁኔታ ተፈጥሮ ነበር፤›› ብለዋል፡፡ ሚኒስትሩ በወቅቱ ተፈጠሮ በነበረው አመፅና ተቃውሞ ወጥቶ መግባት አዳጋች የሆነበት ደረጃ ላይ ተደርሶ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

ይኼንን ጉዳይ መንግሥት በመደበኛ የሕግ ማስከበር ሥርዓት መቆጣጠር እንደማይችል በመገምገም፣ በአገሪቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተደንግጎ ቆይቷል፡፡ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 93 መሠረት ከመስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ አገሪቱ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቆይታለች፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከታወጀበት ጊዜ አንስቶ ኮማንድ ፖስቱ በአገሪቱ ውስጥ ያሉ የፀጥታ ኃይሎችን በአንድ ሥር በማድረግና በተለያዩ ቀጣናዎች ከፋፍሎ በማደራጀት ወደ ሥራ ገብቷል፡፡ ሦስት መመርያዎችንም አውጥቶ ተግባራዊ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡

ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሳ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሲነሳ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ባቀረቡት ሪፖርት፣ በአገሪቱ ተከስቶ በነበረው አመፅና ተቃውሞ ወቅት በኦሮሚያ፣ በአማራና በደቡብ ክልሎች እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር 28,846 ዜጎች ሠልጥነው መለቀቃቸውንና የተወሰኑትም በቁጥጥር ሥር ውለው ጉዳያቸው እስካሁን ድረስ በፍርድ ቤት እየታየ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

‹‹በዚህም የተነሳ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲታወጅ መነሻ የነበሩ ሁኔታዎች በከፍተኛ ደረጃ እንዲቀንሱ ተደርገዋል፡፡ በአንዳንድ በውል የሚታወቁ አካባቢዎች የቀሩ አነሰተኛ ሥራዎች ቢኖሩም፣ በመደበኛው የሕግ አግባብ መቆጣጠር ይቻላል፤›› ብለው ነበር፡፡ እነዚህ በውል የሚታወቁ አካባቢዎች እነማን እንደሆኑ እንዲጠቅሱ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ጥያቄ የቀረበላቸው ቢሆንም ከመግለጽ ተቆጥበው ነበር፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም ለአሥር ወራት ያክል ተጥሎ የነበረውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ዓርብ ሐምሌ 28 ቀን 2009 ዓ.ም. አንስቷል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሲታወጅ ተደንግገው የነበሩ ዕግዶች ማለትም ሁከትና ጥብብጥ የሚያነሳሳ ቅስቀሳና ማድረግ፣ ከሽብርተኛ ጋር ግንኙነት ማድረግ፣ ያለፈቃድ ሠልፍና የአደባባይ ስብሰባ ማድረግ፣ በትምህርት ተቋማት አድማ ማድረግ፣ የተሽከርካሪዎችን እንቅስቃሴ ማወክ፣ በመሠረተ ልማቶች ላይ ጉዳት ማድረስ፣ ለሕዝብ አገልግሎት አለመስጠት፣ ወዘተ በሚሉ ጉዳዮች ላይ ገደቦች ተጥለው እንደነበር ይታወሳል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመነሳቱ በፊት በኮማንድ ፖስቱ ተደንግገው የነበሩ አንዳንድ ድንጋጌዎች ሲጣሱም ተስተውሏል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ከቀን ገቢ ግምት ጋር በተያያዘ በአዋጁ የተደነገገውን ለሕዝብ አገልግሎት አለመስጠት የሚለውን ድንጋጌ በመሻር፣ በክልሉ ውስጥ ያሉ ነጋዴዎች ለተወሰኑ ቀናት የንግድ ተቋማቸውን ዘግተው መዋላቸው ይታወሳል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በመሰል ልማቶችና ንብረቶች ላይ ጉዳት አለማድረስ የሚለውን ድንጋጌ በመሻር በክልሉ ከቀን ገቢ ግምት ጋር በተያያዘ በአምቦ ከተማ ተቀስቅሶ በነበረው ተቃውሞ በተሽከርካሪዎች ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡

በአማራ ክልል ጎንደር ከተማ የጦር መሣሪያ ይዞ መገኘት የሚለውን ድንጋጌ በመተላለፍ ሐምሌ 26 ቀን 2009 ዓ.ም. በከተማዋ ጥቃት ለማድረስ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሰዎች፣ በመንግሥት ቁጥጥር ሥር እንደዋሉም ተገልጾ ነበር፡፡

አቶ ሲራጅ በውል ያልታወቁ አንዳንድ አካባቢዎች የሚቀሩ ሥራዎች እንዳሉ ጠቅሰው እነዚህ አካባቢዎች እነማን እንደሆኑ ባይገልጹም፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመነሳቱ በሁለት ቀናት ልዩነት በባህር ዳር ከተማ የቦምብ ፍንዳታ ተከስቷል፡፡ በሳምንቱ ደግሞ በከተማዋ ለሁለተኛ ጊዜ የቦምብ ፍንዳታ ተከስቷል፡፡ በዚህም የተነሳ ዜጎች የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሲነሳ በአገሪቱ የተሻለ መረጋጋት እንደሚታይ ቢገመትም፣ ይኼ ሲሆን ግን እምብዛም አልታየም፡፡

አዋጁ ከተነሳ በኋላም በክልሎች በተለይም በአማራ ክልል የንግድ ተቋማትን የመዝጋት ተቃውሞ ታይቷል፡፡ በተለይም በምሥራቅ ጎጃም ዞን ውስጥ የሚገኙ ወረዳዎች ለምሳሌ በቢቡኝ፣ ስናንእንዲሁም ደቡብ ጎንደር ደብረ ታቦርና ደቡብ ወሎ ዞን ውስጥ ባሉ ወረዳዎች ተቃውሞ ተስተውሏል፡፡

የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) ማክሰኞ ነሐሴ 9 ቀን 2009  ዓ.ም. ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በአማራ ክልልም ሆነ በኦሮሚያ ክልል ፀረ ሰላም የሆኑ ኃይሎች በአገሪቱ እየተፈጠረ ያለውን ሰላምና መረጋጋት ለማደፍረስና ወደ ቀድሞ ሁኔታው ለመመለስ ጥረዋል፡፡ ‹‹ቢሆንም ግን ሕዝቡ ሰላም ወዳድ በመሆኑ ዓላማቸውን ማሳካት አልቻሉም፤›› ብለዋል፡፡

አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ በኋላም በአገሪቱ የተለየ ነገር ተደርጎ እንዳልታየም ገልጸዋል፡፡ አሁን ለተፈጠረው ሰላምና መረጋጋት ዋነኛው ምክንያት በአገሪቱ ታውጆ የነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንደነበር ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡

የመድረክ የውጭ ግንኙነት ኃላፊ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ግን አስቸኳይ ጊዜያዊ አዋጁ ተነሳም አልተነሳም፣ በአገሪቱ ያሉ ችግሮችን መቅረፍ እንዳልተቻለ ይሞግታሉ፡፡ የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ይልቃል ጌትነት (ኢንጂነር) በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ ችግር ከአስቸኳይ ጊዜያዊ አዋጁ መነሳትና አለመነሳት ጋር እንደማይያያዝ ይናገራሉ፡፡ ኢትዮጵያን ለዚህ ችግር የዳረጓት ዋነኛ ምክንያቶች የፖለቲካ ምኅዳሩ መጥበብ እንደሆነ አቶ ይልቃል ጠቁመዋል፡፡

ሚኒስትሩ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ በኋላ በአገሪቱ የፖለቲካ ይዞታ ላይ የተረጋጋ ሁኔታ መፈጠሩን ገልጸዋል፡፡ አቶ ይልቃል ግን በመሠረታዊነት በፖለቲካ ይዞታው ላይ ከአዋጁ መነሳት በኋላ የታየ ለውጥ የለም ብለው፣ በአዋጁ መነሳት የሕዝቡም ሆነ የመንግሥት ባህሪ እንዳልተቀየረ አመልክተዋል፡፡ ዜጎች አሁንም ተቃውሟቸውን በተለያዩ ዘዴዎች እየገለጹና መንግሥትም ዕርምጃ እየወሰደ መሆኑን ያብራራሉ፡፡

ፕሮፌሰር በየነ በበኩላቸው፣ ‹‹አዋጁ በነበረበት ጊዜም ሕዝቦች ሲጋጩ ነበር፡፡ አማሮና ጉጂ በሚባል አካባቢ ተነስቶ የነበረው ግጭት አዋጁ ከመነሳቱ በፊት ነው የነበረው፡፡ በዚህ ግጭት የብዙ ሰው ሕይወት ጠፍቷል፣ ንብረት ወድሟል፡፡ ይኼንን መሰል  ተቃውሞና ግጭት በአንዳንድ አካባቢዎች አሁንም አለ፤›› ብለዋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ ገና ትንሽ ጊዜ በመሆኑና በእነዚህ ቀናት ውስጥ ልዩነቶች ይመዘገባሉ ተብሎ እንደማይጠበቅ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ከአዋጁ በኋላም በአገሪቱ ተዓምር ተፈጥሯል ማለት አይቻልም ብለዋል፡፡ ምክንያታቸውን ሲያብራሩም በተለይ የሁለተኛው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከታወጀ ወዲህ በአገሪቱ የነበሩ ነገሮች ወደ ቀድሞ ሁኔታዎች ተቀይረው እንደነበርም አብራርተዋል፡፡ ሕዝቡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ስለመኖሩ ይጠራጠር እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ይኼ ደግሞ ሆነ ተብሎ የተደረገ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

‹‹በውጭው ዓለም በአንድ ዜና ብቻ ገበያው ከፍና ዝቅ የሚልበት ሁኔታ ቢኖርም፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ግን አስቸኳይ ጊዜያዊ አዋጁ በነበረ ጊዜም ሆነ ከተነሳ በኋላ ተፅዕኖ አላመጣም፤›› ብለዋል፡፡

ነገር ግን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ በኋላ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ መረጋጋት መታየቱን ገልጸዋል፡፡ ከአዋጁ መነሳት በኋላ በኢትዮጵያ የሚገኘው የእንግሊዙ ከፊ ሚነራልስ የስቶክ ኤክጄንጅ ዋጋ ከፍ ማለቱን እንዳስታወቀ መዘገባችን ይታወሳል፡፡

‹‹በአገር ውስጥ ያሉ ውስን ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለይም በድርድሩ ለመሳተፍ ፈቃደኛ ባይሆኑም፣ ከቀን ገቢ ግምቱ ጋር በተያያዘ የተነሳውን ተቃውሞ እንደ ዕድል በመቁጠር ኅብረተሰቡ በመንግሥት ላይ ጥርጣሬ እንዲኖረው ለማድረግ ሞክረዋል፡፡ ይኼ ድርጊታቸው ከአዋጁ መነሳት በኋላም የቀጠለ ቢሆንም፣ በሚገርም ሁኔታ ለእነሱ ምላሽ አልሰጠንም፤›› ብለዋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንዲነሳ ምክንያት ከሆኑት ጉዳዮች መካከል ዋነኛው በአገሪቱ በአሁኑ ወቅት የተሻለ ሰላምና መረጋጋት መፈጠሩ ነው፡፡ ይኼም ሆኖ ግን በባህር ዳርና  ውስን ሌሎች አካባቢዎች ተቃውሞ እየተነሳ ነው፡፡ ለዚህ ዋነኛ ምክንያቱ ምንድነው? የሚል ጥያቄ ለሚኒስትሩ ቀርቦላቸው በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹በሰላማዊ መንገድ ሳይሆን የፖለቲካ ሥልጣን መያዝ የሚቻለው በአመፅ ነው ብለው የሚያስቡ የፖለቲካ ተዋንያን፣ በተለይም ደግሞ ከውጭ ሆነው በተለያዩ የመረጃ መረቦች ማኅበራዊ ሚዲያን ጨምሮ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰላም የለም፣ አመፁ ቀጥሏል በማለት ለማደናገር በመሞከራቸው ነው፤‹› ብለዋል፡፡

አዋጁ መውጣት እንደሌለበትና ተፈጥሮ የነበረውን አመፅና ተቃውሞ በሃይማኖትም ሆነ በባህላዊ ዘዴ መፍታት ይቻል እንደነበር የገለጹት ፕሮፌሰር በየነ፣ ከወጣ በኋላም መንግሥት ዜጎችን ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ ለማሰር የተጠቀመት ዘዴ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

ባለፉት ሁለት ዓመታት ለተፈጠሩት ቀውሶች እንደ ምክንያት ከተወሰዱ ጉዳዮች መካከል አንዱ ከወጣቱ የሥራ ዕድል ፈጠራ ጋር የተያያዘ እንደሆነ መንግሥት በተደጋጋሚ ጊዜ ሲናገር ተደምጧል፡፡ ይኼንን ችግር ለመፍታትም አሥር ቢሊዮን ብር ተዘዋዋሪ ፈንድ በመበጀት ወጣቶች ወደ ሥራ እንዲገቡ መለማድረግ እየጣረ መሆኑን ገልጿል፡፡ ይኼ ተዘዋዋሪ ፈንድ ሙሉ በሙሉ በአገሪቱ ያሉ ወጣቶችን ችግር ይፈታል ተብሎ ባይታሰብም፣ ጥሩ ጅምር መሆንን የተለያዩ ባለሙያዎች በተለያየ ጊዜ ሲገልጹ ተደምጧል፡፡ ዶ/ር ነገሪም በአገሪቱ ተከስቶ የነበረውን የወጣቶች ችግር ለመቅረፍ መንግሥት ይኼን ተዘዋዋሪ ፈንድ መበጀቱ፣ ለሕዝብ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ያለውን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ተናግረዋል፡፡ ይኼን ተዘዋዋሪ ፈንድ በመጠቀም በአሁኑ ወቅት በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ወጣቶች ተጠቃሚ መሆናቸውንም አክለው ገልጸዋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ በኋላ መንግሥት ከወሰዳቸው ዕርምጃዎች መካከል ሌላው ጉዳይ ከሙስና ጋር በተያያዘ ተጠርጣሪዎችን ተጠያቂ ማድረግ መጀመሩን ነው፡፡ ከመልካም አስተዳደር ዕጦትና ከብልሹ አሠራር ጋር በተያያዘ በአገሪቱ ከፍተኛ ተቃውሞ ሲነሳ ቆይቷል፡፡ በዚህም የተነሳ በአሁኑ ወቅት በሙስና ከ50 በላይ ዜጎች በሕግ እንዲጠየቁ ለማድረግ ሒደቱ ተጀምሯል፡፡ ዶ/ር ነገሪ ይኼንን ጉዳይ በተመለከተ፣ ‹‹በመልካም አስተዳደር ችግር የተነሳ ዜጎች መብቶቻቸውን በአግባቡ ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል፡፡ በእነዚህ ኪራይ ሰብሳቢዎች ላይ እየተወሰደ ያለው ዕርምጃም ሕዝቡ ያነሳቸውን ጥያቄዎች ለመመለስ ታልሞ ነው፤›› ብለዋል፡፡

አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተነሳ ማግሥት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የውጭ ዲፕሎማቶችን ሰብስቦ እንደነበር የተገለጸ ሲሆን፣ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በመነሳቱ ምክንያት በቱሪዝም ዘርፍ ተከስቶ የነበረው ክፍተት ሊሞላ እንደሚችል የብዙዎች ተስፋ መሆኑ ተገልጿል፡፡

አቶ ይልቃል በቱሪዝም ዘርፍም ሆነ በኢኮኖሚው ለውጥ እንዳልታየ ይናገራሉ፡፡ ሚኒስትሩ ግን በቱሪዝምና በኢንቨስትመንት ዘርፎች አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ ወዲህ መሻሻሎች መታየቸውን ጠቁመዋል፡፡

ለአሥር ወራት በአገሪቱ ተጥሎ የነበረው አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከተነሳ ከአንድ ሳምንት በላይ ቢሆንም፣ ብዙ ነገሮች እየተሻሻሉና ለውጥ ያሳያሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ምንም እንኳ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በነበረበት ጊዜም ቢሆን ከዚያ በፊት በነበሩት ጊዜያት የተለየ ብዙም ሁኔታ እንዳልነበረ በተደጋጋሚ ጊዜ ሲገልጽ ቢሰማም፣ ዜጎች በተቀመጡ ገደቦች ላይ ከፍተኛ ፍርኃት አድሮባቸው እንደነበር ይገልጻሉ፡፡ አንዳንዶች አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ኖረም አልኖረ ፍርኃት እንዳለባቸው ይናገራሉ፡፡ መንግሥት ደግሞ በአስቸኳይ አዋጁ ተደንግገው የነበሩ ገደቦች በመነሳታቸው ሕጋዊና ሰላማዊ እንቅስቃሴ ማድረግ ይቻላል ይላል፡፡

 

Standard (Image)

በደቡብ ሱዳን ባገረሸው ጦርነት ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ መግባታቸውን ቀጥለዋል

$
0
0

በደቡብ ሱዳን መንግሥትና በአማፅያኑ ጦር መካከል ዳግም ባገረሸው ጦርነት፣ በርካታ ሲቪል ደቡብ ሱዳናውያን ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ መሆኑ ታወቀ፡፡

የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትር ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በደቡብ ሱዳን እየተካሄደ ባለው ጦርነት ንፁኃን ዜጎች ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ ነው፡፡ ነገር ግን ሚኒስትሩ ጨምረው እንደገለጹት፣ የታጠቁ ኃይሎች ወደ ኢትዮጵያ (ጋምቤላ) እየገቡ ነው የሚለው መረጃ ትክክል አይደለም፡፡

ሰሞኑን በደቡብ ሱዳን መንግሥትና በአማፂው ኃይል መካከል እንደ አዲስ ውጊያ መከፈቱ ይታወሳል፡፡ ሁለቱም ኃይሎች ጦርነቱን ድል እያደረጉ መሆኑን እየገለጹ ሲሆን፣ አማፂው ኃይል ፓጋክ የተሰኘውን ከተማ መቆጣጠሩን አስታውቋል፡፡  የደቡብ ሱዳን መንግሥት ግን ይኼ መረጃ  ትክክል እንዳልሆነ ገልጿል፡፡

በዚህ መካከል ሕይወታቸው አደጋ ውስጥ የገባ የደቡብ ሱዳን ሲቪል ዜጎች አካባቢያቸውን እየለቀቁ ወደ ጋምቤላ እየተሰደዱ መሆኑ ታውቋል፡፡ በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የስደተኞችና የስደት ተመላሾች ጉዳይ አስተዳዳር የኮሙዩኒኬሽንና ኢንፎርሜሽን ቡድን መሪ አቶ ሱሌይማን አሊ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከደቡብ ሱዳን በርካታ ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ ነው፡፡

አቶ ሱሌይማን እንደገለጹት፣ እስካሁን ከ380 ሺሕ በላይ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች ኢትዮጵያ ገብተዋል፡፡ አሁንም በመግባት ላይ ናቸው፡፡ የሚገቡት ስደተኞች በጋምቤላና በኦሮሚያ ድንበር ላይ በሚገኙ ሰባት የስደተኞች ካምፕ ውስጥ እየተስተናገዱ እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡

‹‹አብዛኛዎቹ ስደተኞች ሕፃናትና ሴቶች ናቸው፡፡ ተዋጊ ኃይል ወደ ካምፖቹ እንዳይገባ የመለየት ሥራ ይካሄዳል፤›› ሲሉ አቶ ሱሌይማን አክለዋል፡፡

 

Standard (Image)

አራተኛው የሥነ ሕዝብና ጤና ሪፖርት የሕፃናት ሞት የመቀነስ አዝማሚያ አሳይቷል አለ

$
0
0

በዳዊት እንደሻው

በማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ ይፋ የተደረገው አራተኛው የሥነ ሕዝብና ጤና ሪፖርት፣ በኢትዮጵያ የሕፃናት ሞት የመቀነስ አዝማሚያ ማሳየቱን አስታወቀ፡፡

ማክሰኞ ነሐሴ 9 ቀን 2009 ዓ.ም. የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ፕሮፌሰር ይፍሩ ብርሃኔና የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ ኃላፊዎች በተገኙበት ይፋ የተደረገው ጥናት፣ ከ2003 ዓ.ም. እስከ 2008 ዓ.ም. ያለውን ጊዜ የሚያካትት ነው፡፡ በሥነ ሕዝብና በጤና ዘርፍ የተለያዩ ግኝቶችን ይዟል፡፡

ዕድሜያቸው ከ15 እስከ 49 የሆኑ 15,783 ሴቶች፣ 12,688 ወንዶች፣ እንዲሁም 16,650 አባዎራዎችን እንደ ናሙና በመውሰድ በዘጠኙ ክልሎችና በሁለቱ የፌዴራል ከተሞች ላይ ጥናቱ መከናወኑም ተጠቁሟል፡፡

ጥናቱ የሕፃናት ሞት ከአምስት ዓመት በፊት ከነበረው አኃዝ ቅናሽ እንዳሳየ አመልክቷል፡፡ ከአምስት ዓመት በፊት ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች ከሆኑ 1,000 ሕፃናት 88 የሚሆኑት የአምስተኛ የልደት በዓላቸውን ከማክበራቸው በፊት ይሞቱ ነበር፡፡ ነገር ግን አሁን በወጣው ሪፖርት ይህ ቁጥር ወደ 67 ቀንሷል፡፡ ይህ ማለት ዕድሜያቸው በተጠቀሰው ክልል ውስጥ ከሚገኙ 15 ሕፃናት አንዱ ዕድሜው አምስት ከመሙላቱ በፈት ይሞታል ማለት ነው፡፡ ይህ አኃዝ ከክልል ክልል ይለያያል፡፡ በአፋር ክልል ውስጥ ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች ከሆኑት 1,000 ሕፃናት ውስጥ 125 ይሞታሉ፡፡ ይህም በአገር አቀፍ ደረጃ ትልቁ ነው፡፡ በተቃራኒው አዲስ አበባ ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆኑ 39 ሕፃናትን በማጣት የመጨረሻውን ደረጃ ይዟል፡፡

ሌላው በሪፖርቱ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል የተባለው በሕፃናት ላይ እየታየ ያለው የቀይ ደም ሕዋሳት እጥረት መጨመር ነው፡፡ ሪፖርቱ ዕድሜያቸው ከ15 እስከ 49 ወር ከሆኑ ሕፃናት ውስጥ ወደ 57 በመቶ የሚሆኑት እጥረት አለባቸው ብሏል፡፡ ይህ አኃዝ ከአምስት ዓመት በፊት 44 በመቶ ብቻ ነበር፡፡

‹‹ይህ የጥናት ሪፖርት ትኩረት የሚያስፈልገውና በጥልቅ መታየት ያለበት ነው፤›› ሲሉ የጤና ሚኒስትሩ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡

‹‹ከዚህም ጥናት ውጤት ተነስተን በሕፃናት ላይ የተለያዩ ሥራዎች እናከናውናለን፡፡ ለምሳሌ የትምህርት ቤት ውስጥ የምገባ ሥርዓት ማጠናከር፣ ለቀይ ደም ሕዋሳት እጥረት መፍትሔ የሚሆኑ መድኃኒቶች በቤቶችና በትምህርት ቤቶች ማሠራጨት ይከናወናል፤›› ብለዋል፡፡

ከሴቶች ግርዛት ጋር ያሉ አኃዞች መጠነኛ መሻሻል ማሳየቱን ያመለከተው ሪፖርቱ፣ ዕድሜያቸው ከ15 እስከ 49 ካሉ ሴቶች ውስጥ 65 በመቶ የሚሆኑት የተገረዙ ሲሆን፣ ይህም በ1997 ዓ.ም. ከነበረው 77 በመቶ ቅናሽ አሳይቷል፡፡

አኃዙ በክልል ሲታይ በሶማሌ 99 በመቶ ሲሆን፣ ይህም ክልሉን በአንደኝነት አስቀምጦታል፡፡ በተቃራኒው ትግራይ ክልል 24 በመቶ በመያዝ መጨረሻ ደረጃን ይዟል፡፡ አዲስ አበባ 54 በመቶ በመያዝ 33 በመቶ የያዘውን ጋምቤላ ክልልን በመከተል በሦስተኛ ደረጃ ተቀምጧል፡፡

ሌላው በጥናቱ ላይ የተመለከተው የወሊድ መጠን ሲሆን፣ ከ16 ዓመት በፊት ከነበረው 5.5 ልጆች በአንድ ሴት አማካይ ቁጥር የ0.9 ልጆች ቅናሽ በማሳየት በአገር አቀፍ ደረጃ 4.6 ልጆች በአንድ ሴት ደርሷል፡፡

ይህ አኃዝ በክልል ከአምስት ዓመት በፊት የነበረው ደረጃ ሲታይ በአፋር፣ በሐረሪ፣ በአዲስ አበባና በትግራይ ክልሎች የሚገኙ ሴቶች የወሊድ መጠን ጨምሯል፡፡ በተቃራኒው እንደ አማራ፣ ኦሮሚያ፣ ቤኒሻንጉል ጉምዝ፣ ደቡብ ክልል፣ ጋምቤላ እንዲሁም የድሬዳዋ አስተዳደር ቅናሽ አሳይተዋል፡፡

በክልሎች ያለውን የወሊድ መጠን ሲታይ ሶማሌ 7.2፣ አፋር 5.5፣ እንዲሁም ኦሮሚያ 5.5 ልጆች በአማካይ በአንድ ሴት በመሆን ከአንድ እስከ ሦስት ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡ በሌላ በኩል አዲስ አበባ 1.8 ልጆች በመሆን የመጨረሻውን ደረጃ ይዟል፡፡

‹‹ከወሊድና ከጋብቻ ጋር በተያያዘ ዕድሜያቸው ከ15 እስከ 49 ከሚሆኑ ሴቶች 13 በመቶ የሚሆኑት የመጀመርያ ልጃቸውን ያረገዙ ወይም የወለዱ ናቸው፤›› ሲል ሪፖርቱ ያመላክታል፡፡ ከጋብቻ ጋርም በተያያዘ ወደ 11 በመቶ የሚሆኑት ዕድሜያቸው ከ15 እስከ 49 የሚሆኑ ሴቶችና አምስት በመቶ የሚሆኑት በተመሳሳይ ዕድሜ ያሉ ወንዶች ከአንድ በላይ ሚስት ወይም ባል አላቸው ተብሏል፡፡

በተመሳሳይ የዕድሜ ክልል ውስጥ ከሚገኙ ያገቡ ሴቶች መካከል 35 በመቶ የሚሆኑት ብቻ ዘመናዊ የወሊድ መከላከያ እንደሚጠቀሙ ተመልክቷል፡፡ በተመሳሳይ በክልል ደረጃ ሶማሌ ክልል ውስጥ ካገቡ ሴቶች ውስጥ አንድ በመቶ የሚሆኑት ብቻ ዘመናዊ የወሊድ መከላከያ የሚጠቀሙ ሲሆን፣ ይህም ክልሉን በአገር አቀፍ ደረጃ መጨረሻ ደረጃ ላይ አስቀምጦታል፡፡ በተመሳሳይ በአዲስ አበባ ከተማ ከሚኖሩ ያገቡ ሴቶች ውስጥ ግማሽ ያህሉ የመከላከያው ተጠቃሚ በመሆን በአገር አቀፍ ደረጃ ቀዳሚ ሆነዋል፡፡

ዕድሜያቸው ከ12 እስከ 23 ወራት ለሆኑ ሕፃናት ከሚሰጠው ክትባት ጋር በተያያዘ በአገር አቀፍ ደረጃ 39 በመቶ የሚሆኑት ስምንቱንም ክትባቶች እንደተከታተሉ ተመልክቷል፡፡ በክልል ደረጃ አዲስ አበባ 89 በመቶ፣ ትግራይ 67 በመቶ፣ እንዲሁም ቤኒሻንጉል ጉምዝ 37 በመቶ በመያዝ ከአንድ እስከ ሦስት ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡

ይህ ለአራተኛ ጊዜ የወጣው ሪፖርት ከተለያዩ ለጋሽ ድርጀቶች ጋር በመተባበር የተሠራ ሲሆን፣ ስድስት ሚሊዮን ዶላር ወጪ እንደተደረገበት ተገልጿል፡፡

 

 

Standard (Image)

በባህር ዳር ከተማ ቦምብ በማፈንዳት የተጠረጠሩ ግለሰቦች መያዛቸው ተገለጸ

$
0
0

አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ ሁለት ሳምንት ሳይሞላው ለሁለተኛ ጊዜ በባህር ዳር ከተማ ቦምብ በማፈንዳት የተጠረጠሩ ግለሰቦች፣ ጫካ ውስጥ ሲንቀሳቀሱ መያዛቸውን የከተማው ፖሊስ መምርያ አስታወቀ፡፡

የመምርያው ኃላፊ ኮማንደር ዋለልኝ ዳኘው ማክሰኞ ነሐሴ 9 ቀን 2009 ዓ.ም. ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ቅዳሜ ምሽት በባህር ዳር ከተማ ቀበሌ 04 በተለምዶ ብሔራዊ ሎተሪ ቅርንጫፍ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ቦምብ በማፈንዳት የተጠረጠሩ ወጣቶች ወደ ትውልድ ቦታቸው ጎንደር ለማምለጥ ጫካ ውስጥ ሲንቀሳቀሱ ተይዘዋል፡፡

ፍንዳታው በተከሰተበት ወቅት ተጠርጣሪ መያዝ እንዳልተቻለ የጠቆሙት ኃላፊው፣ በሒደት በተደረገው ጥረትና በኅብረተሰቡ ድጋፍ ሦስት ተጠርጣሪዎች መያዛቸውን ገልጸዋል፡፡ አንደኛው ቦምብ ገዝቶ ለአፈንጂዎች እንደሰጠ የተጠረጠረ ሲሆን፣ ሁለቱ ደግሞ ከድርጊቱ ጋር ተሳትፈዋል ተብለው የተጠረጠሩ መሆናቸውን አክለዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ ድርጊቱ በተከሰተ በሁለተኛው ቀን ሰኞ ነሐሴ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. መያዛቸውን ጠቁመው፣ ባህር ዳር ውስጥ በመንግሥት ሥራ ላይ እንደነበሩ አስረድተዋል፡፡ ሁለቱ የትውልድ ቦታቸው ደቡብ ጎንደር ዞን ውስጥ መሆኑንና ወደዚያ ሄደው ለማምለጥ ሲሉ መያዛቸውን ገልጸዋል፡፡

እነዚህ ሦስት ተጠርጣሪዎች አፈነዱት በተባለው ቦምብ በሁለት ወጣቶች ላይ ጉዳት መድረሱን ኮማንደሩ አክለው ገልጸዋል፡፡ ጉዳት ከደረሰባቸው ወጣቶች መካከል አንደኛው የ25 ዓመት ዕድሜ እንዳለው፣ ጉዳት የደረሰበትም ኳስ ጨዋታ ለማየት ከቤቱ ወጥቶ ሲሄድ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሌላኛዋ ተጎጂ ደግሞ የ22 ዓመት ወጣት እንደሆነችና ከሥራ ወደ ቤቷ ስትገባ ጉዳት የደረሰባት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ሁለቱ ተጎጂዎች የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች መሆናቸውን ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅት በፈለገ ሕይወት ሆስፒታል የሕክምና ዕርዳታ እያገኙ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

እንደ ኮማንደር ዋለልኝ ገለጻ፣ ሁለት ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በባህር ዳር ከተማ ሁለት የቦምብ ፍንዳታዎች አጋጥመዋል፡፡ በዚህ ሳምንት ውስጥ ሌሎች ተጨማሪ ሊፈነዱ ተዘጋጅተው የነበሩ ሁለት ቦምቦችን ማምከን መቻሉንም ተናግረዋል፡፡

‹‹ይህ ችግር ሊፈጠር የቻለው ፀረ ሰላም ኃይሎች በከተማዋ ውስጥ ያሉ ወጣቶችን በማታለልና ገንዘብ በመስጠታቸው ነው፤›› ብለዋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተነሳ ማግሥት የአማራ ክልል መዲና በሆነችው ባህር ዳር ባለፈው ዓመት የሞቱ ዜጎችን ለማሰብ በተካሄደው ተቃውሞ ጋር በተያያዘ፣  የተለያዩ ሰዎች ስለመታሰራቸው መዘገባችን ይታወሳል፡፡ 

Standard (Image)

ለሕዝብና ቤት ቆጠራ የተገዙ ኮምፒዩተሮችና ፓወር ባንኮች እስካሁን አልቀረቡም

$
0
0

በዳዊት እንደሻው

      የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ በሚቀጥለው ዓመት ለሚያከናውነው የሕዝብና ቤቶች ቆጠራ የተገዙ 180 ሺሕ ታብሌት ኮምፒዩተሮችና 126 ሺሕ ፓወር ባንኮች እስካሁን አልቀረቡም፡፡ ኤጀንሲው በአንድ ወር ውስጥ እንዲቀርቡለት ጠይቋል፡፡

      በሐምሌ ወር በተደረገ የኮንትራት ውል ሌኖቮና ህዋዌ የተባሉ ሁለት ዓለም አቀፍ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዕቃዎች አምራች ድርጀቶች፣ በ665 ሚሊዮን ብር ክፍያ ዕቃዎችን እንዲያቀርቡ መታዘዙ ይታወሳል፡፡

በዚህም መሠረት ሁለቱ ኩባንያዎች እያንዳንዳቸው 90 ሺሕ ኮምፒዩተር ታብሌቶችን፣ እንዲሁም ፓወር ባንኮችን በተመለከተም እያንዳንዳቸው 36 ሺሕ እንዲያቀርቡ ተብሎ ነበር፡፡

ዕቃዎቹን እያመረቱ ከሥር ከሥር እንዲያቀርቡና በሦስት ወራት ውስጥ እንዲያጠናቅቁ ስምምነት ላይ ተደርሶ ነበር፡፡

ነገር ግን እስካሁን አንዳቸውም ኩባንያዎች የመጀመርያውን ዙር አቅርቦት እንኳን እንዳልጀመሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በኅዳር 2010 ዓ.ም. የሚደረገው የሕዝብና የቤቶች ቆጠራ የተለያዩ ዝግጅቶች ሲደረጉለት የቆዩ ሲሆን፣ ይህ ግዥ በነበረው የተጫራቾች እሰጥ አገባና ቅሬታ ምክንያት ከተጠበቀው በላይ ጊዜ ፈጅቷል፡፡

ጨረታው መጀመርያ ሲጀመር ዕቃዎቹ በግንቦት 2009 ዓ.ም. ይቀርባሉ ተብሎ የነበረ ቢሆንም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡

‹‹ከሁለቱ ኩባንያዎች የሚቀርቡት ዕቃዎች ቢያንስ የመጀመርያው ዙርና አብዛኛው አቅርቦት መስከረም ላይ እንዲመጣ ጫና እየፈጠርን ነው፤›› ሲሉ፣ የኤጀንሲው ምክትል ዳይሬክተር አቶ አሰልፌው አበራ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ወደ ሦስት ቢሊዮን ብር ተበጅቶለት እየተከናወነ ያለው የሕዝብ የቤቶች ቆጠራ ዝግጅት፣ ወደ 40 በመቶ የሚሆነው ወጪ በለጋሾች የሚሸፈን ነው፡፡

‹‹በቅርቡ አጠቃላይ ዝግጅቶቹንና ቀጣይ ሥራዎችን ይፋ እናደርጋለን፤›› ሲሉ የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ቢራቱ ይገዙ ገልጸዋል፡፡

 

Standard (Image)

መኢአድና ሰማያዊ ሕዝባዊ ስብሰባ ለማካሄድ ተቸግረናል አሉ

$
0
0

በአገሪቱ ወቅታዊ ጉዳይ ከአዲስ አበባ ሕዝብ ጋር እሑድ ነሐሴ 7 ቀን 2009 ዓ.ም. በመብራት ኃይል አዳራሽ ውይይት ለማድረግ ያስገቡትን የዕውቅና ጥያቄ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምላሽ ባለመስጠቱ ምክንያት የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና ሰማያዊ ፓርቲ (ሰማያዊ) ዕቅዳቸውን መሰረዛቸውን አስታወቁ፡፡

ፓርቲዎቹ ይህን ያስታወቁት ቴዎድሮስ አደባባይ አካባቢ በሚገኘው የመኢአድ ዋና ጽሕፈት ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሆን፣ መግለጫውን የሰጡት ደግሞ የመኢአድ ፕሬዚዳንት በዛብህ ደምሴ (ዶ/ር)፣ የሰማያዊ ፕሬዚዳንት አቶ የሺዋስ አሰፋና የመኢአድ ዋና ጸሐፊና የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አዳነ ጥላሁን ናቸው፡፡

‹‹ሕዝባዊ ሰብሰባ እንደምናደርግ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በአንድ ደብዳቤ ብናሳውቅም፣ ‹ሁለቱ ፓርቲዎች በጋራ ስብሰባ ለማካሄድ በአንድ ደብዳቤ መጠየቅ አይችሉም› የሚል አሳማኝ ያልሆነ መልስ ተሰጥቶናል፡፡ ምንም እንኳን የተሰጠንን መልስ ባናምንበትም ለፕሮግራማችን መሳካት ሲባል አስተዳደሩ ባሳሰበው መሠረት፣ በየፓርቲዎቹ ፕሬዚዳንት ፊርማ በተናጠል በድጋሚ በጽሑፍ ጠይቀናል፡፡ ሆኖም  ጥያቄያችንን ተቀብሎ የሚያስናግድ አካል ባለመኖሩ ከአዲስ አበባ ሕዝብ ጋር ውይይት ማካሄድ አልቻልንም፤›› በማለት የፓርቲዎቹ መግለጫ ያትታል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት የሰላማዊ ሠልፍና ሕዝባዊ ስብሰባ ክፍል በበኩሉ ከፓርቲዎቹ ደብዳቤ እንደደረሰው ያረጋገጠ ሲሆን፣ ነገር ግን ኃላፊነት የሚወስድ አካል ከፓርቲዎቹ ባለመቅረቡ ምንም ዓይነት ነገር ማድረግ አለመቻሉን ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ አንድ ኃላፊ ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡

‹‹ፓርቲዎቹ ደብዳቤ አስገብተዋል፡፡ ነገር ግን ማሟላት ያለባቸውን ቅድመ ሁኔታዎች አላሟሉም፡፡ ደብዳቤውን ብቻ ጥለው ነው የሄዱት፡፡ ከዚህ አንፃር ኃላፊነት የሚወስድ አካል በሌለበት ሁኔታ ምን ማድረግ እንችላለን?›› በማለት የፓርቲዎቹን ስሞታ በጥያቄ ሞግተዋል፡፡

ምንም እንኳን አስተዳደሩ ይህን ቢልም፣ ‹‹በጋራ የሚለውን ቃል ከደብዳቤው እንድናወጣ፣ ካልሆነ ፎርም እንደማያስሞሉን ገልጸውልናል፡፡ ነገር ግን ይህን የሚገልጽ ደብዳቤ ስጡን ስንል ደብዳቤ የመስጠት ግዴታ የለብንም የሚል ምላሽ ሰጥተውናል፡፡ ስለዚህ ይህ ሆን ተብሎ ሰብሰባውን የማደናቀፍ ተግባር ነው፤›› በማለት አቶ የሺዋስ የአስተዳደሩን ምላሽ ተችተዋል፡፡

የሕዝባዊ ስብሰባው ዋነኛ ዓላማ ከሕዝቡ ጋር በወቅታዊና በአንገብጋቢ ጉዳዮች ላይ ለመወያየት እንደነበር አቶ የሺዋስ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

‹‹የስብሰባው ዋነኛ ዓላማ የነበረው ለአሥር ወራትና ከዚያም በፊት ለዓመታት ተዘግቶ የነበረውን በፓርቲዎችና በሕዝብ መካከል የነበረውን ግንኙነት መክፈት ነበር፡፡ ከሕዝቡ ጋር እንነጋገራለን የሚለውንም እንሰማለን የሚል ዓላማ ነበረው፡፡ ነገር ግን መንግሥት ይህንን ዕድል ነው የዘጋብን፤›› በማለት አክለው አስረድተዋል፡፡

‹‹ምንም እንኳን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተነስቷል ተብሎ ወደ መደበኛው የሕግ ሥርዓት ተመልሰናል ቢባልም፣ እየሆነ ያለው ነገር ግን ከዚያ የባሰ ነው፤›› ሲሉ አቶ የሺዋስ በምሬት ገልጸዋል፡፡ ‹‹በዚህ ሁኔታ ውስጥ እንዴት ፖለቲካ መሥራት ይቻላል? ሕዝቡንና አገሪቷንስ እንዴት ወደ ሰላም ማምጣት ይቻላል?›› ሲሉ አቶ የሺዋስ ይሞግታሉ፡፡

‹‹ገዢው ፓርቲ ፍርኃት ውስጥ ነው፡፡ ፍርኃት ውስጥ ሆኖ ደግሞ ምንም አማራጭ ለሕዝብ እንዳናቀርብ እያደረገን ነው፡፡ ያ ደግሞ አገሪቱን የባሰ ችግር ውስጥ የሚጥል በመሆኑ መንግሥት ለሕዝብ ማሰብ አለበት፡፡ የፓርቲዎችን ሥራ ማክበርና ሥራቸውን እንዳይሠሩ እንቅፋት መፍጠር የለበትም፤›› ሲሉ አቶ የሺዋስ አስረድተዋል፡፡

የመኢአድ ፕሬዚዳንት በበኩላቸው የእንደዚህ ዓይነት ስብሰባዎች ውጤት የሚጠቅመው መንግሥትን እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

‹‹እሑድ ዕለት በመብራት ኃይል አዳራሽ ለማካሄድ አቅደነው የነበረው ስብሰባ ዋናው ቁም ነገር የነጋዴው ኅብረተሰብ አባላት አለብን የሚሉት ችግር ላይ ለመወያየት ነው፡፡ እንዲህ ያለው ውይይት ደግሞ የሚጠቅመው ለራሱ ለመንግሥት ነው፤›› ብለዋል፡፡

ዶ/ር በዛብህ መንግሥት ስብሰባ እንዳይካሄዱ የሚፈራበት ምክንያት ሊገባቸው እንዳልቻለም ገልጸዋል፡፡ ‹‹እኛ ድብቅ አጀንዳ የለንም፡፡ በግልጽ ነው የምንታገለውና የመንግሥትን ድክመት ለማጋለጥ የምንሞክረው፡፡ ይህ ደግሞ ሥራችንም ነው፡፡ ለዚሁ ነው ተመዝግበን የምንታገለው፡፡ እንደዚሁ ለጨዋታ ወይም የምናገኘው ፍርፋሪ ስላለ አይደለም፡፡ በራሳችን ነው የምንታገለው፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡

በመሆኑም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሁለቱ ፓርቲዎች ለጠየቁት ጥያቄ አፋጣኝና በጎ ምላሽ መስጠት ሲገባው፣ ይህን ለማድረግ ፈቃደኛ ባለመሆኑ የሁለቱን ፓርቲዎች ሕገ መንግሥታዊ መብት መጋፋቱን አጥብቀው እንደሚያወግዙ ፓርቲዎቹ በጋራ መግለጫቸው ገልጸዋል፡፡

 

Standard (Image)

የገቢዎችና ጉምሩክ የቀረጥ ነፃ ማስፈጸሚያ መምርያ ኃላፊ በድጋሚ ጊዜ ቀጠሮ ተጠየቀባቸው

$
0
0

በኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን በመንግሥት የተሰጡ ከቀረጥ ነፃ መብቶች ማስፈጸሚያ መምርያ ኃላፊ፣ በተጠረጠሩበት ከአሥር ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት ማድረስ ወንጀል በድጋሚ 14 ቀናት ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ተጠየቀባቸው፡፡

የመምሪያ ኃላፊዋ ዓለምፀሐይ ግርማይ (ዶ/ር) የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን በቁጥጥር ሥር ያዋላቸው፣ ወደ ውጭ አገር ሊወጡ ሲሉ መሆኑን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

መርማሪ ቡድኑ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሁለተኛ ወንጀል ችሎት ነሐሴ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዳስረዳው፣ ተጠርጣሪዋ የተለያዩ ድርጅቶች ከቀረጥ ነፃ እንዲያስገቡ ከተፈቀደላቸው በላይ እንዲያስገቡ በመፍቀድ፣ መንግሥት ማግኘት የነበረበትን 10,697,468 ብር በማሳጣት ጉዳት አድርሰዋል፡፡

መኖርያ ቤታቸው ተበርብሮ የተለያዩ ማስረጃዎች መሰብሰቡን የገለጸው መርማሪ ፖሊስ፣ ለኦዲተር በማቅረብ ሙያዊ ትንተና እያሠራ መሆኑን ገልጿል፡፡ ዕቃዎችን ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት የተለያዩ ድርጅቶች የጠየቁባቸውን ደብዳቤዎች መሰብሰቡንና የውስን ኦዲት ምርመራ ቃል መቀበሉንም አስረድቷል፡፡

ከውጭ አገር የሚያስመጣቸው ዲክላራሲዮኖች እንዳሉ፣ የተለያዩ ሰነዶችን መሰብሰብ እንደሚቀረው፣ የምስክሮችና የባለሙያዎች ምስክሮችን ቃል መቀበል እንደሚቀረው፣ ከባለሥልጣኑ ማብራሪያ እንደሚጠይቅ፣ ውስን የኦዲት ምርመራ እንደሚቀረውና የፎረንሲክ ምርመራ ውጤት እንደሚቀረው በማስረዳት፣ ተጨማሪ 14 ቀናት የምርመራ ጊዜ እንዲፈቀድለት ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡

ተጠርጣሪዋ በጠበቃቸው አቶ አበበ አሳመረ አማካይነት ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት፣ መርማሪ ቡድኑ እፈልጋቸዋለሁ የሚላቸው ሰነዶች በሙሉ በተቋሙ የሚገኙ ናቸው፡፡ ደንበኛቸው የተያዙት ከቀረጥ ነፃ የተፈቀዱ ዕቃዎችን ከተፈቀደላቸው በላይ እንዲያስገቡ ፈቅደዋል ተብለው መሆኑን አቶ አበበ አስታውሰው፣ ዕቃዎቹ ሲገቡ ዲክላራሲዮን የሚያዘጋጀው ባለሥልጣኑ መሆኑ እየታወቀ፣ መርማሪው ዲክላራሲዮን ሳይይዝ ደንበኛቸውን ማሰሩ ተገቢ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡፡

ተጠርጣሪዋ የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና ወንጀል ጠርጥሯቸው ከ2005 ዓ.ም. እስከ 2008 ዓ.ም. ድረስ ምርመራ ተደርጎባቸው ምንም ነገር ስላልተገኘባቸው በነፃ መሰናበታቸውንና ማረጋገጫ ሠርተፊኬት እንደተሰጣቸውም ጠበቃው ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ተቋሙን ከለቀቁ አራት ዓመታት፣ ከኃላፊነት ከተነሱ ደግሞ ስድስት ዓመታት እንዳለፋቸውም አክለዋል፡፡

መርማሪ ቡድኑ በሰጠው ምላሽ፣ ተጠርጣሪዋ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረውና በምርመራ ነፃ የተባሉት በአሁኑ አሠራር ሳይሆን ቀድሞ በነበረው የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን መሆኑን አስረድቷል፡፡ አሁን ግን 10,697,648 ብር ጉዳት ማድረሳቸውን አክሏል፡፡ የተያዙትም በወንጀል እንደሚፈለጉ አውቀው ከአገር ሊሸሹ ሲሉ መሆኑንም መርማሪ ቡድኑ ተናግሯል፡፡ ምርመራ እየተጣራባቸው በመሆኑም የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ በማድረግ የጠየቀውን የ14 ቀናት ተጨማሪ ጊዜ እንዲፈቀድለት ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡

ተጠርጣሪዋ ፍርድ ቤቱ እንዲናገሩ እንዲፈቅድላቸው ጠይቀው ሲፈቀድላቸው እንደተናገሩት፣ ከገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የታገዱት በ2005 ዓ.ም. ነው፡፡ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ለአንድ ዓመት አጥንተው ከአሜሪካ ሲመለሱ፣ ፀረ ሙስና ኮሚሽን ምርመራ አካሂዶባቸው ነፃ ሆነው በመገኘታቸው ሠርተፊኬት ተሰጥቷቸዋል፡፡

የታገዱ ካርታ፣ የባንክ ደብተሮችና ሌሎች ንብረቶችም እንደተመለሱላቸው አስረድተዋል፡፡ አሁን የሚሠሩት ኢንቨስትመንት ላይ ከሚሠራ የአሜሪካ ድርጅት ጋር መሆኑንና የውጭ ባለሀብቶችን እያግባቡ በኢትዮጵያ ኢንቨስት እንዲያደርጉ በመሥራት ላይ መሆናቸውን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ባለፈው በጀት ዓመትም ለኢትዮጵያ ከ20 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሪ ማስገኘታቸውንም አክለዋል፡፡

ተጠርጣሪዋ እንዴት እንደተያዙ ለፍርድ ቤቱ ሲያስረዱ፣ አለቃቸውን ለአምስት ቀናት አስፈቅደው ዱባይ ደርሰው ለመመለስ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ፣ በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት ሠራተኞች መያዛቸውንና ለፌዴራል ፖሊስ ተላልፈው መሰጠታቸውን ተናግረዋል፡፡ ትዳርም ሆነ ልጅ እንደሌላቸው በመግለጽ ፍርድ ቤቱ ትኩረት ሰጥቶ እንዲያይላቸው ጠይቀዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ ግራ ቀኙን ከሰማ በኋላ በሰጠው ትዕዛዝ መርማሪ ቡድኑ የጠየቀውን 14 ቀናት ሳይሆን ሰባት ቀናት ለመጨረሻ ጊዜ መፍቀዱን አስታውቆ፣ ተጠርጣሪዋ የጠየቁትን ዋስትና እንዳልተቀበለው ነግሯቸው ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷቸዋል፡፡ 

Standard (Image)

ለሚኒስትር ዴኤታው ግማሽ ሚሊዮን ብር ጉቦ በማቀባበል የተጠረጠሩ ግለሰብ ታሰሩ

$
0
0
  • በከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች ላይ ድጋሚ የምርመራ ጊዜ ተፈቀደ

ለገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ዓለማየሁ ጉጆ 500,000 ብር ጉቦ በማቀባበል የተጠረጠሩት አቶ ኢዮብ በልሁ፣ በቁጥጥር ሥር ውለው ነሐሴ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀረቡ፡፡

የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን ነሐሴ 6 ቀን 2009 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር እንደዋሉ ገልጾ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሁለተኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ተጠርጣሪው፣ የትራንስ ናሽናል ኮምፒዩተር ቴክኖሎጂ ኩባንያ ሠራተኛ መሆናቸውን ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ መርማሪ ቡድኑ እንዳስረዳው ተጠርጣሪው ለሚኒስትር ዴኤታው 500,000 ብር ጉቦ ሰጥተዋል፡፡

ተጠርጣሪው ለፍርድ ቤቱ እንደተናገሩት የተያዙበትን ጉዳይ በዕለቱ ከመስማታቸው ውጪ የሚያውቁት ነገር የለም፡፡ ‹‹እኔ ፕሮፌሽናል ነኝ፡፡ ወደ መሥሪያ ቤቱ የገባሁት ጨረታ ወጥቶና አሸንፎ ከተጠናቀቀ በኋላ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ነሐሴ 6 ቀን 2009 ዓ.ም. በድንገት ተይዘው ስለታሰሩ ቤተሰቦቻቸው የት እንዳሉ እንደማያውቁና ማንም እንዳልጠየቃቸው ለፍርድ ቤቱ ተናግረዋል፡፡ የዋስትና መብታቸው እንዲከበርላቸውም ጠይቀዋል፡፡

ሌላው ለመጀመርያ ጊዜ ፍርድ ቤት የቀረቡት ከቤተሰቦቻቸው ጋር በአሜሪካ አገር ዕረፍት አድርገው እንደተመለሱ በቁጥጥር ሥር የዋሉት፣ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሳምሶን ወንድሙ ናቸው፡፡

መርማሪ ቡድኑ አቶ ሳምሶንን በምን እንደጠረጠራቸው ተጠይቆ እንዳስረዳው፣ ተጠርጣሪው ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊ ሲሆኑ፣ የተሰጣቸውን ኃላፊነት ወደጎን በመተውና ከባለሀብቶች ጋር በመመሳጠር ያልተጠናቀቁና ችግር ያለባቸውን የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክቶች እንደተጠናቀቁና ያላንዳች ችግር ግንባታቸው እንዳለቀ አስመስለው በመገናኛ ብዙኃን አስተላልፈዋል፡፡ አንድ ተቋራጭ የሌለውን የግንባታ ማሽነሪ እንዳለው በማስመሰልና ለመሥሪያ ቤታቸው በመግለጽ ደረጃው ከፍ እንዲልና እንዲያሸንፍ በማድረግ፣ በሕዝብና በመንግሥት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሳቸውን አስረድቷል፡፡

‹‹ከፍተኛ ጉዳት ማለት ምን ማለት ነው? በከፍተኛ ኃላፊነት ላይ ሆነው ሲሠሩ ማለት ምን ማለት ነው?›› በማለት ፍርድ ቤቱ ላነሳው ጥያቄ መርማሪ ቡድኑ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ አቶ ሳምሶን በተቋሙ የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር መሆናቸውን፣ አድርሰዋል የተባለው ከፍተኛ ጉዳትም የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር የነበሩት እነ አቶ ዛይድ ወልደ ገብርኤል በተጠረጠሩበት አምስት የመንገድ ፕሮጀክቶች ላይ ተፈጽሟል በተባለው የ1.3 ቢሊዮን ብር ጉዳት ጋር የተገናኘ መሆኑን አስረድቷል፡፡ በአቶ ሳምሶን ላይ አምስት ምስክሮች እንዳሉትና ቃላቸውን እንዳልተቀበላቸው፣ ሀብታቸውን ማጥናት፣ ቢሮአቸው ሲበረበር የተገኙ ሰነዶችን መተንተን፣ በባንክ ያደረጉትን የገንዘብ ልውውጥ የሚያሳዩ የባንክ የሒሳብ መግለጫ ጠይቆ ማየት እንደሚቀረው በማስረዳት፣ ተጨማሪ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡

አቶ ሳምሶን በጠበቃቸው አማካይነት ባደረጉት ክርክር ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት፣ በቢሮአቸው ብርበራ ተደርጎ ሰነዶች ተወስደዋል፡፡ የተያዙት ሌሎች የተቋሙ ተጠርጣሪዎች በተያዙበት የ1.3 ቢሊዮን ብር ጋር በተገናኘ ነው መባሉንም ተቃውመዋል፡፡ የእሳቸው ተሳትፎ ተገልጾና መጀመርያ መረጃዎችን አጠናክሮ መያዝ ሲገባ፣ አስሮ ማስረጃ መፈለግ ሕገወጥ ድርጊትና ተገቢ ያልሆነ ዕርምጃ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡ የባንክ የሒሳብ መግለጫ የሚገኘው ከመንግሥት ወይም ከግል ተቋማት በመሆኑ ከእሳቸው ጋር የሚያገናኘው ነገር እንደሌለና እሳቸው የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ በመሆናቸው፣ ከሌሎች ተጠርጣሪዎች ጋር የሚያገናኛቸው የሙያም ሆነ የኃላፊነት አንድነት እንደሌለ አስረድተዋል፡፡ ከኃላፊዎቻቸው የሚደርሳቸውን መረጃ በመገናኛ ብዙኃን ማስተላለፍ ከሆነም፣ ሊታሰሩ ስለማይገባ ዋስትና ተፈቅዶላቸው በውጭ ሆነው ጉዳያቸውን እንዲከታተሉ ጠበቃቸው ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል፡፡

የፌዴራል ፖሊስ መርማሪ ቡድን ለሁለተኛ ጊዜ አቅርቦ ተጨማሪ 14 የምርመራ ቀናት የጠየቀባቸው የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ኃላፊ የነበሩት እነ ወ/ሮ ፀዳለ ማሞ ናቸው፡፡

የፕሮጀክት ጽሕፈት ቤቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ወ/ሮ ፀዳለ ማሞ፣ ምክትላቸው አቶ የማነ ፀጋዬ፣ የጽሕፈት ቤቱ ማስተባበሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ሽመልስ ዓለማየሁ፣ የጽሕፈት ቤቱ የመሬት ዝግጅትና መሠረተ ልማት ዲዛይን ረዳት ኃላፊ ወ/ሮ ሳባ መኮንንና የየማነ ግርማይ ጠቅላላ ተቋራጭ ባለቤት አቶ የማነ ግርማይ ፍርድ ቤት ቀርበው ተከራክረዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ የፕሮጀክት ጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ሆነው ሲሠሩ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሳቸውን የሚያስረዱ ሦስት ምስክሮችን ቃል መቀበሉን፣ የአንድ ኦዲተር የሙያ አስተያየት መቀበሉን፣ ከመኖርያ ቤትና ከተለያዩ ቦታዎች የተሰበሰቡ ሰነዶችን ለይቶ መተንተን ላይ መሆኑን፣ የባንክ ማስረጃዎችን እየሰበሰበ መሆኑን፣ አስተዳደሩ ማስረጃ እንዲሰጠው ደብዳቤ መጻፉን፣ የወንጀል ፍሬ ናቸው ያላቸውን ንብረቶች በኤግዚቢትነት መያዙንና 14 ጥራዝ ክፍያ የተፈጸመባቸው ፋይሎች መሰብሰቡን አስረድቷል፡፡ የ12 ምስክሮች ቃል መቀበልና የሁለት ኦዲተሮችን አስተያየት መቀበል እንደሚቀረው፣ ከኤሌክትሮኒክሶች ላይ ያገኘውን መረጃ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት ተቋም መጠየቅ፣ ንብረት ማሳገድና ለፎረንሲክ የተላኩ ሰነዶችን ውጤት መጠባበቅ እንደሚቀረው ገልጾ የጠየቀው ጊዜ እንዲፈቀድለት መርማሪ ቡድኑ ጠይቋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ የመርማሪ ቡድኑን ክርክር በመቃወም እንደተናገሩት፣ ድርጊቱ ተፈጸመ የተባለው በ1999 ዓ.ም. ነው፡፡ ከ2007 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ታኅሳስ ወር መጨረሻ ድረስ ምርመራ ሲደረግበት የከረመ መዝገብ ነው፡፡ መርማሪ ቡድኑ ተጠርጣሪዎችን አስሮ ሌላ ማስረጃ ሊፈልግ አይገባም፡፡ ያለፉት 14 ቀናት ከበቂ በላይ በመሆናቸው የተጠርጣሪዎቹን ቃል ተቀብሎ ማጠናቀቅ ነበረበት፡፡

ወ/ሮ ፀዳለ ተቋሙን ከለቀቁ ስምንት ዓመታት እንዳለፋቸውና በዋስ ቢወጡ እንኳን ምስክሮችን ኃላፊዎችንም ሊያውቁ እንደማይችሉ በጠበቃቸው አማካይነት አስረድተዋል፡፡ ሰነዶች ሁሉ በተቋሙ ስለሆኑ ታስረው የሚቆዩበት ምክንያት እንደሌለና መርማሪ ቡድኑ በ14 ቀናት ውስጥ ሦስት ምስክሮችን ብቻ ተቀብያለሁ ማለቱ በአግባቡ እየሠራ አለመሆኑን እንደሚያሳይም ተናግረዋል፡፡ ከቤተሰብና ከጠበቃ ጋር አለመገናኘት ችግሮች እንደቀጠሉም ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ሁሉም ተጠርጣሪዎች ተመሳሳይ ተቃውሞ በማቅረብ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው አመልክተዋል፡፡

በዋስ ቢወጡ ምስክሮችን እንደሚያባብሉበት፣ ሰነዶችን ሊያስጠፉ እንደሚችሉና ያላከናወናቸው ሥራዎች ብዙ መሆናቸውን መርማሪ ቡድኑ በማስረዳት የተጠየቀውን ዋስትና እንደሚቃወም በመግለጽ፣ የጠየቀው የ14 ቀናት ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር ካዳመጠ በኋላ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በእነ ወ/ሮ ፀዳለ ማሞ ላይ የቀረበውን ምርመራ ሥራ ሲመለከተው ቀሪ ሥራዎች እንዳሉት መገንዘቡን ጠቁሞ፣ ነገር ግን መርማሪ ቡድኑ በአግባቡ ሥራውን እያከናወነ እንዳልሆነ በመረዳቱ መዝገቡን በልዩ ክትትል እንደሚያየው በመግለጽ አሥር ቀናት ተጨማሪ ጊዜ መፍቀዱን ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡ በሕገ መንግሥቱ የተቀመጡ መብቶች እንዲከበሩ በተደጋጋሚ መግለጹን በማስታወስ፣ መርማሪ ቡድኑ በቀጣይ ቀጠሮ የጠያቂዎችን ዝርዝር ቃል በማካተት ሪፖርት እንዲያቀርብም ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም የዋስትና ጥያቄውን ውድቅ በማድረግ ለነሐሴ 18 ቀን 2009 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ አቶ ሳምሶን ወንድሙ የጠየቁት የዋስትና መብት ታልፎ፣ በእነ አቶ ዛይድ ወልደ ገብርኤል መዝገብ ተካተው ነሐሴ 15 ቀን 2009 እንዲቀርቡ፣ አቶ ኢዮብ በልሁም በእነ አቶ ዓለማየሁ ጉጆ መዝገብ ተካተው ነሐሴ 15 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ 

Standard (Image)

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና ፕሬዚዳንት አልሲሲ የዓባይ ተፋሰስ አገሮችን እየጎበኙ ነው

$
0
0

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝና የግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ የዓባይ ተፋሰስ አገሮችን በየፊናቸው እየጎበኙ ነው፡፡

በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም የሚመራው ከፍተኛ የኢትዮጵያ መንግሥት ልዑክ፣ ከማክሰኞ ነሐሴ 9 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በሱዳን ካርቱም ይፋዊ የሥራ ጉብኝት ማድረግ ጀምሯል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በሱዳን በሚያደርጉት የሥራ ጉብኝት፣ ከፕሬዚዳንት ኦማር ሐሰን አልበሽር ጋር ተገናኝተው በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ ሰፋ ያለ ምክክር እንደሚያደርጉ፣ የልዑኩ አካል የሆኑት የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትሩ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) ወደ ሱዳን ከመጓዛቸው በፊት ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም በበኩላቸው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት በሱዳን ፕሬዚዳንት አልበሽር ግብዣ የሚካሄድ መሆኑን፣ በአካባቢ ጉዳዮችና በተለያዩ የሁለቱ አገሮች የተለያዩ ግንኙነቶች ላይ እንደሚመክሩ ገልጸዋል፡፡ በዚህ ወቅት የግድቡ ወይም የዓባይ ጉዳይ ሊነሳ ቢችልም፣ በግድቡ ጉዳይ ላይ በተለየ ሁኔታ አጀንዳ የሚፈጥር ሁኔታ አለመፈጠሩን ገልጸዋል፡፡ በተመሳሳይ የኢትዮጵያና የሱዳን ድንበር ጉዳይ ሊነሳ ቢችልም፣ የተለየ አጀንዳ ለማድረግ የተፈጠረ አዲስ ነገር እንደሌለ አመልክተዋል፡፡

ይሁንና የናይል ጉዳይ በራሱ የውይይት አጀንዳ እንደማይሆን ቃል አቀባዩ ገልጸዋል፡፡ የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስትሩ ስለሺ በቀለ (ዶ/ር) የልዑካን ቡድኑ አባል መሆናቸውም ታውቋል፡፡

ሁለቱ አገሮች በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ ተመሳሳይ አቋም ማራመድ ከጀመሩ ዓመታት የተቆጠሩ ሲሆን፣ ይህንኑ የፖለቲካ አቋማቸውን ለማጠናከርና ተመሳሳይ አቋም ለማራመድ የሚያስችል ውይይት ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በተለይ ግብፅ የዓባይ ተፋሰስ አገሮች ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ሰነድ በድጋሚ እንዲከለስ ጠይቃ የሌሎች የተፋሰሱ አገሮችን ይሁንታ ለማግኘት እየሠራች በመሆኑ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ጉብኝት ይህንን የግብፅ ጥረት ማክሸፍ ዋነኛ ዓላማው ለመሆኑ የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከህዳሴው ግድብ ውጪ ባሉ የሁለትዮሽ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይም እንደሚመክሩ፣ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትሩ አስረድተዋል፡፡ በተመሳሳይ የግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ከሰኞ ነሐሴ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በሩዋንዳና በታንዛኒያ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት በማድረግ ላይ ናቸው፡፡

የዓባይ ተፋሰስ አገሮች ትብብር ማዕቀፉን በመጀመርያ ያፀደቀችው ኢትዮጵያ ስትሆን፣ በመቀጠልም ሩዋንዳና ታንዛኒያ በሕግ መወሰኛ ምክር ቤቶቻቸው ማፅደቃቸው ይታወሳል፡፡

ከወራት በፊት በኡጋንዳ በተካሄደ የተፋሰሱ አገሮች መሪዎች ውይይት ላይ ግብፅ የትብብር ማዕቀፉ በድጋሚ ለድርድር እንዲቀርብ ያደረገችውን ጥያቄ ኢትዮጵያ ውድቅ ያደረገችው፣ የትብብር ማዕቀፉ በሕግ መወሰኛ ምክር ቤቶች ፀድቆ ሕግ ሆኗል በማለት ነበር፡፡

የግብፅ ፕሬዚዳንት በታንዛኒያና በሩዋንዳ ሰሞኑን ያደረጉት ጉብኝት የሁለቱን አገሮች ይሁንታ ለማግኘት እንደሆነ ባለሙያዎች ይገልጻሉ፡፡ 

Standard (Image)

የአሥራ ሁለት አምባሳደሮች ምደባ ይፋ ሆነ

$
0
0

ፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ ሐምሌ 19 ቀን 2009 ዓ.ም. የሰጡት የአሥራ ሁለት አምባሳደሮች ሹመት ምደባ ይፋ ሆነ:: የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃለ አቀባይ ጽሕፈት ቤት በፌስቡክ ገጹ ይፋ እንዳደረገው፣ አምባሳደር ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ አቶ ሥዩም መስፍንን ተክተው የቻይና ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ሆነው ተመድበዋል:: አቶ ካሳ ተክለ ብርሃንም አቶ ግርማ ብሩን ተክተው የአሜሪካ ባለሙሉ ባለሥልጣን አምባሳደር ሆነዋል::

በተመሳሳይ የቀድሞ የሲቪል ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ሚኒስትር ወ/ሮ አስቴር ማሞ የካናዳ፣ የቀድሞው የትምህርት ሚኒስትር ሽፈራው ተክለ ማርያም (ዶ/ር) የደቡብ አፍሪካ፣ እንዲሁም የቀድሞ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ የስዊዲን ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ሆነው ተመድበዋል::

ከዚህ በተጨማሪ አምባሳደር ተበጀ በርሄ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ፣ አቶ መታሰቢያ ታደሰ የኳታር፣ የቀድሞው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር አድማሱ ፀጋዬ የኢንዶኔዥያ፣ ወ/ሮ ሉሊት ዘውዴ የሩዋንዳ፣ የሥነ ምግባር ፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ዓሊ ሱሌይማን የፈረንሣይ፣ እንዲሁም አቶ ሙሉጌታ ዘውዴ የሱዳን ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ሆነው ተመድበዋል::

የጠቅላይ ሚኒስትሩ ልዩ ረዳት የነበሩት አቶ እውነቱ ብላታ በብራሰልስ የአውሮፓ ኅብረት አምባሳደር መሆናቸው ታውቋል::

 

Standard (Image)

በኢሕአዴግና በተቃዋሚ ፓርቲዎች የመጀመርያው ዙር ድርድር ተጠቃሚው ማነው?

$
0
0

 

‹‹በዚህ ሁኔታ ውስጥ እንዴት ፖለቲካ መሥራት ይቻላል? ሕዝቡንና አገሪቷንስ እንዴት ወደ ሰላም ማምጣት ይቻላል?›› ሲሉ ጥያቄ አዘል አስተያየታቸውን ሰሞኑን ለሪፖርተር የሰጡት የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት አቶ የሺዋስ አሰፋ ናቸው፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ (ሰማያዊ) ከመላው የኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ጋር ነሐሴ 7 ቀን 2009 ዓ.ም. በወቅታዊ የአገሪቱ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ሕዝባዊ ውይይት ለማድረግ ለአዲስ አበባ አስተዳደር በጋራ ያቀረቡት የዕውቅና ጥያቄ ተቀባይነት አለማግኘቱን ተከትሎ፣ የውይይት ፕሮግራሙን ለመሰረዝ በመገደዳቸው የፈጠረባቸውን ስሜት የገለጹበት መንገድ ነው፡፡

‹‹ገዥው ፓርቲ ፍርኃት ውስጥ ነው፡፡ ፍርኃት ውስጥ ሆኖ ደግሞ ምንም አማራጭ ለሕዝብ እንዳናቀርብ እያደረገን ነው፡፡ ያ ደግሞ አገሪቱን የባሰ ችግር ውስጥ የሚጥል በመሆኑ መንግሥት ለሕዝቡ ማሰብ አለበት፡፡ የፓርቲዎችን ሥራ አለማክበርና ሥራቸውን እንዳይሠሩ እንቅፋት መፍጠር የለበትም፤›› ሲሉ አቶ የሺዋስ ይከራከራሉ፡፡

በፖለቲካ ጉዳዮች ላይ ሕዝባዊ ውይይት ለማድረግ፣ እንዲሁም ሰላማዊ ሠልፍ ለማካሄድ ሕጋዊ ዕውቅና የማግኘት ችግር ለተቃዋሚ ፓርቲዎች አዲስ ፈተና አይደለም፡፡ በተለይ ከ1997 ዓ.ም. ምርጫ በኋላ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በተለያዩ መሰናክሎች ሲጨናገፍ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ ከ1997 ዓ.ም. ጀምሮ ላለፉት 12 ዓመታት ከቀረቡ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሰላማዊ ሠልፍ ፈቃድ ጥያቄዎች ይሁንታ ያገኙት አምስት አይሞሉም፡፡

ሰማያዊና መኢአድ ነሐሴ 7 ቀን 2009 ዓ.ም. ለማካሄድ አቅደውት ለነበረው ሕዝባዊ የፖለቲካ ውይይት በተነፈጉት ዕውቅና ዕቅዳቸው መሰናከሉን ልዩ የሚያደርገው፣ በጥቅሉ 16 ተቃዋሚ ፓርቲዎች የአገሪቱን የፖለቲካ ምህዳር ምቹ ለማድረግ ከገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ ጋር ድርድር በጀመሩ ማግሥት መሆኑ ነው፡፡ ሪፖርተር ባደረገው ማጣራት የአዲስ አበባ አስተዳደር ሰማያዊና መኢአድ ሕዝባዊ የፖለቲካ ውይይት ለማድረግ ያቀረቡትን የይሁንታ ጥያቄ መቀበል ያልቻለው ‹‹ኃላፊነት የሚወስድ አካል›› ከፓርቲዎቹ መቅረብ ባለመቻሉ ነው፡፡

ፓርቲዎቹ ጥያቄያቸውን በደብዳቤ ቢያቀርቡም ማሟላት የሚገባቸውን ቅድመ ሁኔታ ሳያሟሉ ደብዳቤያቸውን ጥለው በመሄዳቸው፣ ኃላፊነትን የሚወስድ አካል በሌለበት ፈቃድ ለመስጠት መቸገሩን አስተዳደሩ ይገልጻል፡፡

ጥያቄውን ያቀረቡት የፖለቲካ ፓርቲዎች በአገሪቱ ሕግ መሠረት በፖለቲካ ፓርቲነት የተመዘገቡና ሕጋዊ ፈቃድ ያላቸው እስከሆኑ ድረስ፣ ዋነኛ ተልዕኳቸው የሆነውን የፖለቲካ እንቅስቃሴ ለማከናወን ‹‹ኃላፊነትን የሚወስድ አካል ባለመኖሩ›› በሚል አስተዳደሩ ፈቃድ መከልከሉ ሕገ መንግሥታዊ መብትን መፃረር ከመሆኑም ባለፈ፣ በሚያዘጋጁት መድረክ ለሚፈጸም ሕግን መተላለፍ ተጠያቂነት እንዳለባቸው በፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ በግልጽ የተቀመጠ መሆኑን በመጥቀስ አስተዳደሩ የሰጠውን ምክንያት የሕግ ባለሙያዎች ተችተዋል፡፡

የፖለቲካ ስብሰባና ሰላማዊ ሠልፍ ማድረግ ገደብ የሌለበት ሕገ መንግሥታዊ መብት መሆኑን የሚጠቅሱት ባለሙያዎች፣ በዚህ ተግባር መሳተፍ የሚፈልጉ ዜጎችም ሆነ የፖለቲካ ፓርቲዎች ፕሮግራሙ ለሚካሄድበት የአስተዳደር አካል እንዲያሳውቁ በሕግ የተቀመጠው ቅድመ ሁኔታ ለፕሮግራሙ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር፣ እንዲሁም በሰላማዊ መንገድ ተካሂዶ እንዲጠናቀቅ የአካባቢው አስተዳደር ዝግጅት እንዲያደርግና ምቹ ሁኔታዎች በሌሉበት ነባራዊ ሁኔታ ደግሞ አማራጮችን እንዲያስቀምጥ ስለመሆኑ ይገልጻሉ፡፡

በሥራ ላይ ያለው የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ ‹‹ሕጋዊ ሰውነት ያገኘ የፖለቲካ ፓርቲ … ዓላማውን ተከትሎ ማናቸውም ሕጋዊ ተግባር ማከናወን ይችላል፡፡ እንዲሁም ግዴታውን የመወጣት ኃላፊነት አለበት፤›› በማለት በአንቀጽ 7(2) ላይ የሚደነግግ በመሆኑ፣ ለጠየቁት ሰላማዊ ሠልፍም ሆነ ሕዝባዊ ውይይት ሕጋዊ ኃላፊነት የወሰዱት የፓርቲ ፈቃድ ሲወስዱ እንደሆነ በመግለጽ የአስተዳደሩ ምክንያት ዕርባና ቢስ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡

ከዚህ ባለፈም ይኸው የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ ‹‹ማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ በኃይል ወይም በማስፈራራት የፖለቲካ ዓላማውን ለማስረፅ ማንኛውንም ሰው ወይም ቡድን ማደራጀት ወይም ማሠልጠን ወይም ሰዎችን በግድ መመልመል በሕግ ያስቀጣል፤›› በማለት እንደሚደነግግ ያስረዳሉ፡፡

በመሆኑም ተጠያቂነት የፖለቲካ ፓርቲ ዕውቅና ያገኘ ፓርቲ ላይ ከጅምሩ የተጣለ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች የተቋቋሙበትን ዓላማ ለመፈጸምም አለመቻላቸውን ለዓመታት ሲገልጹ ቆይተው፣ ይህንኑ ተግባራቸውን ያለ ተፅዕኖ መፈጸም አሁንም አቀበት እንደሆነባቸው ይናገራሉ፡፡

ይህ በአገሪቱ የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ የተጋረጠ መሠረታዊ ፈተና ነው፡፡ በአገሪቱ የፖለቲካ አለመረጋጋት በተለይም ከ2008 ዓ.ም. ወዲህ ያለው ተቃውሞን መፍታት እንዳለበት የተገነዘበው ገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ ጎርባጣ የፖለቲካ ሜዳውን ለመደልደል፣ እንዲሁም የተመጣጣኝ ውክልና የምርጫ ሥርዓትን በኢትዮጵያ ለመተግበር ቃል በመግባት ሕጋዊ ዕውቅና ካላቸው አገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ወደ ፖለቲካዊ ድርድር ገብቷል፡፡

በዚህ የፖለቲካ ድርድር 16 ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአንድ ወገን ሆነው ከገዥው ፓርቲ ጋር በጀመሩት ድርድር 12 የድርድር አጀንዳዎችን ቀርፀዋል፡፡ ከተቀረፁት አጀንዳዎች ውስጥ ቀዳሚ የውድድር አጀንዳ እንዲሆን ከሙግት በኋላ ስምምነት አግኝቶ የተመረጠው የፖለቲካ ፓርቲዎች የምዝገባ አዋጅ ነው፡፡ በዚህ አዋጅ ላይ ፓርቲዎቹ ድርድር አድርገው ሊሻሻሉ የሚገባቸው ባሏቸው አንቀጾች ላይ የተስማሙባቸውንና ሊካተቱ ይገባል ባሏቸው አንቀጾች ላይ ተከራክረው ከስምምነት የደረሱባቸውን በመለየት፣ ወደ ቀጣይ የድርድር አጀንዳ ለመግባት ቀጣይ ቀጠሮ ይዘዋል፡፡

የፖለቲካ ፓርቲዎች የምዝገባ አዋጅ ማሻሻያዎች

ለድርድር የተቀመጡት የፖለቲካ ፓርቲዎች ከመረጧቸው 12 የድርድር አጀንዳዎች ውስጥ ቅድሚያ የድርድር አጀንዳ እንዲሆን የተመረጠው የፖለቲካ ፓርቲዎች የምዝገባ አዋጅ ነው፡፡

በዚህ አዋጅ ላይ የተደረገውም ሆነ ወደፊት የሚደረጉት ድርድሮች ለሚዲያዎች ዝግ በመሆናቸው የድርድሩን መንፈስ ማወቅ አዳጋች ነወ፡፡ ይሁን እንጂ የድርድሩ ውጤትን አስመልክቶ በወጣው መግለጫ መሠረት፣ ፓርቲዎቹ የፖለቲካ ፓርቲ ምሥረታን አስመልክቶ የተቀመጡ አንቀጾች እንዲሻሻሉ ወስነዋል፡፡

በሥራ ላይ የሚገኘው የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ አንድ አገር አቀፍ ፓርቲን ለመመሥረት 1,500 መሥራች አባላት ሊኖሩት እንደሚገባ የሚደነግገው አንቀጽ እንዲሻሻልና 3,000 መሥራች አባላት ሲኖሩት በሚል እንዲሻሻል ወስነዋል፡፡

በሥራ ላይ ያለው አዋጅ መሥራች አባላት ስምምነታቸውን በፊርማቸው የገለጹ መሆን አለባቸው የሚለውን ‹‹ስምምነታቸውን የሚገልጽ የተረጋገጠ ፊርማና የተረጋገጠ ነዋሪነት ማረጋገጫ ማቅረብ አለባቸው፤›› በሚል እንዲሻሻል ወስነዋል፡፡

በሌላ በኩል ቢያንስ በአራት ክልሎችና በሁለቱ የፌዴራል ከተሞች (አዲስ አበባና ድሬዳዋ) ጽሕፈት ቤት ያለው መሆኑ ሲረጋገጥ የአገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲ ምዝገባ ፈቃድ ሊያገኝ እንደሚችል ተደርጎ እንዲሻሻል ወስነዋል፡፡ በተጨማሪም የክልል የፖለቲካ ፓርቲ ምሥረታን አስመልክቶ በተስማሙት መሠረት፣ 750 የነበረውን የመሥራች አባላት መጠን ወደ 1,500 ከፍ እንዲል ወስነዋል፡፡

በሌላ በኩል በክልል መንቀሳቀስ የሚፈልግ ፓርቲ ክልላዊ የፖለቲካ ፕሮግራም እንዲኖረው እንደ መሥፈርት የተቀመጠ ሲሆን፣ በሚቋቋምበት ክልል ውስጥ ቢያንስ 25 በመቶ በሚሆኑ ቦታዎች ፓርቲው ጽሕፈት ቤቶች ያሉት መሆኑ ሲረጋገጥ የሚል አንቀጽ እንዲጨመርም ወስነዋል፡፡

ፓርቲዎቹ ባደረጉት ድርድር የደረሱበትን ስምምነት የፖለቲካ ተንታኞችም ሆነ ከድርድሩ ራሳቸውን ያገለሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ይተቻሉ፡፡ የፖለቲካ ትኩሳት በተቆጠረ ቁጥር ገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ የሚከፍተው መዝገብ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅን እንደሆነ የሚገልጹት፣ ስማቸውን እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የፖለቲካ ተንታኝ ናቸው፡፡

‹‹ከ1997 ዓ.ም. በፊት ኢሕአዴግ ካድሬ ተኮር ፓርቲ ነበር፤›› የሚሉት እኚሁ ተንታኝ፣ በምርጫው ተቃዋሚ ፓርቲዎች ካደረሱበት ጡጫ ካገገመ በኋላ ትኩረቱን ያደረገው የአባላቱን ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ በማስፋት የፖለቲካ ምኅዳሩን በካድሬዎች ማጨናነቅ፣ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትን በመተናኮል ፍርኃት ውስጥ እንዲወድቁ ማድረግ ነበር ሲሉ ይተቻሉ፡፡

ከ1997 ዓ.ም. በፊት ሁለት ሚሊዮን የማይሞሉት የገዥው ፓርቲ አባላት ከ1997 በኋላ በተደረገ ከፍተኛ ዘመቻ 6.16 ሚሊዮን መድረሳቸውን በመጥቀስ የዘመቻውን መጠን ይገልጻሉ፡፡

ከዚህ በተጨማሪም የወጣት ወንዶችና የወጣት ሴቶች ሊግ በመመሥረት በሁለቱም ምድቦች እንደየቅደም ተከተላቸው 1.25 ሚሊዮንና 1.6 ሚሊዮን አባላትን መልምሎ እያሳተፈ ስለመሆኑ ይናገራሉ፡፡ የመንግሥት መካከለኛና ዝቅተኛ አመራሮችም ለምሳሌ ያህል በ2005 ዓ.ም. 28,823 መካከለኛ አመራሮች በፓርቲው የፖሊሲ ጉዳዮች ሥልጠና እንዲወስዱ መደረጉን ያወሳሉ፡፡

በአጠቃላይ በገዥው ፓርቲ ዓይን የሚመለከቱ ዓይኖች ፖለቲካውን እንዲያማትሩ በማድረግ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ብቻ ሳይሆን ማኅበረሰቡን ትንፋሽ አሳጥተዋል ሲሉ ይከራከራሉ፡፡ በማሳያነትም ሆቴሎች ለተቃዋሚ ፓርቲዎች አዳራሽ ማከራየት መፍራታቸውን፣ የመንግሥት ማተሚያ ቤቶች ሳይቀሩ የተቃዋሚ ፓርቲዎች የኅትመት ውጤቶችን አላትምም እንዳሉ ይጠቅሳሉ፡፡

በዚህ ሁኔታ ውስጥ ያለው የአገሪቱ የፖለቲካ ሥርዓትን በማሻሻል ምቹ የመጫወቻ ሜዳ ለመደልደል ለድርድር የተሰየሙት ፓርቲዎች፣ ከገዥው ፓርቲ ጋር በመሆን ሳያውቁት ይሁን ወይም ሆን ብለው የፖለቲካ ምኅዳሩን ለራሳቸውም ጭምር መልሰው እየዘጉ ነው ሲሉ ይከራከራሉ፡፡

‹‹እንኳን የመሥራች አባላት ቁጥር ይቅርና የትኛው ተቃዋሚ ፓርቲ ነው ሦስት ሺሕ ደጋፊዎች ያሉት?›› ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ሊቀመንበር አቶ ሙሉጌታ አበበ በበኩላቸው፣ በዚህ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ ላይ የተደረገው ድርድር ዓላማም በአገሪቱ የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ የሚጫወቱ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ቁጥር መቀነስ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

‹‹60 ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአገሪቱ እንዲንቀሳቀሱ ማድረግ ብቻውን የዴሞክራሲ መገለጫ ነው?›› ሲሉ የሚጠይቁት አቶ ሙሉጌታ፣ ‹‹በኢትዮጵያ ፓርቲ የማቋቋም ችግር የለም፡፡ ችግሩ የፖለቲካ ተግባራችንን እንዳንፈጽም የሚገድቡ ተፅዕኖዎች መፈጠራቸው ነው፤›› ሲሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በዓለም አቀፍ ደረጃ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላት ቁጥር እየቀነሰ መምጣቱን የሚያነሱት የፖለቲካ ተንታኙ የሚዲያ ተቋማት መጠናከር፣ የማኅበራዊ ሚዲያው ጎልቶ መውጣትና የፖለቲካ ልሂቃን ወደ ፖለቲካው መሳብ በዓለም የፖለቲካ ሥርዓት ላይ አዲስ ተፅዕኖ እንደፈጠረ ያስረዳሉ፡፡

ይኸውም የፓርቲ አባላት ብዛት ትኩረት የማይሰጥ፣ በርዕዮት ዓለምና በፖለቲካ ፕሮግራም ላይ የሚያነጣጥሩ የፖለቲካ ልሂቃን ፓርቲዎች የመፈጠር አዝማሚያዎች እየታዩ መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡

በኢትዮጵያ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ቁጥር የመቀነስ አዝማሚያ ያሳየው ከዚህ አንፃር ነው ባይባልም፣ የፖለቲካ ፓርቲ አባልነት በከፍተኛ ደረጃ ወድቋል ብለዋል፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ቁጥርን የፖለቲካ ፓርቲ ለመመሥረት እንደ መሥፈርት ማስቀመጥ፣ ገዥው ፓርቲ ለመገንባት ለሚፈልገው የአንድ ፓርቲ ሥርዓት የቴክኒክ ትብብር ማድረግ ነው ሲሉ ይከራከራሉ፡፡

የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት አቶ የሺዋስ አሰፋም ይህንኑ ሐሳብ ይጋራሉ፡፡ ‹‹በአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትርም ሆነ በአገሪቱ ፕሬዚዳንት ቃል የተገባው ምቹ የፖለቲካ ምኅዳር ለመፍጠር ሆኖ ሳለ፣ የፖለቲካ ድርድሩ የመጀመርያ ውጤት ግን መፈናፈኛ የሚያሳጣ ሥርዓት ለመፍጠር የዳዳ መሆኑን አሳይቷል፤›› ብለዋል፡፡

ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ በውስጥ ጉዳያቸው በረባ ባልረባ ምክንያት ጣልቃ እየገባ እንቅስቃሴያቸውን እንደሚያውክ ቅሬታ ሲያቀርቡ መስማት አዲስ ነገር አይደለም፡፡

በድርድሩ የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ለምርጫ ቦርድ ተጨማሪ ሥልጣን እንዲሰጥ ነው የወሰኑት፡፡ ይህም ስለጠቅላላ ጉባዔ፣ ስለአባላት ቁጥር፣ ስለተወሰዱ ውሳኔዎች፣ መደበኛ ስብሰባ ስለሚካሄድበት ቁርጥ ጊዜ፣ ስለስብሰባ ዝግጅትና ስለመሳሰሉት ጉዳዮች ለቦርዱ ማሳወቅን ይጨምራል፡፡ የፓርቲዎቹ ፕሮግራም የአባላቱን ተሳትፎና የፓርቲውን ውስጠ ዴሞክራሲ የሚያሻሽል ስለመሆኑ መወሰንም የቦርዱ አዲስ ሥልጣን ሆኗል፡፡

በርካታ የፖለቲካ ተንታኞች ድርድሩ ይህን መሰል ሥልጣን ነፃና ገለልተኛ ስለመሆኑ ጥያቄ ለሚቀርብበት ቦርድ መስጠቱ በድርድሩ ዋናው ተጠቃሚ ኢሕአዴግ እንደሆነ አስረግጦ ያሳያል ሲሉ ክርክር ያቀርባሉ፡፡ በዚህ ሥልጣንም የቦርዱ ጣልቃ ገብነት ከመቼውም በላይ እንዳይሰፋ ሥጋት ገብቷቸዋል፡፡

በአጠቃላይ ድርድሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በነፃነት የሚሠሩበትንና የሚንቀሳቀሱበትን ምኅዳር እንደሚያሰፋ በሰፊው የተወራለት ቢሆንም፣ ውጤቱ ግን በተቃራኒው የማጥበብ አዝማሚያ አሳይቷል፡፡

በድርድሩ እየተሳተፉ ባሉ ፓርቲዎች አቅም ላይ የቆየ ጥርጣሬና ጥያቄ ያለ ቢሆንም፣ የድርድሩ ውጤት ግን ለራሳቸውና ለመድበለ ፓርቲ ሥርዓት መዳበር የቆሙ ስለመሆኑ ተጨማሪ ጥያቄ እየፈጠረ ነው፡፡

ኢሕአዴግም ቢሆን የመድበለ ፓርቲ ሥርዓቱን የማሰፋው ለፓርቲዎቹ የግል ጥቅም ሳይሆን ለሕዝቡ ነው በማለት ምላሽ ቢያንስ ላለፉት ሁለት ዓመታት ሲሰጥ ከመቆየቱ አንፃር፣ ድርድሩን የራሱን ሥልጣን ለማጠናከር መጠቀሙ ትዝብት ላይ እንደጣለው ይነገራል፡፡ (ለዚህ ዘገባ ነአምን አሸናፊ አስተዋጽኦ አድርጓል)  

Standard (Image)

የመንግሥት ባለ በጀት መሥሪያ ቤቶች ወጪ እንዲቀንሱ ጥብቅ መመርያ ወጣ

$
0
0

 

በዳዊት እንደሻው

የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር የፌዴራል ባለ በጀት መሥሪያ ቤቶች በቅርቡ ያሠራጨውን የበጀት ወጪ ቅነሳ ማቅረቢያ ቅጽ ሞልተው፣ እስከ ነሐሴ 30 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ እንዲያቀርቡ አዘዘ፡፡ በመመርያው መሠረት በርካታ አላስፈላጊ ወጪዎችን እንዲቀንሱ ጠበቅ ያሉ ክልከላዎች ተደርገዋል፡፡

በ2010 በጀት ዓመት ተግባራዊ እንዲደረግ ሚኒስቴሩ በቅርቡ ካዘጋጀው የወጪ ቅነሳ መመርያ ጋር አብሮ የወጣው ቅጽ፣ አስፈጻሚ መሥሪያ ቤቶች በጀታቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ ያዛል፡፡ ሚኒስቴሩ ባለበጀት መሥሪያ ቤቶች በ2010 ዓ.ም. ወጪያቸውን በመቀነስ በጀታቸውን ቁጠባን መሠረት ባደረገ አሠራር እንዲጠቀሙበት አሳስቧል፡፡

ዓመታዊ ፕሮግራም፣ ግብና ውጤትን መሠረት ያላደረገ የበጀት ዝውውርና የተጨማሪ በጀት ጥያቄ መሥሪያ ቤቶች እንዳያቀርቡ መመርያው ከልክሏል፡፡

መመርያው መደበኛ ወጪን በተመለከተ 19 ያህል ግዥዎችና የተለያዩ ወጪዎች ላይ ጥብቅ የሆነ አሠራርና አንዳንዶቹም ላይ ክልከላን አስቀምጧል፡፡

መሥሪያ ቤቶች በየዓመቱ እንደ ቀን መቁጠሪያ ካላንደር፣ አጀንዳዎች፣ የመጽሔት ኅትመትና የደስታ መግለጫ ካርድ ግዢዎችን ከልክሏል፡፡ በተጨማሪም የወረቀት፣ የቶነር፣ የማስታወሻ ደብተርና የእስክሪብቶ ግዢን መቀነስ እንዳለባቸው፣ ነገር ግን የኢንፎርሜሽንና ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ (ICT) እንዲጠቀሙ ያዛል፡፡

ለሠራተኞች በየመሥሪያ ቤቱ የሚከፋፈሉ የፅዳት አላቂ ዕቃዎችን ግዢ በተመለከተ፣ መሥሪያ ቤቶቹ የግዢውን መጠን እንዲቀንሱ ማሳሰቢያ ተሰጥቷቸዋል፡፡

በተለምዶ በየመሥሪያ ቤቱ የሚደረጉ የመስተንግዶ ወጪዎችን በተመለከተ ከአሁን በኋላ ለሚደረጉ ስብሰባዎች፣ ዓውደ ጥናቶችና ሴሚናሮች እንደ ሻይ፣ ቡናና ውኃ ከመሳሰሉት በስተቀር ተጨማሪ ግብዣዎች እንዳይደረጉ ይከለክላል፡፡ የሚደረጉት ስብሰባዎችም በተቻለ መጠን በየተቋማቱ አዳራሾች እንዲደረጉና ለሆቴል የሚወጡ ወጪዎች እንዳይኖሩ ያስገነዝባል፡፡

በተጨማሪም ለስብሰባዎችና ለክብረ በዓላት ቦርሳዎችን፣ ቲሸርቶችን፣ ኮፍያዎችን፣ ስካርፎችንና የተለያዩ የአገር ባህል አልባሳትን መግዛትም በጥብቅ ተከልክሏል፡፡

የውጭ አገር ጉዞን በተመለከተም መመርያ ወጥቷል፡፡ የሚኒስቴሮችና በሥራቸው ያሉ ተጠሪ መሥሪያ ቤቶች ኃላፊዎች ጭምር የውጭ አገር ጉዞ ፕሮግራም ሲኖራቸው የፕሮግራሙ ዓላማ፣ የተሳታፊዎች ብዛት፣ የቆይታቸው ጊዜና ወጪን የሚያሳይ የውጭ ጉዞ መርሐ ግብር በማዘጋጀት ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ቀርቦ መፈቀድ እንዳለበት መመርያው ያሳስባል፡፡

የሠራተኞች የትርፍ ሰዓት ክፍያን በተመለከተም በፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ሚኒስቴር ሲፈቀድ ብቻ መከፈል እንዳለበት ይደነግጋል፡፡

ሌላው ድጋፍና ስጦታን በተመለከተም በመመርያው እንደተገለጸው፣ ባለበጀት መሥሪያ ቤቶች በዩኒቨርሲቲዎች ከሚማሩ የክረምት ተማሪዎችና አካል ጉዳተኞች በስተቀር ለማንኛውም ድርጅት ሆነ ግለሰብ የገንዘብ ድጋፍ ወይም ስጦታ መስጠት አይችሉም፡፡

በተጨማሪም ከተለያዩ አካላት የሚቀርቡ የስፖንሰርሺፕ ጥያቄዎችም በመንግሥት ባለበጀት መሥሪያ ቤቶች እንዳይስተናገዱ በመመርያው ታዟል፡፡

ከካፒታል ወጪ ጋር በተያያዘም በበጀት አዋጁ ከፀደቀው ፕሮጀክት ውጪ ፕሮጀክቶችን ማካሄድ እንደማይቻል፣ የተቀፈዱ ፕሮጀክቶችም በታቀደው ጊዜ፣ ወጪና ጥራት እንዲከናወኑ የፕሮጀክት ማኔጅመንት ሥርዓት ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ተጠቁሟል፡፡ 

Standard (Image)

በባህር ዳር ከተማ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጁን ጥሰዋል የተባሉ 17 ሰዎች ታሰሩ

$
0
0

             

በባህር ዳር ከተማ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጁን በመጣስ ለሽብር ሲንቀሳቀሱ ነበር የተባሉ 17 ግለሰቦች መታሰራቸውን፣ የከተማው ፖሊስ መምርያ አስታወቀ፡፡

የመምርያው ኃላፊ ኮማንደር ዋለልኝ ዳኘው ዓርብ ነሐሴ 12 ቀን 2009 ዓ.ም.  ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በከተማዋ ውስጥ ቦምብ በማፈንዳት ሽብር ለመፍጠር ተንቀሳቅሰዋል የተባሉ 17 ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ  በእጃቸውም የእጅ ቦምቦችና ሽብር ለመፈጸም የሚያግዙ ዕቅዶች ይዘው እንደተገኙ ገልጸዋል፡፡ ለዚህ ድርጊት ማስፈጸሚያ የሚሆንም 22 ሺሕ ብር በእጃቸው ላይ መገኘቱን ኮማንደሩ ጠቁመዋል፡፡

በአምስት ቀናት ልዩነት ውስጥ የፈነዱ ቦምቦችን ጨምሮ ሌሎች ቁጥራቸው የበዛ የሽብር ድርጊቶችን ሊፈጽሙ የነበሩ ግለሰቦች፣ በከተማዋ የፀጥታ ኃይል አማካይነት መያዛቸውን ኃላፊው አክለዋል፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ባህር ዳር ላይ ያነጣጠረ የሽብር ድርጊት መኖሩን የገለጹት ኮማንደሩ፣ ይህ ጉዳይ የከተማዋ ፖሊስ መምርያን ብቻ ሳይሆን የክልሉን መንግሥትና ሕዝብም እንደሚያሳስብ ተናግረዋል፡፡

የባህር ዳር ፖሊስ መምርያ በዚህ ላይ ባደረገው ግምገማ ከተማዋ ለዚህ መሰል ድርጊት በተደጋጋሚ ጊዜ ተጋላጭ ልትሆን የቻለበት አንዱ ምክንያት ለቱሪስት ምቹ በመሆኗ ምክንያት እንደሆነ ጠቅሰው፣ ሕገወጥ መንገድ የሚከተሉ የመንግሥት ተቃዋሚዎች በዚህ አካባቢ ይህን መሰል ድርጊት ቢፈጸም ትልቅ ኪሳራ ሊያደርስ እንደሚችል የተሳሳተ ሥሌት ውስጥ እንደገቡ ተናግረዋል፡፡

በእነዚህ የሽብር ድርጊቶች ውስጥ ተሳታፊ ከሆኑ ግለሰቦች መካከል የቀድሞው  ሠራዊት አባላት አሉበት ብለዋል፡፡ በዚህ የሽብር ድርጊት ተሳታፊ የሆኑ ግለሰቦች በዋናነት፣ ቦምብ እንዴት እንደሚፈነዳና እንዴት እንደሚጣል ልምድ ያላቸው ግለሰቦች መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡

በሽብር ድርጊቶች ምክንያት በከተማዋ ውስጥ እስካሁን ድረስ መደናገሮች እንዳሉ ጠቁመው፣ ይህንን ችግር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመቅረፍ የከተማዋ ፖሊስ ሌት ከቀን እየሠራ ነው ብለዋል፡፡

በሌላ በኩል በባህር ዳር ከተማ ባለፈው ዓመት ተካሂዶ በነበረው አመፅና ተቃውሞ ላይ ሕይወታቸው ያለፉ ግለሰቦችን ለማሰብ ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም. መደብሮቻቸውን የዘጉና የትራንስፖርት አገልግሎቶችን ያቋረጡ ዜጎች መታሰራቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ መደብሮችንና የትራንስፖርት አገልግሎቶችን በመዝጋትና በማቋረጥ ተቃውሞ እጃቸው እንዳለበት ተጠርጥረው ከተያዙት መካከል ከ160 በላይ የሚሆኑት መለቀቃቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ኮማንደር ዋለልኝ በአሁኑ ወቅት 36 ሰዎች በእስር ላይ እንደሚገኙና ጉዳያቸውም በፍርድ ቤት እየታየ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

ምንጮች እንደሚሉት ግን በባህር ዳር ከተማ በቁጥጥር ሥር ውለው ከነበሩት ውስጥ የሆቴል ባለቤቶች፣ በተለያዩ የንግድ ሥራዎች የተሰማሩ ግለሰቦች አሁንም ከታሳሪዎች ውሰጥ ይገኙበታል፡፡

Standard (Image)

ለ8.5 ሚሊዮን የድርቅ ተጎጂዎች ከ480 ሚሊዮን ዶላር በላይ ያስፈልጋል

$
0
0

 

  • በሁለት ወራት ከ1.7 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን በላይ የዕርዳታ እህል ተከፋፍሏል

በዚህ ዓመት በተካሄደው የበልግ ወቅት ጥናት መሠረት፣ በአሁኑ ወቅት ከ8.5 ሚሊዮን በላይ የድርቅ ተጎጂዎች ከሐምሌ 2009 ዓ.ም. እስከ ታኅሳስ 2010 ዓ.ም. የሚያቆይ የምግብና ሌሎች የዕለት ደራሽ ዕርዳታዎችን ለማቅረብ 487.7 ሚሊዮን ዶላር ያስፈልጋል ተባለ፡፡

ብሔራዊ የአደጋና የሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ለሪፖርተር እንዳስታወቀው ከሆነ፣ በቆላማና አርብቶ አደር አካባቢዎች በተደረገ ጥናት መሠረት ይፋ የተደረገው የድርቅ ተጎጂዎች ቁጥር 7.8 ሚሊዮን ነበር፡፡ የዕለት ደራሽ የምግብ ዕርዳታን ጨምሮ የትምህርት፣ የሰውና የእንስሳት ጤና፣ የእርሻና የውኃ አቅርቦቶችን ከግምት ባስገባው አዲሱ የበልግ ጥናት መሠረት፣ 8.5 ሚሊዮን የድርቅ ተጎጂዎች በአገሪቱ እንደሚገኙ የኮሚሽኑ ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ደበበ ዘውዴ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡

በጥናቱ የተሳተፉ 200 ባለሙያዎች በአገሪቱ 177 ወረዳዎች ውስጥ ለ21 ቀናት ተዘዋውረው ባደረጉት የመስክ ጥናት መሠረት፣ ቁጥራቸው ከ8.5 ሚሊዮን በላይ መድረሱ ለተረጋገጠው ተጎጂዎች የሚያስፈልገውን የምግብ፣ የምግብ ነክና ሌሎች አቅርቦቶች ለማሟላት 487.7 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ መረጋገጡን አቶ ደበበ አስታውቀዋል፡፡ በዚህም መሠረት ባለፈው ሐምሌ 1.2 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን እህል ሲቀርብ፣ በዚህ በነሐሴ ወር ደግሞ 550,000 ሜትሪክ ቶን የዕርዳታ እህል መከፋፈሉ ተጠቅሷል፡፡

መንግሥት 63 በመቶውን የ487.7 ሚሊዮን ዶላር እንደሚሸፍን ሲገለጽ፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የዓለም የምግብ ፕሮግራም 20 በመቶውን፣ እንዲሁም 17 በመቶውን ደግሞ ዓለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅቶች እንደሚሸፍኑት አቶ ደበበ ገልጸዋል፡፡ በዚህ ዓመት መንግሥት 170 ሚሊዮን ዶላር ያህል ለዕርዳታ ማዋሉ ሲጠቀስ፣ የአሜሪካ መንግሥት በቅርቡ 137 ሚሊዮን ዶላር እንደለገሰ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡

በ2008 ዓ.ም. በተከሰተው ድርቅ ሳቢያ 10.2 ሚሊዮን ሕዝብ ለአስቸኳይ የዕለት ደራሽ ዕርዳታ ተዳርጎ ቆይቷል፡፡ በወቅቱ ያስፈልጋል ከተባለው የዕርዳታ ገንዘብ ውስጥ መንግሥት 16.5 ቢሊዮን ዶላር ወጪ ማድረጉን አቶ ደበበ አስታውሰዋል፡፡ የተመድ የሰብዓዊ ዕርዳታ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት በሳምንታዊ መግለጫው ባለፈው ሳምንት እንዳረጋገጠው፣ በጥር ወር ከነበረው የ5.6 ሚሊዮን ተረጂዎች ቁጥር ይልቅ በአሁኑ ወቅት ለተመዘገበው የ8.5 ሚሊዮን ተረጂዎች 487.7 ሚሊዮን ዶላር ያስፈልጋል፡፡

ከተረጂዎቹ ውስጥ 3.6 ሚሊዮን ሕፃናት፣ ነፍሰ ጡሮችና የሚያጠቡ ሴቶች የተመጣጠነ የምግብ እጥረት ስለሚታይባቸው የአልሚ ምግብ አቅርቦት ይፈልጋሉ፡፡ 10.5 ሚሊዮን ዜጎች በቋሚነት የንፁህ ውኃ አቅርቦት እንደሚያስፈልጋቸው ተመድ አስታውቆ፣ 2.2 ሚሊዮን አባወራዎችም የቁም እንስሳት ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው ይፋ አድርጓል፡፡ ይህን ያህል አባወራዎች የቁም እንስሳት ድጋፍ ይሻሉ ያለው የተመድ ሪፖርት፣ የሞቱ እንስሳት ቁጥር ምን ያህል እንደሆነ በግልጽ አልጠቀሰም፡፡

ድርቅ እንደ ቀድሞው በአሥርና በአምስት ዓመታት ውስጥ የሚከሰትበትን ዑደት በመቀየር በአሁኑ ጊዜ በየዓመቱ ደጋግሞ መምጣቱ የአየር ንብረት ለውጥ ያመጣው ተፅዕኖ እንደሆነ የሚገልጹት አቶ ደበበ፣ ከድርቅ በተጨማሪ ከዚህ ቀደም በጎርፍ ምክንያት ይከሰት የነበረው አደጋ ግን መቀነሱን አስረድተዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ክልሎች ለጎርፍ መከላከል የሚጠበቅባቸውን ሥራ በማከናወናቸው ነው ብለዋል፡፡ በአንፃሩ በአዲስ አበባ ከተማ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ እንደሆኑ በከተማው አስተዳደርና በኮሚሽኑ የጎርፍ ግብረ ኃይል የተለዩ 25 አካባቢዎች እንዳሉ ጠቁመዋል፡፡ ይሁንና በክረምቱ በረዶ ቀላቅሎ በሚጥለው ዝናብ ሳቢያ፣ በከተማዋ ዋና ዋና መንገዶች ከፍተኛ የጎርፍ ውኃ እየተከሰተ ነው፡፡

 

 

 

 

 

Standard (Image)

የአማራና የቅማንት ሕዝቦችን ፍላጎት የሚለየው ሕዝበ ውሳኔ መስከረም 7 ቀን እንዲካሄድ ተወሰነ

$
0
0

 

የአማራና የቅማንት ሕዝቦች ተቀላቅለው በሚኖሩባቸው 12 ቀበሌዎች በማኀበረሰቦቹ ፍላጎት ላይ የተመሠረተ አስተዳደር ለማቋቋም ሕዝበ ውሳኔ እንዲካሄድ በተወሰነው መሠረት፣ መስከረም 7 ቀን 2010 ዓ.ም. እንዲካሄድ የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ወሰነ።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የአማራና የቅማንት ሕዝቦች ተቀላቅለው የሚኖርባቸው 12 ቀበሌዎች ሕዝበ ውሳኔ እንዲያካሄድ በፌዴሬሽን ምክር ቤት በቀረበለት ጥያቄ መሠረት ቅድመ ዝግጅቶች በማድረግ፣ የሕዝበ ውሳኔውን የጊዜ ሰሌዳ እንዳፀደቀ ከተቋሙ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

በዚህም መሠረት የድምፅ መስጫው ቀን መስከረም 7 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲሆን ቦርዱ ሲወስን፣ ከነሐሴ 29 ቀን 2009 ዓ.ም. እስከ መስከረም 3 ቀን 2010 ዓ.ም. ድረስ የሕዝበ ውሳኔው ተሳታፊዎች ምዝገባ እንደሚካሄድ አስታውቋል።

መስከረም 8 ቀን 2010 ዓ.ም. የሕዝበ ውሳኔው ውጤት በየምርጫ ጣቢያዎቹ እንደሚለጠፍ፣ የተጠቃለለው የሕዝበ ውሳኔ ውጤት መስከረም 15 ቀን 2010 ዓ.ም. ሕዝበ ውሳኔው እንዲካሄድ ላዘዘው የፌዴሬሽን ምክር ቤት እንደሚላክ ቦርዱ አስታውቋል።

የቅማንት የማንነት ጥያቄ በአማራ ክልል ባለፉት ጥቂት ዓመታት ተፈጥሮ የነበረውን አለመረጋጋት ከፈጠሩ ጉዳዮች መካከል አንዱ ነበር፡፡

አስቀድሞ ቅማንት በሕገ መንግሥቱ የተቀመጡ የልዩ ማንነት መሥፈርቶችን አያሟላም በማለት ውድቅ አድርጎ የነበረው የአማራ ክልል፣ የቅማንት ማኅበረሰብ አባላት ባቀረቡት ይግባኝ ላይ ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ጋር ውይይት አድርጎ በድጋሚ ጉዳዩን በማየት ከሁለት ዓመታት በፊት ዕውቅና ሰጥቷል፡፡ ዕውቅናውን በተግባር ለመቀየር የማኅበረሰቡ አባላት ራሳቸውን በራሳቸው እንዲያስተዳድሩ በመርህ ደረጃ ስምምነት ላይም ተደርሶ ነበር፡፡

ይሁንና ይህ አስተዳደር የሚኖረው ደረጃና የሚያካትተው ቀበሌ ቁጥር ላይ ስምምነት መፍጠር አልተቻለም፡፡ ይህም ሌላ ግጭት እንዳይፈጥር በአፋጣኝ ለመወሰን እንዲረዳው፣ ክልሉ የራሱን ሥራ ካከናወነ በኋላ 12 ቀበሌዎች ላይ በብዛት የሚኖረው አማራ ነው? ወይስ ቅማንት? የሚለውን ለመወሰን የፌዴሬሽን ምክር ቤትን ዕርዳታ ጠይቋል፡፡

በእነዚያ ቀበሌዎች ሕዝበ ውሳኔ እንዲደረግ የወሰነው የፌዴሬሽን ምክር ቤት ሲሆን፣ ይህን የማስፈጸም ኃላፊነት ያለው ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በመሆኑ ጉዳዩን ወደ ቦርዱ መርቶታል፡፡

 

Standard (Image)

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርቡ ትዕዛዝ ተሰጠ

$
0
0

 

የተከሰሱበት የሽብርተኝነት አዋጅ አንቀጽ ወደ ወንጀል ሕግ ተቀይሮ እንዲከላከሉ ውሳኔ የተሰጠባቸው አቶ በቀለ ገርባ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝንና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳን በመከላከያ ምስክርነት በመቁጠራቸው ባለሥልጣናቱ እንዲቀርቡ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡

በእነ አያና ጉርሜሳ መዝገብ የተከሰሱት አቶ በቀለ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ለማ መገርሳ፣ የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንትና የከተማ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዓብይ አህመድ፣ የለገዳዲ ከተማ ከንቲባ ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒና የዕድሜ ልክ ፍርደኛው የቀድሞ የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) አመራር የነበሩት አቶ አንዱዓለም አንዳርጌንም በመከላከያ ምስክርነት ቆጥረዋቸዋል፡፡

በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራተኛ ወንጀል ችሎት ክርክራቸውን እያደረጉ የሚገኙት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባና የኦፌኮ አባል አቶ ጉርሜሳ አያና ሌሎች የመከላከያ ምስክሮቻቸውን አሰምተዋል፡፡

ምስክሮቹ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት በ2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ አንዳንድ አካባቢዎች በተቀሰቀሰው የሕዝብ ተቃውሞ ወቅት፣ ተከሳሾች ተቃውሞው በሰላማዊ መንገድ እንጂ በአመፅ መሆን እንደሌለበት ሲናገሩ እንደነበር አስረድተዋል፡፡

ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ለምስክሮቹ መስቀለኛ ጥያቄ አቅርቦ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ምስክርነቱ እየተሰጠ በመሀል ላይ ዓቃቤ ሕጉ የጨጓራ ሕመምተኛ መሆናቸውንና ምግብ መብላት እንዳለባቸው በማስረዳት፣ ችሎቱ ምስክርነቱን ከሰዓት በኋላ እንዲቀጥል ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ፍርድ ቤቱን ጠይቀው ነበር፡፡ ፍርድ ቤቱ ትንሽ ታግሰው ምስክሮች እንዲሰሙ ቢጠይቅም፣ ዓቃቤ ሕጉ እንደማይችሉ ደግመው በማስረዳታቸው ምስክርነቱ ተቋርጦ ከሰዓት በኋላ እንዲቀጥል ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

አቶ በቀለ ገርባ እጅ አውጥተው እንዲናገሩ እንዲፈቀድላቸው ጠይቀው ተፈቅዶላቸዋል፡፡ አቶ በቀለ የዓቃቤ ሕጉ ምክንያት የፈለጉትን መመርያ ለመጠየቅ አመቺ ሁኔታን ለመፍጠር መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እነሱ በማረሚያ ቤት ታስረውና ረሃብን ችለው የሚመላለሱት ፍትሕ ፍለጋ መሆኑን አስታውሰው፣ ድርጊቱ ተቋሙን የማይመጥን መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

ሌላው ፍርድ ቤቱ በተደጋጋሚ የሚሰጠውን ትዕዛዝ አለመፈጸማቸው ተረጋግጦባቸዋል ያላቸውን የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኃላፊዎች፣ ዋና ኢንቴንደንት አሰፋ ኪዳኔና ኦፊሰር ገብሬ አለማን በማስቀረብ የተግሳፅ ቅጣት ጥሎባቸዋል፡፡ ቅጣቱም ለመሥሪያ ቤታቸው በግልባጭ እንዲላክ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ እነ አቶ በቀለ በመከላከያ ምስክርነት የቆጠሯቸውን ከፍተኛ የፌዴራልና የክልል ባለሥልጣናት መከላከያ ምስክርነት ለመስማት፣ ለጥቅምት 27፣ 28 እና 29 ቀን 2010 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ 

Standard (Image)

‹‹ከመንግሥት ባለሥልጣን ጋር የተጠጋ አይነካም የሚለው ነገር ከዚህ በኋላ አይሠራም››

$
0
0

 

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ

የሙስና ወንጀል ተግባራት ጋር ተያይዞ መንግሥት እየወሰደ ያለው ዕርምጃ የዘገየ አለመሆኑንና የባለሥልጣን ከለላ ያላቸው አይነኩም የሚለውን አመለካከት እንደማይቀበሉት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ አስታወቁ፡፡ መንግሥት ከአሁን በኋላ በአገሪቱ አለመረጋጋትን የሚያስከትሉ ክስተቶችን እንደማይታገስም አስጠንቅቀዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ይህንኑ የገለጹት ቅዳሜ ነሐሴ 13 ቀን 2009 ዓ.ም. በተካሄደው በሦስተኛው የመንግሥትና የግሉ ዘርፍ የምክክር መድረክ ላይ ነው፡፡ በተለይ ከሙስና ጋር በተያያዘ በሰጡት ማብራሪያ መንግሥት እየወሰደ ያለውን ዕርምጃ እንደሚገፋበት አመልክተዋል፡፡ ከእሳቸው ማብራሪያ ቀደም ብሎ ግን በኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ሰለሞን አፈወርቅ የቀረበው ሪፖርት፣ የመንግሥት ዕርምጃ የዘገየ ነው የሚል አመለካከትን ያንፀባረቀ ነበር፡፡

በአገሪቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተስፋፋ የመጣውን ሙስናንና እያስከተለ ያለውን አደጋ በአፋጣኝ መፍትሔ መስጠት እንደሚያፈልግ የገለጹት አቶ ሰለሞን፣ ሙስና በአገር ዕድገትና ልማት ላይ ከፍተኛ አደጋ የሚያስከትል ዋነኛ የሥነ ምግባር ችግር መገለጫ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ምንም እንኳን ሙስናን በመከላከል ረገድ በመንግሥት የተከናወኑ የተለያዩ ሥራዎች ቢኖሩም፣ ችግሩን በሚፈለገው መጠን ለመቀነስ ባለመቻሉ ሳቢያ ከፍተኛ መጠን ያለው የአገር ሀብት ለምዝበራና ለብክነት በማጋለጥ አሳሳቢነቱ ከመቼውም ጊዜ በላይ ጨምሯል፤›› ብለዋል፡፡

መንግሥት ሲያስፈልግ ዘግይቶ ሙሰኞችን የሚይዝበት ሳይፈልግ የሚተውበት የሚመስል አሠራር በመተው የግሉን ዘርፍ፣ የፓርላማ አባላትን፣ ሲቪክ ማኅበራትንና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን ያካተተ ወጥነት ያለው አደረጃጀት በመፍጠር ክትትልና ቁጥጥር የሚደረግበት አሠራር መፈጠር ይኖርበታል ብለዋል፡፡

በመንግሥት የሚወሰዱ ዕርምጃዎች አጥፊዎችን በሕግ ከመቅጣት ባለፈ ለሌሎች አስተማሪ ሊሆን የሚገባው በመሆኑ፣ የሚወሰዱ ዕርምጃዎችን ውጤት ለሕዝብ በይፋ እንዲገለጽ ማድረግ እንደሚገባ፣ ዘግይቶ የሚሰጥ ውሳኔ ጊዜ በመግዛት የፍርድ መዛባትን ስለሚያስከትል እንዲህ ዓይነት ጉዳዮችን ብቻ የሚያይ ልዩ ችሎት እንዲቋቋም አቶ ሰለሞን ጠይቀዋል፡፡

አቶ ሰለሞን በዘመቻ መልክ የሚካሄዱ የፀረ ሙስና ሥራዎች የአንድ ወቅት ከመሆናቸው ባለፈ፣ በአጥፊዎች ላይ የሚወሰነው ቅጣት በሕዝብና በመንግሥት ጥቅም ላይ ካደረሱት ጉዳት አንፃር ሲመዘን ተመጣጣኝ ባለመሆኑና ሌሎች አጥፊዎችን ከማስተማር ይልቅ የሚያበረታታ በመሆኑ፣ የተፈለገውን ውጤት ሊያመጣ አልቻለም ብሎ ምክር ቤታቸው እንደሚያምንም ተናግረዋል፡፡ ‹‹በተለይ በቅርቡ በመንግሥት የተወሰደውን ዕርምጃ የተመለከትን እንደሆነ ከዚች ደሃ አገር በቢሊዮኖች የሚቆጠር የሕዝብ ሀብት ያላግባብ ሲመዘበርና ሲባክን የበይ ተመልካች በሆነው ሕዝብም ሆነ መንግሥት በኩል፣ ይህ ሁሉ ሲሆን የት ነበርን የሚያስብል አግራሞትና ትዝብት የሚፈጥር ነው፤›› ብለዋል፡፡

ከዚህ ሐሳብ ጋር የማይስማሙ መሆኑን ያመለከቱት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በበኩላቸው፣ ‹‹አሁን በኋላ መንግሥት እንደ ድሮው ዓይነት አይሆንም፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹እንኳን ከመንግሥት ባለሥልጣን የተጠጋ አሁን የመንግሥት ባለሥልጣናት መያዣ መጨበጫ አጥተዋል፤›› በማለት የሰሞኑን ክስተት አንፀባርቀዋል፡፡ አንዱ ተቆርጦ ሌላው እንደማይቀር ተናግረው፣ ስለዚህ አሁን እከሌ የሚባል ባለሥልጣን አለኝና እሱን ተገን አድርጌ እንደፈለግኩ እኖራለሁ የሚል ሰው ካለ እጁን መሰብሰብ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ ከሙስናና ከሕገወጥ ተግባራት ጋር በተያያዘ እየተወሰደ ያለውን ዕርምጃ በተመለከተም፣ ቀጣዩ የመንግሥት ዕርምጃ በንግዱ ዘርፍ ላይ የሚያነጣጥር መሆኑን ለማስገንዘብ ‹‹የሚቀጥለው ጥናታችን ወደ ንግዱ እየገባ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ይህ ንግግራቸው በትክክል የሚፈጸምና የአገር ጉዳይ በመሆኑ የሚተገበር መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡ ‹‹ይቺ አገር ሰላማዊ ካልሆነች የማናችንም መኖር ዋስትና የለውም፡፡ ከዚህ በፊት አንዳንድ የሚወሩ ነገሮች ነበሩ፡፡ እከሌ የሚባል ባለሥልጣን ዘንድ የተጠጋ ስለሆነ አይነካም፡፡ እስቲ እንደማይነካ እናያለን፡፡ እውነቴን ነው የማይነካ ሰው የለም፡፡ ምክንያቱም ከግለሰቦች አገር ይበልጣል፤›› ብለዋል፡፡

‹‹ይህ ሲደረግ ግን ሕግና ሥርዓትን ተከትለን ነው፤›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በአንድ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ውስጥ ትልቁ ምሰሶ የሕግ የበላይነትን ማስከበር እንደሆነ አስገንዝበዋል፡፡ የአገሪቱ ሕገ መንግሥትና ሕጎች በሚፈቅዱት መሠረት ብቻ ዕርምጃ እንደሚወሰድና eza

 News 1ዕርምጀጃዕር ማንም ቢሆን ራሱን የመከላከል መብት እንደሚኖረው አስገንዝበዋል፡፡

የኪራይ ሰብሳቢነትና የሙስና ምንጭ የሆኑ አምስት ጉዳዮች መኖራቸውን መንግሥት ሲናገር እንደቆየ ያመለከቱት አቶ ኃይለ ማርያም፣ ‹‹ከእነዚህ ውስጥ አንደኛው መሬት ነው፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ከመሬት ሊዝ ጋር የሚገናኝ ችግር አለ፡፡ ይኼ ችግር የሚያጋጥመን በትልልቅ ከተሞች ነው፡፡ ለምሳሌ የሪል ስቴት አልሚዎችን ማየት ይቻላል፡፡ የሪል ስቴት አልሚዎችን ነገሩ ወደ እስር ቤት የሚያስገባም ቢሆንም ግድ የለም እንታገሳቸውና የወሰድከውን ትርፍ መሬት መልስ ከመለስክ በኋላ የቦታውን ትክክለኛ ሊዝ ክፈል ብለን ከባለሀብቶቹ ጋር ተደራድረን እስር ቤቱን ላለማጣበብ ሙከራ አድርገናል፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡

አሁን መንግሥት የወሰደው ዕርምጃ የዘገየ ነው የሚለው አቋም መንግሥትን በማንቋሸሽ ዕርምጃውን ለማስቀረት የሚደረግ ፕሮፓጋንዳ ነው ብለውታል፡፡ ‹‹ይህንን አመለካከት በግሌ የምቀበለው አይደለም፡፡ እቺ እሳት እየተቀጣጠለች ወዴት ትደርሳለች ብሎ ያሰበ ሁሉ እያንቋሸሸ ነው፤›› ያሉት አቶ ኃይለ ማርያም እሳቱ መድረሱ፣ መንግሥትም ጠንክሮ መቀጠሉ እንደማይቀር አመልክተዋል፡፡

የሙስና ዕርምጃው የላይኛውን የሥልጣን አካል አልነካም እየተባለ የሚነገረውም ለማንቋሸሽና ለማኮላሸት የሚደረግ ሙከራ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ‹‹የፕሮፖጋንዳው ምንጭ በአግባቡ ካልጠራ በስተቀር ሒደቱን ለማኮላሸት የሚደረግ ሽረባ ነው፤›› ብለዋል፡፡ የንግዱ ኅብረተሰብ በዚህ ላይ አንድም ጥቆማ ያለመስጠቱን እንደ ምሳሌ አቅርበዋል፡፡

የንግድ ምክር ቤቱም ሆነ የዘርፍ ማኅበራቱ አንድ ጥቆማ ያለማምጣታቸውን የጠቆሙት አቶ ኃይለ ማርያም፣ እስካሁን የደረሱ ጥቆማዎች ከሕዝብ የመጡ እንደሆኑም ገልጸዋል፡፡

‹‹የንግድ ኅብረተሰቡ አንድም ጥቆማ ሳያደርግ ጉዳዩን መንግሥት ላይ ደፍድፋችሁ የፀረ ሙስና ትግል በዚህ ይሄዳል ብላችሁ ካሰባችሁ አያስኬዳችሁም፤›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹ከማንም በላይ ሌባ የምታውቁት እናንተ ናችሁ፡፡ ምንም የሌለው ሰው በአጭር ጊዜ ውስጥ የብዙ ሕንፃዎች ባለቤት ሲሆን የምታውቁት እናንተ ናችሁ፡፡ አብራችሁ የምትበሉ የምትጠጡ፣ በሠርጉም በድግሱም አብራችሁ የምትቆዩት እናንተ ስለሆናችሁ፣ እናንተ እኛን አከናንባችሁ መንግሥት ዘግይቶ እንዲህ አደረገ ማለት አትችሉም፤›› በማለት የንግድ ኅብረተሰቡ ሙሰኞችን በመጠቆም ኃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

የፀረ ሙስና ንቅናቄ ተብሎ በሚደረግ መድረክና ስብሰባ የንግድ ምክር ቤቱ አመራሮች መኖራቸውን በማስታወስ፣ አሁን ምንም እንደማያውቁ አድርገው ያቀረቡት  እንዳልሆነም አመልክተዋል፡፡ ‹‹የፀረ ሙስና ትግል ኅብረተሰባዊ ካልሆነ፣ የሕዝብ ንቅናቄ ያልተፈጠረበት ትግል ካልሆነ ውጤቱ የተኮላሸ ይሆናል፡፡ የምንጋፈጠው ኃይል ቀላል  አይደለም፡፡ የራሱ መስመርና ኃይል ካለው ጋር ነው የምንጋፈጠው፡፡ በዚህ ትግል የንግዱ ኅብረተሰብ በሙሉ ቀልብ ተሳታፊ ከሆነ ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ ይህንን በጋራ ሆነን አጠናክረን ከቀጠልን ፍትሐዊ የንግድ ኢንቨስትመንት ይኖራል፤›› ሲሉም ከመወቃቀስ ይልቅ በትብብር ለመሥራት ጥሪ አድርገዋል፡፡

በቅዳሜው ስብሰባ ላይ ከሙስና ጋር በተያያዘ የሕዝብ ሀብት እየተመዘበረ ለመሆኑ ለቀረበው አስተያየት ጉዳዩን ከቡና የኮንትሮባንድ ንግድ ጋር አያይዘው መልስ ሰጥተውበታል፡፡ ቡና በሕገወጥ መንገድ እንደሚወጣ በመናገር፣ ይህንን የሚያደርጉት በሕጋዊ መንገድ ቡና እያቀረቡ ያሉ ነጋዴዎች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ‹‹በኮንትሮባንድ  ቡና ከአገር የሚያስወጡት አንድ እግራቸውን በማዕከላዊ ገበያ ያደረጉ፣ ሌላውን እግራቸውን ደግሞ ሱዳን ያስቀመጡ ሰዎች ናቸው፤›› በማለት ሕገወጥ ንግዱ ሕጋዊ ፈቃድ ባላቸው የሚከናወን እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ በሁለት እግሮች ይንቀሳቀሳሉ ያሉዋቸውን፣ ‹‹እግራችሁ ሰብሰብ ይበል!›› በማለት ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል፡፡

እንዲህ ያለው ጉዳይ መስተካከል እንዳለበት ያሳሰቡት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹ለዚህም አንድ ጠንካራ ፀረ ኮንትሮባንድ ቡድን አቋቁሜያለሁ፡፡ አከርካሪ ሰብረንም ቢሆን እናስተካክላለን፤›› በማለት በመንግሥት ሊወሰድ የታሰበውን ዕርምጃ ጠቆም አድርገዋል፡፡ ቀጣዩ ዕርምጃ በንግድ ላይ ነው የተባለውም ለዚህ እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ ‹‹እነዚያ አጭበርባሪ ኮንትራክተሮች ንብረታቸው ታግዷል፡፡ ስንትና ስንት ዓመት የለፉበትን ንብረት በሌብነት ምክንያት እያጡት ነው፤›› ያሉት አቶ ኃይለ ማርያም፣ ተዘረፈ የተባለውን በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ለማስመለስ የሚያስችል በቂ ንብረት አለ ብለዋል፡፡ ‹‹የተዘረፈ የሕዝብ ንብረት ተዘርፎ አይቀርም፤›› የሚል ምላሽም ሰጥተዋል፡፡ በዚህ ረገድ ሥጋት እንደሌለም ጠቁመዋል፡፡

ከዚሁ ማብራሪያ ጎን ለጎንም ሰሞኑን ከሙስና ጋር ተያይዞ ተጠርጥረው ስለታሰሩ ግለሰቦችና ስለታገዱ ኩባንያዎች ታዘብን ያሉትን እንዲህ ገልጸው ነበር፡፡ ‹‹ንብረታቸው የታገደባቸው ኩባንያዎች ስም ሲጠራ ብዙ ሰው ቦሌ ነበር፡፡ የመንገድ ፕሮጀክቶች ሲባል ወዲያው ራሱን የጠረጠረም ነበር፡፡ እኛ ያልደረስንበትም የደረስንበትም ነበር፡፡ የዱባይ አውሮፕላን ተጨናንቆ ነበር፤›› ብለዋል፡፡ እዚያ ከመድረስ በፊት መጠንቀቅ እንደሚያሻ ያመለከቱት አቶ ኃይለ ማርያም፣ ‹‹ያንን ሁሉ ለፍተው ያገኙትን ንብረት ጥለው ከመኮብል በፊት አርፎ መቀመጥ ይሻላል፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹በእርግጥ እነዚህ ሰዎች እዚያ (ዱባይ) ገንዘብና ንብረት እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ቢሆንም ዋናው ንብረት እዚህ ነው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ ‹‹የቡናውንም ቢሆን መልክ እናስይዛለን፡፡ ይኼ ካልሆነ አገራችን ችግር ውስጥ መውደቋ አይቀርም፡፡ ስለዚህ በዚህ ትግል ውስጥ በጋራ እንሳተፍ፡፡ ከቡና ጋር ተያይዞ አለ የሚባለውን ችግር ብናይ ጥሩ ነው፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡

በዚህ የምክክር መድረክ አቶ ኃይለ ማርያም አፅኖት ሰጥተው ካስገነዘቡዋቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ፣ በባህር ዳር አካባቢ ከንግዱ ኅብረተሰብ አባላት መታሰር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ‹‹በባህር ዳር አካባቢ ከመረጋጋት ጋር ተያይዞ መንገራገጭ ቢኖርም ይህንን እናስቆመዋለን፤›› ብለዋል፡፡ በአማራ ክልል ታስረዋል የተባሉ ሰዎች ንፁኃን ናቸው የሚለውን አስተያየት አቶ ኃይለ ማርያም እንደማይቀበሉት ገልጸዋል፡፡ ‹‹የታሰሩት ሰዎች ተጠንተው የታሰሩ ናቸው፡፡ ዛሬ ብቻ ሳይሆን ቀድሞም የነበሩ ሰዎች ናቸው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹ሰውዬው ስሙ ማንም ሊሆን ይችላል፡፡ የትኛውም ዓይነት ክብር ሊኖረው ይችላል፡፡ ወጣት፣ ታክሲ፣ ባጃጅ እየቀሰቀሰ፣ ገንዘብ እየሰጠ፣ ዝጉ እያለና እያሰማራ ሕፃናቱን ከፊት እንድናገኝ አናደርገውም፤›› በማለት የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹አሁን ግን ሥሩን ፈትሸን እንነቅላለን፡፡ እስካሁንም ከወጣቶቻችን ጋር የተጋጨነው ይበቃናል፤›› በማለት ሲናገሩ ተሳታፊዎች የሞቀ ጭብጨባ ችረዋቸዋል፡፡

በዚህ የምክክር መድረክ ላይ የተለያዩ ሐሳቦች የተሰነዘሩ ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም ከንግድ ማኅበረሰቡ ለተጠየቁ ጥያቄዎች ተጨማሪ ማብራሪያ ይሰጡ የነበሩ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች፣ በቅዳሜው ስብሰባ ምንም ዓይነት አስተያየት አልሰጡም፡፡

 

 

 

 

Standard (Image)

ኢትዮጵያና ግብፅ በዳግም ዲፕሎማሲያዊ ውጥረት

$
0
0

 

የኢትዮጵያ፣ የግብፅና የሱዳን ግንኙነት በማንኛውም መሥፈርት እጅግ የተወሳሰበ ነው፡፡ ለዘመናት በእርስ በርስ ጦርነት፣ ግጭትና ፖለቲካ ፍትጊያ ውስጥ አልፈዋል፡፡ አልፎ አልፎም ሁለት ሆነው በማበር አንዱ ላይ ጥቃት ለመፈጸም ያሴሩበት አጋጣሚም ነበር፡፡ እንደዚህ ዓይነት ጥምረቶች በተለያዩ ዓውዶች ውስጥ ሲለዋወጡም ተስተውሏል፡፡ ይሁንና የግብፅና የሱዳን ጥምረት ለረዥም ጊዜ የዘለቀ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ ላይ በርካታ ጉዳቶችን አስከትሏል፡፡ ከዚህ እውነት በተቃራኒ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ሱዳን ቀስ በቀስ ከግብፅ እየራቀችና ወደ ኢትዮጵያ እየቀረበች በመምጣቷ፣ አንዳንዶች አዲስ ጥምረት በቅርቡ ሊታይ እንደሚችል መገመት ጀምረዋል፡፡

በናይል ጉዳይ ላይ የሚሠሩ የፖለቲካ ተንታኞች ይህ ግብፅ ከኢትዮጵያ ጋር ያለባትን ዲፕሎማሲያዊ ጦርነት በድል ለመወጣት የተለየ ታክቲክ እንድትጠቀም እንዳስገደዳት ይጠቁማሉ፡፡ በዚህም ከተፋሰሱ አገሮች መካከል አዲስ አጋር ለማግኘት በመኳተን ላይ ትገኛለች፡፡ የግብፅ ፕሬዚዳንትም ወደ እነዚህ አገሮች ሲመላለሱ ማየት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አዲስ ነገር አይደለም፡፡  

ይኼው አዝማሚያ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ በቅርቡ ወደ ሩዋንዳና ታንዛኒያ ባደረጉት ጉብኝት ቀጥሏል፡፡ ነገር ግን ጉብኝቱ ከተደረገበት ጊዜና ቦታ አንፃር ይህን ጉብኝት የተለመደ ነው ብሎ ማለፍ አይቻልም፡፡ ሩዋንዳና ታንዛኒያ ከኢትዮጵያ ጋር በመሆን የናይል ቤዚን ሁሉን አቀፍ የትብብር ማዕቀፍ (ሲኤፍኤ) ያፀደቁ ብቸኛ አገሮች ናቸው፡፡ ጉብኝቱ የተደረገበት ጊዜም ቢሆን የግብፅን ሥሌት ያሳያል፡፡ ከሁለት ወራት በፊት በካምፓላ ኡጋንዳ በዩዌሪ ሙሴቬኒ ግብዣ የተፋሰሱ አገሮች መሪዎች በተገናኙበት ወቅት፣ ግብፅ በቅድመ ሁኔታ ታጅባ ወደ ናይል ቤዚን ኢኒሼቲቭ (ኤንቢአይ) ለመመለስ ጥያቄ አቅርባ ነበር፡፡ ቅድመ ሁኔታዋ በሲኤፍኤው አንቀጽ 14 (ቢ) ላይ እንዲካተት ከምትፈልገው የውኃ ደኅንነት ጋር የተገናኘ ነው፡፡ አዲስ ሲኤፍኤ እንዲረቀቅ ሐሳብ ያቀረበችው ግብፅ በናይል ውኃ ላይ የአንበሳውን ድርሻ የሚሰጣት በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈረመው ስምምነት የዚሁ አካል እንዲሆን ጠይቃለች፡፡ አብዛኞቹ አገሮች ግብፅ ኤንቢአይን በድጋሚ ለመቀላቀል ፍላጎት ማሳየቷን ያበረታቱ ቢሆንም ቅድመ ሁኔታዋን አልተቀበሉትም፡፡

ከተፋሰሱ አገሮች በተለይ ኢትዮጵያ የግብፅን ቅድመ ሁኔታ አምርራ ተቃውማለች፡፡ ኢትዮጵያ ሲኤፍኤው ላይ ክርክርና ድርድር ተደርጎ ካበቃ በኋላ ስምምነቱ ለማፅደቅ ክፍት ተደርጎ ሦስት አገሮች በፓርላማቸው አፅድቀውት እያለ፣ በድጋሚ ለድርድር ክፍት የሚሆንበት ምክንያት እንደሌለ አስረድታለች፡፡ ግብፅ በድጋሚ የኤንቢአይ አባል ለመሆን የምታቀርበው ሐሳብ ላይ በቅርቡ የሚካሄደው የናይል ቤዚን የሚኒስትሮች ምክር ቤት ስብሰባ ላይ በዝርዝር ለመነጋገር  ቀጠሮ መያዙን ከኤንቢአይ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡ የአልሲሲ ጉብኝትም በዚሁ ጉዳይ ላይ ለተሳታፊዎቹ ቅድመ ገለጻ በማድረግ ላይ ያነጣጠረ መሆኑ አያጠራጥርም፡፡

የአልሲሲ ጉብኝት ቻድና ጋቦንን ጨምሮ አራት የአፍሪካ አገሮችን ያካለለ ሲሆን፣ በሩዋንዳና በታንዛኒያ በነበራቸው ቆይታ ወቅት አዲሱን የግብፅ ሐሳብ በማብራራት ለማሳመን መጣራቸው ሚስጥር አልነበረም፡፡ እንደተለመደው እ.ኤ.አ. በ1959 ከሱዳን ጋር የፈረሙትን ስምምነት በመጥቀስ ከናይል ውኃ ዓመታዊ ድርሻቸው 55.5 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ላይ መቀነስ የሚታሰብ እንዳልሆነ አሳስበዋል፡፡ አልሲሲ የግብፅን ሥጋት “የሕይወትና የሞት ጉዳይ” ሲሉ ገልጸውታል፡፡

የታንዛኒያ ፕሬዚዳንት ጆን ማጉፉሊና የሩዋንዳ ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ የግብፅን ሥጋትና ፍላጎት እንደሚገነዘቡ ቢናገሩም፣ ከሲኤፍኤው ወደ ኋላ የማለት አዝማሚያ አላሳዩም፡፡ ሁለቱም መሪዎች ለናይል ውኃ ችግሮች ሁሉም አባል አገሮችን ያቀፈ መፍትሔ መስጠት እንደሚያስፈልግ አስምረውበታል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ወደ ሱዳን በማቅናት ለሦስት ቀናት ይፋዊ  ጉብኝት ያደረጉት፣ በተመሳሳይ ሳምንት መሆኑ የአጋጣሚ ጉዳይ አይመስልም፡፡ እርግጥ ነው የኢትዮጵያ መንግሥት ከግብፅ በተቃራኒ ይህ ጉብኝት የፖለቲካ ግብ እንደሌለው ገልጿል፡፡ በተለይ ከናይል ውኃ ጋር የተያያዘ ልዩ የውይይት አጀንዳ እንዳልነበረ አስታውቋል፡፡ ሁለቱ አገሮች በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሁለትዮሽ ስምምነት ማድረጋቸውም ተመልክቷል፡፡ ይሁንና በርካታ የፖለቲካ ተንታኞች ጉብኝት ከናይል ውኃ ጋር የተያያዘ እንደሆነ ያምናሉ፡፡

ሁለቱ አገሮች በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ውይይት እንዳደረጉ የተገለጸ ቢሆንም፣ ኤንቢአይና ዋነኛ ዓላማው የሆነውን ፍትሐዊ የውኃ ክፍፍልን ዕውን ለማድረግ ቁርጠኛ እንደሆኑ መናገራቸው የመገናኛ ብዙኃኑን ትኩረት ስቧል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና የሱዳን ፕሬዚዳንት ኦማር አል በሽር በሰላምና ደኅንነት፣ በኢኮኖሚያዊ ትስስር፣ በድንበር ጉዳዮችና በመሳሰሉት ላይ መነጋገራቸውም ተገልጿል::

የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ጉብኝት ዓላማ እንደ ፕሬዚዳንት አልሲሲ በግልጽ ከናይል ውኃ ዲፕሎማሲ ጋር የተገናኘ ነው ለማለት አዳጋች ቢሆንም፣ ኢትዮጵያና ግብፅ ዲፕሎማሲያዊ ውጥረት ውስጥ ዳግም ስለመግባታቸው ግን ከበቂ በላይ ማሳያ ነው፡፡ ከዚህ ውጥረት አንፃር የሲኤፍኤው ዕጣ ፈንታ ምን ይሆናል? ብሎ መጠየቅም ምክንያታዊ ነው፡፡

ሲኤፍኤው አደጋ ውስጥ ነውን?

የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ሲኤፍኤውን የአገሪቱና የመንግሥት ዲፕሎማሲያዊ ስኬት ማሳያ አድርገው ያቀርቡታል፡፡ የስምምነቱ ዋነኛ ዓላማም በተፋሰሱ ፍትሐዊ የውኃ ክፍፍልና ተጠቃሚነትን ማስፈን ነው፡፡ ስምምነቱን እስካሁን ኢትዮጵያ፣ ኡጋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ ሩዋንዳ፣ ኬንያና ቡሩንዲ የፈረሙ ቢሆንም ያፀደቁት ግን ኢትዮጵያ፣ ሩዋንዳና ታንዛኒያ ብቻ ናቸው፡፡ ስምምነቱ አስገዳጅ ለመሆንና ወደ ሥራ ለመግባት በስድስት አገሮች መፅደቅ አለበት፡፡

ግብፅና ሱዳን እ.ኤ.አ. የ1959 ስምምነታቸውን የሚንድ በመሆኑ ሲኤፍኤውን ይቃወማሉ፡፡ በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ሌሎች የተፋሰሱ አገሮችን በተለይም ስምምነቱን ፈርመው እስካሁን ያላፀደቁትን ኡጋንዳን፣ ኬንያንና ቡሩንዲን በማሳመን እንዲያፀድቁት በማድረግ ሲኤፍኤውን ወደ ሥራ ለማስገባት እየጣረች ትገኛለች፡፡

ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳን በሲኤፍኤው ያላቸው ልዩነት እንዳለ ሆኖ በ2003 ዓ.ም. የታላቁ ህዳሴ ግድብ ይፋ ከሆነ በኋላ በግንኙነታቸው ላይ ውጥረት ነግሶ ነበር፡፡ ግድቡ በሁለቱ አገሮች ላይ መሠረታዊ ጉዳት ያስከትላል? አያስከትልም? የሚለው ጉዳይ አዲስ የውዝግብ አጀንዳ ሆኖ ነበር፡፡ በተለይ ግብፅ የግድቡ ግንባታ በፍጥነት ካልተገታ የኃይል ዕርምጃ ለመውሰድ እንደምትገደድ ሁሉ አስጠንቅቃ ነበር፡፡

ኢትዮጵያ ግድቡ በታችኛው ተፋሰስ አገሮች ላይ መሠረታዊ ጉዳት እንደማያስከትል እየተገነባ መሆኑን በመግለጽ የተፅዕኖ ግምገማ ጥናት ከግብፅና ከሱዳን ጋር ለማካሄድ ፈቃደኝነቷን አሳየች፡፡ ይህን ለማከናወን የተቋቋመው ዓለም አቀፍ የኤክስፐርቶች ፓናል በ2004 ዓ.ም. መቋቋሙም ይታወሳል፡፡ በግንቦት ወር 2005 ዓ.ም. ጥናቱ ይፋ ሲሆን ተጨማሪ ጥናቶች እንዲደረጉ ነው ምክረ ሐሳብ የቀረበው፡፡ እነዚህን ተጨማሪ ጥናቶች ለማድረግ ሦስቱ አገሮች እስካሁን በርካታ ውጣ ውረዶችን ቢያዩም አልተጠናቀቀም፡፡ ሒደቱ ከግድቡ ግንባታ ጋር የተገናኘ እንዳልሆነ፣ ይልቁንም በሌሎቹ አገሮች ዘንድ መተማመን እንዲፈጠር ለማድረግ ያለመ እንደሆነ ኢትዮጵያ ትገልጻለች፡፡ ግብፅ አሁንም ግድቡ መሠረታዊ ጉዳት ያስከትልብኛል የሚል አቋም ያላት ሲሆን፣ ሱዳን ግን ግድቡ ከጉዳት ይልቅ ዘርፈ ብዙ ጥቅም እንደሚሰጣት በሒደት ተቀብላለች፡፡

በዚህ መሀል በ2007 ዓ.ም. ሦስቱ አገሮች በህዳሴ ግድቡ ላይ የመርህ መግለጫ ስምምነት ተፈራረሙ፡፡ ስምምነቱ ከዓለም አቀፍ የውኃ ሕግና ከሲኤፍኤው የተወሰኑ ድንጋጌዎችንና መርሆዎችን ይዟል፡፡

የመርህ መግለጫ ስምምነቱ ይፋ ከሆነ በኋላ በሁሉም አገሮች ማለት ይቻላል ውዝግብ አስነስቷል፡፡ አንዳንዶች እንደ ትልቅ ስኬት ሲቆጥሩት፣ ሌሎች ግን በናይል ውኃ ፍትሐዊ አጠቃቀም ለመፍጠር እየተደረገ ባለው ድርድር ላይ መሰናክል እንደሆነ ይከራከራሉ፡፡

ሱዳናዊው የዓለም አቀፍ ሕግ ኤክስፐርት ዶ/ር ሳልማን መሐመድ በዚህ ስምምነት ግብፅና ሱዳን ሌሎች የተፋሰሱ አገሮች በናይል ውኃ ላይ የመጠቀም መብት እንዳላቸው በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ዕውቅና ከመስጠታቸው አንፃር፣ እንደ ትልቅ ዕርምጃ እንደሚወስዱት ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ “በእኔ እምነት የ1902፣ 1929 እና 1959 ስምምነቶችን የሻረ ነው፤” ብለዋል፡፡ ሌሎች ኤክስፐርቶች ግን ሰነዱን እንደ ሕግ ሰነድነት እንኳን ለመውሰድ ይቸገራሉ፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሚያስተምሩት የዓለም አቀፍ ሕግ ኤክስፐርቱ ዶ/ር ደረጀ ዘለቀ ከዚህ በተቃራኒ የመርህ መግለጫ ስምምነቱ ለዘመናት ከቆየው የኢትዮጵያ የውኃ ፖሊሲ ጋር አብሮ እንደማይሄድ ይከራከራሉ፡፡ “ስምምነቱ ለኢትዮጵያ ትልቅ የፖለቲካ ኪሳራ የሚያመጣ ነው፡፡ ሌሎች የተፋሰሱ አገሮች እንዲጠራጠሯት ያደርጋል፡፡ ዋነኛዋ የአጀንዳው ባለቤት ሲኤፍኤውን ከሚቃወሙ አካላት ጋር በአንድ ፕሮጀክት ላይ የጎንዮሽ ስምምነት የምታደርግ ከሆነ፣ ሌሎች አገሮች ስለቀጣይ ዕርምጃቸው እንዲጠነቀቁ ያደርጋቸዋል፡፡ በሲኤፍኤው ኢትዮጵያ ሌሎች አገሮችን ስታግባባ የነበረው የውኃ ጉዳይን ሁሉ ተቋማዊ አሠራር በመዘርጋት ሕግና መርህ ላይ ተመርኩዞ እንዲፈታ የማድረግን አስፈላጊነት ነበር፡፡ ከዚህ አንፃር ኢትዮጵያ ይህን ስምምነት መፈረሟ ኃላፊነት የጎደለው ዕርምጃ ነው፡፡ ሎሎቹ አገሮች ከግብፅ ጥቅም ለማግኘት ብለው ሲኤፍኤውን ቢተውት አይገርመኝም፤” ብለዋል፡፡

ዶ/ር ደረጀ የመርህ መግለጫ ስምምነቱን መሰል ስምምነት በተናጠል ከሌሎች አገሮች ጋር የመፈጸም ዕድል ካገኘች ግብፅ ሲኤፍኤው ተረስቶ እንዲቀር ልታደርግ እንደምትችል ይጠራጠራሉ፡፡ ‹‹በናይል ውኃ ጉዳይ ላይ ያላትን ፍፁም የበላይነት ለመጠበቅ እንድትችል ተቋማዊና ሕጋዊ አሠራር እንዳይኖር ትሠራለች፡፡ ለዚህ ደግሞ እያንዳንዱ አገር የሚፈልገውን አንገብጋቢ ጉዳይ መስጠት አንዱ ታክቲክ ነው፡፡ የፖለቲካ ሥልጣናቸው አስተማማኝ መሠረት የሌላቸው መንግሥታት በገንዘብ ሊገዙም ይችላሉ፡፡ ስለዚህ አሁን ያላቸው የበላይነት መሠረታዊ ለውጥ እንዳያሳይ ጠንክረው ይሠራሉ፡፡ በዚህም እየተሳካላቸው ነው ብየ አምናለሁ፤” ብለዋል፡፡

የሱዳን ቁልፍ አጋርነት

የኢትዮጵያና ሱዳን ግንኙነት ካላቸው የኋላ ታሪክ አኳያ በከፍተኛ ውጥረት የተሞላ ነው፡፡ የኢትዮጵያና የሱዳን ግንኙነት አሁን የያዘውን የወደጅነትና የትብብር ቅርፅ ከመያዙ በፊት ያሉት ጊዜያት ከ19ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በጥርጣሬ፣ ይበልጡን ደግሞ በጠላትነት እየተፈራረጁ ነው ያሳለፉት፡፡

የኋላውን አንድ ክፍለ ዘመን ትተን አሁን ሥልጣን ከያዘው ኢሕአዴግ ወይም ከመሥራቹ ሕወሓት ጋር ያለው ግንኙነት ቢታይ፣ የወዳጅነትና የጠላትነት ጊዜያት መፈራረቃቸውን እናስተውላለን::

የሱዳን መንግሥት ለኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች፣ የኢትዮጵያ መንግሥትም ለሱዳን ተቃዋሚዎች ድጋፍ በመስጠት አንዳቸው በአንዳቸው ላይ ጉዳት ለማድረስ ሥራ የጀመሩት ከሱዳን ነፃ መውጣት ጀምሮ ነው፡፡ በተጨማሪም በ1980ዎቹ በእስልምና ርዕዮተ ዓለም ላይ የተመሠረተው የሱዳን መንግሥት የሃይማኖት ጽንፈኝነትን በኢትዮጵያ ለማስፋፋት እንደሚሠራ ኢትዮጵያ ትተች ነበር፡፡

ኢትዮጵያ ራሷን ከሽብር ጥቃት ለመታደግ፣ በዓባይ ወዝን አጠቃቀም ዙርያ ሱዳን ያላት አቋም፣ ከተቃዋሚዎች ጋር ሱዳን ያላት ግንኙነት፣ ሱዳን በምሥራቅ አፍሪካና በኢትዮጵያ ያለው የልማትና የደኅንነት እንቅስቃሴ ላይ ያላት ተፅዕኖ፣ ኢትዮጵያ ከሱዳን ጋር ያላትን ግንኙነት ለማሻሻል እንደገፋፏት የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ይተነትናል፡፡

በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ በፖለቲካ ሳይንስ የፒኤችዲ ዕጩ ተማሪው አቶ ጎይቶም ገብረልዑል “Revamping Ethiopia’s Foreign Policy Strategy” በሚል ርዕስ በቅርቡ ዲስኮርስ መጽሔት ላይ ባወጡት ጽሑፍ፣ ስተራቴጂው ኢትዮጵያ ከአጎራባች አገሮች ጋር በተለይ ከሱዳን ጋር ያላትን ግንኙነት እንድታሻሽል ትልቅ ሚና እንደተጫወተ ገልጸዋል፡፡ የሱዳንን ስኬት ልዩ የሚያደርገው የሁለቱ አገሮች የኋላ ታሪክ እንደሆነም አመልክተዋል፡፡ ከዚህ የታሪክ ሸክም ወጥተው ንግድ፣ ትምህርትና ዲፕሎማሲን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች መልካም ግንኙነት ማድረግ መቻላቸው የሚደነቅ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ ከሁሉም በላይ የዚህ መልካም ግንኙነት መገለጫ እ.ኤ.አ. በ2013 ሱዳን ለህዳሴ ግድቡ ዕውቅና መስጠቷ እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡

ይሁንና ሱዳን ሲኤፍኤው ላይ ያላት አቋም አሁንም አልተቀየረም፡፡ የፖሊሲ ስትራቴጂው ኢትዮጵያ ከሱዳን ጋር መልካም ግንኙነት ለመፍጠር ሁለቱ አገሮች በፍትሐዊ የውኃ አመቃቀም ላይ መስማማታቸው ቅድመ ሁኔታ እንደማይሆን ይገልጻል፡፡ ለግንኙነቱ ዘላቂነት በዚህ ጉዳይ መስማማታቸው ስለሚጠቅም ይህ እንዲቀየር ኢትዮጵያ እንደምትጥርም ተመልክቷል፡፡ ባለፉት 15 ዓመታት ሁለቱ አገሮች ጥሩ ግንኙነት ቢፈጥሩም የሱዳን አቋም ባለመለወጡ፣ በርካቶች መቼ እንደሚለወጥ በመጠየቅ ላይ ናቸው፡፡

ይህ መሠረታዊ ልዩነት ይኑር እንጂ የሁለቱ አገሮች ግንኙነት በበርካታ ዘርፎች ላይ እመርታ እያሳየ ነው፡፡ በዚህም ሁለቱ አገሮች እርስ በርስ እየተሰጣጡ ካለው ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ዲፕሎማሲያዊ ዕርዳታና ድጋፍ አንፃር ሱዳን በቅርቡ ሲኤፍኤውን ፈርማ ከኢትዮጵያ ጎን ልትሠለፍ ትችላለች በሚል ተስፋ የሚያደርጉ አሉ፡፡ ሆኖም ሱዳን ይህን መሠረታዊ የአቋም ለውጥ ብታደርግ የሚመጣባትን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ኪሳራ መቋቋም ስለመቻሏ የሚጠራጠሩ አሉ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ጥያቄዎች ለኢትዮጵያም ይሠራሉ፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተጠናከረ የመጣው የኢትዮጵያና የሱዳን ግንኙነት እንደ ጅቡቲ፣ ኡጋንዳና ደቡብ ሱዳን ያሉ አገሮችን ቅር ሊያሰኝ ይችላል፡፡

ስለዚህ ኢትዮጵያ ይህን ሁሉ አደጋ ለሱዳን ስትል በመጋፈጥ የምታገኘው ትርፍ ምን እንደሆነ በድጋሚ እንድታጤን የሚጠይቁት በርካቶች ናቸው፡፡ ለግብፅ የልብ ልብ የሰጠውን ሲኤፍኤው ላይ በድጋሚ እንደራደር አጀንዳ ያመጡት የኡጋንዳ ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ናቸው፡፡ በሱዳንና በደቡብ ሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት የደቡብ ሱዳን ደጋፊ የነበሩት ሙሴቬኒ ከሱዳን ጋር መልካም የሚባል ግንኙነት የላቸውም፡፡

ዶ/ር ደረጀ ሲኤፍኤው ላይ ከግብፅ ጋር አንድ አቋም ያላት ሱዳን የአቋም ለውጥ ማምጣቷ የዲፕሎማሲ ስኬት ሆኖ መቅረቡ እንደማይዋጥላቸው ገልጸዋል፡፡ “ከግብፅ እየሸሸች ወደ ኢትዮጵያ እየቀረበች ነው ከተባለ ሲኤፍኤውን ከመፈረም ምን ያዛት?” ሲሉም ጠይቀዋል፡፡

 

Standard (Image)

ኤርትራ የተጣለባትን ማዕቀብ በመጣሷ የፀጥታው ምክር ቤት አጣሪ ቡድን ሊልክ ነው

$
0
0

እ.ኤ.አ. ከ2009 ጀምሮ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የፀጥታው ምክር ቤት ማዕቀብ የተጣለባት ኤርትራ፣ ማዕቀቡን በመጣሷ ምክንያት ምክር ቤቱ ጉዳዩን የሚያጣራ ቡድን ሊልክ መሆኑ ታወቀ፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም ነሐሴ 18 ቀን 2009 ዓ.ም. ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ እንደተናገሩት፣ ኤርትራ የተጣለባትን ማዕቀብ በተደጋጋሚ ጊዜ እየጣሰች መሆኑን ኢትዮጵያ ለተመድ የፀጥታው ምክር ቤት አባላት በተደጋጋሚ ጊዜ ስታጋልጥ ቆይታለች፡፡ የፀጥታው ምክር ቤት ጉዳዩን የሚያጣራ ቡድን ሊልክ መሆኑን ደግሞ ምንጮች ለሪፖርተር አመልክተዋል፡፡

ኢትዮጵያ የፀጥታው ምክር ቤት ተለዋጭ አባል በመሆኗ የኤርትራን ሕገወጥ እንቅስቃሴ ለዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡ ይፋ መሆኑንና በምክር ቤቱ አባላት ዘንድ ተቀባይነት ማግኘቱን አቶ መለስ ገልጸዋል፡፡

ኢትዮጵያ በተመድ የፀጥታው ምክር ቤትን ለአንድ ወር ፕሬዚዳንትነት እንደምታገኝ አቶ መለስ ጠቁመዋል፡፡ ከመስከረም ወር ጀምሮ የፀጥታው ምክር ቤት ፕሬዚዳንትነት ከግብፅ እንደምትረከብ የገለጹት ቃል አቀባዩ፣ በተለምዶ ኒውዮርክ ይካሄድ የነበረው ስብሰባም ከጳጉሜን 2 እስከ 3 ቀን 2009 ዓ.ም. በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ገልጸዋል፡፡ በዚህ ስብሰባ ላይ የምክር ቤቱ ቋሚና ተለዋጭ አባል አገሮች እንደሚሳተፉ ተጠቁሟል፡፡

በአዲስ አበባ በሚካሄደው የአፍሪካና የተመድ የምክክር ስብሰባ ኢትዮጵያ የሁለቱን ምክር ቤቶች ሰብሳቢ እንደምትሆንም አቶ መለስ ተናግረዋል፡፡ አዲስ አበባ በሚካሄደው ጉባዔ የአፍሪካ ኅብረትና የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት የጋራ ውይይት እንደሚያደርጉ የተገለጸ ሲሆን፣ 15 የምክር ቤቱ አባላት በአዲስ አበባ በሚኖራቸው ቆይታ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ጋር እንደሚገናኙም ተነግሯል፡፡

ኢትዮጵያ ለዓለም ሰላምና ፀጥታ መረጋገጥ ኃላፊነቷን ለመወጣት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ እንደምትገኝም ቃል አቀባዩ ገልጸዋል፡፡

በፕሬዚዳንትነቷ ወቅት ሁለት ዓበይት ፕሮግራሞችን እንደምትመራ የተገለጸ ሲሆን፣ እነሱም ከጳጉሜን 2 እስከ 3 ቀን 2009 ዓ.ም. በአዲስ አበባ፣ መስከረም 10 ቀን 2009 ዓ.ም. በኒውዮርክ የሚካሄዱ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

በአዲስ አበባ በሚካሄደው ስብሰባ በሶማሊያ፣ በደቡብ ሱዳንና በቻድ ሐይቅ አካባቢ ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ፣ ስለዓለም የሰላምና ፀጥታ ጉዳዮች፣ በአፍሪካ ኅብረትና በተመድ መካከል ስላለው ትብብር ምክክር እንደሚደረግ አቶ መለስ ተናግረዋል፡፡

መስከረም 10 ቀን 2009 ዓ.ም. በኒውዮርክ የሚደረገውን ስብሰባ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም እንደሚመሩት፣ ስብሰባው በተመድ የሰላም ማስከበር ተልዕኮና በቀጣይ መከናወን በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ እንደሚመክር ጠቁመዋል፡፡

ስብሰባው በአዲስ አበባ ሲካሄድ ኢትዮጵያ ብዙ ጥቅሞችን ልታገኝ እንደምትችል አቶ መለስ ገልጸዋል፡፡ ከእነዚህ መካከል አገሪቱ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተሰሚነት ማሳደግና አዲስ አበባ የዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ ማዕከል መሆኗን ማረጋገጥ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡  

ኢትዮጵያ የፀጥታው ምክር ቤት ተለዋጭ አባል በመሆኗ ውጤት ማስመዝገብ መቻሏንም አስረድተዋል፡፡ ከእነዚህ መካከልም የአፍሪካ ኅብረት ውሳኔዎችን ማስፈጸም፣ የደቡብ ሱዳንን ግጭት ለመፍታት ኢጋድ ስለሚያደርጋቸው ጥረቶች የፀጥታው ምክር ቤት ጠንካራ ድጋፍ እንዲኖረው መደረጉ፣ በሶማሊያ ዘላቂ ሰላም እንዲኖር ድጋፍ እንዲጠናከር፣ የሰላም ማስከበር ሥራ ማስገንዘብና የሶሪያ የእርስ በርስ ግጭት ዕልባት ሊያገኝ የሚችለው በፖለቲካዊ መንገድ ብቻ መሆኑን ማስረዳት መቻሏን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡

ኢትዮጵያ በታሪኳ ለሦስተኛ ጊዜ የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ተለዋጭ አባል መሆኗ ይታወሳል፡፡

 

Standard (Image)

በኦሮሚያ የሥራ ማቆም አድማ በ29 ወረዳዎች የትራንስፖርትና የንግድ አገልግሎቶች ተቋርጠው ነበር

$
0
0
  • በጅማ የቦምብ ጥቃት 13 ሰዎች ተጎድተዋል

በኦሮሚያ ክልል በማኅበራዊ ሚዲያ ከረቡዕ ነሐሴ 17 እስከ እሑድ ነሐሴ 21 ቀን 2009 ዓ.ም. በተጠራው የሥራ ማቆም አድማ፣ በ29 ወረዳዎች የትራንስፖርትና የንግድ አገልግሎቶች ተቋርጠው መሰንበታቸውን የክልሉ መንግሥት አስታወቀ፡፡

የክልሉ የመንግሥት የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ አዲሱ አረጋ ዓርብ ነሐሴ 19 ቀን 2009 ዓ.ም. ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በክልሉ ውስጥ ካሉ 315 ወረዳዎች መካከል በ29 ወረዳዎችና በአራት ዋና ዋና ከተሞች ለሦስት ቀናት የሥራ ማቆም አድማ ተደርጓል፡፡

ለዚህ ሥራ ማቆም አድማ መሠረታዊ ተደርጎ በማኅበራዊ ሚዲያ ሲዘዋወሩ ከነበሩ ጉዳዮች መካከል በኦሮሚያ ክልል ከአዋሳኝ አካባቢዎች ጋር ያለው ድንበር በአግባቡ ባለመካለሉ ተደጋጋሚ የሆነ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እንዳሉ፣ የቀን ገቢ ግምቱ ትክክል አለመሆኑን፣ የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) አመራሮች ይፈቱ የሚሉ መሆናቸውን አቶ አዲሱ አስረድተዋል፡፡

በዚህም ሳቢያ በተጠራው የተቃውሞ ጥሪ በስድስት ዞኖች ውስጥ በሚገኙ ወረዳዎችና ከተሞች የትራንስፖርትና የንግድ እንቅስቃሴዎች ተቋርጠው ነበር፡፡ ለአብነትም ሆሮ ወረዳ፣ አምቦ ከተማ፣ ግንደበረት፣ ጀልዱ፣ ሚዳቀኝ፣ ጮኬ፣ ጮቢ፣ አቡናና፣ ሜጀሬ፣ አሰቦ፣ መኢሶ፣ አወዳይ፣ ሀረማያ፣ ኮምቦልቻ፣ ነቀምቴ፣ ሆለታ፣ ቄለም፣ ደንቢዶሎ ወዘተ እንደሚገኙበት ጠቁመዋል፡፡

በእነዚህ ወረዳዎች ውስጥ ሕገወጥ እንቅስቃሴ ሲፈጽሙ የነበሩ ግለሰቦች እንደነበሩም አቶ አዲሱ ጠቁመዋል፡፡ የንግዱ ማኅበረሰብም በእነዚህ ወረዳዎችና ከተሞች በተነሳው ተቃውሞ እንደተሳተፈ ገልጸው፣ የተደራጁ ቡድኖች በማኅበራዊ ሚዲያ በሚያስተላልፉት መልዕክት ሐሳባቸውን በግድ የመጫን አዝማሚያ እንደነበር አስረድተዋል፡፡

‹‹ሐሳብን በተለያየ መንገድ መግለጽ ሕገ መንግሥታዊ መብት እንደመሆኑ መጠን የሌላውንም ፍላጎት ማክበር ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡ መደብሮቻቸውን የዘጉ ነጋዴዎች በዚህ ሕገወጥ ድርጊት ሙሉ በሙሉ እንደማያምኑበትም አቶ አዲሱ ተናግረዋል፡፡

መደብሮቻቸውን በሚከፍቱ ነጋዴዎች ላይም በማኅበራዊ ድረ ገጾች በመታገዝና ዕርምጃ ይወሰድባቸው ብሎ በማስፈራራት፣ አስገድዶ የማዘጋት እንቅስቃሴዎች እንደነበሩ አቶ አዲሱ አስታውቀዋል፡፡

ከዚህ ባለፈም ቀን ከፍተው በነበሩ ነጋዴዎች ላይ በሌሊት በመደብሮቻቸው ላይ ዕርምጃ ሲወስዱ እንደነበረ ጠቁመዋል፡፡ በአወዳይ ከተማ የዚህ ዓይነት ችግር መከሰቱን አቶ አዲሱ ለአብነት አንስተዋል፡፡

በተለይም በመጀመሪያዎቹ ሦስት ተከታታይ ቀናት ውስጥ በሰው አካልና በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን ገልጸዋል፡፡ ሆለታ አካባቢ የሁለት አውቶብሶች መስታወት እንደተሰበረ ጠቁመው፣ የክልሉ መንግሥት የሠራተኞች ሰርቪስ ላይም ተመሳሳይ ጥቃት መድረሱን አስረድተዋል፡፡

ሐሙስ ነሐሴ 18 ቀን 2009 ዓ.ም. ደግሞ በጅማ ከተማ ቦምብ በማፈንዳት በ13 ሰዎች ላይ የአካል ጉዳት መድረሱንም አስታውቀዋል፡፡ ጉዳት የደረሰባቸው በጅማ ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል የሕክምና ዕርዳታ እንደተደረገላቸው፣ ከተጎጂዎቹ ውስጥም የአሥር ዓመት ታዳጊና ሁለት ሴቶች እንደሚገኙበት ተገልጿል፡፡

አቶ አዲሱ ‹‹መንግሥት ቤት ውስጥ በመዋል አድማ የማድረግ ፍላጎት ያላቸውን ዜጎች መብት እንደሚያከብር ሁሉ፣ ሱቃቸውን ከፍተው መሸጥ የሚፈልጉና ሰላማዊ ሕይወት መምራት ለሚፈልጉ ሰዎች ከለላ የመስጠት ግዴታ አለበት፤›› ብለዋል፡፡

የአድማ ጥሪው ከተላለፈ በኋላ ጫት ከኦሮሚያ ክልል ወደ ድሬዳዋ፣ ሐረርና ሶማሌ ክልሎች እንዳይሄድ ሰፊ ቅስቀሳ ሲደረግ እንደነበር አቶ አዲሱ ገልጸዋል፡፡

የክልሉ መንግሥት በዚህ ድርጊት የተሳተፉ ዜጎችን በመለየት እየያዘና ለሕግ ተጠያቂ እያደረገ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፣ ምን ያህል ዜጎች ከዚህ ጋር በተያያዘ እንደታሰሩ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ እስካሁን ቁጥሩ በውል እንደማይታወቅ ተናግረዋል፡፡

የክልሉ መንግሥት ይህ የተቃውሞ ጥሪ መሠረት እንደሌለው ቢገለጽም፣ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ግን ይህን ሐሳብ ተቃውመዋል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ የወቅቱ ፕሬዚዳንት አቶ የሺዋስ አሰፋ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ‹‹ይህ ተቃውሞ ቀድሞ የተተነበየ ነው፤›› ብለዋል፡፡ አቶ የሺዋስ ከ2007 ዓ.ም. ምርጫ በኋላ ሕዝቡ መንግሥትን አልመረጥኩም እያለ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

 አቶ የሺዋስ ይህን ጉዳይ ሲያብራሩ፣ ‹‹መንግሥት በርካታ የፖለቲካ ጥያቄዎች እየተጠየቀ የወጣቶች ፈንድ አቋቋምኩ በማለት ለራሱ ነው መልስ የሰጠው፡፡ ይህ ደግሞ መንግሥት እያጭበረበረ መቀጠሉን ያሳያል፤›› ብለዋል፡፡ 

በኦሮሚያ ክልል የተከሰተውን ተቃውሞ ተከትሎ የአሜሪካ መንግሥት ወደ ኦሮሚያ፣ ጎንደርና ባህር ዳር የጉዞ ዕገዳ በዜጎቿ የጣለ ሲሆን፣ ይህን ጉዳይ በተመለከተ ሪፖርተር ለውጭ ጉዳዩ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም ጥያቄ አቅርቧል፡፡

አቶ መለስ በምላሻቸውም፣ ‹‹ኤምባሲዎች ዋነኛ ሥራቸው እንደዚህ ዓይነት ትንንሽ ጉዳዮች ሲፈጠሩ ይህንን መሰል ማስጠንቀቂያ ማውጣት ነው፡፡ ለምሳሌ የአሜሪካ ኤምባሲ ባለፈው ጊዜ አውጥቶት የነበረውን የጉዞ ክልከላ ስህተት ሆኖ ስላገኘው ይቅርታ ጠይቋል፤›› ብለዋል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ከሦስት ሳምንት በፊት ከቀን ገቢ ግምት ጋር በተያያዘ ተነስቶ በነበረው ተቃውሞ በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱ ይታወሳል፡፡

Standard (Image)
Viewing all 475 articles
Browse latest View live